የሉቃስ ወንጌል

መግቢያ

ይህ ወንጌል የተፃፈው ለአህዛብ ሲሆን በተለይም ለቴዎፍሎስ ነበረ::  ፀሃፊውም እራሱ እስራኤላዊ አይደለም:: በዚህ ወንጌል ውስጥ ብቻ የሚገኙ ታሪኮች አሉ::  ለምሳሌ የመልአክት ዝማሬ እረኞች  ባሉበት ስፍራ መገለጡ ጌታ እየሱስ ሲወለድ: ርኅሩኁ ሳምራዊ ምሳሌ: የጠፋው ልጅ ታሪክ እናም የእየሱስ በልጅነቱ ወደ ቤተመቅደስ መሄዱ::

ይህ ወንጌል  የተፃፈው በዓይን ያዩትና የቃሉ አገልጋዮች የሆኑት እንዳስተላለፉልን ነው::  በማለት እርሱ የዓይን እማኝ እንዳልሆነ ይገልጣል::  የተፃፈውም በጥንቃቄ ሁሉን ከመጀመሪያው ተከትዬ በየተራው ነው የፃፍኩት ብሎ ይላል::

ሉቃስ 1:1-4፤ የከበርህ ቴዎፍሎስ ሆይ፥ ከመጀመሪያው በዓይን ያዩትና የቃሉ አገልጋዮች የሆኑት እንዳስተላለፉልን፥ በኛ ዘንድ ስለ ተፈጸመው ነገር ብዙዎች ታሪክን በየተራው ለማዘጋጀት ስለ ሞከሩ፥ እኔ ደግሞ ስለ ተማርኸው ቃል እርግጡን እንድታውቅ በጥንቃቄ ሁሉን ከመጀመሪያው ተከትዬ በየተራው ልጽፍልህ መልካም ሆኖ ታየኝ።

ጌታ ሆይ ተመስገን ይህንን ቃልህን እንደዚህ በጥንቃቄ የተፃፈውን እንድንማረውና ገንዘባችን እንድናደርገው እርዳን::

ሉቃስ 1:5፤ በይሁዳ ንጉሥ በሄሮድስ ዘመን ከአብያ ክፍል የሆነ ዘካርያስ የሚባል አንድ ካህን ነበረ፤ ሚስቱም ከአሮን ልጆች ነበረች፥ ስምዋም ኤልሳቤጥ ነበረ። 6፤ ሁለቱም በጌታ ትእዛዝና ሕግጋት ሁሉ ያለ ነቀፋ እየሄዱ በእግዚአብሔር ፊት ጻድቃን ነበሩ።7፤ ኤልሳቤጥም መካን ነበረችና ልጅ አልነበራቸውም፤ ሁለቱም በዕድሜያቸው አርጅተው ነበር።

እንግዲህ ሉቃስ ቃል እንደገባው ከመጀመርያ ጀምሮ ነው ስለተማረው ቃል እርግጡን እንዲያውቅ ለቴዎፍሎስ እየፃፈ ያለው እግዚአብሔር እኛን እያየ ነበረና ይኸው ዛሬ እኛጋር ደርሷል::

የጀመረውም ከዘካርያስና ከኤልሳቤጥ ነበረ በዚህ ውስጥም ስለ ሄሮድስም አንስቷል ይህ ገዢ ነው ህፃናትን የጨፈጨፈው እየሱስን ለመግደል አስቦ::  እርሱ የመሰለው ስልጣኑን የሚቀማው እየሱስ ግን በዚህኛው ዓለም ብቻ ሳይሆን በሚመጣውም ዓለም ገዢ ነው:: እርሱ የነገስታት ንጉስና የጌቶችም ጌታ ነው::

እነዚህ ባልና ሚስት ሁለቱም ከካህናት ዘር እንደሆኑ ይገልፃል ደግሞም በጌታ ትእዛዝና ሕግጋት ሁሉ ያለ ነቀፋ እየሄዱ በእግዚአብሔር ፊት ጻድቃን ነበሩ ይላል::  ልጅ የሌላቸውና እድሜያቸውም መግፋቱን ልጅ ማግኛው ዘመን ማለፉን ያመላክታል:: ፃድቅ ነበሩ የሚለው አሳብ እንዴት ይገርማል ::  ነገር ግን እንደነ አብረሃም በእምነት እንጂ በአዲስ ኪዳን እንዳለው ፃድቅነት አይደለም ምክንያቱም ሁሉም ኃጥያትን አድርገዋል የእግዚአብሔር ክብር ጎሏቸዋል ይላልና ቃሉ::   በብሉይ ኪዳን የኃጥያት ስርየት በእንስሳት ደም ማግኘት ይቻል ነበር ነገር ግን ዘላቂ አልነበረምና የእግዚአብሔር በግ እየሱስ መጣልንና አፀደቀን ልጅም አደረገን::  አሜን!

አባት ሆይ ተመስገን በደምህ ዋጅተህ ልጅ ስላደረከን::  ጌታ ሆይ አንተን የሚይዝህ ነገር የለም ከዚህ አለመቻል ውስጥ ዮሃንስ ተወልዷልና ዛሬም በህይወታችን ትሰራለህ የሚያቆምህ ምንም ነገር የለም ተመስገን! እታመንሃለሁ ጌታዬ!

ሉቃስ 1:8፤ እርሱም በክፍሉ ተራ በእግዚአብሔር ፊት ሲያገለግል፥ . . . ሉቃስ 1:11፤ የጌታም መልአክ በዕጣኑ መሠዊያ ቀኝ ቆሞ ታየው። . . . ሉቃስ 1:13፤ መልአኩም እንዲህ አለው፦ “ዘካርያስ ሆይ፥ ጸሎትህ ተሰምቶልሃልና አትፍራ፡ ሚስትህ ኤልሳቤጥም ወንድ ልጅ ትወልድልሃለች፥ ስሙንም ዮሐንስ ትለዋለህ።

በብሉይ ኪዳን ጥቂት ሰዎች ናቸው ጻድቅ ተብለው የተጠሩ ከነዛ መካከል  ዘካርያስ አንዱ ሆነ::  ይህ ሰው ካህን ነውና በተራው ገብቶ እግዚአብሔርን ያገለግላል ምንም እንኳን መሃንነት በህብረተሰቡ ዘንድ ጥያቄ ውስጥ የሚያስገባ ቢሆንም::  

የእግዚአብሔር የጉብኝት ሰዕት ሲደርስ ግን መልአኩን ልኮ የምስራች ነገረው::  ጸሎትህ ተሰምቶልሃልና አትፍራ!  በዚች አንድ ቀን ጉብኝት ወደ ዘካርያስ ቤት እየመጣ ያለውን ብናይ:- 

   – ደስታና ተድላም ይሆንልሃል፥ 

   – በመወለዱም ብዙዎች ደስ ይላቸዋል 

   – በጌታ ፊት ታላቅ ይሆናልና፥ የሚለው አሳብ ይገርማል ጌታ እየሱስ ስለእርሱ ሲመሰክር  “እላችኋለሁ፥ ከሴቶች ከተወለዱት መካከል ከመጥምቁ ዮሐንስ የሚበልጥ ማንም የለም፤ ብሎ ነበረ:: 

   – ገናም በእናቱ ማኅፀን ሳለ መንፈስ ቅዱስ ይሞላበታል የሚለው ይገርማል::  ህፃን ነው ገና በሆድ ግን መንፈሱ አገኘውና አላማውን እንዲተገብር ረዳው:: የጌታ አሰራር! 

ዘካርያስ ግን እስከአሁን ልጅ ስጠኝ ብሎ እየለመነ አይመስልም ጸሎቱን ከሁኔታዎች የተነሳ የተወው ይመስላል::   ጌታ ግን ለመመለስ መጣ ምንም እንኳን ዘካርያስ ዝግጁ ባይሆንምና ይህን በምን አውቃለሁ ብሎ ምልክትን ቢጠይቅም::  ምልክት ትፈልጋለህ እንግዲያውስ ዲዳ ሆነህ ቆይ እስኪፈፀም:: ለካስ እራሱ ነው ምልክት የጠየቀው?! 

አባት ሆይ በፀሎት በፊትህ የቀረብኩትን ሁሉ ሰምተኸኛል ዛሬ ያልተመለሱ ቢኖሩም ይመለሳሉ አንተ ታላቅ ነህና ተመስገን!  ተስፋ ባለመቁረጥ በቤትህ እንዳገለግልህ ጸጋህን ለእኔና ለወገኖቼም አብዛልን::  ዛሬ የቆየ ጥያቄ የሚመለስበት ቀን ይሁን::  አሜን!

ሉቃስ 1:14፤ ደስታና ተድላም ይሆንልሃል፥ በመወለዱም ብዙዎች ደስ ይላቸዋል።

በመልአኩ ለዮሃንስ የተሰጠው ተስፋና የሚመጣበት ዓላማ ወይም አገልግሎቱ በደንብ ለዘካርያስ ተነግሮታል::

ለቤተሰቡ:- ደስታና ተድላም ይሆንልሃል እንዲሁም ብዙዎች ደስ ይላቸዋል::

የእስራኤል ህዝብ ለመሲሁ መምጣት የተዘጋጀ አይደለምና ለማዘጋጀት የተላከ ከአወላለዱ ጀምሮ ማን ይሆን በሚያስብል ተአምራት የመጣ ልጅ ነው::

በጌታ ፊት ታላቅ ይሆናልና፥  – ተስፋ ነው::  ጌታ እየሱስም መስክሮለታል::

የወይን ጠጅና የሚያሰክር መጠጥ አይጠጣም፤ – ትእዛዝ

ገናም በእናቱ ማኅፀን ሳለ መንፈስ ቅዱስ ይሞላበታል፤ – የሚፈጸም ተስፋ ነው

ከእስራኤልም ልጆች ብዙዎችን ወደ ጌታ ወደ አምላካቸው ይመልሳል – አገልግሎቱ

እርሱም የተዘጋጁትን ሕዝብ ለጌታ እንዲያሰናዳ – መንገድን የመጥረግ አገልግሎት::  ህዝቡን እያጠመቀ እኔ እርሱ አይደለሁም እያለ እየመሰከረ ለሚመጣው ጌታ አዘጋጀ::   ደቀ መዛሙርቱንም የጌታ ሆኑ በስተመጨረሻ::

የአባቶችን ልብ ወደ ልጆች – አገልግሎት  ሲሆን ከአሮጌው ኪዳን ወደ አዲስ እንዲመጡና  እንደልጅ ሆነው እንዲቀርቡ እንዲያደርግ:: ባጭሩ ለውጥን እንዲቀበሉ

የማይታዘዙትንም ወደ ጻድቃን ጥበብ ይመልስ ዘንድ  – የማንቃት አገልግሎቱ

በኤልያስ መንፈስና ኃይል በፊቱ ይሄዳል – ይህ አገልግሎት መንገድን ለእየሱስ ለሚጠርገው የተሰጠ ነው:: በትንቢትም ኤልያስ ከመሲሁ ፊት ይመጣል ብለው ይጠብቁ ነበር ግን ሲስቱ እናያለን:: ይህ ህፃን ገና በእናቱ ሆድ እያለ በመንፈስ ቅዱስ ይሞላል በኤልያስም መንፈስና ኃይል ያገለግላል:: ታላላቆች ግን አላወቁም::

የእኔ አገልግሎት ምንድነው? ብለን ቆም ብልእን ልንጠይቅና ለተጠራንለት ዓላማ ልንቆም ያስፈልጋል:: በክርስቶስ አስቦ ወለደን እንደሚል ምን ይሆን ለእያንዳንዳችን ያሰበው?

አባት ሆይ ለእኔም እንዲሁ የሰጠኸኝ አገልግሎት አለና ከመንፈስ ቅዱስ ጋር ተስማምቼ እንዳገለግልህና መክሊቴንም እንዳተርፍበት እርዳኝ::  አሜን!

ሉቃስ 1:18 25

ዘካርያስም መልአኩን፦ “እኔ ሽማግሌ ነኝ ምስቴም በዕድሜዋ አርጅታለችና ይህን በምን አውቃለሁ?” አለው።

በእጣ ክፍሉ በታማኝነት በሚያገለግልበት ቦታና ሰዓት የምስራች ለዘካርያስ መጣለት::  ምንም እንኳን በእድሜው ያረጀ ቢሆንም እግዚአብሔር ሲናገር ማመን አልቻለምና ምልክትን ጠየቀ::  መልአኩም በጊዜው የሚፈጸመውን ቃሌን ስላላመንህ፥ ይህ ነገር እስከሚሆን ቀን ድረስ ዲዳ ትሆናለህ መናገርም አትችልም፡” አለው። አገልግሎም ሲወጣ ህዝቡ ራዕይ እንዳየ አስተዋሉ::

የእግዚአብሔር ቃል የሚፈፀም ነውና የተናገረንን አምነን እንጠባበቅ:: ለእርሱ የሚሳነው የለምና በሙሉ ልባችን እንመነው::

ከዚህም ወራት በኋላ ሚስቱ ኤልሳቤጥ ፀነሰችና፦ “ነቀፌታዬን ከሰው መካከል ያስወግድልኝ ዘንድ ጌታ በተመለከተበት ወራት እንዲህ አድርጎልኛል፡” ስትል ራስዋን አምስት ወር ሰወረች።  እርጉዝ ነኝ ብላ ማውራት አላስፈለጋትም ጊዜው ሲደርስ ሆድዋ እራሱ ይናገር ነበረና እራስዋን ሸሸገች!

አባት ሆይ ተመስገን የሰጠኸንን ቃል የምትፈጽም ጌታ ነህና የተናገርከንንም ሁሉ  እንወርሳለን::  አሜን!

እንደተናገረው ለሚያደርግ አምላክ ክብር ይሁን!  አሜን!

ሉቃስ 1: 26-33

27፤ ከዳዊት ወገን ለሆነው ዮሴፍ ለሚባል ሰው ወደ ታጨች ወደ አንዲት ድንግል ከእግዚአብሔር ዘንድ ተላከ፥ የድንግሊቱም ስም ማርያም ነበረ።

መልአኩ ገብርኤል  ያመጣላት መልእክት

እነሆም፥ ትፀንሻለሽ ወንድ ልጅም ትወልጃለሽ፥ 

ስሙንም ኢየሱስ ትዪዋለሽ – ይህ ስም የተቀባ ስም ዛሬም እንድንበት ዘንድ የተሰጠን ስም::  በላይ በሰማይ በምድር ከምድርም በታች ሁሉ ይንበረከክለታል::

እርሱ ታላቅ ይሆናል – አሜን ታላቅ ነው

የልዑል ልጅም ይባላል – የምወደው ልጄ ይህ እርሱን ስሙት ብሎ አብ መስክሮለታል::

ጌታ አምላክም የአባቱን የዳዊትን ዙፋን ይሰጠዋል – ቃል እንደገባው 2 ሳሙኤል 7:16፤ ቤትህና መንግሥትህም በፊቴ ለዘላለም ይጠነክራል፥ ዙፋንህም ለዘላለም ይጸናል።

በያዕቆብ ቤትም ላይ ለዘላለም ይነግሣል፥ 

ለመንግሥቱም መጨረሻ የለውም።

አሜን የጌታ መንግስት ለዘላለም የጸና ነው::  ለዚህ ቃሉን ተናግሮ ለሚፈጽም ጌታ ክብር ይሁን::  ዛሬም በስራ ላይ ነው:: ሁሉም ነገር እንዳለው ይሆናልና በዙሪያችን ባለውነገር አንሸበር የመጨረሻው ውሳኔ የጌታ ነው::  ሃሌሉያ!

ሉቃስ 1: 34-38

34፤ ማርያምም መልአኩን፦ “ወንድ ስለማላውቅ ይህ እንዴት ይሆናል?” አለችው።

የተፈጥሮን ነገር ሁሉ ያላሟላ ስለሆነ መልእክቱ ግራ ገብቷት መጠየቅዋ ትክክል ነበረ::  ምንም እንኳን  በእግዚአብሔር ፊት ጸጋ አግኝተሻልና አትፍሪ የተባለች ብትሆንም እርስዋም አዳኝ ያስፈልጋታልና እንዴት ከስዋ የመጣ ያድናል የሚለውን ጥያቄ ይመልሳል::  መልአኩም መልሶ እንዲህ አላት፦ “መንፈስ ቅዱስ በአንቺ ላይ ይመጣል፥ የልዑልም ኃይል ይጸልልሻል ስለዚህ ደግሞ ከአንቺ የሚወለደው ቅዱስ የእግዚአብሔር ልጅ ይባላል። አሜን! እርሱ በድንግልና የተወለደ  የእግዚአብሔር ልጅ ነው:: ቃል ስጋ ሆነ ጸጋንና እውነትን ተሞልቶ በእኛ አደረ!

በዚሁ ሌላ መልካም ዜና ነገራት:- ዘመድሽ ኤልሳቤጥ፥ እርስዋ ደግሞ በእርጅናዋ ወንድ ልጅ ፀንሳለች፥ ለእርስዋም መካን ትባል ለነበረችው ይህ ስድስተኛ ወር ነው አላት የሁለቱ ልጆች ግንኙነትና ተልእኮ ባይገባትም እንኳን በጉብኝቱ ደስ ብሏታል::  

ወንድ የማታውቀው አርግዛ እንድትወልድ እንዲሁም ያረጀችው ልጅ እንድታቅፍ የሚያደርግ ጌታ ስሙ ይባረክ::  ሳይንሱን ሁሉ የገለባበጠው ጌታ ይባረክ::  ለእግዚአብሔር የሚሳነው ነገር የለምና። አሜን!

በዚህ ውስጥ ማርያምም፦ “እነሆኝ የጌታ ባሪያ እንደ ቃልህ ይሁንልኝ፡” አለች። መልአኩም ከእርስዋ ሄደ። ከጌታ ጋር ተስማማች ምንም እንኳን በባህሉ ከትዳር ውጪ አርግዞ መገኘት ዋጋ ቢያስከፍልም እርሱ ብሏል ብላ ቆመች::  እርሱም የሚሳነው የለምና ቃሉን ይፈጽማል:: 

ለተናገረን ነገር እኛ በእምነት እንቁም ሌላውን ሁሉ ኤልሻዳዮ ጌታ ይወጣዋል::

አባት ሆይ ተመስገን ቃልህ ከእኛ ጋር ይዋሃድና ይጥቀመን::  እንደተናገርከንም መታዘዝ ይሁንልን ምሕረትህ ዛሬ በእኛ ላይ ትገለጥ::  አሜን!

ሉቃስ 1: 39-45

41፤ ኤልሳቤጥም የማርያምን ሰላምታ በሰማች ጊዜ ፅንሱ በማኅፀንዋ ውስጥ ዘለለ፤ በኤልሳቤጥም መንፈስ ቅዱስ ሞላባት፥ 

ማርያም ኤልሳቤጥን ልትጠይቅ  መጣች:: እግዚአብሔር ለዘካርያስ በነገረው መሰረት  ይኸው ህፃኑ በመንፈስ ቅዱስ ተሞልቶ በማኅፀንዋ ውስጥ ዘለለ:: ቃል ስጋ ሆንዋል በማህፀንም እያለ ይሰራል:: 

እነሆ፥ የሰላምታሽ ድምጽ በጆሮዬ በመጣ ጊዜ ፅንሱ በማኅፀኔ በደስታ ዘሎአልና።

ከጌታ፤ የተነገረላት ቃል ይፈጸማልና ያመነች ብፅዕት ናት። እግዚአብሔር እንደተናገረው እንደቃሉ ነውና የተስፋ ቃላችንን ሁሉ እንወርሳለን ምክንያቱም የተናገረው የታመነ ነው:: አሜን! 

ሉቃስ 1: 46-56

46፤ ማርያምም እንዲህ አለች፦ “ነፍሴ ጌታን ታከብረዋለች፥ 47፤ መንፈሴም በአምላኬ በመድኃኒቴ ሐሴት ታደርጋለች፤

ማርያም እንደቃልህ ይሁንልኝ ብላ ለእግዚአብሔር ቃል ታዘዘችና ቃል የሆነው እየሱስ በእርስዋ ውስጥ ተፀነሰ::  ኤልሳቤጥም በመንፈስ ተሞልታ ትንቢትን እንደተናገረች ሁሉ ማርያምም ቃል እየጠቀሰች በመንፈስዋ ሃሴት እያደረገች ጌታን ማክበርና መባረክ ይዛለች::  የእየሱስ እናት መሆን እንዴት የሚገርም መመረጥ ነው? ነገር ግን እርስዋም የእግዚአብሔር ክብር ይጎድላታልና አዳኝ አስፈልጏታል:: 

እርስዋም:- ብርቱ የሆነ እርሱ በእኔ ታላቅ ሥራ አድርጎአልና፤ ስሙም ቅዱስ ነው። ብላለች አሜን እርሱ ቅዱስነው::  እናውቃለን ብለው የታበዮትን አዋረዳቸው ለትሁታን ግን ፀጋን ሰጠ!

አምላካችንን እናመስግን እናድንቅ እናወዳድሰው ስለሚገባው ይህ ንጉስ እኛን ፍለጋ ሲመጣ ይህንን ሁሉ ነገር ሰርቶ ነውና ይክበርልን:: አሜን! እኛም እንደማርያም ነፍሴ ጌታን ታከብረዋለች እንበል::

ሉቃስ 1: 57-66

57፤ የኤልሳቤጥም የመውለጃዋ ጊዜ ደረሰ፥ ወንድ ልጅም ወለደች። 58፤ ጎረቤቶችዋም ዘመዶችዋም ጌታ ምሕረቱን እንዳገነነላት ሰምተው ከእርስዋ ጋር ደስ አላቸው።

የጌታን መልእክት እንዴት ይሆናል ብሎ እንዳላለ ዘካርያስ እንደተባለው አባት ሆነ::  ይህንንም በዓይኑ አይቶ ሙሉ ለሙሉ እስኪታዘዝ ድረስ ዲዳ ነበረ::  እነሆም፥ በጊዜው የሚፈጸመውን ቃሌን ስላላመንህ፥ ይህ ነገር እስከሚሆን ቀን ድረስ ዲዳ ትሆናለህ መናገርም አትችልም፡” አለው። የእግዚአብሔር ቃል የሚፈጸም ነው::  አሜን!

ጌታ ምሕረቱን እንዳገነነላት ሰምተው ከእርስዋ ጋር ጎረቤቶችዋና ዘመዶችዋ ደስ አላቸው። ምሕረቱን በእያንዳንዳችን ቤት ላይ ያግንነው::

ስም ሊያወጡለት የፈለጉት የአባቱን ስም ነበረ ነገር ግን እናትምአባትም ተቃወሙና ስሙ ዮሐንስ ነው ሲሉ እነርሱም፦ “ከወገንሽ ማንም በዚህ ስም የተጠራ የለም፡” አሉአት። የእግዚአብሔር ነገር ሰው ባሰመረለትና በተለመደው መንገድ አይሰራምና መቀበል ግድ ነበረ::  አይሆንም ባይሉ ግን ስሙን ይቀይሩት ነበረ ማለት ነው:: 

አባት ሆይ ያልከው እንደሚፈፀም አውቀን በሰጠን የተስፋ ቃል እንድንታመንና እንድንጠብቅ እርዳን:: አሜን!

ሉቃስ 1: 65-71

67፤ አባቱ ዘካርያስም መንፈስ ቅዱስ ሞላበትና ትንቢት ተናገረ እንዲህም አለ፦

68፤ “የእስራኤል ጌታ አምላክ ይባረክ፥ ጐብኝቶ ለሕዝቡ ቤዛ አድርጎአልና፤

እዚህ ምዕራፍ ላይ ኤልሳቤጥ በመንፈስ ቅዱስ ተሞልታ ትንቢትን ስትናገር አይተናል እንዲሁም ማርያም አሁን ደግሞ ዘካርያስ:: እርሱም የጀመረው እግዚአብሔርን በመባረክ ነው::   አሁን ያሉት ዮሃንስ ሊገረዝ ባለበት ስርዓት ላይ ቢሆንም እንኳን  አባትየው በመንፈስ ተነድቶ  ስለመሲሁ እየተናገረ ነው:: ጐብኝቶ ለሕዝቡ ቤዛ አድርጎአልና እያለ::  አሜን የሰውን ልጅ ያሰበው ጌታ ይባረክ::

ሲቀጥልም ከጥንት ጀምሮ በነበሩት በቅዱሳን ነቢያት አፍ እንደ ተናገረ፥ 

በብላቴናው በዳዊት ቤት የመዳን ቀንድን አስነስቶልናል::  ይህ የመዳን ቀንድ የሆነው መሲሁ እየሱስ ‘ማዳኑም ከወደረኞቻችንና ከሚጠሉን ሁሉ እጅ ነው ብሎ መንፈስ ቅዱስ መሰከረለት::  አሜን  ከሚጠሉን ከሰይጣንና ከአጋንንቶች እጅና መንጋጋ ነው::  ጨለማችንን አብርቶ ፤  በደላችንንም ይቅር ብሎ ፤   በጽድቁ አጽድቆ ፤  በቤቱ ተክሎን ፤   ከዓለም ውጡና የተለያችሁ ሁኑ ብሎ አባት ሆኖን፤  በእጁም መዳፍ ቀርጾ ማንም ከእጄ አያወጣችሁም ብሎን ፤   አይዞአችሁ ዓለምን አሸንፌአለሁ ብሎን ፤  በእኛ ውስጥ ለመኖር መጣ:: ምን አይነት ህይወት ነው?!

አባት ሆይ ተመስገን ክብርህን ጥለህ የባርያን መልክ ይዘህ ተዋርደህ ለእኛ የመጣህ ጌታ እናመሰግንሃለን:: እኛነታችን ሁሉ የአንተ ነውና ክበርበት! አሜን

ሉቃስ 1: 72-75

72-73፤ እንደዚህ ለአባቶቻችን ምሕረት አደረገ፤ ለአባታችን ለአብርሃምም የማለውን መሐላውን ቅዱሱን ኪዳን አሰበ፤ 74-75፤ “በእርሱም ከጠላቶቻችን እጅ ድነን በዘመናችን ሁሉ ያለ ፍርሃት በቅድስናና በጽድቅ በፊቱ እንድናገለግለው ሰጠን።

ዘካርያስ ትንቢቱን ሲቀጥል ለአባታችን ለአብርሃምም የማለውን መሐላውን ቅዱሱን ኪዳን አሰበ አለ እንዲህ ያለውን:-

ዘፍጥረት 22:16 – 18፤ እንዲህም አለው፦ “እግዚአብሔር፦ ‘በራሴ ማልሁ፡’ ይላል፤ ይህን ነገር አድርገሃልና፥ አንድ ልጅህንም አልከለከልህምና፣ በእውነት በረከትን እባርክሃለሁ፥ ዘርህንም እንደ ሰማይ ከዋክብትና በባሕር ዳር እንዳለ አሸዋ አበዛዋለሁ፤ ዘርህም የጠላቶችን ደጅ ይወርሳል፤ የምድር አሕዛብ ሁሉም በዘርህ ይባረካሉ፥ ቃሌን ሰምተሃልና።”

አብርሃም ቃሉን ሰምቶ አንድ ልጁን መስዋእት ለማድረግ ስላልሳሳ  በራሱ ምሎ እራሱ መጣና ተቤዥን::  በአብርሃም የምድር አሕዛብ ሁሉም በዘርህ ይባረካሉ  እንደሚል ይኸው እኛ ከአህዛብ ወገን የሆንን ለዚህ ቃል መፈጸም የቆምን ምልክቶች ነን:: አሜን!

በእርሱም ከጠላቶቻችን እጅ ድነን በዘመናችን ሁሉ ያለ ፍርሃት በቅድስናና በጽድቅ በፊቱ እንድናገለግለው ሰጠን። ሃሌሉያ! ! ዓለም ሳይፈጠር፥ በፊቱ ቅዱሳንና ነውር የሌለን በፍቅር እንሆን ዘንድ በክርስቶስ መረጠን::  አሜን!

ሉቃስ 1: 76-80

78፤ ይህም ከላይ የመጣ ብርሃን በጐበኘበት በአምላካችን ምሕረትና ርኅራኄ ምክንያት ነው፤ 79፤ ብርሃኑም በጨለማና በሞት ጥላ ተቀምጠው ላሉት ያበራል እግሮቻችንንም በሰላም መንገድ ያቀናል።”

ስለዮሃንስ ደግሞም አንተ ሕፃን ሆይ፥ የልዑል ነቢይ ትባላለህ፥ መንገዱን ልትጠርግ በጌታ ፊት ትሄዳለህና፤ “እንደዚህም የኃጢአታቸው ስርየት የሆነውን የመዳን እውቀት ለሕዝቡ ትሰጣለህ ነው የመጣበት አገልግሎት::  እራሱም መስክሯል እኔ እርሱአይደለሁም በማለት:: መንገድን መጥረግና የመዳንን እውቀት ለሕዝቡ መግለጥ ነበረ ::  ጌታ የሰጠን ስራ ምን ይሆን?  የተሰጠንማ ስራ አለን::  ይህንኑ ጌታ ይግለጥልን::

ይህም ከላይ የመጣ ብርሃን በጐበኘበት በአምላካችን ምሕረትና ርኅራኄ ምክንያት ነው::  አሜን!  የአምላካችን ምሕረትና ርኅራኄ ጉብኝት አገኘን::  ይህ ብርሃን በራልን ጨለማችንም በራ! 

ብርሃኑም በጨለማና በሞት ጥላ ተቀምጠው ላሉት ያበራል እግሮቻችንንም በሰላም መንገድ ያቀናል። አሜን!  በሞት ጥላ ተቀምጠን ነበረ ያለ መፍትሄ ምንም መውጫ የሌለበት::  በኢየሱስ ግን አመለጥን ውደ ህይወት ተሻገርን!  ጨለማችንንም አበራው!  እግሮቻችንንም በሰላም መንገድ ያቀናው ምሕረቱንና ርህራሄውን ያበዛልን ጌታ ይባረክ!

አባት ሆይ ተመስገን መፍትሄ የሌለውን ፍፃሜያችንን ለውጠህ አባ አባት የምንልበትን መንፈስ ሰጥተህ በቤትህ አለመለምከን::  በአብ ቀኝ ተቀመጥን!

ሉቃስ 2: 1-7

7፤ የበኵር ልጅዋንም ወለደች፥ በመጠቅለያም ጠቀለለችው፤ በእንግዶችም ማደሪያ ስፍራ ስላልነበራቸው በግርግም አስተኛችው።

በዚያም ወራት ዓለሙ ሁሉ እንዲጻፍ ትእዛዝ ወጣ ይህ ትእዛዝ ከነገስታት የወጣ ይምሰል እንጂ ወራቱን ጠብቆ ትእዛዝ ያወጣው አምላካችን ነው::  ትእዛዙም የወጣው ትንቢቱ እንዲፈፀም እየሱስ በቤተልሔም ይወለድ ዘንድ ነውና ዮሴፍም ለመቆጠር እጮኛውን ይዞ ወደ ቤተልሐም መጣ:: ትንቢቱም  በሚክያስ 5:2፤ አንቺም ቤተ ልሔም ኤፍራታ ሆይ፥ አንቺ በይሁዳ አእላፋት መካከል ትሆኚ ዘንድ ታናሽ ነሽ፤ ከአንቺ ግን አወጣጡ ከቀድሞ ጀምሮ ከዘላለም የሆነ፥ በእስራኤልም ላይ ገዥ የሚሆን ይወጣልኛል። የሚለው ነው:: በዝችው ከተማ ነበረ ዳዊትም የተቀባው::

የትንቢቱ ትእዛዝ ሲፈፀም እንደመቃብሩ ሁሉ የከበሬታን ቦታ ማዘጋጀት ይችል ነበረ ነገር ግን  የነገስታት ንጉስና የጌቶቹ ጌታ ስፍራ ጠፍቶ በከብቶች በረት  በግርግም ተወለደ::  እውነትም እንዴት ነው እራሱን አዋርዶ የመጣልን?! እየሱስ ተወለደ ዓለም ሁሉ አላወቀም::  ዓለሙን ሁሉ በቃል የፈጠረው ጌታ መወለዱን ከጥቂቶች በቀር አብዛኛው አላወቀም::  እርሱም እውቅና ስጡኝ አላለም::   ትሁት ጌታ! ተመስገን!  የእኛም ህይወት ከዚህ ግርግም የማይለይ ቁሻሻ ነበረ እርሱ ሲገባ ግን በደሙ አነፃንና ፃድቅ ቅዱሳን ተባል! ሃሌሉያ!

አባት ሆይ የዝቅታን ዝቅታ ስለእኛ አየህ::  ተመስገን ስለተወለድክና ስለመጣህልን እናመሰግንሃለን!  ልጆችህ ስላደረከን ከፍ በል! ይህንን የመጣህበትን የማዳን ወንጌል ይዘን እንድንወጣና እንድንመሰክር እርዳን በጸጋህንም ሙላን::  አሜን

ሉቃስ 2: 8-20

10፤ መልአኩም እንዲህ አላቸው፦ “እነሆ፥ ለሕዝቡ ሁሉ የሚሆን ታላቅ ደስታ የምሥራች እነግራችኋለሁና አትፍሩ፤

11፤ ዛሬ በዳዊት ከተማ መድኃኒት እርሱም ክርስቶስ ጌታ የሆነ ተወልዶላችኋልና።

12፤ ይህም ምልክት ይሆንላችኋል፤ ሕፃን ተጠቅልሎ በግርግምም ተኝቶ ታገኛላችሁ።”

እየሱስ ለህዝብ ሁሉ የሚሆን ታላቅ ደስታ የምሥራች እረኞች ተነገራቸው::  ይህም የምስራች መድኃኒት እርሱም ክርስቶስ ጌታ የሆነ ተወልዶላችኋል የሚል ነበረ::  ይህ ለሊት ምን አይነት የተለየ ለሊት ነው? አምላክ ሰው ሆኖ የተወለደበት ለሊት::  ዓለሙ ሁሉ በእንቅልፍ ላይ ነው እነዚህ እረኞች በማንም አጀንዳ ላይ የማያሰፍራቸው ይህንን ክብር ያዮ ዘንድ ተመረጡ:: የመልአኩን መልአክት ሰሙ አብረውም ያሉትን መልአክትን ዝማሬ አደመጡ:- 

“ክብር ለእግዚአብሔር በአርያም ይሁን ሰላምም በምድር ለሰውም በጎ ፈቃድ።”

እነዚህ እረኞች ሰምተው ብቻ ዝም አላሉም መላእክቱ ከእነርሱ ተለይተው ወደ ሰማይ በወጡ ጊዜ፥ እረኞቹ እርስ በርሳቸው፦ “እንግዲህ እስከ ቤተ ልሔም ድረስ እንሂድ እግዚአብሔርም የገለጠልንን ይህን የሆነውን ነገር እንይ፡” ተባባሉና ታዘዙ::  ዛሬም ወድያው መታዘዝ ይሁንልን ጌታ በሚያሳየንና በሚያዘን ነገር ላይ::  ጸጋህን ስጠን!

በፍጥነትም መጡ ህፃኑንም በግርግም ተኝቶ አገኙት::  ከቤተሰቡ በተጨማሪ እነዚህ እረኞች ናቸው ያወቁት ስለመሲሁ:: ማርያም ግን ይህን ነገር ሁሉ በልብዋ እያሰበች ትጠብቀው ነበር። የተቀበልነውን ነገር እምነታችንን እንዳይጎዳ በልባችን እንጠብቅ:: 

እረኞችም እንደ ተባለላቸው ስለ ሰሙትና ስላዩት ሁሉ እግዚአብሔርን እያመሰገኑና እያከበሩ ተመለሱ። እኛም ዛሬ ይህንን መሲህ እኛን ያሰበውን እናመስግን::

ሉቃስ 2: 21 – 28

21፤ ሊገርዙት ስምንት ቀን በሞላ ጊዜ፥ በማኅፀን ሳይረገዝ በመልአኩ እንደ ተባለ፥ ስሙ ኢየሱስ ተብሎ ተጠራ።

ገና ሳይፀነስ መልአኩ እንደተባለው ስሙን ኢየሱስ  ብለው ጠሩት:: ማርያም እንደቃልህ ብላ ተስማምታ ነበረና የዘካርያስ እጣ አልደረሰባትም::  ታዘዘች ይኸው  እግዚአብሔርም እንደተናገረ ወንድ ልጅን እርሱም የዓለምን መድኃኒት አቀፈች::

እነሆም፥ በኢየሩሳሌም ስምዖን የሚባል ሰው ነበረ፥ ይህም ሰው የእስራኤልን መጽናናት ይጠባበቅ ነበር፤ ጻድቅና ትጉህም ነበረ፥ መንፈስ ቅዱስም በእርሱ ላይ ነበረ። በጌታም የተቀባውን ሳያይ ሞትን እንዳያይ በመንፈስ ቅዱስ ተረድቶ ነበርና ሲያመጡት ተቀብሎ አቀፈው::  ይህ ሰውን ከምድር አፈር ያበጀ ጌታ  ሰውእጅ ገባ::  ምን አይነት ዝቅታ ነው በሰው እጅ መታቀፍ በሰው እጅ መብላት መጠጣት መታቀፍ እንደማንኛውም ልጅ ቋንቋ መማር  መዳህ መውደቅ መነሳት ሁሉን አድርጏል::  ስናስበው ግን ማንም  ሊቀርበው በማይችል ብርሃን ውስጥ የሚኖር  ጌታ: በሲና ተራራ ሲገለጥ የቀረበ ሰው ወይም እንሰሳ ሁሉ ይሞት ነበረ: ዮሃንስ እንኳን በደንብ የሚያውቀው መቆም አልቻለም በፊቱ::  እንግዲህ ይህንን ጌታ ነው ተቀብሎ ያቀፈው::  ክብሩን ሁሉ ጥሎ እራሱን አዋርዶ መጣ::  ኃጥያት ባይኖርበትም እንደህጉ ለእርሱም መስዋእት ቀረበ::

ስምኦን ጌታውን ጠበቀ በመንፈስ እንደተረዳውም ተቀብሎም አቀፈው::  የተሰጠን የተስፋ ቃል የሚወረስ ነው::  አምላካችን የተናገረውን የሚፈጽም ነው:: አሜን! 

አባት ሆይ ክብርህን ትተህ እኔን ፍለጋ ተዋርደህ ስለመጣህልኝ አመሰግናለሁኝ:: እገዛልሃለሁኝ: አመልክሃለሁኝ! አሜን!

ሉቃስ 2:29-35

30-31፤ ዓይኖቼ በሰዎች ሁሉ ፊት ያዘጋጀኸውን ማዳንህን አይተዋልና፤ 32፤ ይህም ለአሕዛብ ሁሉን የሚገልጥ ብርሃን ለሕዝብህም ለእስራኤል ክብር ነው።”

ስምእኦን የምጠብቀውን አይቻለሁና አሰናብተኝ እያለ ነው::  የሚገርመው ይህ ሰው የተቀባውን ሳያይ ሞትን እንዳያይ በመንፈስ ቅዱስ ተረድቶ ነበርና ጌታን ባመጡትበት ቀን በመንፈስ ተመርቶ ወደ መቅደስ መጣ:: መጥቶም የሚጠባበቀውን ጌታ አቀፈ::ብዙዎች እናውቃለን ያሉ በመካከላቸው የተገኘውን ጌታ አላወቁትም::

እንደስምኦን ከመንፈስ ቅዱስ ጋር የበረታ ህብረት ሊኖረን ይገባል እርሱ መቼም አያደላ በፊቱ እንሁን እንጂ ይመራል ይናገራል::  ጌታ እየሱስ እንዳለን ከእኔ ወስዶ ለእናንተ ይነግራል ስለወደፊቱም ያሳውቃችኃል ብሏል::  እንጠማው መንፈስ ቅዱስን ያለ እርሱ አንዳች ማድረግ አይቻልም::

ስምኦን ስለጌታ ያለውን እናስተውል ያዘጋጀኸውን ማዳንህን እንዲሁም ለአሕዛብ ሁሉ የሚገልጥ ብርሃን ለሕዝብህም ለእስራኤል ክብር ነው። ይሄ ቃል ኪዳን የተገባው ለአብርሃም ነበረ በአንተ የምድር  ነገዶች ሁሉ ይባረካሉ ተብሎ ነበረ:: ይህ የሚባርክ ጌታ ለአህዛብ ሁሉ መጣ ወይም ለሰው ልጆች!  በደህንነት ስራው ውስጥ አህዛብን ሁሉ ያሰበ ጌታ ይባረክ!  ዛሬ በፊቱ ይህ ብርሃን በርቶልን ቆመናልና ክብር ምስጋና ይብዛለት!

አባት ሆይ ከአንተ ጋር ህብረት ማድረግ በመንፈስ መመላለስ የጊዜውንና የውደፊቱን እቅድህን ከአንተ በመስማት የነቃን አድርገን በምትሰራበትም ጊዜ ገንዘቦችህ አድርገን::  አሜን!

ሉቃስ 2: 36-40

38፤ በዚያችም ሰዓት ቀርባ እግዚአብሔርን አመሰገነች፤ የኢየሩሳሌምንም ቤዛ ለሚጠባበቁ ሁሉ ስለ እርሱ ትናገር ነበር።

40፤ ሕፃኑም አደገ፥ ጥበብም ሞልቶበት በመንፈስ ጠነከረ፤ የእግዚአብሔርም ጸጋ በእርሱ ላይ ነበረ።

ነብይት ሃና በጣም አርጅታ ነበር፤ በጾምና በጸሎትም ሌሊትና ቀን እያገለገለች ከመቅደስ አትለይም ነበር። አርጅታም እንኳን ከአገልግሎት አልታጣችም በዚህም ላይ ጨምራ በጾምና በጸሎት ሌሊትና ቀን ትተጋ ነበረ::  ይገርማል!!  ጌታ ግን አይቷት ነበረና ወደ ቤተመቅደሱ ባመጡት በዚያው ሰዓት የምትጠባበቀውን ጌታ አገኘችው::  ይገርማል በዚያች ሰዓት ተገኘች!  እርስዋም የኢየሩሳሌምንም ቤዛ ለሚጠባበቁ ሁሉ ስለ እርሱ ትናገር ነበር።

እኛም ዛሬ ጌታ ሊመጣ በደጅ ባለበት ሰዓት ላይ ነንና በትጋት እንጠባበቅ ስምኦንም ሃናም ያደረጉት ይህንኑ ነው ደግሞም አላፈሩም አገኙት::  ሌላው ስለእርሱ ትናገር ነበረ ይላል::  ወንጌልን ልንናገር የተጠራን ነንና ስለጌታችንና አምላካችን ማዳን በነፃ ስለሆነው ወንጌል እንናገር::

ሕፃኑም አደገ፥ ጥበብም ሞልቶበት በመንፈስ ጠነከረ፤ የእግዚአብሔርም ጸጋ በእርሱ ላይ ነበረ። አሜን!  ይህ የእግዚአብሔር ጸጋ በእኛም ላይ ይሁን ጥበብን ይሙላብን ያበርታን ያጠንክረንለተጠራንለትጥሪ ያስታጥቀን::

አባት ሆይ ልትመጣ በደጅ ነህና  ተዘጋጅተን በመክሊታችንም አትርፈን ዘይታችንም ሞልቶ እንድንገኝ እርዳን:: አሜን!

ሉቃስ 2: 41-52

49፤ እርሱም፦ “ስለ ምን ፈለጋችሁኝ? በአባቴ ቤት እሆን ዘንድ እንዲገባኝ አላወቃችሁምን?” አላቸው።

50፤ እነርሱም የተናገራቸውን ነገር አላስተዋሉም።

የአንድ ቀን መንገድ ከሄዱ በኃላ ነበረ ዮሴፍና ማርያም ብላቴናው ኢየሱስ ከፋሲካው በዓል አብሯቸው እንዳልተመለሰ ያስተዋሉትና ፍለጋ የተመለሱት:: ባዩትም ጊዜ ተገረሙ፥ እናቱም፦ “ልጄ ሆይ፥ ለምን እንዲህ አደረግህብን? እነሆ፥ አባትህና እኔ እየተጨነቅን ስንፈልግህ ነበርን፡” አለችው። እርሱ ግን  “ስለ ምን ፈለጋችሁኝ? በአባቴ ቤት እሆን ዘንድ እንዲገባኝ አላወቃችሁምን?” ሲላቸው እነርሱ ግን አላስተዋሉም:: በዓመት አንድ ጊዜ ወንድ ሁሉ በእግዚአብሔር ፊት መታየት ስላለበት ይህንኑ ለመፈጸም መገኘታቸውን ብቻ ነው ያሰቡት::  ሊፈልጉት የሄዱት ጌታ በመካከላቸው እየተመላለሰ እንዳለ ባወቁ!

እየመለሰላቸው ያለው አባቴ እግዚአብሔር ነው የምገኘውም በቤቱ ነው እያላቸው ነው:: በ12 ዓመቱ የአባቱን ቤት ስራ እየሰራ ነበረ::  ከቤተሰቡ ስር እንኳን ወደኃላ ቢቀርም ብዙም አልተሰማውም::  እኛም ጉዳያችን ሁሉ ስለቤቱ ስራ መሆን አለበት:: ልጆቻችንንም ወደቤቱ እንዲመጡና እንዲተከሉ እናድርግ ደግሞም እንጸልይ::

አባት ሆይግድ የሚለን የአንተ ቤት ስራ ይሁን የምትናገረንንም እንድናስተውል እርዳን::  ልጆቻችንም በቤትህ ይለምልሙ እራስህንም ግለጥላቸው:: በኢየሱስ ስም አሜን!

ሉቃስ 3: 1-20

2፤ ሐናና ቀያፋም ሊቃነ ካህናት ሳሉ፥ የእግዚአብሔር ቃል ወደ ዘካርያስ ልጅ ወደ ዮሐንስ በምድረ በዳ መጣ።

አንድ ሊቀ ካህናት መኖር ሲገባው ሁለት ናቸው ሐናና ቀያፋ::  በትክክለኛው በእግዚአብሔር የሚ ታወቀው ቀያፋ ነበረ ህዝብ ሁሉ ከሚጠፋ አንድ ሰው ስለህዝቡ ይሙት ብሎ ትንቢትን የተናገረ ነው:: ታሪክ እንደሚነግረን ግን ሮማዎች እንዲወርድ አስገድደውት ነው::

የእግዚአብሔር ቃል ወደ ዘካርያስ ልጅ ወደ ዮሐንስ በምድረ በዳ መጣ ይላል::  መጥምቁ ዮሐንስ ትልቅ አገልግሎት ይዞ የመጣ ነው:: ይህንንም እንዲፈጽም በመንፈስ ቅዱስ ተሞልቷል::  መንገዱን ለጌታ የሚያስተካክል ሰው ነበረ::  ከፍ ያሉትን ቃሉን እናውቃለን ከእኛ ሌላ ማን አለ የሚሉትን ዝቅ በሉ ዝቅ ያሉትን ቀራጭ የነበሩትን ለእናንተም ነው ጌታ የመጣው ተጠባበቁ:: ህይወታቸው የተበለሻሸውንም እንደነ መቅደላዊት ማርያም ያሉትን ጠብቁ መፍትሄ እየመጣ ነው ያለ ድምጽ ነው:: ድምጹም:- “ሥጋም የለበሰ ሁሉ የእግዚአብሔርን ማዳን ይይ፡”  አሜን!  እኛም አህዛቦች ይኸው ማዳንህን አየን! ተመስገን!

ሁሉን አንድ ሊያደርግ የመጣ ጌታ አይሁድ የለ አህዛብ ወይም ወንድ የለ ሴት ደግሞም ጨዋ የለ ባርያ! ሁሉም በክርስቶስ አንድ ነው::  የጥሉን ግድግዳ ሁሉ አፈረሰው:: 

ማነህ ሲባል ዮሐንስ:- ዮሐንስ መልሶ፦ “እኔስ በውኃ አጠምቃችኋለሁ፤ ነገር ግን የጫማውን ጠፍር መፍታት ከማይገባኝ ከእኔ የሚበረታ ይመጣል፤ እርሱ በመንፈስ ቅዱስና በእሳት ያጠምቃችኋል፤ መንሹም በእጁ ነው፥ አውድማውንም ፈጽሞ ያጠራል፥ ስንዴውንም በጎተራው ይከታል፥ ገለባውን ግን በማይጠፋ እሳት ያቃጥለዋል፡” አላቸው።

አባት ሆይ አንተ በመንፈስ ቅዱስና በእሳት አጠመከን::  ዮሐንስ የተላከበትን ስራውን በፍጹም ታዘዘና አገለገለህ::  እኛም የተጠራልነትን ስራህን እንድናገለግል እርዳን ጸጋ ይጨመርልን::  አሜን!

ሉቃስ 3: 21-38

21፤ ሕዝቡም ሁሉ ከተጠመቁ በኋላ ኢየሱስ ደግሞ ተጠመቀ። ሲጸልይም ሰማይ ተከፈተ፥ 22፤ መንፈስ ቅዱስም በአካል መልክ እንደ ርግብ በእርሱ ላይ ወረደ፤ የምወድህ ልጄ አንተ ነህ፥ በአንተ ደስ ይለኛል የሚል ድምፅም ከሰማይ መጣ።

ኢየሱስ ስለኃጥያት መጠመቅ አልነበረበትም እርሱ ግን ታዘዘና ተጠመቀ ትንቢቱ ይፈፀም ዘንድ::  በዚህ ጊዜ መንፈስ ቅዱስም በአካል መልክ እንደ ርግብ በእርሱ ላይ ወረደ፤ የምወድህ ልጄ አንተ ነህ፥ በአንተ ደስ ይለኛል የሚል ድምፅም ከሰማይ መጣ።

የምወድህ ልጄ አንተ ነህ፥ በአንተ ደስ ይለኛል ተባለ::  ይህንን ጌታ ልበሱት ተብለን ለበስነው አሁንም በአብ ፊት መታያችን እርሱ ነው::  አንድ ጊዜ አባቱንደስ አሰኝቷልና በእኛም ላይ ሲያየው ደስ ይለዋል::  እንጂ በአንዳች በስራችን ተቀባይነትን ያገኘን አይደለንም::

ኢየሱስም ሊያስተምር ሲጀምር ዕድሜው ሠላሳ ዓመት ያህል ሆኖት ነበር እንደመሰላቸው የዮሴፍ ልጅ ሆኖ፥ የኤሊ ልጅ አልነበረም::  እርሱ የእግዚአብሔር ልጅ ነው::  መንፈስ ቅዱስ በእርሱ ላይ ከመጣ በኃላ አገልግሌቱን ጀመረ::  እኛም መንፈስ ቅዱስ  እጅግ ያስፈልገናል ያለ እርሱ አንዳች ማድረግ አንችልም:: ኃይልን እስክትቀበሉ በእየሩሳሌም ቆዮ የተባሉትም ለዚሁ ነው ከመጣ በኃላ አገልግሎታቸውና ህይወታቸው እንዴት እንደተቀየረ እናውቃለን::

አባት ሆይ በመንፈስ ቅዱስ ኃይላችንን አድስ አንተን ደስ ማሰኘትና ማገልገል ይሁንልን::  አሜን!

ሉቃስ 4: 1-2

1፤ ኢየሱስም መንፈስ ቅዱስ መልቶበት ከዮርዳኖስ ተመለሰ፥ በመንፈስም ወደ ምድረ በዳ ተመርቶ፥ 2፤ አርባ ቀን ከዲያብሎስ ተፈተነ። በነዚያም ቀኖች ምንም አልበላም፥ ከተጨረሱም በኋላ ተራበ።

በዮሃንስ እጅ ዝቅ ብሎ ከተጠመቀ በኃላ መንፈስ ቅዱስ መልቶበት ከዮርዳኖስ ተመለሰ::   እንዲሁም በሐዋ. ሥራ 10:38፤ እግዚአብሔር የናዝሬቱን ኢየሱስን በመንፈስ ቅዱስ በኃይልም ቀባው፥ እርሱም መልካም እያደረገ ለዲያብሎስም የተገዙትን ሁሉ እየፈወሰ ዞረ፥ እግዚአብሔር ከእርሱ ጋር ነበረና፤ ይላል::

በመንፈስም ወደ ምድረ በዳ ተመርቶ፥  ሲወጣ የሆነው ነገር አልጋ ባልጋ አልነበረም::  የጠበቀው አርባውንም ቀን መፈተን ነው:: ቃሉም እንደሚል አርባ ቀን ከዲያብሎስ ተፈተነ።  ጌታ ሆኖ በመንፈስ ቅዱስ  ኃይልም ተሞልቶ እያለ ጠላት አልተኛም ስለዚህ በምናልፍበት በማንኛውም ፈተና ጌታ መፈተኑን እያየን እንበርታ::   በነገር ሁሉ የተፈተንና የሚራራ አምላክ ነው ያለን::

በነዚያም ቀኖች ምንም አልበላም፥ ከተጨረሱም በኋላ ተራበ። ጠላታችን ዲያቢሎስ የሚውጠውን ፈልጎ ያለ እረፍት ይዞራል ነገር ግን ጌታ ከእኛ ጋር ነውና አሸናፊዎች ነን::  ጠላት እንደሆነ መሞከሩን አይተውም  እኛም መታመናችንን አንተውም:: በፈተና የሚጸና  ብጹእ ነው እንደሚል እንጽና ጌታም መውጫውን ይሰጠናል አንደናገጥ አንርበትበት ከእኛ ጋር ያለውን እንወቅ::

ሉቃስ 4:3-4

3፤ ዲያብሎስም፦ “የእግዚአብሔር ልጅ ከሆንህ፥ ይህን ድንጋይ፦ ‘እንጀራ ሁን፡’ ብለህ እዘዝ፡” አለው። 4፤ ኢየሱስም፦ “ ‘ሰው በእግዚአብሔር ቃል ሁሉ እንጂ በእንጀራ ብቻ አይኖርም፡’ ተብሎ ተጽፎአል፡” ብሎ መለሰለት።

አርባውን ቀን ሁሉ በዲያቢሎስ ሲፈተን የቆየው ጌታ በነዚህ ቀናት ምንም አልበላምና ተራበ::  ሁሉን የፈጠረ ጌታ ተራበ?!  ይህንን ክፍተት ያወቀ ጠላት ቃል ይዞ ብቅ አለ:: ሄዋን ጋር  ተሳክቶለት ነበረና ይህንኑ ልምዱን ይዞ መጣ::  ይዞ የመጣው ቃል ጌታ እየሱስ ተጠምቆ ሲወጣ ድምጽ ከሰማይ መቶ ነበረና እሱኑ ይዞ መርዝ ቀላቅሎ መጣ::

የእግዚአብሔር ልጅ ከሆንህ፥ ይህን ድንጋይ፦ ‘እንጀራ ሁን፡’ ብለህ እዘዝ፡” አለው።  መርዙ ልጅ ከሆንክ ላይ ነው::  እንደሆነማ ተመሰከረ!  የሌላውን ማረጋገጫ ያላስፈለገው ጌታ ግን በኤፌሶን 6 ላይ እንደተማርነው ቃሉ የመንፈስ ሰይፍ ነውና አውጥቶ ተጠቀመበት:: ሰው በእግዚአብሔር ቃል ሁሉ እንጂ በእንጀራ ብቻ አይኖርም፡’ ተብሎ ተጽፎአል፡” ብሎ መለሰለት። አሜን! 

በጠላት ኃይል ሁሉ ላይ ስልጣን ተሰቶናል የሚጎዳንም የለም::  ጠላት የቀረለት ሽንገላ ነውና  ለዚህ ሽንገላው አንንበርከክ እናሳደው ከአሸናፊዎች በላይ ነንና በአይምሯችን መታደስ እንለወጥ ቃሉ ይለውጠው አስተሳሰባችንን::  መልክት ጌታ ሲናገር ጠላትም እየሰማ እንደሆነ እንወቅ::  እንንቃ ጠላት ዙሪያችንን የሚዞር ምንም ማድረግ የማይችል ነው እድል ካልሰጠነው::  ስለዚህ በቃሉ እውነት እንሞላ እንደቃሉም እናስብ::  የተቀበልነውን የተስፋ ቃል አጥብቀን እንያዝ እንዳያስጥለን:: የምንዋጋበትን የእግዚአብሔርን ቃል እንያዝ በዚህ ሁሉ ላይ  ደግሞ በጌታና በኃይሉ ችሎት እንበርታ!

ሉቃስ 4: 5-8

7፤ ስለዚህ አንተ በእኔ ፊት ብትሰግድ፥ ሁሉ ለአንተ ይሆናል፡” አለው። 8፤ ኢየሱስም መልሶ፦ “ ‘ለጌታ ለአምላክህ ስገድ እርሱንም ብቻ አምልክ፡’ ተብሎ ተጽፎአል፡” አለው።

አርባ ቀን ሙሉ ሲፈትነው የቆየው ዲያቢሎስ መቼም ኢችን ሶስት ሽንገላ ብቻ አይደለም ወደእርሱ ይዞ የመጣው ብዬ አስባለሁ::  ልጅ ከሆንክ የሚለው ወጥመዱ መክሸፉን ሲያይ ስገድልኝና ክብርን ሁሉ ልስጥህ ብሎ መጣ::

የሚገርመኝ ነገር የዓለምን መንግሥታት ሁሉ በቅጽበት አሳየው።  ይህ ሥልጣን ሁሉ ክብራቸውም ለእኔ ተሰጥቶአል፥ ለምወደውም ለማንም እሰጠዋለሁና ለአንተ እሰጥሃለሁ ማለቱ ነው:: ማን ሰጠውና? አዳምም አይደል?  አሁን መቀምያው እንደሆነ አላወቀ!  ለመስቀል ሞት በመታዘዝ ከስም ሁሉ በላይ የሆነ ስምን ሰቶን እናንበረክከዋለን ዛሬ::  በትንሳኤው ጉልበት ኢየሱስ ከሞት ተነስቶ የሞትና የሲኦልን ቁልፍ ይዟል::  ለዲያብሎስ የቀረ ስልጣን የለም ሁሉንም ተቀምቷል ያለው ሽንገላ ብቻ ነውና በቃሉ እውነት ተሞልተን ስራውን እናፍርስበት:: 

ሰው ዓለሙን ሁሉ ቢያተርፍ ነፍሱን ግን ቢያጣ ምን ይጠቅመዋል?!  መርዙ ቀላል አይደለም የሚመጣበት መንገድ ረሃብን እንዲሁም ብልጽግናንና ክብርን አስታኮ መጣ::  ድፍረቱ ለፈጠረው ጌታ ይህንን ሁሉ ክብር ስገድልኝ እንጂ እሰጥሃለሁ ይላል ::  በዙሪያችንም ስናይ ማን ለእርሱ ሰግዶ በሰላም ተቀመጠ?  ፍፃሜያቸውን አይተናል::  የእኛ ጌታ ግን እውነተኛ እረኛ የዓለምን ክብር ሳይሆን እራሱን ሰጠን ወደንና ፈቅደን ደስም ብሎን እንሰግድለታለን::

ኢየሱስም መልሶ፦ “ ‘ለጌታ ለአምላክህ ስገድ እርሱንም ብቻ አምልክ፡’ ተብሎ ተጽፎአል፡” አለው። አሜን!  ሊሰገድለትና ሊመለክ የሚገባው ለእርሱ ብቻ ለፈጠረን በደሙም ለዋጀን ለእውነተኛው ጌታ ብቻ ነው::  አሜን!!

አባት ሆይ እኔም ትውልዴም አንተን ብቻ እናመልካለን ለአንተም ብቻ እንሰግዳለን! አሜን! 

ሉቃስ 4:9-13

ሉቃስ 4:12፤ ኢየሱስም መልሶ፦ “ ‘ጌታን አምላክህን አትፈታተነው’ ተብሎአል፡” አለው።

ወድቀህ ብትሰግድልኝ ይህንን ሁሉ ክብር ለምወደው እሰጣለሁ ሲል ትንሽ ስቅጥጥ አይለውም ሲዋሽ::  ምን መውደድ አለው መግደልና ማጥፋት እንጂ! ይሄኛው ፈተናው ስለከሸፈበት ወደ ታች ራስህን ወርውር በሚለው ፈተና ተገለጠ:: 

ጠላት ያለውን ሁሉ ወርድሯል ከዚህ በላይ ምንም ማድረግ አይችልም ምክንያቱም ፍጥረት ነው ያልቅበታል::  ይዞ  የሚመጣውም ፈተና እስከአሁን የተጠቀመበትን ነው:: ብትወድቅ መልአክቱን ስለአንተ ያዝልሃል ሲለው ኢየሱስም መልሶ፦ “ ‘ጌታን አምላክህን አትፈታተነው’ ተብሎአል፡” አለው። በቃሉ መለሰለት እንጂ  ጌታችን በሌላ መልኩ ሲጋበዝ አናየውም ጀግና ጀግና መጫወት የለብንም::  ቃሉና ስሙ በቂ መዋግያ ነው::

በ1 ዮሐንስ 2:15-16፤ ዓለምን ወይም በዓለም ያሉትን አትውደዱ፤ በዓለም ያለው ሁሉ እርሱም የሥጋ ምኞትና የዓይን አምሮት ስለ ገንዘብም መመካት ከዓለም ስለ ሆነ እንጂ ከአባት ስላልሆነ፥ ማንም ዓለምን ቢወድ የአባት ፍቅር በእርሱ ውስጥ የለም። የጌታን መፈተን በዚህ ቃል ውስጥ እስኪ እንየው ያልተፃፈልን አቅጣጫ የለምና:- 

የሥጋ ምኞት የሚለውን ምሳሌው ድንጋዮን ዳቦ አድርግ ያለበት አይነት ነው::

የዓይን አምሮት – (ሄዋንንም የጣለበት) ወድቀህ ብትሰግድልኝ ይህንን ሁሉ ክብር እሰጥሃለሁ ያለው ነው::

ስለ ገንዘብም መመካት – ትምክህት/ትዕቢት ብዙ መገለጫ አለው  እኛ ግን የተባልነው ትሁት እንድንሆን ነው በፈተና  ከመውደቅ ይጠብቀናልና:: የሚመካ በጌታ ይመካ!

ስለዚህ በምናልፍበት ነገር አናድንቅ ለሁሉ ነውና ፈተና:: በ1 ቆሮንቶስ 10:13፤ ለሰው ሁሉ ከሚሆነው በቀር ምንም ፈተና አልደረሰባችሁም፤ ነገር ግን ከሚቻላችሁ መጠን ይልቅ ትፈተኑ ዘንድ የማይፈቅድ እግዚአብሔር የታመነ ነው፥ ትታገሡም ዘንድ እንድትችሉ ከፈተናው ጋር መውጫውን ደግሞ ያደርግላችኋል።

ዲያቢሎስም ፈተናውን ሁሉ ከጨረሰ በኋላ እስከ ጊዜው ከእርሱ ተለየ። በያዕቆብ 4:7፤ እንግዲህ ለእግዚአብሔር ተገዙ፤ ዲያብሎስን ግን ተቃወሙ ከእናንተም ይሸሻል::  ተመልሶ አይመጣም አልተባልንም ይሸሻል ወይም ለጊዜው ተለየ እንጂ::  እግዚአብሔር ማንንም አይፈትንም ዲያቢሎስ ነው የሚፈትነን በቃሉ ተሞልተን ጸንተን እንቃወም::  ነገራችንን ከሰው ጋር አናያይዝ ከኃላ ያለውን እንንቃበትና እንምታው! 

ሉቃስ 4: 1-13 (ክለሳ)

1፤ ኢየሱስም መንፈስ ቅዱስ መልቶበት ከዮርዳኖስ ተመለሰ፥ በመንፈስም ወደ ምድረ በዳ ተመርቶ፥

ይህንን ክፍል ትንሽ ደቆስ አድርገን እንጭመቀው ብዬ ነው እንደገና ያጠናሁት::  ምክንያቱም በተለያየ ፈተና እናልፋለንና ጠላት ምን ላይ እንደሚያተኩርና እኛስ ምን ማድረግ አለብን እንድናስተውል ነው::

ከሶስቱ ፈተናዎች ሁለቱ ልጅ ከሆንክ ነው የሚሉት::  ለምን ልጅነትን ይመታል? እሱን ከወሰደብን ሌላ የምንቆምበት መሰረት ያሳጣናልና ነው::  አንቺን ብሎ ክርስትያን ሲለን እውነትም ብለን ስብር እንልና ምህረትና ጸጋ እንዳለ እንረሳለን::  ያኔ ለእርሱ ይመቸዋል ከቅዱሳንና ከቤተክርስትያን  ያርቀናል ከዛማ ካልነቃን ከባድ ነገር ውስጥ ይከተናል::  ብንደክም ለጌታ ብንበረታ ለጌታ::  ለፈተናው መመለስ ያለብን እየሱስ ነው በእኔ ውስጥ ክርስትያን ድሮውንም በራሴ አልጸደኩ:: እንዲያውም ጠላቴ በድካሜ ጸጋውን ይሰጠኛል  በትከሻውም የሚሸከመኝ እረኛ አለኝ ሮጬ ወደ እርሱ እሄዳለሁ ይረዳኛል ብለን መመለስና መበርታት  ይገባናል:: በክርስቶስ ምን እንደሆንን ከቃሉ ጠንቅቀን እንወቅ::  

ምን እናድርግ:-

ወደ ፈተና እንዳትገቡ ትጉና ጸልዮ ተብለናል::  ፈተና የለም አላለንም አሸንፌያለሁ ብሎናል:: እራሱም እየሱስ በመጨረሻዋ ሰዓት ብቻውን ተጋ እንጂ ሐዋርያቱማ እንቅልፍ እንቅልፍ ብሏቸው ነበረና ጌታ ስለእነርሱም ማለደ::  ስለእራሳችን ብቻ ሳይሆን ስለቅዱሳንም መማለድን አንርሳ::  ፈተናው መጥቶ ሲመታን በአለቱ ላይ ቤታችንን ሰርተናልና ሰባብሮ ይዞን  አይሄድም::

እንዳንረታ በክርስትና ዋናው ሃብታችን መንፈስ ቅዱስ ነው::  ጌታ እየሱስ በመንፈስ ተሞልቶ ነው አርባውንም ቀን እየተፈተነ በርትቶ ለአንዱም የሰይጣን ፈተና ሳይወድቅ እኛን ተቤዥቶ ያለው:: ዛሬ የሚራራልን ሊቀ ካህናት ቢፈተንም ያልተረታ አለልን::  ስለዚህ ዕለት ዕለት በመንፈስ ተሞሉ እንደሚል ጠይቀን  እንሞላ::  እርሱ እንደሆነ በልግስና ሳይሰፍር መንፈሱን ይሰጠናል::  ስሙ ይባረክ! 

ሌላው ጌታ እየሱስ ከዲያቢሎስ ጋር አታካራ አልገባም ::  ይመልስ የነበረው የተጻፈው ቃል ነበረ:: ስለዚህ ዛሬም መዋጊያችን በሁለት በኩል የተሳለው የመንፈስ ሰይፍ ነው:: ቃሉን እንብላ እናሰላስለው ከእርሱም ፈቀቅ አንበል በጸሎትም እንትጋ:: 

ሉቃስ 4: 14-21

17-19፤ የነቢዩንም የኢሳይያስን መጽሐፍ ሰጡት፥

ኢየሱስም በመንፈስ ኃይል ወደ ገሊላ ተመለሰ፤ ስለ እርሱም በዙሪያው ባለችው አገር ሁሉ ዝና ወጣ።   ከአርባ ቀን ጾም በኃላ ኢየሱስ የበረታው  በመንፈስ ኃይል ነበረ::   የጌታ ዝና እየወጣ ሄደ በምኩራብም ያስተምር ጀመረ::  በዚህም ጊዜ ነው የኢሳያስን መጽሐፍ የሰጡትና አንብቦ ሳያብራራ የተቀመጠው:: ምን ማብራራት ያስፈልጋል በፊታቸው ቆሞ እየፈጸመው?!  ማስተዋል ይስጠን ከጌታ ጋር እንዳንተላለፍ::

ክፍሉም የሚለው: የጌታ መንፈስ በእኔ ላይ ነው፥ አሜን ይህ መንፈስ በእኛም ላይ ነው:: ምን ለማድረግ?

– ለድሆች ወንጌልን እሰብክ ዘንድ ቀብቶኛልና፤ 

– ለታሰሩትም መፈታትን 

– ለዕውሮችም ማየትን እሰብክ ዘንድ፥ 

– የተጠቁትንም ነጻ አወጣ ዘንድ 

– የተወደደችውንም የጌታን ዓመት እሰብክ ዘንድ ልኮኛል፡:

የተላከበትን ዓላማ ቁልጭ አድርጎ ነገራቸው::  እኛም የተላክነው ለዚሁ ነው:: እኛም የተላክነው ለድሆች: ለታሰሩ: ለዕውሮችና ለተጠቁት ነው::  ወንጌል ስለእየሱስ ነው ይህንን ሁሉ የሚያደርግና የሚሰራ እራሱ በመንፈሱ ነው:: እንዲሁም የተወደደችውንም የጌታን ዓመት ሰበከ ይህም ማለት እዮበልዮ ነው በዕዳ ሁሉ የተያዙት በየ50 ዓመቱ ነፃ የሚወጡበት ጊዜ ነውና የጌታ ዓመት ሲላቸው በደንብ ይገባቸዋል:: ማንም ዕዳ አይኖርበትም ብሎ አወጀ እኛም ነፃ ሆንን የሚከሰን እስከማይኖር ድረስ – ማንም በክርስቶስ ቢሆን ኩነኔ የለበትም:: ይህንን እንድንሰብክ ተጠርተናል::  ማለትም የእግዚአብሔር በግ እየሱስ ተገልጧል የዕዳው  ጽህፈት ተደምስሷል ሞትና ሲዖልም ድል ተነስተዋል አርነት ታውጇል ብለን እናውጃለን:: አሜን!

አባት ሆይ ስራችንን ችላ እንዳንል እርዳን! አሜን

ሉቃስ 4: 22-30

22፤ ሁሉም ይመሰክሩለት ነበር ከአፉም ከሚወጣው ከጸጋው ቃል የተነሣ እየተደነቁ፦ “ይህ የዮሴፍ ልጅ አይደለምን?” ይሉ ነበር።

ወንጌል ምን እንደህነና ለማን እንደሆነ ከትንቢቱ ነገራቸው:: ወንጌል ለድሆች: ለታሰሩት: ለዕውሮችና ለተጠቁት ነው::  ይህንን መስፈርት ስላሟላን ይህንን ጌታ አወቅን እንጂ አንዳች በእኛ ባልሆነ መንገድ ዳንን::  ይህንንም ወንጌል ልናደርስ አደራ ተሰጠን:: እንዲሁም የተወደደችውን የጌታን ዓመት ይኸውም የመምጣቱንና የመመለሱን ዜና እንድንናገር ተጠርተናል::ማራናታ!

ከልጅነቱ ጀምሮ ወዳደገበት ወደ ገሊላ መጥቶ ሲያስተምር ይህ የዮሴፍ ልጅ አይደለምን? ማለትን ጀመሩ ከአፉ ከሚወጣው ከጸጋው ቃል የተነሳ እየተደነቁ::  መተላለፍ ሆነባቸው ከእግዚአብሔር ልጅ ጋር የዮሴፍ ልጅ መስሏቸው::  ስለዚህም ይለይላችሁ ብሎ የኤልያስን ወደ ሰረፕታዋ መበለት መላክና ስለንዕማን ለምጽ ነገራቸው:: 

ብዙ መበለቶች በእስራኤል ቢኖሩም እንኳን የተላከው ወደ አህዛቢቷ ሴት ነበረ::  በእስራኤልም ብዙ ለምጻሞች እያሉ ከሩቅ መጥቶ ንዕማን ተፈወሰ::  ስለዚህ የእግዚአብሔርን ማዳን ካልተቀበላችሁ አሁንም ይኸው ነው የሚሆነው እያላቸው ነው::  በቅድሚያ ለጠፋው ለእስራኤል ነበር ወንጌል አልሰማም ሲሉ ወደ አህዛብ ደረሰ::  ይኸው ዛሬ የከበረውን ቃል እየተመገብን ከመንፈሱም እየጠጣን አለን::  እስራኤል ግን እስከዛሬ ጠፍታለች::  አቤቱ ለዚህ ህዝብ ወንጌል ይድረስ ደንዳናውን ልባቸውንም ፈስው:: አሜን!

ይህ ንግግሩ አስቆጥቷቸው ከከፍታ ላይ ሊጥሉት  ወሰዱት  እርሱ ግን ጊዜው አልደረሰምና  በመካከላቸው አልፎ ሄደ::  ሰው በዚህ እንኳን እንዴት አያስተውልም?!  በሌላ ስፍራ ካለማመናቸው የተነሳ ብዙ ማድረግ አልቻለም ነበር::  ነብይ በአገሩ አይከበርም::

አባት ሆይ እኛን የበረሃ ወይራ የነበርነውን አሰብከን በወይኑም ግንድ ላይ አደረከን ተመስገን::  ወንጌልን ይዘን እንሮጥ ዘንድ ልጆችህን እርዳን::  አሜን!

ሉቃስ 4: 31-37

32፤ ቃሉ በሥልጣን ነበርና በትምህርቱ ተገረሙ።

ባደገበት ከተማ የዮሴፍ ልጅ አይደለምን ብለው ሳይሰሙት ቀሩ:: ወደ ቅፍረናሆም ወርዶ ሲያስተምር ቃሉን በስልጣን ያስተምር ነበረና በትምህርቱ ተገረሙ::

እያስተማረም አጋንንት ያደረበት ሰው “ተው፥ የናዝሬቱ ኢየሱስ ሆይ፥ ከአንተ ጋር ምን አለን? ልታጠፋን መጣህን? ማን እንደ ሆንህ አውቄሃለሁ፥ አንተ የእግዚአብሔር ቅዱሱ፡” አለ። ኢየሱስም፦ “ዝም በል ከእርሱም ውጣ” ብሎ ገሠጸው። ጋኔኑም በመካከላቸው ጥሎት ሳይጐዳው ከእርሱ ወጣ።

ማን እንደ ሆንህ አውቄሃለሁ፥ አንተ የእግዚአብሔር ቅዱሱ::  አጋንንት በደንብ አውቀውታል የእግዚአብሔር ህዝብ ግን አላወቀም::  የጠላትን ምስክርነት አንፈልግም የልጅነት ስልጣን የተሰጠንና ከአሸናፊዎችም በላይ መሆናችንን ቃሉ መስክሮልናልና ሌላ ምስክር አያስፈልገንም:: ዛሬም ይህንን የተሸነፈ አጋንንት በስሙ ስልጣን እያወጣን ሰዎችን ለጌታ እንማርክ::  እርሱም ይወጣል! 

ከዚህ ተአምር በኃላ ዝናው  በዙሪያው ባለች አገር ወደ ስፍራው ሁሉ ስለ እርሱ ወጣ። ይህ እንዲሆን ቅናቴ ነው – የኢየሱስ ዝና ይውጥና ሰዎች ወደ እርሱ ይሰብሰቡ!  እኛን ሳይሆን እርሱ ይታይ! መዳን ይታወጅ!  ለታሰሩትና ለታወሩት ወንጌል ይድረስ::  አሜን!  አንብበንና ሰምተን እንድንሄድ ሳይሆን እንጸልይ የመከሩ ጌታ የመከሩን ሰራተኞች እንዲጨምርና እኛንም እንዲልከን:: 

አባት ሆይ እኔንም ላከኝ ወደ መከሩ ሰውን አጥማጅ አድርገኝ::  አሜን

ሉቃስ 4: 38-41

40፤ ፀሐይም በገባ ጊዜ በልዩ ልዩ ደዌ የተያዙ በሽተኞችን ሁሉ ወደ እርሱ አመጡአቸው፤ እርሱም በእያንዳቸው ላይ እጁን ጭኖ ፈወሳቸው።

በእያንዳቸው ላይ እጁን ጭኖ ፈወሳቸው።  እንዴት ደስ ይላል ባለመለየት ሁሉንም ፈወሰሰ:: ጌታ ኢየሱስ ዛሬም ይፈውሳል::  በመገረፉ ቁስል እኛ ተፈወስን::  መፈወሳችንም ደስ ያሰኘዋል የልጆችም እንጀራ ነው ብሎ ጠርቶታልና በአባታችን ቤት መብል አንከለከልም:: አጋንንትም በስሙ ይወጣል!

አባት ሆይ ስምህ ይባረክ!  ረውስን ለህዝብህ ሰተሃልና ዛሬም በህመም የሚሰቃዮ በኢየሱስ ስም ይፈወሱ::  አሜን!

ሉቃስ 4:42-44

43፤ እርሱ ግን፦ “ስለዚህ ተልኬአለሁና ለሌሎቹ ከተማዎች ደግሞ የእግዚአብሔርን መንግሥት ወንጌል እሰብክ ዘንድ ይገባኛል፡” አላቸው።

በጸባም ጊዜ ወጥቶ ወደ ምድረ በዳ ሄደ፤ ሕዝቡም ይፈልጉት ነበር፤ ምክንያቱም ፈውስንና የአጋንንትን መታዘዝ አይተው ነበረና  ወደ እርሱም መጡ፥ ከእነርሱም ተለይቶ እንዳይሄድ ሊከለክሉት ወደዱ። እዚህ ኑር አስተምረን ፈውሰን የትም አትሂድ ነው አባባላቸው::  

እርሱግን በየስፍራው ሁሉ የመንግስትን ወንጌል እየሰበከ ዞረ:: ዛሬም በስፍራ ሁሉ መሰበክ አለበት ጌታ ሊመጣ በደጅ ነውና ከወገን ከቋንቋ ሁሉ ሰዎች ወደ ኢየሱስ ዘወር እንዲሉ::  ጌታ ጸጋውን ያብዛልን ይህንን ወንጌል ይዘን እንድንሮጥ::

ሉቃስ 5: 1-3

3፤ ከታንኳዎቹም የስምዖን ወደ ነበረች ወደ አንዲቱ ገብቶ ከምድር ጥቂት ፈቀቅ እንዲያደርጋት ለመነው፤ በታንኳይቱም ተቀምጦ ሕዝቡን ያስተምር ነበር።

ጌታ ጴጥሮስን ጥቂት ፈቀቅ እንዲያደርጋት ለመነው::  ለመነው የሚለው ነገር ልቤን ነካው የለመነውም ሊያገለግልበት ነው ውስጡ ከገባ በኃላ::  እኛም ውስጥ የገባው ጌታ በሮሜ 12:1፤ እንግዲህ፥ ወንድሞች ሆይ፥ ሰውነታችሁን እግዚአብሔርን ደስ የሚያሰኝና ሕያው ቅዱስም መሥዋዕት አድርጋችሁ ታቀርቡ ዘንድ በእግዚአብሔር ርኅራኄ እለምናችኋለሁ፥ እርሱም ለአእምሮ የሚመች አገልግሎታችሁ ነው። ተብለናልና ለጌታ  ያለ ስስት እራሳችንን እናቅርብ!  ጌታ ሆይ ጸጋህ ያግዘን!

ሉቃስ 5 : 4-7

4: ነገሩንም ከጨረሰ በኋላ፥ ስምዖንን፦ “ወደ ጥልቁ ፈቀቅ በል መረቦቻችሁንም ለማጥመድ ጣሉ፡” አለው።

ለሊቱን ሙሉ ባለሙያ የሆኑት ዓሳ አጥማጆች ምንም እንዳልያዙ ቢነግሩትም እርሱ ግን ጣሉት አላቸው:: በቃሉ ሰማይና ምድርን የፈጠረው ጌታ ዛሬ ቢደግምስ መፍጠሩን?  እነሆም በቃሉ መሰረት መረቡን መተው ሞሉት::  ዛሬም ጌታ ይህንን ማድረግ ይችላልና ሁኔታን አይተን አንመላለስ የጌታን ፊት እንጂ!  እርሱ ተአምራትን ያደርጋል እውቀታችንን አንደገፍ::

ሉቃስ 5: 8-11

8 ስምዖን ጴጥሮስ ግን ባየ ጊዜ በኢየሱስ ጕልበት ላይ ወድቆ፦ “ጌታ ሆይ፥ እኔ ኃጢአተኛ ነኝና ከኔ ተለይ፡” አለው። 9 ስላጠመዱት ዓሣ እርሱ ከእርሱ ጋርም የነበሩ ሁሉ ተደንቀዋልና፥

ሲፈልጉ አድረው ያጡትን ዓሳ በቃሉ መረባቸውን በሞላ ጊዜ ጴጥሮስ ማለት የቻለው “ጌታ ሆይ፥ እኔ ኃጢአተኛ ነኝና ከኔ ተለይ፡” አለው። አሁን ስለ ኃጥያት ምን አመጣው?  የፈለገውን አገኘ ግን የእግዚአብሔርን ልግስና የማይገባኝ ነኝ እኔ ኃጥያተኛ ነኝ ከእኔ ራቅ አለ::  የጌታ መገኘት ማንነቱን አሳየው::  ጌታም አትፍራ ሰውን አጥማጅ አደርግሃለሁ ብሎ ወደ አገልግሎት ጠራው:: የኃጥያተኞች ወዳጅ የተባለው  ጌታ ማንንም ሳይለይ አጥቦ አንጽቶ ይጠቀምብናል::  ሃሌሉያ!!

ሉቃስ 5: 12-16

12 ከከተማዎችም በአንዲቱ ሳለ፥ እነሆ፥ ለምጽ የሞላበት ሰው ነበረ፤ ኢየሱስንም አይቶ በፊቱ ወደቀና፦ “ጌታ ሆይ፥ ብትወድስ፥ ልታነጻኝ ትችላለህ፡” ብሎ ለመነው። 13 እጁንም ዘርግቶ ዳሰሰውና፦ “እወዳለሁ፥ ንጻ፡” አለው፤ ወዲያውም ለምጹ ለቀቀው።

በብሉይ ኪዳን ለምፃምን መንካት ያረክሳል  ስለዚህ ማንም አይቀርበውም የተገለለ ነው::  የዚህ ሰው ጥያቄ ግን ይገርማል ምን ቢያይና ቢተማመን ነው አንፃኝ ብሎ የጠየቀው?! ጌታ ግን ሳይሸሸው እንዲያውም ዳሶ እወዳለሁ ንፃ ብሎ ፈወሰውና ራስህን ለካህን አሳይ አለው::  ዋዉ ጌታ መታሰባችንን ይወዳል ስሙ ይባረክ!

ምንም እንኳን አትናገር ቢለውም ዝናው ወጣ ብዙ ሕዝብም ሊሰሙትና ከደዌአቸው ሊፈወሱ ይሰበሰቡ ነበር::  ዝናው በወጣ ጊዜ ግን እርሱ ወደ ምድረ በዳ ፈቀቅ ብሎ ይጸልይ ነበር ይላል::  እኛስ?  ያውም ጌታ ስራውን ሲሰራ መቼም እኛ አይደለን የምንፈውስ ወዴት ይሆን የምንሮጠው?  ወደ እግሮቹ  ይሁንልን! ከፊቱ አንታጣ!  እርሱ ዛሬም ይሰራል::  ጌታዬ ሆይ ክብርህን ወደ ራሳችንም ይሁን ወደ ሌላ ስጋ ለባሽ በመውሰድ እንዳንበድልህ እርዳን!

ሉቃስ 5:17 አንድ ቀንም ያስተምር ነበር፤ ከገሊላና ከይሁዳ መንደሮችም ሁሉ ከኢየሩሳሌምም መጥተው የነበሩ ፈሪሳውያንና የሕግ መምህራን ይቀመጡ ነበር፤ እርሱም እንዲፈውስ የጌታ ኃይል ሆነለት።

እነዚህ ፈሪሳውያንና የሕግ መምህራን ሲያስተምር ሰምተው ስህተት ለማግኘትና እርሱን ለመክሰስና ነገር ን ለመፈለግ ነው የሚከታተሉት እንጂ ለመማር ወይም የእግዚአብሔርን ድንቅ ስራ ለማየት አይደለም::  ያም ሆነ ይህመምጣታቸው ጥሩ ነው ቢያንስ ኒቆዲሞስን ወደጥያቄ አምጥቶታልና::

ለጌታ እየሱስ እንዲፈውስ የጌታ ኃይል ሆነለት ይላል:: ምን እንዲያደርግ? እንዲፈውስ!!!  መፈወሳችንን የሚወድ ጌታ ስሙ ይባረክ!!  ዛሬም ይሄ ኃይል ይገለጥ በእያንዳንዳችን ምክንያቱም ብዙዎች ፈውስ ያስፈልጋቸዋልና:: ያቺ ሴት ስትፈወስ ኃይል ከእኔ ወጣ አለ ብዙዎች እያጋፉት እርስዋ ግን ተንጠራርታ የልብሱን ጫፍ በእምነት ነካችና ፈውስ ሆነላት:: 

አባት ሆይ ይህ ኃይል በእኛም ህይወት ይስራ::  አሜን

ሉቃስ 5:18 – 26

20 እምነታቸውንም አይቶ፦ “አንተ ሰው፥ ኃጢአትህ ተሰረየችልህ፡” አለው።

ይህንን ሰው ወደጌታ ይዘው የመጡ ሰዎች የሚገርሙና የመጡበትን ዓላማ ሳይፈጽሙ የማይመለሱ ናቸው:: በእነርሱ እምነት ይህ ሰው ተፈወሰ::  እኛም ዛሬ በእምነት ወድፊቱ የምናቀርበው ልመና ይመለሳል::  በሌላው አንፃር ይህንን ንግግሩን ያልወደዱለት ነበሩ::  ያለ አንዱ እግዚአብሔር በቀር ማን ኃጥያትን ማስተሰረየት ይችላል ብለው አሰቡ::  ጌታም በምድር ላይ ኃጢአት ሊያስተሰርይ ለሰው ልጅ ሥልጣን እንዳለው እንድታውቁ፡” ብሎ፥ ሽባውን፦ “አንተን እልሃለሁ፥ ተነሣ፥ አልጋህን ተሸክመህ ወደ ቤትህ ሂድ፡” አለው። ወድያውም እንደተባለው አደረገ ፈውሱንም ተቀበለ:: ሊቀ ካህናቱም ይሁን ማን ይህንን ማድረግ አይችሉም የታረደው በግ ግን ኃጥያትን ይቅር ማለና መፈወስ ይችላል::  አሜን!

ከዚህም የተነሳ ሁሉንም መገረም ያዛቸው፥ እግዚአብሔርንም አመስግነው፦ “ዛሬስ ድንቅ ነገር አየን፡” እያሉ ፍርሃት ሞላባቸው።

ሉቃስ 5: 27-32

31 ኢየሱስም መልሶ አላቸው፦ “ሕመምተኞች እንጂ ባለ ጤናዎች ባለ መድኃኒት አያስፈልጋቸውም፤ 32 ኃጢአተኞችን ወደ ንስሐ እንጂ ጻድቃንን ልጠራ አልመጣሁም።”

ወንጌል ዛሬም ይኸው ነው!  ለሕመምተኞችና ለኃጢአተኞች ነው ኢየሱስ የመጣው ሊፈርድባቸው ሳይሆን ሊያድናቸው ነው::  ማኅበረሰቡ ከሚለው ባህላችን ከሚለው የምድር ቀመሮች ከሚያወሩት ሁሉ ወተን ሰውን በሰውነቱ አይተን የእግዚአብሔርም ክብር እንደጎደለው አውቀን ክርስቶስን ባለማዳላት እንስበክ::  ከጌታ ጋር ታረቁ እንበል::  እንደባህሉ ቢሆንማ ማቴዎስ ደቀ መዝሙር ባልሆነም ነበር:: ጌታ ይርዳን!

ሉቃስ 5: 33-39

35 ነገር ግን ወራት ይመጣል፥ ሙሽራውም ከእነርሱ ሲወሰድ ያንጊዜ፥ በዚያ ወራት ይጦማሉ።” 36: ደግሞም ምሳሌ እንዲህ ሲል ነገራቸው፦ “የአዲስ ልብስ እራፊ ባረጀ ልብስ ላይ የሚያኖር የለም፤ ቢደረግ ግን አዲሱን ይቀደዋል ደግሞም አዲስ እራፊ ለአሮጌው አይስማማውም።

ጥያቄያቸው “የዮሐንስ ደቀ መዛሙርት ስለ ምን ብዙ ይጦማሉ ጸሎትስ ስለ ምን ያደርጋሉ፥ ደግሞም የፈሪሳውያን ደቀ መዛሙርት ስለ ምን እንደዚሁ ያደርጋሉ፤ የአንተ ደቀ መዛሙርት ግን ይበላሉ ይጠጣሉም?” ነበር::  እነርሱ የሚጾሙትና የሚጸልዮት አንዱ ምክንያት መሲሁ እንዲገለጥ ነበረ እርሱ በመካከላቸው ቆሟል::  ጊዜውን ያልዋጀ ነበረ (የልማድ)::  ጊዜያችንን እንድንዋጅ ጌታ ይርዳን ከጌታ ተረድተን የጊዜውን ማድረግና በሚያስፈልግ ጊዜ ጾምን ማወጅ:: በተመደው አካሄድ ከመሄድ በአዲሱ በመረቀልን መንገድ  የጌታን ፈቃድ እያወቁ ከአዲስ አሰራሩ ጋር ተዋህዶ በመንፈስ እየተመላለሱ መጾምና መጸለይ ይሁንልን::

ሉቃስ 6:1-5

5 የሰው ልጅ የሰንበት ጌታ ነው፡” አላቸውም።

ስለጾም አነሱ መለሰላቸው ጌታ የሚፈልገው ጾም ምን አይነት እንደሆነም አያውቁም::  ኢሳ 58:1-9 ያለውን አይነት ውጤት ያለው ጾም እንጂ ልማድን አይደለም የሚፈልገው::  

እዚህም ክፍል ላይ ሰንበትን አልጠበቁም በእርሻው መካከል ሲያልፉ እሸት ቀጥፈው በልተዋል ነው ክሱ:: የሰንበት ጌታ እንደሆነ አውጆ ክሱ ተቀባይነት አላገኘም ከዚህ የባሰ ዳዊት አድርጏል ብሎ ሻረው ቃሉን ማንበብና ማወቅ ይለያያል ያወቀ ይኖርበታል::  አቤት ትኩረታቸው ሁሉ ልምድ ላይ ነው::  እኛም ሳናስብ በልምድ ተይዘን ዋናውን የተጠራልለትን ሰውን መውደድና ወደ ጌታ ማምጣት አስትቶን እንዳይሆን ጌታ ሆይ እርዳንና ሰፊ ልብን ስጠን!

በሆሴዕ 6:6 ከመሥዋዕት ይልቅ ምሕረትን፥ ከሚቃጠልም መሥዋዕት ይልቅ እግዚአብሔርን ማወቅ እወድዳለሁና::  አሜን!

አባት ሆይ በልምና በባህል ተጠርዤ እንዳልገኝ እርዳኝ የመረጥከውን አይነት ህይወት እንድመላለስና ቃልህንና ኃይልህን እንዳልስት እርዳኝ::

ሉቃስ 6: 6-11

9 ኢየሱስም፦ “እጠይቃችኋለሁ፤ በሰንበት በጎ ማድረግ ተፈቅዶአልን ወይስ ክፉ? ነፍስ ማዳንን ወይስ መግደል?” አላቸው።

ጥያቄውን እንኳን ያስተዋሉ አይመስለኝም::  እነሱን የያዛቸው ነገር ሰንበት ተደፈረ ነው::  የሰንበት ጌታ እንደሆነ ከሳምንት በፊት ነግሯቸው ነበር እነርሱ ጋር  ግን ቃሉ ጠብ አላለምና እንደወጥመድ ሊጠቀሙበት ተነስተዋል::  ጌታ መሆን የማይገባው ጌታ ሆኖ ፈውስን ሊከለክል ነበረ::  ጌታ ግን ወደ ምኩራብም ሲመጣም ያንን እጁ የሰለለችን ሰው አይቶት እጎበኘዋለሁ ብሏልና አሳቡን አላስቀየሩትም በሰንበት በጎ አደረገ!  ፍቅሩ ብዙ የሆነ ጌታ ስሙ ይባረክ!

ሁላቸውንም ዙሪያውን አየና ሰውዬውን፦ “እጅህን ዘርጋ፡” አለው። እርሱም እንዲህ አደረገ፥ እጁም እንደ ሁለተኛይቱ ዳነች። አሜን!  ሰውን በማዳንና በመፈወስ ደስ የሚለው ጌታ ዛሬም አልተለወጠም በዚሁ አሳብ ላይ ነውና ወደፊቱ እንምጣና እንፈወስ ሌሎችንም እናምጣና የጌታችንን ማዳን እናሳይ! ሃሌሉያ!

ሉቃስ 6: 12-16

12 በነዚህም ወራት ይጸልይ ዘንድ ወደ ተራራ ወጣ፥ ሌሊቱንም ሁሉ ወደ እግዚአብሔር ሲጸልይ አደረ።

ሙሉ ለሊት መጸለይ?!  እንዴት ደስ የሚል ነገር ነው? ከእኛም የሚጠበቅ ነው ምክንያቱም ጸጋን በልግስና ይሰጣልና::  በራሳችን በተለያየ ዘዴ ለተወሰነ ሰዓት ለጸሎት መትጋት ይቻል ይሆናል በጸጋ ግን ሲሆን ቀላል ነው::  እንደፈቃዱ አንዳች ብንለምን ይሰማናልና ይህንን በፊቱ የምንተጋበትን  ጸጋ ያፍስስልን!  አሜን! 

ጌታለሊቱን ሙሉ ሲጸልይ አድሮ በማግስቱ ያደረገው ነገር ደቀመዛሙርትን መርጦ መጥራት ነበረ::  እነዚህ በዚህ ሁሉ ጸሎት ውስጥ የተመረጡ ናቸው ወንጌልን ለዓለም ያደረሱት:: ለመንግስቱ ስራ እንበርታ!

ሉቃስ 6:17-19

19 ከእርሱም ኃይል ወጥቶ ሁሉን ይፈውስ ነበርና ሕዝቡ ሁሉ ሊዳስሱት ይሹ ነበር።

ወደ ጌታ ኢየሱስ ይመጡ የነበረው ሊሰሙትና ሊፈወሱ ነበር::  ኃይልም ወጥቶ ሁሉን ይፈውስ ነበርና :: ከርኵሳንም መናፍስት ይሠቃዩ የነበሩት ተፈወሱ:: 

ለሐዋርያት ያላቸው ከመሄዱ በፊት ኃይልን እስክትቀበሉ ድረስ በእየሩሳሌም  ጠብቁ ነበረ::  ይህ ኃይል ዛሬም ያስፈልገናልና ለመቀበል በፊቱ እንገኝ:  

አባት ሆይ ኃይልህን ሙላንና በእኛ ተጠቀም:: አሜን!

ሉቃስ 6:20-26

22 ሰዎች ስለ ሰው ልጅ ሲጠሉአችሁ ሲለዩአችሁም ሲነቅፉአችሁም ስማችሁንም እንደ ክፉ ሲያወጡ፥ ብፁዓን ናችሁ። 23 እነሆ፥ ዋጋችሁ በሰማይ ታላቅ ነውና በዚያን ቀን ደስ ይበላችሁ ዝለሉም፤ አባቶቻቸው ነቢያትን እንዲህ ያደርጉባቸው ነበርና።

የእግዚአብሔር ነገር ተቃራኒ ነው ለድሃው ጽድቅን ይሰጣል::   ስለስሙ ስንጠላ  ብጹዓን ናችሁ ይለናል ዋጋችሁም በሰማይ ታላቅ ነውና በዚያን ቀን ደስ ይበላችሁ ዝለሉም ይለናል እንጂ ተክዙ አላለንም::  በስሜ የሚያፍርብኝን አፍርበታለሁ የማያፍረውን ደግሞ እመሰክርለታለሁ ብሎናልና በህይወታችን እርሱን እናሳይ ደግሞም እንመስክር::  ጥላቻ ከመጣም እንደሰት:: አንድ በህብረታችን ውስጥ የነበሩ አባት ወግ ደርሶኝ ከእድር ተባርሬአለሁና አመስግኑልኝ ያሉትን አልረሳውም:: የገባው እንደዚህ ይላል::

ሉቃስ 6: 27

27 “ነገር ግን ለእናንተ ለምትሰሙ እላችኋለሁ፥ ጠላቶቻችሁን ውደዱ፥ ለሚጠሉአችሁ መልካም አድርጉ፥

ጆሮ ያለው ይስማ:-

ከሰማን ጌታ ይናገራል ዙሩን እያከረረው ነው ያለው::  ጠላቶቻችሁን ውደዱ?! እንዴት ይቻላል?! ጠላት የተባለው በምክንያትም አይደለም እንዴ?  ጠላት እንዳለን ጌታም ያውቃል ግን ደግሞ ብቃትን ሰቶናልና የጌታ መልስ ለዚህ ጥያቄ በአዲሱ ሰው ይቻላል ነው በመንፈስ ተመላለሱ የሚል ነው::

ደቀመዝሙር  መሆናችን የሚታወቀው በፍቅራችን ነው የምንወደው ለይተን አይደለም የወዳጅና የጠላት የሚል ግሩኘ የለንም ሁሉ ወዳጅ ነው በጌታ ዲክሽነሪ:: ማስተዋል ይሁንልን እንደቃሉ እንድንመላለስ::  በክርስቶስም የተፈጠርነው መልካምን ለማድረግ ነውና ሰውን ሳንለይ መልካም እናድርግ::

ሉቃስ 6:28 የሚረግሙአችሁንም መርቁ፥ ስለሚበድሉአችሁም ጸልዩ።

የሚረግሙንን መመረቅ?  ቢያንስ መመረቁ ቀርቶ ዝም ብለን እንለፍ የሚለው ትንሽ ይሻላል የሰጡትን ሰፍሮ መመለስ ለሚያውቀው አእምሮ::  ነገር ግን በአእምሮ አንመራም የምንመራው በመንፈስ የምናመልከው በመንፈስ ነውና ልባችንን ወደ ጌታ እናንሳ::  ይህ የምንኖርበት አዲስ የህይወት መንገድና ዘይቤ ነው እንጂ ስንፈልግ ኦን ስንፈልግ ኦፍ የምናደርገው አይደለም::  እኛስ የክርስቶስ ልብ አለን:: ሰው በደህናው ክፉ አይሆንምና ክርስቶስን እንዲያውቁ እየባረክን እንጸልይላቸው  ለክፉ ንግግራቸውም እግዚአብሔር ይባርካችሁ እንበል:: ጠላት አንዳች እንዳያገኝ በድል መመላለስ እንዲሆንልን እራሳችንን በቃሉ እንፈትሽ! 

ስለሚበድሉአችሁም ጸልዮ ሲለን ጌታ ከዚህ በላይ ኖሮ ነው:: ለገረፉት ለተፉበት ለሰቀሉት የሚያደርጉትን አያውቁምና ይቅር በላቸው  ብሎ ጸልዮ አሳይቶን ነው::  ማንም ጸጋ ቢጎድለው በልግስና የሚሰጠውን ጌታን ይጠይቅ እንደሚል ቃልህ ጌታዬ ሆይ ሁሉን እየወደድን የምንጸልይበትን ጸጋ ስጠን በመንፈስ ቅዱስ በልባችን የፈሰሰውን ፍቅር  አያሳፍርምና ግለጠው:: አሜን!

ሉቃስ 6:29 “ጕንጭህን ለሚመታህ ደግሞ ሁለተኛውን ስጠው፥ መጐናጸፊያህንም ለሚወስድ እጀ ጠባብህን ደግሞ አትከልክለው።

ይሄ መቼም በእርግጥ መምታት ብቻ አይደለም ለምሳሌ:- ጌታ ኢየሱስን “ጋኔን አለበት፡ አብዶአልም፤ ስለ ምንስ ትሰሙታላችሁ?”   እንዲሁም “በአጋንንት አለቃ አጋንንትን ያወጣል” ሁሉ ይሉት ነበረ:: እርሱ ለዚህ ስድባቸው ሲመልስና ለእራሱ ሲከራከር አናይም::  በዘመናችን ዱላን ብዙም ላንቀምስ እንችላለን ስድብና ማሽሟጠጥ ግን አይቀሩም::  ይሉኝን (ይሉኝታን) አውጥተን ጥለን ፍቅርን ተሞልተን በመልካም ልብ ሳንፈርድ ቁጣም ሳይሞላን እንመላለስ::  ለሁሉ ፍቅርን እንስጥ:: የጌታ ጸጋ በዛ ውስጥ ይገለጣል::

እርሱ ህይወቱን እንደሰጠን እያሰብን ማካፈልንና መስጠትን እንድንለማመደው ጌታ ይርዳን::  ሌሎችን በመባረክ ደስ ይበለን:: ህይወትን እንኑሩው እንጂ ማንበብ ብቻ አይሁንብን::  

ጌታ ሆይ እንድንዘረጋ ወደምትፈልገው ሁሉ እንዘረጋ ዘንድ ጸጋህን ስጠን በውስጣችንም ያለው ፍቅር ወጥቶ ይውደድ – እኛ የምንሰጠው የለንምና! ተባረክ::  አሜን!

ሉቃስ 6: 30-31

30 ለሚለምንህ ሁሉ ስጥ፥ ገንዘብህንም የሚወስድ እንዲመልስ አትጠይቀው። 31 “ሰዎችም ሊያደርጉላችሁ እንደምትወዱ እናንተ ደግሞ እንዲሁ አድርጉላቸው።

ሰውን በለመስጠት ለመባረክ የሚያስፈልገን ከገንዘቡ በላይ ፍቅር ነው::  ፍቅር ካለ መስጠት ይቀላልና የተቸገሩትን ለማሰብ የክርስቶስ ፍቅር ይሙላን::

ሰዎችም ሊያደርጉላችሁ እንደምትወዱ ማድረግ የሚለው እራሳችንን እንድናይ የሚያደርገን ሚዛን ነው::  ይህንን ምክር ወርቃማው ህግ ብለው ይጠሩታል::  እንዲድረግብን የማንፈልገውን አናድርግ:: በማስተዋል እንመላለስ ለሌሎችም እንቅፋት እንዳንሆን::  

አባት ሆይ በልግስና ያለ ስስትእንድንሰጥናሌሎችን ልክ አንተ እንደወደድካቸው መውደድ እንድችል እርዳኝ::  አሜን!

ሉቃስ 6: 32-33

32 የሚወዱአችሁንማ ብትወዱ፥ ምን ምስጋና አላችሁ? ኃጢአተኞች ደግሞ የሚወዱአቸውን ይወዳሉና። 33 “መልካምም ለሚያደርጉላችሁ መልካም ብታደርጉ፥ ምን ምስጋና አላችሁ? ኃጢአተኞች ደግሞ ያን ያደርጋሉና።

የአዲሱ ኪዳን ህይወት ከብሉይ ይለያል::  ጥሩ ተብለው የሚባሉትን ሁሉ የሚቀይር ነው::  የሚወዱንን መውደድ ወይም መልካም ላደረጉልን መልካም መመለስ ጥሩ ነው  ምን ክፋት አለው? እንል ይሆናል::  ነገር ግን በውስጣችን እየኖረ ያለው ፍቅር የሆነ ጌታ ለዚህ አይደለም የመጣሁት እያለ ነው:: ይህንንማ ሰው ሁሉ ማድረግ ይችላል::  የእኔ ደቀ መዝሙር ግን በፍቅሩ ይታወቃል ስለተደረገለት ወይንም ወሮታን ለመመለስ አይደለም የሚወደው ነገር ግን እግዚአብሔር ሰውን በወደደበት መውደድ እየወደደ ምላሽን ሳይጠበቅ የእግዚአብሔርን ፈቃድ ማገልገል ነው::  እግዚአብሔር ይርዳን የሰው ልጆችን ሁሉ ሳንለይ እንድንወድድና መጥፋታቸው ግድ ብሎን የምስራቹን እንድንመሰክር:: ከፍቅርም በቀር ሌላ  እዳ  አይኑርብን:: ያለዛ ግን እንደሚሿሿ ፀናፅል ነን ከድምጽ ውጪ ምንም ፍሬ የሌለው ማለት ነው::  ጆሮ ያለው ይስማ! ሁሉን በጸጋው ለሚያደርገው እረኛ እራሳችንን እናቅርብ!

ሉቃስ 6: 34-36

35 “ነገር ግን ጠላቶቻችሁን ውደዱ፤ መልካም አድርጉ፤ ምንም ተስፋ ሳታደርጉም አበድሩ፥ ዋጋችሁም ታላቅ ይሆናል፥ የልዑልም ልጆች ትሆናላችሁ፥ እርሱ ለማያመሰግኑ ለክፉዎችም ቸር ነውና። 36 አባታችሁ ርኅሩኅ እንደ ሆነ ርኅሩኆች ሁኑ።”

ዋጋችሁም ታላቅ ይሆናል፥ የልዑልም ልጆች ትሆናላችሁ ያስባለው ነገር እየሱስን እየመሰሉ መመላለሱ ነው::  አምላካችን ለማያመሰግኑ ለክፉዎችም ቸር  ነውና ከእኛም ይህ አባታችንን መምሰል ይጠበቅብናል::  ጠላትን እንደ ክርስቶስ በመውደድ ፤ እንዲሁም በክርስቶስ የተፈጠርነው መልካም ለማድረግ ነውና መልካምን እያደረግንና ምንም ተስፋ ሳናደርግ  ማበደርን እየተለማመድንጌታን እናሳይ:: አባታችን  ርኅሩኅ እንደ ሆነ እኛም ርኅሩኆች እንሁን። ልክ እንደ አባታችን የሰው ልጅ ሁሉ ያሳዝነን የምንራራም እንሁን::  ጌታ ማስተዋልን ይስጠን!

ሉቃስ 6:37 “አትፍረዱ አይፈረድባችሁምም፤ አትኰንኑ አትኰነኑምም። ይቅር በሉ ይቅርም ትባላላችሁ።

የእግዚአብሔርን ርኅራኄ የቀመስንና ያስተዋልን እኛ እንጂ  ዓለም አይደለችም:: ርኅራኄውን እንደቀመሰ ሰው ስንመላለስ በሌሎች ላይ እንዳንፈርድ ፤  እንዳንኮንንና ይቅርታን እንዳንነፍግ::  ይልቁንም ሰፊ ልብ ይዘን ሌሎችን ማቀፍና የቀመስነውን ጌታ መስለን መማረክ ይሁንልን::  

ጌታ ይቅር በሉ ሲለን ሳያልፍበት ቀርቶ አይደለም::  ማንም በማይቀርበው ብርሃን ይኖራል የተባለው ጌታ ሲመቱት ፤  ሲገርፉት ፤  ሲተፉበትና ሲሰቅሉት  ይቅር አላቸው:: ከማን እንማር ታድያ ይቅርታችን በአጭር የቀረ አይሁን እንደተቀበልን በልግስና እንስጥ:: ጌታ ይርዳን! ቃሉን እንኑርበት እንጂ አንብበን አንለፈው እራሳችንን እንይበት በዚህ መስታወት::  

አባት ሆይ እንዳን ከፍቅር በቀር ሌላ ዕዳ አይኑርባችሁ ስትለን በሌላ ዕዳ ውስጥ ተይዘን እንዳንገኝ ዓይኖቻችንን ክፈትልን::  አሜን!

ሉቃስ 6:37 “አትፍረዱ አይፈረድባችሁምም፤ አትኰንኑ አትኰነኑምም። ይቅር በሉ ይቅርም ትባላላችሁ።

የእግዚአብሔርን ርኅራኄ የቀመስንና ያስተዋልን እኛ እንጂ  ዓለም አይደለችም:: ርኅራኄውን እንደቀመሰ ሰው ስንመላለስ በሌሎች ላይ እንዳንፈርድ ፤  እንዳንኮንንና ይቅርታን እንዳንነፍግ::  ይልቁንም ሰፊ ልብ ይዘን ሌሎችን ማቀፍና የቀመስነውን ጌታ መስለን መማረክ ይሁንልን::  

ጌታ ይቅር በሉ ሲለን ሳያልፍበት ቀርቶ አይደለም::  ማንም በማይቀርበው ብርሃን ይኖራል የተባለው ጌታ ሲመቱት ፤  ሲገርፉት ፤  ሲተፉበትና ሲሰቅሉት  ይቅር አላቸው:: ከማን እንማር ታድያ ይቅርታችን በአጭር የቀረ አይሁን እንደተቀበልን በልግስና እንስጥ:: ጌታ ይርዳን! ቃሉን እንኑርበት እንጂ አንብበን አንለፈው እራሳችንን እንይበት በዚህ መስታወት::  

አባት ሆይ እንዳን ከፍቅር በቀር ሌላ ዕዳ አይኑርባችሁ ስትለን በሌላ ዕዳ ውስጥ ተይዘን እንዳንገኝ ዓይኖቻችንን ክፈትልን::  አሜን!

ሉቃስ 6:38 ስጡ ይሰጣችሁማል፤ በምትሰፍሩበት መስፈሪያ ተመልሶ ይሰፈርላችኋልና፥ የተጨቈነና የተነቀነቀ የተትረፈረፈም መልካም መስፈሪያ በእቅፋችሁ ይሰጣችኋል።”

ከላይ ያነበብነው አታድርጉ የተባልነውን ነው:- አትፍረዱ፤  አትኮንኑና ይቅር በሉ::  ቀላል ይመስላል ስናነበው ስናልፍበት ግን እንዴት እንሆን?  ይህንን ሁሉ ነገር የምናደርገው ለራሳችን ስንል ነው ሲደርስብን አንወደውም ያመናል ሲፈረድብን ስንኮነን  ስንቀምሰው መራራ ነውና እናስወግደው::  

አሁንም ስጡ እየተባልን ነው::  የምንሰጠው ስለሚሰጠን ሳይሆን ርኁሩኅ የሆነውን አባታችንን እንድንመስል ብለን ነው::  እርሱ ለኃጥያተኛም ለፃድቁም እኩል ፀሐይን ያወጣልና::  ስንሰጥም በልግስና ደስ እያለን እንስጥ::  እርሱ ታማኝ ነውና በሰጠነው መስፈርያ ይሰፍርልናል:: መስጠት ይዋሃደን ዘንድ ጌታ ይርዳን::  ሰውን በችግሩ መድረስ እንድንችል ጌታ ዓይናችንን ይክፈትልን ጸጋውንም ያብዛልን::

ሉቃስ 6: 39-40

39 ምሳሌም አላቸው፦ “ዕውር ዕውርን ሊመራ ይችላልን? ሁለቱ በጕድጓድ አይወድቁምን? 40 ደቀ መዝሙር ከመምህሩ አይበልጥም፤ ፈጽሞ የተማረ ሁሉ ግን እንደ መምህሩ ይሆናል።

የሚመራን ማን እንደሆነ ውሳኔው የእኛ ነው እውር እንዳንከተል በቃሉ እውነት መርምረን የህይወትንም ፍሬ እያየን መሆን አለበት::

እረኛችን ግን ሲያስተምረንና ሲቀርጸን እርሱን እንድንመስል ነው::  ይኸው ነው የተወሰነው በሮሜ 8:29 . . . አስቀድሞ ያወቃቸው የልጁን መልክ እንዲመስሉ አስቀድሞ ደግሞ ወስኖአልና::  በኃላም ስንገለጥ እርሱን እንመስላለን:: እውር ያስተማረው ጥሩ እውር ይሆናል ከጌታም የተማረ ጌታን እየመሰለ ይመጣል::  እርሱን የምንመስለው እንዴት ነው?  በፍቅራችን፤ በትህትና፤ በርኅራኄና በመንፈሳዊ ፍሬዎች ሁሉ በማሸብርቅ ነው::  እነዚህን የሚቃወም የዓለምም ህግ የለም::  እግዚአብሔር ትልቅ ነው!!

ሉቃስ 6: 41-42

41 “በወንድምህም ዓይን ያለውን ጉድፍ ስለ ምን ታያለህ፥ በራስህ ዓይን ግን ያለውን ምሰሶ ስለ ምን አትመለከትም?

ሌሎችን መርዳትን አይደለም ጌታ እየተቃወመ ያለው ነገር ግን እራስህንም መርምር በሌላው ከምታየው የበለጠ በአንተ እንዳይገኝ ነው::  ዳዊት አንዲት በግ የነበረችው ታረደችበት የሚለውን ታሪክ ሲሰማ ቡራ ከረዮ አለ እርሱ መሆኑን ባለማወቁ::  ማለት የነበረበት:- እኔም ወድቄያለሁና ንስሃ ልግባና ከዚህ ሰው ጋር ከዛ በኃላ እነጋገራለሁ ማለት ነበረበት::  ያችም ስታመነዝር የተገኘች ሴት ከሳሾችዋ በሙሉ ባለ ምሰሶ ሆነው ተገኙ::  እራሳችንን ብንመረምር ባልተፈረደብን ነበር::  ሌሎችን እዮ የተባልነው በክርስቶስ ውስጥ ነውና እያንዳንዱን ቅዱሳን ስንመለከት ክርስቶስን እንይና ከእኛ እንደሚበልጡ እንረዳ ድሮስ እንዴት ከእየሱስ እንወዳደር? ትህትናን ለብሰን በእውነት ገብቶን እንመላለስ:: 

ሉቃስ 6: 43-45

43 “ክፉ ፍሬ የሚያደርግ መልካም ዛፍ የለምና፥ እንዲሁም መልካም ፍሬ የሚያደርግ ክፉ ዛፍ የለም።

ዛፍ ስም የሚወጣለት በፍሬው ነው::  የብርትኳን ዛፍ ወይም የማንጎ ዛፍ ያስባለው ከሚያፈራው ፍሬ የተነሳ ነው::  እንግዲህ እናስተውል አፍሩ የተባልነው የመንፈስ ፍሬ ነው::  ሐዋርያቱ ምንም ያልተማሩ ነበሩና ከእየሱስ ጋር እንደነበሩ አወቋቸው:: ውሎ አዳራችን ከእየሱስ ጋር ከሆነ እየሱስን እንመስላለን:: የህይወት ቃል አለህ ወዴት እንሄዳለን ብለዋልና:: ይህ ቃል መንፈስ ነው እውነትም ነውና መልካም መሬት ሆነን እንቀበለው እርሱም ያፈራል::

በልብ ሞልቶ ከተረፈው አፉ ይናገራልና መልካም ሰው ከልብ መልካም መዝገብ መልካሙን ያወጣል፥ ክፉ ሰውም ከልብ ክፉ መዝገብ ክፉውን ያወጣል። የተሞላነው ምንድነው?  ቃሉን?  ዕለት ዕለት በመንፈስ ቅዱስ ተሞሉ ተባልን አለዚያ ዓለም ክፍተቱን ተጠቅማ መራራውን እውቀት ትሞላናለችና::  ክርስቶስን ወደ መምሰል አንመጣም:: ቃሉን ስናሰላስል እንዋል እርሱ ነው በአእምሯችን መታደስ የሚለውጠን:: የእግዚአብሔር እርሻ ነንና ልባችን በቃሉ ይሞላና የምንናገረው ቃል ሰውን የሚያንጽ የጥበብ ቃል ይሁን::  ቃሉ በሙላት ይኑርባችሁ ተብለናልና ለቃሉ ጊዜና ክብር ይኑረን! 

ሉቃስ 6: 46-49

46 “ስለ ምን፦ ‘ጌታ ሆይ፥ ጌታ ሆይ፥’ ትሉኛላችሁ፥ የምለውንም አታደርጉም?

ጥያቄውን መመለስ የእያንዳንዳችን ግዴታ ነው::   ለምን በአፋችን ብቻ ጌታ ሆይ ጌታ ሆይ ማለት እንዳይሆንብን ህይወታችንን በቃሉ ላይ መስርተን እንኑርበት::  ጌታ ሶስት ነገሮችን እየነገረን ነው:- 

1. ወደ እኔ የሚመጣ ሁሉ – እራስን መካድ: ማስገዛትና ጌታን መከተል

2. ቃሌንም የሚሰማ – ደቀ መዝሙር መሆን

3. የሚያደርገው፥ – መታዘዝ

በዚህ መልኩ የሚከተል ማንን እንዲመስል አሳያችኋለሁ ብሎ:-  ቤት ሲሠራ አጥልቆ የቆፈረ በዓለት ላይም የመሠረተ ሰውን ይመስላል፤ ጐርፍም በመጣ ጊዜ ወንዙ ያን ቤት ገፋው፥ በዓለት ላይም ስለ ተመሠረተ ሊያናውጠው አልቻለም። እምነታችንን የሚፈትን መከራ መምጣቱ አይቀርም ያኔ እንጸናለን ወይንስ ትተን እንሄዳለን?

ይህንን ያላደረገው ደግሞ ያለ መሰረት (እናስምርበት) ቤቱን የሰራ ነው አይጸናም:: ክርስትና ክርስቶስን መምሰል እንጂ በአፍ ብቻ መከተል አይደለም በቃሉ ላይ እንደግ እንመስረትበትም::

ከ12  አንዱ ሲክደው ምንም ምልክትን አላሳየም ሌሎቹ አላወቁበትም ጌታ እንጂ::  እነሱኑ ነበር የሚመስለው ጠላት አሳብ አስገባበት እርሱም አስተናገደው::  ከውጪ ጥሩ ክርስትያን መምሰልና ሰውን ማታለል ይቻላል በጌታ ፊት ግን ሁሉ የተራቆተ ነው::  በመጨረሻው ጌታ ጌታ ሆይ ሲሉት አላውቃቸውም ከሚባሉት ውስጥ በስምህ አጋንንት አላወጣንም እንደዛና እንደዚህ አላደረግንም የሚሉ አሉበት:: እራሳችንን በቃሉ ብርሃን እንመርምር  አገልግለን የተጣልን እንዳንሆን::

ሉቃስ 7: 1-7

7 ስለዚህም ወደ አንተ ልመጣ እንዲገባኝ ሰውነቴን አልቈጠርሁትም፤ ነገር ግን ቃል ተናገር፥ ብላቴናዬም ይፈወሳል።

ቃል የገባው ይህንን ይላል!  ጌታ እየሱስን ስለቃል በደንብ አድርጎ ሰበከው::   ይህ ሰው የተመሰከረለት ጥሩ ሰው ነው ህዝቡን የሚወድና ምኩራብም የሚሰራ በኢየሱስ ፊት ግን ለመቆም ወይም ወደ ቤቱ እንዲገባ እራሱን የተገባው አድርጎ አልቆጠረምና መልክተኞችን ላከ::  መሲሁን ከሚጠባበቁት ይልቅ ይህ ምንም የማያውቅ አህዛብ ጌታን በግርማው ተቀበለው:: 

ዛሬም የሚያስፈልገን ይህ ህያው  ቃል ነው ለቃሉ ክብር ይኑረን::  ቃሉ በከበረበት ጌታም ይገኛል::

ሉቃስ 7: 8-10

9 ኢየሱስም ይህን ሰምቶ በእርሱ ተደነቀ፥ ዘወርም ብሎ ለተከተሉት ሕዝብ፦ “እላችኋለሁ፥ በእስራኤልስ እንኳ እንዲህ ያለ ትልቅ እምነት አላገኘሁም፡” አላቸው። 10 የተላኩትም ወደ ቤት ተመልሰው ባሪያውን ባለ ጤና ሆኖ አገኙት።

ይህ ሰው መልካም እንደሆነ መስክረውለታል ከስራውም ማየት ይቻላል  ለልጁ አይደለም  እንደዚህ  የተጋው:: ኢየሱስንና በአካባቢው ላሉት ሁሉ የባለስልጣን ቃል ምን ማለት እንደሆነ ሰበካቸው:: ይህንን ሁሉ የሚመላለሰው በመልክተኛ ነው ፊቱ ለመቆምማ አልደፈረም::  የጌታ ቃል ስልጣኑ ይግባን!!  ሁሉን ወደመኖር ያመጣው በቃሉ ነው::  አሁንም የምንኖርባትን ትልቁን ዓለም ያጸናት ጥሩ በሆነ መሰረት ላይ መስርቶ ሳይሆን በቃሉ ነው ደግፎ የያዘው!  ሃሌሉያ! 

እስራኤሎች ይህንን ቢሉ አይደንቅም ብዙ የአምላካቸው አሻራ አለና በዙሪያቸው::  ሙት ከሆነው አብረሃም የተገኙ:  ቀይባህርና ዮርዳኖስ የተከፈለላቸው: እያሪኮ በመዞር ብቻ የፈረሰላቸው:  ያልገነቡትን ከተማ የወረሱ: ብዙ ነገስታትን ድል የነሱ ብዙ ብዙ መጥቀስ  ይቻላል:: እነሱ ተለማምደውታልና ብዙም አልታያቸው::  እኛስ እንዳንለምደውና ታላቅነቱ እንዳይደበዝዝብን! 

ጌታ ኢየሱስም ተገርሞበት እላችኋለሁ፥ በእስራኤልስ እንኳ እንዲህ ያለ ትልቅ እምነት አላገኘሁም አለ:: ምን አይነት እምነት? ትልቅ! ጌታ እየሱስ ምንም አላለም ነገር ግን መልክተኞቹ ሲመለሉ ባርያውን ድኖ አገኙት!!!!  ሃሌሉያ ክብር ይሁንለት!!  ጆሮ ያለው ይስማ!!  ቃሉ ህያው ነው በሁለት በኩልም የተሳለ ነው!! ይሰራል ሳይሰራም አይመለስም! ቃል!  ቃል!  ቃል! 

ሉቃስ 7: 11-15

13 ጌታም ባያት ጊዜ አዘነላትና፦ “አታልቅሽ፡” አላት። 14 ቀርቦም ቃሬዛውን ነካ፥ የተሸከሙትም ቆሙ፤ አለውም፦ “አንተ ጐበዝ፥ እልሃለሁ፥ ተነሣ።” 15 የሞተውም ቀና ብሎ ተቀመጠ ሊናገርም ጀመረ፥ ለእናቱም ሰጣት።

ናይን ወደምትባለው ከተማ በአጋጣሚ አልመጣም ቀኑን የትና እንዴት እንደሚውል የሚያውቅ ጌታ::  ቀጥታ እርሰዋን ሊረዳት መጣ ስለታሪክዋ የነገረው የለም ግን አያትና አዘነላት አንድ ልጅዋን አታለችና:: 

ጸሎትን ከጌታ እንማር እርሱ ነገሮችን ያዛል ::  ከየት እንዳመጣነው የማይገባኝ ድምፃችንን ሁሉ ለውጠን የለቅሶ ዘይቤ አስይዘን እንጸልያለን ወይም ደግሞ እርሱ መረጃ የጎደለው ይመስል እንወተውታለን::  ማንም ምንም ሳይነግረው አውቆ አዘነላትና ልጅዋን በሰውኛ ሬሳ የሆነውን እርሱ ግን አናገረው አንተ ጎበዝ ብሎ ጠርቶ ተነሳ አለው እርሱም ተነስቶ ተቀመጠ ለእናቱም ሁለተኛ ሰጣት ድሮውንስ ልጅ የሚሰጥ እርሱ አይደለምን?!  በአላዛርም ይህንኑ ነው ያደረገው::

የሞተም ይሰማዋል!  እኛም ስንጸልይ ጉዳዮን አድሬስ እናድርግ እንጂ አንዘብዝብ::  ስትጸልዮ እንደአህዛብ አትሁኑ ተብለናል:: እግዚአብሔር መንፈስ ነው!  እንወቀው ሰምቶ የሚመልስ ነው የለመነውን እንደተቀበልን ብንቆጥር ለእኛ ይሆናል::  የጌታን የሚያዝን ልብ ይስጠን ሌሎች ሲያዝኑ አብሮ የሚያዝንና የሚጸልይ ማንነትን ያብዛልን::

ሉቃስ 7: 16-17

16 ሁሉንም ፍርሃት ያዛቸውና፦ “ታላቅ ነቢይ በእኛ መካከል ተነሥቶአል፥” ደግሞ፦ “እግዚአብሔር ሕዝቡን ጐበኘ፡” እያሉ እግዚአብሔርን አመሰገኑ።  17 ይህም ዝና ስለ እርሱ በይሁዳ ሁሉ በዙሪያውም ባለች አገር ሁሉ ወጣ።

ሁሉንም ፍርሃት ያዛቸው ይላል ቃሉ::  ለምን?! እንደዚህ አይነት ነብይ በህይወት ዘመናቸው ያላዮና የነብያትን አገልግሎት በዝና እንጂ በተግባር ያላዮ ትውልድ ናቸው:  ይህንን ያደረጉት ነብያት እነኤልያስና ኤልሳዕ ነበሩ::  ኢየሱስ ግን ከነብያትም የሚበልጥ የእግዚአብሔር ልጅ የሚጠብቁት መሲህ መሆኑን አልተረዱም::  መሲሑ ሲመጣ የሚያደርገውን ተአምራት እያደረገ ነውና::  እነርሱ ግን ታላቅ ነቢይ በእኛ መካከል ተነሥቶአል፥” ደግሞ፦ “እግዚአብሔር ሕዝቡን ጐበኘ፡” አሉ::  ይህንን ያሉት ከሮም አገዛዝ ያወጣናል ብለው ነበረ እንጂ የእግዚአብሔር እቅድ ዓለምን ሁሉ ለማዳንና የሰይጣንን መንግስት ለመጣል እንደሆነ በጥልቀቱ አልተረዱትም::

ተአምራት ሲደረግ የጌታ ስም ይገናል ዝናውም ይወጣል ብዙዎችንም ወደ እግዚአብሔር መንግስት ያመጣል::  እነዚህ ጸጋዎች በቤተክርስቲያን እንዲገለጡ እንጸልይ:: ብዙዎች እያነከሱ በቤቱ እየተመላለሱ ነው ያሉት::  የዚህች ሴት መጎብኘት ደስ አይልም? አንድ ልጅዋን መልሶ ሰጣት! አሜን! ይህንን ክብሩን ያሳየን::

ሉቃስ 7: 18-20

20 ሰዎቹም ወደ እርሱ መጥተው፦ “መጥምቁ ዮሐንስ፦ ‘የሚመጣው አንተ ነህን ወይስ ሌላውን እንጠብቅ?’ ብሎ ወደ አንተ ላከን፡” አሉት።

ይህንን ጥያቄ ከመጥምቁ ዮሃንስ መስማት ያስገርማል::  ምክንያቱም ሲያጠምቀው መንፈስ ቅዱስ በእርግብ መልክ መጥቶ  ሲቀመጥበት በአይኖቹ አይቶ እንደዚሁም ከአብ ዘንድ ድምጽን ሰምቶ ነበረና ነው::  በእርግጠኝነትም ይህ የእግዚአብሔር በግ እያለም አውጆለት ሲያበቃ ይህንን መጠየቁ ነው ያስገረመኝ::

አንዳንዴ ግራ ሲገባኝ እነዮሃንስም ያንን ሁሉ ምልክት ተሰቷቸው ጥያቄ ጠይቀዋል ብዬ  እጽናናለሁ::  ስለዚህ  እኛ ብቻ አይደለንም ግራ የሚገባን ከሴቶች ሁሉ ከተወለዱት ይበልጣል የተባለውም ወሳኙ ነብይ ጠይቋል::  ደስ የሚለው ጌታ አይታዘበን ወይንም አይቆጣን በነገር ሁሉ የተፈተነው ካህን ይረዳናል::  በድካማችን ኃይሉ ይገለጣል ደግሞም ጸጋን ይሰጠናል::  አሜን!!  ሃሌሉያ!

ሉቃስ 7: 21-23

ዮሃንስ ለላከው ጥያቄ በቃል ወይም በንግግር አልመለሰም ያላቸው ያያችሁትን የሰማችሁትንም አውሩለት ነበረ::  ወንጌል የሚታይና የሚሰማ ነው::  በኢሳያስም መጽሐፍ በትንቢት እንደተነገረው:-

ዕውሮች ያያሉ፥ 

አንካሶችም ይሄዳሉ፥ 

ለምጻሞችም ይነጻሉ፥ 

ደንቆሮዎችም ይሰማሉ፥ 

ሙታንም ይነሣሉ፥ 

ለድሆችም ወንጌል ይሰበካል፤

ይህ መሲሁ ሲመጣ የሚሰራው ነውና ስራው እየተሰራ ነው::  ዮሃንስን የገረመው ለምን እስከአሁን ቆየህ ነፃ አውጣን ነበረ::  ለምን በእስር ቤትስ እቆያለሁ ቶሎ መንግስትህን መስርት ነው ጥያቄው::  ኢየሱስ የመጣው የሰማይን መንግስት ለመመስረት ነው::  የሐዋርያቱም ጥያቄ ሊያርግ ሲል ይኸው ነበረ:: 

ስለዚህ ብዙዎች በዚህ ይሰናከላሉ ምክንያቱም የሚፈልጉት የእስራኤልን መንግስት እንጂ የማይታየውን የእግዚአብሔርን መንግስት አይደለም:: ንጉስ  አንግስልን አሉት በሳሙኤልም ዘመን ጌታም እኔን ነው የናቁት አለ::  እነርሱ የፈለጉት  እንደ አህዛብ  ያለ በፊታችን የሚሄድ ንጉስ ነበረ:: እግዚአብሔር ግን በቀን በደመና በለሊትም በእሳት አምድ እየመራቸው ነበረ::  ንጉሳችን እግዚአብሔር ነው!

ዛሬም ኢየሱስ በእኛ ውስጥ እየኖረ ስለሆነ እነዚህ ተአምራት ይቀጥላሉ::  ኃይሉን እንጠማ!!!

ሉቃስ 7: 24-28

ዮሃንስ ከሴቶች ከተወለዱት መካከል እንደሚበልጥ ጌታ መሰከረ ምክንያቱም  ሌሎቹ ነብያት ይመጣል ብለው አንዳንዶችንም ከሩቅ ተሳለሙት ሲል ዮሃንስ ግን ይኸው ብሎ ማወጅና ይመጣል የተባለውን መሲህ ማየት ሆነለት::   

የብሉይ ኪዳን አገልጋይ ሆኖ ሳለ ኢየሱስን ማየት ብቻም ሳይሆን ስለእርሱ ሲመሰከር በጆሮው የእግዚአብሔርን ድምጽ ሰማ መንፈስ ቅዱስም ሲወርድ አየ!   ዮሃንስ ማለት በመልአክ መልክት ይመጣል ተብሎ  የመጣ ፥  በበረሃ የኖረ ፥  ከሰው የማይነካካ የሚበላውና የሚለብሰው ሁሉ የተለየ ፥ እራሱን ሙሉ በሙሉ ለተላከለት አገልግሎት የሰጠ ነው::   ይህ ሁሉ ቢሆንም ቅሉ  በክርስቶስ የጸደቀ ግን ይበልጠዋል::  ምክንያቱም እርሱን ለብሰን፥  በደሙ ታጥበን ፥  እርሱን በልባችን ሾመን ፥  በእርሱ ተሞልተናልና ነው::  አሜን!  መዳናችን እጅግ ክቡር ነውና  ይህንን ሁሉ ሳናደርግ ድነናልና ይህንን ህይወት አንለማመደው በየዓለቱ እንደነቅ!

ሉቃስ 7: 29-30

ዮሃንስ የጌታን መንገድ ሊያቀና ከፊቱ የተላከ ነበረ::  ህዝቡን ወደ ንስሃ የሚያመጣ ከፍ ያለውን የትቢት ልብ ዝቅ የሚያደርግ አልበቃም ብሎም ዝቅ ያለውን ከፍ አድርጎ ልብን ሁሉ አደላድሎ የሚጠብቅ ነብይ::  ነገር ግን ህዝቡ ሁሉ ቀራጮች እንኳን ሳይቀሩ መተው ተጠምቀው ሲጠብቁት አውቀናል የሚሉት ፈሪሳውያንና ሕግ አዋቂዎች ግን በእርሱ አልተጠመቁምና የእግዚአብሔርን ምክር ከራሳቸው ጣሉ። እንዴት ከባድ ንግግር ነው? ! የእግዚአብሔርን ምክር ከራሳቸው መጣል? የጌታ ምክር በይወታችን ይጽና!  እግዚአብሔር ፈቃድ አለው ምንድነው ፈቃዱ በህይወታችን? እርሱን እንወቅና ፈቃዱን እንፈጽም እንጂ ሞኞች አንሁን::

ይህ ሰው ተራ ሰው እንዳልሆነ ያውቃሉ ብዙም ጊዜ አንተ እርሱ ነህን ብለው ጠይቀውታል እርሱም እኔ እርሱ አይደለሁም መንገድን የማዘጋጅ ነኝ ብሏል ልብ አላሉምና አለፋቸው::  ጌታም ሲመጣ አልተዘጋጁምና አልተጠቀሙበትም::  ጥምቀት በብሉይ ኪዳን አይታወቅም ግን ዮሃንስ አጠመቀ በኤልያስም መንፈስ ተገለጦ እንደ ትንቢቱ አገለገለ::

ሉቃስ 7: 31-35

32 በገበያ የሚቀመጡትን ልጆች ይመስላሉ፥ እርስ በርሳቸውም እየተጠራሩ እንዲህ ይላሉ፦ ‘እንቢልታ ነፋንላችሁ አልዘፈናችሁምም፤ ሙሾ አወጣንላችሁ አላለቀሳችሁምም’።

ይህንን ምሳሌ ሲናገር ጌታ የመጥምቁን የዮሐንስና የራሱን አገልግሎት ለማለት ነው:- ሙሾ አወጣንላችሁ አላለቀሳችሁምም’። ዮሃንስ ንስሃ ግቡ እናንተ የእፉኝት ልጆች ይላቸው ነበረ::  አኗኗሩ ሁሉ የተለየ ሲሆንባቸው ጋኔን አለበት አሉት::  

በሌላ አንፃር እግዚአብሔር ጌታ የሱስን ላከ  የምስራቹን ይዞ መጣ:- እንቢልታ ነፋንላችሁ አልዘፈናችሁምም::  የተገፉትንና የተጣሉትን ሁሉ ወደ መንግስቱ የሚያስገባ የኃጥያተኞች ወዳጅ የሆነ የእግዚአብሔር በግ::  ለእርሱም ምላሽ አልሰጡምና፤ እግዚአብሔር በምንም አይወቀስም::  ጥበብም ለልጆችዋ ሁሉ ጸደቀች አላቸው::  ጥበብ በብዙ ተጣርታለች ምክሩን ያልጣሉት ግን የእግዚአብሔር ጥበብ የሆነውን እየሱስን አወቁ::  እኛም አወቅን! ተመስገን ጌታ ሆይ!

ሉቃስ 7: 36-39

36 ከፈሪሳውያንም አንድ ከእርሱ ጋር ይበላ ዘንድ ለመነው፤ በፈሪሳዊው ቤትም ገብቶ በማዕድ ተቀመጠ።

ልመናን የማያልፍ ጌታ በዚህ ፈሪሳዊ  ቤት ለመስተናገድ መጣ::  ይህ ሰው የጋበዘው ነብይ መስሎት ነው ምክንያቱም ነብይ ቢሆን ኖሮ ይህችን ሴት ባወቃት ነበር አለ::  ከነብይነትም አወረደው::  እርሱ ግን በቤቱ ጋብዞ በሰው ላይ ይፈርዳል የሚገርመው ነገርና ያላወቀው ፈራጅ የሆነው ጌታ በዚያ በቤቱ ተቀምጦ ነበር::   ዛሬስ እኛ እንዴት ነን በጉባኤ መካከል በእህት ወንድሞቻችን መካከል ከፍቅርና እርስ በእርስ ከመቀባበል ባለፈ የፍርድ ልብ እንዳንይዝ እናስወግድ ወይም ስህተትን ካየን እንጸልይላቸው:

እርስዋ ግን ሰውየው ያሰበውን ሳታውቅ በቤቱ ገብታ ሳትጋበዝ ይሉኝታም ሳይዛት አገልግሎትዋን ቀጠለች አካሉን ለቀብር ማዘጋጀት ይህንን ወግ ጌታ አያገኝምና:: 

ያደረገችውም:-

– ሽቱ አምጥታ

– በእግሩ አጠገብ በመሆን እራስዋን ዝቅ አድርጋ: 

– ከፍቅርዋ የተነሳ እያለቀሰች 

– በእንባዋ እግሩን እያራሰች

– በራስ ጠጕርዋም እያበሰች  እራስዋን አዋርዳ 

– እግሩንም በመሳም ፍቅርዋን እየገለጠች 

– ሽቱ ቀባችው::

አገልግሎታችን ምንድነው? ማንም አይሰራልንምና ተነስተን እናገልግል የጌታ ውለታ የበዛብን ነን! 

ሉቃስ 7: 40-50

47 ስለዚህ እልሃለሁ፥ እጅግ ወዳለችና ብዙ ያለው ኃጢአትዋ ተሰርዮላታል፤ ጥቂት ግን የሚሰረይለት ጥቂት ይወዳል።”

ይሉኝታ ሳይዛት ሰው ሁሉ ለመብላት ተሰብስቦ ባለበት እርስዋ ግን አሳብዋንም ዓይንማንም በጌታ ላይ አድርጋ ለማምለክ ተገኝታለች::  አካባቢውን ሁሉ በዚህ ውድ ሽቶ አውዳ አመለከችው::

ስምዖን ግን ጌታን በልቡ እያማ ነው ማንነትዋን ነብይ ቢሆን ኖሮ ያውቅ ነበረ እያለ ባለበት ጌታ የልቡን አሳብ አውቆ መመለስ ጀመረ::  ለምን እንደዚህ እየሆነች እንዳለች ገለጸለት::  እርሱ ምንም አላደረገለትም እርስዋ ግን ብዙ ተትቶላታልና ብዙ ወደደች ፍቅርዋንም በተግባር ገለጸች:: እርስዋንም፦ “ኃጢአትሽ ተሰርዮልሻል፡” ብሎ ገበናዋን ሳይገልጥ ይቅር አለላት:: በነገር ሁሉ የተፈተነና ምንም ኃጥያት ያልተገኘበት ሊቀ ካህን ዛሬም ይራራል ይቅርም ይላል::ስምዓን ቤት ስትገባ ስብር ብላ እንደነበረችው አይደለም ስትወጣ ቀና ብላ ወጣች እዳዋ ሁሉ ተከፍሎ::  

እኛንም ቀና ያደረገን አባ አባ እንድንል ያደረገን በከበረ ደሙ አንጽቶናን ለመንግስቱ ዋጅቶ ነውና ስሙ ይባረክ! የሚያጸድቅ እርሱ የሚኮንን ማነው?!

ሉቃስ 8: 1-3

1 ከዚህም በኋላ እየሰበከና ስለ እግዚአብሔር መንግሥት የምሥራች እየተናገረ በየከተማይቱ በየመንደሩም ያልፍ ነበር፤

በብዙ መንገድ እግዚአብሔር ተናግሮ ነበረ አሁን ግን ልጁ ስለ እግዚአብሔር መንግሥት የምሥራች እየተናገረ ዞረ::  አሜን!!  የሚናገረው የምስራች ነው!  ምንድነው ይህ የምስራች?!  እውቀት ደብቀኸናልና የእባቡ ምክር ይሻላል አንፈልግህም ብላችሁ ጥላችሁት ወደ መከራ ከገባችሁበት የምርጫሁ መከራና ጨለማ  ሊያወጣችሁና ሊታረቃችሁ ፈጣሪያችሁ መጥቷል ይመስለኛል በቀላል ቋንቋ:: ዛሬም ዝናው በምድር ነገዶች ሁሉ ዘንድ ይሰማል::

ጌታ ሲወለድ መልአኩ ለእረኞቹ ያላቸው ታላቅ የምስራች እነግራችኋለሁ ነበረ::  ዛሬም ይህ ለሰው ልጆች ሁሉ የሚሆን የምስራች ይሰበካል!!  የምስራች አለን! የእግዚአብሔር  በግ ተገልጧል እንታረቅም ይላል ብለን የምንሰብክ አምባሳደሮች ነን!!

በዚያ ዘመን የነበሩ አገልጋዮች ሴቶችን ከእቁብ አያስገቡም ነበር  ጌታ ግን ሁሉ ያለው የሁሉ ፈጣሪ በገንዘባቸውም እንዲያገለግሉት ፈቀደ እንዲሁም  ከ12 ጋር አብረው ነበሩ::  “እምነትሽ አድኖሻል፤ በሰላም ሂጂ፡” ያላት ብዙ ወዳለች የተባለችው የሽቶዋ ባለቤት መቅደላዊት ማርያምም አንድዋ አገልጋይ ነበረች:: በገላትያ 3:28 አይሁዳዊ ወይም የግሪክ ሰው የለም፥ ባሪያ ወይም ጨዋ ሰው የለም፥ ወንድም ሴትም የለም፤ ሁላችሁ በክርስቶስ ኢየሱስ አንድ ሰው ናችሁና። አሜን አንድ ነን በሁሉም ጌታ ይጠቀማል!  እናገልግለው!

ሉቃስ 8: 4-15

10 እርሱም እንዲህ አለ፦ “ለእናንተ የእግዚአብሔርን መንግሥት ምሥጢር ማወቅ ተሰጥቶአችኋል፤ ለሌሎች ግን እያዩ እንዳያዩ እየሰሙም እንዳያስተውሉ በምሳሌ ነው።” 11 “ምሳሌው ይህ ነው። ዘሩ የእግዚአብሔር ቃል ነው።

ጌታ በዚህ ስፍራ ላይ ስለዘሪው ሲያስተምርና ፍቺውንም ለሐዋርያቱ ሲነግራቸው እናያለን::   ዘሩ ቃሉ ነው የሚዘራውም በተለያየ አይነት ልብ ላይ ነው::  የሰውን የልብ አይነት ማወቅ ለእኛ አልተሰጠንም  የተሰጠን መዝራት ነውና እንዝራ::  የሚያበቅል መንፈስ ቅዱስ ነው!  ተስፋ ሳንቆርጥ ሳንሰለች እንዝራ!  ሰይጣንም ይልቀመው:  በፈተና የሚከዱም ይሁኑ: በዓለም ነገር የተጠላለፉም ይሁኑ መቶ እጥፍም የሚያፈሩ ይሁኑ እኛ ልባቸውን ስለማናውቅ አምነን እየጸለይን እንዝራ::

የእግዚአብሔርን መንግሥት ምሥጢር ማወቅ ስለተሰጠን እንጂ እኛም ይህንን ሚስጥር ማወቅ አንችልም ነበረ:: 

ሉቃስ 8:16 “መብራትንም አብርቶ በዕቃ የሚከድነው ወይም ከአልጋ በታች የሚያኖረው የለም፥ የሚገቡት ሰዎች ብርሃኑን እንዲያዩ በመቅረዝ ላይ ያኖረዋል እንጂ።

በህይወታችን ላይ የነበረውን ጨለማ ገፎ በብርሃኑ ሞላው ::  በዓለም ስንመላለስ የዓለም ብርሃን የተባልነውም ለዚሁ ነውና ይህንን ጨለማ ዓለም ሳንሸማቀቅ እናብራው::  ባይመስለንም እንኳን የሰው ልጅ ክርስቶስን ካላወቀ  እርዳታ የሚያስፈልገው ምስኪን የሚጠፋ ፍጥረት እንደሆነ አውቀን በብርሃኑ ወደ ብርሃን እንምራው::  እንጂ ብርሃናችንን ደብቀን አብረን በጨለማ አንመላለስ::  ክፉን በክፉ አንመልስ:  የሚጠሉንን እንውደድ:  ለሚያሳድዱን እንጸልይ እና ሌላም ሌላም በውስጣችን የበራው ብርሃን ህይወትን በዓለም ቀመር እንዳንኖረው ግድ ይለናልና አዲሱ ሰው ክርስቶስ ህይወቱን በእኛ ይኑር:: አሜን!

ሉቃስ 8: 17-18

18 እንግዲህ እንዴት እንድትሰሙ ተጠበቁ፤ ላለው ሁሉ ይሰጠዋልና፥ ከሌለውም ሁሉ፥ ያው ያለው የሚመስለው እንኳ ይወሰድበታል።”

ተሰውሮ የሚቀር ነገር የለም ሁሉ በግልጥ ይታያል አንድ ቀን ስለዚህ ማንም አገልግሎ የተጣለ እንዳይሆን ይጠንቀቅ!

መስማት ለሰው አቅጣጫን የሚያስይዝ ነውና እንዴት እንድትሰሙ ተጠበቁ፤ እየተባልን ነው::  ጌታም ጆሮ ያለው ይስማ ይላል ደጋግሞ::  በጎቼ ድምጼን ይሰማሉ ተብለናልና ልባችንን መልካም መሬት አድርገን እንስማ! ከላይም እንዳለው ቃል የሰው ልብ የተለያየ ነው ቃሉን ሲሰማ መልካም መሬት ላይ ካላረፈ ቃሉ አያፈራም::  ለዚህም ነው በአእምሯችሁ መታደስ ተለወጡ እንጂ ይህንን ዓለም አትምሰሉ የተባልነው መለወጥና መታደስ የሚመጣው በቃሉ ነው:: አለበለዚያ አለን ብለን የምናስበውም ይወሰዳል::  ለጊዜው ተቀብያለብ ብለን ብናስብም::  የሎዶቅያ ቤተክርስቲያን ይህንኑ ብላ ነበረ ጌታ ግን በራእይ 3:17 ሀብታም ነኝና ባለጠጋ ሆኜአለሁ አንድም ስንኳ አያስፈልገኝም፡ የምትል ስለ ሆንህ፥ ጐስቋላና ምስኪንም ድሀም ዕውርም የተራቆትህም መሆንህን ስለማታውቅ ልተፋህ ነው ይላቸዋል::

ጌታ አስተውሎ መስማትን ይስጠን!

ሉቃስ 8: 19-21

21 እርሱም መልሶ፦ “እናቴና ወንድሞቼስ የእግዚአብሔርን ቃል ሰምተው የሚያደርጉት እነዚህ ናቸው፡” አላቸው።

ይህንን ማለቱ መቼም ቤተሰቡን መናቁ ወይም ችላ ማለቱ አይደለም::  ከላይ ጀምሮ ሲያስተምር የነበረውን ቃሌን በማስተዋል ስሙ ኑሩትን በቤተሰብ ምሳሌ አጠናቀቀው:: የእግዚአብሔር ቤተሰብ መሆን ምን ማለት እንደሆነ ገለጸልን ይኸውም ቃሉን መስማትና ማድረግን እንደሚጠይቅ አሳወቀን::  ቃሌ በእርሱ ዘንድ ያለችው የሚወደኝ እርሱ ነው ይልና ወደ እኛ እንደሚመጣና መኖርያም እንደሚያደርግ ይገልፃል እንዲሁም ጸሎታችን እንደሚሰማ ይናገር የለም በሌላ ስፍራም? ቃሉን ሰምተን ስንኖርበት እናተርፋለን!

ቃሉ በልባችን እርሻ ተዘርቶ ይብቀልና ይውረሰን::  ቃሉን እንዴት እንደምንሰማም እንጠንቀቅ በአውቃለሁ ሳይሆን ሁልጊዜ በትህትና ሊሆን ይገባል::  በቃሉ ይሰራናል ስንኖረውም የማን ወዳጅና ቤተሰብ እንደሆንን ያሳውቃል::  ጌታ ይርዳን ላይ ላዮን ሳይሆን ጠለቅ ብለን እንድንመላለስና ልጁን እንድንመስለው:: አሜን!

ሉቃስ 8: 22-25

25 እርሱም፦ “እምነታችሁ የት ነው?” አላቸው። ፈርተውም ተደነቁ፥ እርስ በርሳቸውም፦ “እንዲህ ነፋሳትንና ውኃን እንኳ የሚያዝ ለእርሱም የሚታዘዙለት ይህ ማን ነው?” አሉ።

እንሻገር ብሏቸው መንገድ ጀምረው ሳይጨርሱ ማዕበል መንገዳቸውን ያዘውና ያስጨንቃቸው ጀመር::  እነዚህ ሰዎች አብዛኞቹ በውሃ ላይ ልምድ ያላቸው ናቸው ታድያ ለምን እንደዚህ ደነገጡ ያልን እንደሆነ ምክንያቱ ይህ ዓውሎ ንፋስ አጥፊ እንደሆነና መውጫም የሌለው ገዳይ እንደሆነ ስለሚያውቁ ነው::  ከልምዳቸው ይልቅ አጠገባቸው ያለውን ጌታ ቢያዮ ይሻል ነበር::

ለሊቱን ሲጸልይ የሚያድረው ጌታ ቢተኛ አይደንቅም ጀልባዋ በውሃ እየተሞላች እርሱም በውሃው ውስጥ እንቅልፉን ቀጠለ::  ጠፋን ብለው ሲቀሰቅሱት እርሱም ነቅቶ ነፋሱንና የውኃውን ማዕበል ገሠጻቸው፤ ተዉም፥ ጸጥታም ሆነ። ፍጹም አምላክ ፍጥረትን ሁሉ የሚያዝ ፍጹም ሰው ደክሞት የሚተኛ  ነበረና::  

ከዚህ በኃላ እምነታችሁ የት ነው? ብሎ ጠየቃቸው በማዕበሉ ላይ ወይንስ በእኔ ላይ ነው? ነው ጥያቄው::  ዛሬ የት ነው እምነታችን ጌታ ያሻግራል!  ሲቀሰቅሱትም ተነሳና ረዳቸው  እኛም ዛሬ ስንጠራው በዙፋኑ ያለ የሚሰማ ሊቀ ካህናት አለን::  የገረመኝ ማዕበሉን ፈርተው ቀሰቀቁሱት ገስጾ ጸጥ ሲያደርገውም ፈርተውም ተደነቁ ይላል::  ደግሞም ይህ ማነው? አስባላቸው ይሄኛው ፍርሃታቸው ለየት ያለ ነው በጀልባ አብሯቸው የሚጏዘውን ገና በደንብ አላወቁትም ነበር:: እርሱ ግን የእግዚአብሔር ልጅ ኢየሱስ መሲህ ነው!    የተከተልነውማ ጌታ የጌቶችም ጌታ ነው::  አሜን! 

በእየሱስ ስም ያቆመን ማዕበል ሁሉ ከፊታችን ጸጥ ይበል!  ጸሎታችንንም የምንቀበልበት ቀን ይሁን!  ዓይናችንም በእርሱ ላይ ይጽና ሁሉን ጸጥ ያደርግና በሰላም ያሻግረናልና!  ሃሌሉያ!!!

ሉቃስ 8:26-35

35 የሆነውን ነገር ሊያዩ ወጥተውም ወደ ኢየሱስ መጡ፥ አጋንንትም የወጡለትን ሰው ለብሶ ልቡም ተመልሶ በኢየሱስ እግር አጠገብ ተቀምጦ አገኙትና ፈሩ።

ይህንን ሰው ሊረዳው የመጣለት እየሱስ ብቻ ነው::  ሰዎች የሚችሉትን ረዱት ይኸውም በብረት አስሮ ማስቀመጥ ነው እንጂ ከዛ ያለፈ አልቻሉም::  እየሱስ የመጣበት አንዱ አላማ የተጠቁትን ነፃ ማውጣት ነበረና በማዕበል ሊቋቋመው ቢነሳም እንኳን አላቆመውም::  አልፎ መጥቶ ነፃ አወጣው::  አጋንንቱ የሚወስደው ወደ መቃብር ስፍራ ነው ከሙታን መካከል እራቁቱን ሊያኖረው::  አዳምና ሄዋን በኃጥያት ሲወድቁ እራቁታቸውን መሆናችውን አወቁ እንደዛ ሊያዋርዳቸው ነበረ  ተሳካለት::  እየሱስ መቶ ታደገንና ወደ ክብራችን መለሰን::  

ጠላት ሞትን እንጂ ህይወትን አይሰጥም ህይወትን የሚሰጠው እየሱስ ነው::  ህይወት እንዲበዛልን መጣ!  ዛሬም ስሙ ከስም ሁሉ በላይ ነው!  ጌታ እየሱስ ክርስቶስ ትናንትናም ዛሬም እስከዘላለም ድረስ ያው ነው::  ሰውን ለመርዳት እንደእየሱስ ግድ ይበለን::  እርዳታ የሚያስፈልገውን ሰው ሁሉ ወደ እርሱ እናምጣ::  ዛሬም ነፃ ያወጣል ይረዳልና!  አምላካችን በስራ ላይነው!  አሜን! 

ሉቃስ 8: 36-39

39 “ወደ ቤትህ ተመለስ፥ እግዚአብሔር እንዴት ያለ ታላቅ ነገር እንዳደረግልህ ንገር፡” ብሎ አሰናበተው። ኢየሱስም እንዴት ያለ ታላቅ ነገር እንዳደረገለት በከተማው ሁሉ እየሰበከ ሄደ።

ይህ ሰው የሚታወቀው ታላቅ ነገር የተደረገለት ተብሎ ነው:: ይህ ሰውከእየሱስ ጋር መኖር ፈልጎ ነበር ምናልባትም እነዚያ አስጨናቂ መናፍስት ይመለሳሉ ብሎ ይሁን ወይንም ውለታው በዝቶብኛል ብሎ ይሆናል ጌታ ግን አልፈቀደም::  የእግዚአብሔር አሰራር ግን ለየት ስለሚል ወደ ቤትህ ሂድ አለው::  የከተማው ሰው ሁሉ ወተው ሂድልን ብለው ለመኑት ጸሎታቸውንም ሰማና ሄደላቸው::  ነገር ግን ወንጌላዊ ወደ ከተማቸው ማስገባቱን አላወቁም::  ሰውየውም በከተማው ሁሉ እየሰበከ ሄደ ይላል:: ይህንን ሰው ለመርዳት ተሻግሮ የመጣውጌታ ፍሬ እፍርቶ ተመለሰ የከሰረ ቢመስልም ሂድልን ሲሉት::  በመንፈስ ግን የተሰራ  ስራ አለ::  ሂድልን ሲሉት ሰውየውንም ይዞባቸው በሄደ ነበር ስለሚወዳቸው ግን እሱን ሰጣቸው በእርሱ ተጠቅሞ ይረዳቸዋልና::

ምንም እንኳን እነዚህ ሰዎች አህዛብ ናቸው ተብሎ ቢታሰብም የሰማርያ  ህዝብ ያችን ሴት ሰምተው ከእነርሱ ጋር እንዲቆይ ለመኑትና ከተማው ሁሉ ተከተለው በተቃራኒው::  የዛሬ ምኞቴ ለአገራችንም  ይኸው ነው እርሱን መከተልና መፈለግ ይሁንልን:: የእግዚአብሔር ፍቅር በምድራችን ይስራ!! አሜን!!

ሉቃስ 8:40-42

42 አሥራ ሁለት ዓመት የሆናት አንዲት ሴት ልጅ ነበረችውና፤ እርስዋም ለሞት ቀርባ ነበረች። ሲሄድም ሕዝቡ ያጨናንቁት ነበር።

በአጋንንት የተያዘውን ሰው ነፃ አውጥቶ የከተማውም ሰው ሁሉ ሂድልን ብለውት እየተመለሰ ነበር::  በተቃራኒው በዚህኛው የባህሩ በኩል ደግሞ ብዙ ህዝብ በጉጉት እየጠበቁት ነበር ከነዚህም አንዱ ይህ የምኩራብ አለቃ ነበረ::  እርሱም  እየሱስ እግር ላይ ወድቆ ወደ ቤቱ እንዲመጣና የታመመችውን ልጁን እንዲፈውስለት ለመነው::  እርግጠኛ መሆን የሚቻለው በዛ ያለው ሰው ሁሉ ያውቀዋል እንዴት እግሩ ስር ወደቀ? እየሱስን የሚያሳድዱት የእርሱ ቢጤዎች ናቸው ይሄ እንዴት ተለየ?  

ቸሩ ጌታ ለምን እንደ መቶ አለቃው አላመንክም ከዚሁ ቃል ብናገር ትድናለች አላለውም ይህችን ብላቴና እቤቱ ሄዶ ለመፈወስ ተስማምቶ  መንገድ ጀመረ::  ያለንበት ድረስ መቶ የሚገናኘን ጌታ አይፈርድብንም  ጸጋን ሰጥቶ ያቆመናል እርሱ እንደሰው አይደለምና በደረስንበት እምነት እንመላለስ::  የሚረዳንና የሚያዝንልን ሊቀ ካህናት አለን!! ሊቀ ካህኔ እየሱስ እኔን ልትረዳ ስለምትፈጥን ተመስገን!! እንደሰው ስላይደለህ ተመስገን!!  ስለምትረዳኝም ተመስገን!!

ሉቃስ 8: 43-48

46 ኢየሱስ ግን፦ “አንድ ሰው ዳስሶኛል፥ ኃይል ከእኔ እንደ ወጣ እኔ አውቃለሁና፡” አለ።

ሰው ሁሉ እያጨናነቁትና እያጋፋት ባለበት ውስጥ የዳሰሰኝ ማነው? ሲል ሐዋርያቱም ተገረሙ::  መዳሰሱንና በእምነት መነካቱን የሚያውቅ ጌታ ግን ማነው አለ::  አስራ ሁለት ዓመት የተሰቃየችበትን በቅጽበት ዳሰሳ የተገላገለችው ሴት እየተንቀጠቀጠች ተናዘዘች::  ፈውስዋንም አረጋገጠች::  የምናጋፋ ሳይሆን አስተውለን በእምነት የምንነካ ያድርገን::  ነገርዋን ለማንም ሳትነግር ከልብዋ  ጋር ተማክራ  በእምነት መጥታ ዳስሳው ፈውስዋን አገኘች::  እምነትን የማያልፍ ጌታ በዛ ሁሉ ፍትግጊያ  ውስጥ  ዳሰሳን ሰማ::  በፊቱ የምንለምነውን የሚሰማ ተራ ያዙ ቢዚ ነኝ የማይል ጌታ ስሙ ይባረክ!

እርሱም፦ “ልጄ ሆይ፥ እምነትሽ አድኖሻል፤ በሰላም ሂጂ፡” አላት። እንዴት ልብ ያረካል ንግግሩ ልጄ ሆይ ብሎ ጠርቶ ፈውሷን በአደባባይ አወጀው! ያለ እምነት እግዚአብሔርን ደስ ማሰኘትም ሆነ ከእጁ መቀበል አንችልም::  እምነትም የሚመጣው ህያው የሆነውን ቃል በመስማት ነው::  ይህች ሴት ብዙ ስለእየሱስ ሰምታለች ማለት ነው መጥታ የዳሰሰችው::  ባህሉ ባይፈቅድላትም የነካችው እንደሚረክስ ብታውቅም ቅሉ መጣች::  እየሱስ ይቀድሳል እንጂ በምንም አይረክስም!!  

ቅዱስ አባት ሆይ የጸሎታችንን ለሆሳስ እንኳን ታዳምጥና ትመልሳለህና ክብር ይሁንልህ!!!

ሉቃስ 8: 49-56

50 ኢየሱስ ግን ሰምቶ፦ “አትፍራ፤ እመን ብቻ ትድንማለች፡” ብሎ መለሰለት።

ልጅህ ሞታለች የሚል መርዶ ለደረሰው አባት አትፍራ!! እመን ብቻ ትድንማለች እንዴት ይባላል?  አባትየውማ የመጣው በህይወት እያለች ከመቼው ያንን ባህር ተሻግሮ ተመልሶ ብሎ በጉጉት ጠብቆ ሲያገኘው በእግሩ ወድቆ የለመነው ይህ እንዳይሆን ነበረ::  ነገር ግን የፈራው ደረሰ ጌታም ጊዜውን ወሰደ ሌላም ሴት ለመርዳት ቆየ::  የመጣበትን ሳያደርግ የማይመለስ ጌታ የጉብኝት ጊዜዋ ከዚህ በላይ እንዲቆይ አልፈለገምና አሰባት የደምዋም ምንጭ ደረቀ!  ሃሌሉያ!!

አርፋለች ለተባለው መልክት ትድናለች ብሎ ማለት ይገርማል::  ጊዜ በእርሱ ላይ ተጽዕኖ የለውም ከጊዜ ውጪ ይኖራል የእኛ ጌታ::  የዘገየብን የመሰለን ይመጣል ጌታ አይቀርም::  በኢያኢሮስ ቤትም ሲደርሱ ልምድ ያላቸው ነበሩና ይህ የህይወት ንጉስ አልሞተችም ሲላቸው ሳቁበት በኃላ ለማፈር::  አብርሃምም ይህንኑ ሆንዋል ምን ትሰጠኛለህ ያለልጅ እሄዳለሁ አለ ጌታም ሙት ከሆነው ማህጸን ውስጥ ይስሃቅን ሰጥቶ አሳቀው::  ጌታ በስራ ላይ ነው:: ወላጅዎችዋንና ከተወሰኑት ሐዋርያትን ብቻ ይዞ ገባ ክብሩን ለማየት ጥቂቶች ተመረጡ::  ጌታም እጅዋን ይዞ፦ “አንቺ ብላቴና፥ ተነሺ፡” ብሎ ጮኸ።ነፍስዋም ተመለሰች፥ ፈጥናም ቆመች፥ ወላጆችዋም ተገረሙ ይላል::  ከሞት ትነሳለች ብለው ጠብቀው ይሆን?! እንጃ!! ብቻ ግን ልጃቸው ተነሳች!  ምስጋና ይድረሰው!  የሞተብን፥ የተውነውና የረሳነው ነገር ሁሉ ህይወት ያግኝ!  በእየሱስ ስም አሜን! 

ሉቃስ 9: 1-6

1 አሥራ ሁለቱንም ሐዋርያት በአንድነት ወደ እርሱ ጠርቶ በአጋንንት ሁሉ ላይ ደዌንም ይፈውሱ ዘንድ ኃይልና ሥልጣን ሰጣቸው፤2 የእግዚአብሔርንም መንግሥት እንዲሰብኩና ድውዮችን እንዲፈውሱ ላካቸው፥

እግዚአብሔር አብርሃምን ሲጠራው የምድር ነገዶችን ሁሉ በአንተ እባርካለሁ ብሎት ነበር::  ከአብርሃም ይስሃቅ ከዛም ያዕቆብ ከእርሱም 12 ነገዶች ወጡ::  ይኸው እዚህ ቃል ላይ እዛው ተስፋ ላይ ሲመለስ እናያለን አሳቡን የማይቀይር ጌታ መልሶ 12ቱን ነገዶች አስነሳና ላካቸው::  ሲልካቸውም በአጋንንት ሁሉ ላይ ደዌንም ይፈውሱ ዘንድ ኃይልና ሥልጣን ሰጣቸው፤ የእግዚአብሔርንም መንግሥት እንዲሰብኩና ድውዮችን እንዲፈውሱ ላካቸው::  መንግስት የእርሱ ብቻ ነው የሰይጣን መንግስት መሸነፍና መልቀቅ መፍረስም አለበት::  ይኸው ተስፋ በእኛ ቀጥሏል ሊቀ ካህናችን እየሱስ እየማለደልን በአብ ቀኝ ነውና ዛሬም ድል የእኛ ነው::  እግዚአብሔር ዛሬም በጤና እንድንሆን ፈቃዱ ነው:: በመጀመርያ የእግዚአብሔርን መንግስት እንዲሰብኩ ላካቸው ይህ ዋናው የተላኩበት አገልግሎታቸው ነው ከዛም ደዌን መፈወስ እኛንም ልኮናል:: አሜን!

ሉቃስ 9: 7-9

7 አንዳንድ ሰዎች፡— “ዮሐንስ ከሙታን ተነሣ፥” 8 ሌሎችም፡— “ኤልያስ ተገለጠ፥” ሌሎችም፡— “ከቀደሙት ነቢያት አንዱ ተነሥቶአል፡” ይሉ ስለ ነበሩ፡ አመነታ።

ሄሮድስን ግራ ይግባው እንጂ ዝናው እየተሰማ ያለው ዮሃንስ ከሙታን ተነስቶ አይደለም፥ ኤልያስም አይደለም ወይንም  ከቀደሙት ነቢያት አንዱም አይደለም! እነርሱን አስቀድሞ የላከ ጌታ እንጂ የጫማውን ጠፍር እንኳን ለመፍታት የማይበቁ መሆናቸውን ያወቁ ባርያዎቹ ናቸው እነዚህ::

እግዚአብሔር ለአዳምና ለሄዋን ገና በኃጥያት ሲወድቁ ቃል የገባውን ለአብርሃምም እንደነገረው የዓለምን ሁሉ ነገዶች ሊታደግ የመጣው እራሱ ፈጣሪ የሆነው ታዳጊው አምላካችን ነው:: የእግዚአብሔር በግ ንጹህ በግ ስለኃጥያታችን ተላልፎ የሚሰጥ በግ ነው እየሱስ! እራሱን ያለስስት በእኔ እግር ገብቶ የተገኘ ወዳጅ!  ድንቅና ተአምራትን እያደረገ የተገለጠ ጌታ ሁሉን የፈወሰ የሞቱትን ያስነሳ ዛሬም ያልተቀየረ የሚሰራ ጌታ ነው!  አሜን

ሉቃስ 9:10 ሐዋርያትም ተመልሰው ያደረጉትን ሁሉ ነገሩት። ከእርሱ ጋርም ወስዶአቸው ቤተ ሳይዳ ከምትባል ከተማ አጠገብ ወደ ምድረ በዳ ለብቻው ፈቀቅ አለ።

ጌታ እየሱስ አሥራ ሁለቱን ሐዋርያት ጠርቶ በአጋንንት ሁሉ ላይ ደዌንም ይፈውሱ ዘንድ ኃይልና ሥልጣን ሰጥቶ ላካቸው::  ከተማሪነት አልፈው ወደ  ማገልገል መጡ:: ለማገልገል ሲወጡ ስንቅ ሳይሆን የያዙት ኃይልና ሥልጣን ነበረ የተቀበሉት::  ከአገልግሎትም መልስ የሆነውን  ሁሉ ነገሩት::  እርሱ ግን ወደ ምድረ በዳ ይዟቸው ሄደ::

ለምን ወደ ምድረበዳ ወሰዳቸው?  አገልግሎቱን አገልግለው የመጡት እርሱ በሰጣቸው ኃይልና ሥልጣን ነው በራሳቸው አይደለምና በፊቱ እርፍ ብለው ኃይላቸው እንዲያድሱና እንደገና በኃይል መውጣት ይሆንላቸው ዘንድ ነው:: አገልግለን የተጣልን እንዳንሆን እራሳችንን በእግሩ ስር ማድረግን እንማር::  እየሱስም ሲጠመቅ አብ ከመሰከረለትና መንፈስ ቅዱስም በእርሱ ላይ ካረፈ በኃላ የሄደው ወደ ምድረበዳ ነው ለብቻው ከአባቱ ጋር ለመቆየት::  እኛም ይህንን ወደ ጸጋ ዙፋኑ መቅረብን ልናዘወትር ይገባል::  

ይህንኑ ሐዋርያት ሲተገብሩት እናያለን እኛ ለቃሉና ለጸሎት እንተጋለን ሲሉ እንዲሁም በግልጥነት እንድንናገር  ስጠን ሲሉትና በኃይል ሲሞላቸው እናያለን::  እንትጋ!

ሉቃስ 9:11 ሕዝቡም አውቀው ተከተሉት፤ ተቀብሎአቸውም ስለ እግዚአብሔር መንግሥት ይነግራቸው ነበር፥ መፈወስ ያስፈለጋቸውንም ፈወሳቸው።

ወደ ምድረበዳ ሐዋርያቱን ለማሳረፍ ይዞ ቢወጣም ህዝቡ ግን ተከተሉት::  መልካሙ ጌታ አልመለሳቸውም እንደልማዱ ስለ መንግስቱ ይነግራቸው ነበረ::  በመጀመርያ ቃሉን ያስተምርና መንግስቱን ይገልጥ ነበር በቃሉ::  ዛሬም መንግስቱን በቃሉ ውስጥ ያስተምራል:: ቃሉን ካስተማረ እምነትም ከቃሉ ከተፈጠረ በኃላ መፈወስ ያስፈለጋቸውንም ፈወሳቸው። ከእምነታቸው የተነሳ የሰራበት ከእምነትም መጉደል የተነሳ ምንም ማድረግ ያልቻለበት አጋጣሚ አለ:: 

ያለ እምነት እግዚአብሔርን ደስ ማሰኘት አይቻልም!  እምነት ከመስማት የምንሰማውም የእግዚአብሔርን ቃል ነው::  ከቃሉ ውጪ እምነት ከየትም አይመጣምና!  ለቃሉ ጊዜ ይኑረን በእግሮቹ ስር ቁጭ ብለን እንደማርያም እንማር! ቃሉን ላከ ፈወሳቸው ከመከራቸውም አዳናቸው እንደሚል ጌታ ቃሉን ይልካል ካለንበትም ያወጣናል ይፈውሰንማል!  አሜን

ሉቃስ 9:  12-17

16 አምስቱንም እንጀራና ሁለቱን ዓሣ ይዞ፥ ወደ ሰማይ አሻቅቦ አየና ባረካቸው ቆርሶም ለሕዝቡ እንዲያቀርቡ ለደቀ መዛርሙርቱ ሰጠ።

እንደሐዋርያቱ ምክር ቢሆን ስለመሸ ባሰናበታቸው ነበረ::  እርሱ ግን ጥቂቱን ባርኮ አጠገባቸውና ተረፈ! የእኛ ምክር ይኸው ነው የእርሱ ግን ተፈጥሮን ሁሉ ያልፋልና እረፉ እኔም አምላክ እንደሆንኩ እወቁ ያለን ለዚሁ ነው::

ዛሬ እጃችን ላይ ምን አለ?  ያለውን እናቅርብለት በትንሽዬዋ አይምሯችን አስበን አውጥተን አውርደን አይሁን::  ያለንን በእምነት ወደ እርሱ ይዘን እንቅረብ አንዳንዴ ከምናልፍበት ነገር የተነሳ አምላካችን ማን እንደሆነ ይጠፋናል መሰለኝ::  እርሱ ሁሉን የፈጠረ ነው፥ በሁሉ ላይ ስልጣን ያለው፥  መንደርደርያና መነሻ አያስፈልገውም የሌለውን እንዳለ አድርጎ የሚጠራ ጌታ ነው! እንታመንበት ከስጋችን ሳንማከር ወደ እርሱ እንቅረብ  እርሱም እንደታላቅነቱ መጠን ይሰራል::

ሉቃስ 9: 18-20

20 “እናንተስ እኔ ማን እንደ ሆንሁ ትላላችሁ?” አላቸው። ጴጥሮስም መልሶ፡— “ከእግዚአብሔር የተቀባህ ነህ፡” አለ።

እየሱስ ጠፍቶት አይደለም ሌሎች ስለእኔ ምን ይላሉ ብሎ የጠየቃቸው ለሚቀጥለው ጥያቄ መንደርደርያ እንዲሆን እንጂ::  ለእናንተ ማን ነኝ?!  ዛሬም ይህንን ጥያቄ መመለስ አለብን::  ጴጥሮስም አንተማ ከእግዚአብሔር የተቀባህ መሲህ ነህ አለው:: 

ለእኔ?  የእግዚአብሔር በግ ነህ!  ስለዚህ ኩነኔ የለብኝም!  በሞትህም ሞቴ ተሻረ – አዳኜና ማምለጫዬ ነህ:: ዕዳዬን የከፈልክ! ቅድስናዬ ጽድቄ የዕዳው ጽህፈት የተሻረልኝ!! የእግዚአብሔር ወገን አደረከኝ! ከቁጣህም አዳንከኝ!  ወዳጅ ሆንኩኝ! እየሱስ ጌታዬና አምላኬ ነህ እገዛልሃለሁ!

ሉቃስ 9:21—22 እርሱ ግን፡— “የሰው ልጅ ብዙ መከራ ሊቀበል በሽማግሌዎችም በካህናት አለቆችም በጻፎችም ሊጣል ሊገደልም በሦስተኛውም ቀን ሊነሣ ይገባዋል፡” ብሎ ለማንም ይህን እንዳይናገሩ አስጠንቅቆ አዘዘ።

ማንነቱን ሲጠይቃቸው ከእግዚአብሔር የተቀባህ ብሎ ጴጥሮስ በመንፈስ ተረድቶ መለሰ::  ጌታም ከዚህም የበለጠ ስለእኔ እወቁ ብሎ በእርሱ ላይ የሚሆነውን  ገለጸላቸው::  

የሚደርስበትን ሲዘረዝር:-

መከራ እንደሚቀበል 

በሽማግሌዎችም በካህናት አለቆችም በጻፎችም ሊጣል – ግንበኞች የጣሉት የማዕዘን ራስ እየሱስ

ሊገደልም – ስለእኛ በደል ሙሉ ዋጋ ሊከፍል

በሦስተኛውም ቀን – የሞትንና የሲዖልን ቁልፍ ተቀብሎና መቃብሩን ፈንቅሎ ሊነሳ!!

ሊከብርና ሊገንን ይገባዋል!!  አሜን!

እነሱ የሚፈልጉትና የሚጠብቁት የምድር ንጉስ ከሮም አገዛዝ ነፃ የሚያወጣ እርሱ የሚለው እሞታለሁ::  በመጨረሻ ወደ ሰማይ ሊያርግ ሲል መንግስትን ለእስራኤል መቼ ትመልሳለህ ነበረ ጥያቄያቸው:: መንፈስ ቅዱስ ሲመጣ እንጂ ይህንን ጥልቅ እውነት የተረዱት ከዛ በፊት ምንም አልገባቸውም:: 

ዛሬም በመረዳት እንመላለስ የዳነው በስራ ሳይሆን በእርሱ መስዋትነት ነውና የምንመካበትም የለንምና ዝቅ ብለን በትህትና ጌታን እናገልግል ከማንም አንሻልም::  ይህንንም የመዳን እውነት ለፍጥረት እንንገር::

ሉቃስ 9:23 ለሁሉም እንዲህ አላቸው፡— “በኋላዬ ሊመጣ የሚወድ ቢኖር፥ ራሱን ይካድ መስቀሉንም ዕለት ዕለት ተሸክሞ ይከተለኝ።

የሚደርስበትን መከራ ነግሯቸው ሲያበቃ እነሱንም እንደሚጠብቃቸው ነገራቸው::  እነርሱ  እያዘኑ ያሉትና ልባቸው የከበደው ስለእርሱ ነበር ለካስ እነርሱም መስቀል መሸከም ይጠብቃቸዋል::

በዘመኑ መስቀል ተሸክሞ መሄድ እንጂ መመለስ የለምና የሚናገረው በዘመኑ የሮም አገዛዝ የሚፈጸም ቅጣት ስለሆነ ጠንቅቀው ያውቁታል::  የሚሰቀሉበትን መስቀል የመሸከም ግዴታ የሟቹ ነው::  ራስን ካልካዱ በስተቀር ወደዚህ ህይወት ማን ይገባል?!  ይህ መሸከም የሚቀጥል ነው በየዕለቱም ነው::  እኛ የራሳችን አይደለንም በዋጋ ተገዝተናል!

ሉቃስ 9:24-27

25 ሰው ዓለሙን ሁሉ አትርፎ ራሱን ቢያጠፋ ወይም ቢያጐድል ምን ይጠቅመዋል?

መስቀል ተሸክማችሁ ተከተሉኝ ያለውን ችላ ማለትና ለዓለም ትርፍ መሮጥም ሆነ በኃጥያት ማግበስበስ በምድር እንዲመቸን ሊያደርግ ይችል ይሆናል ነገር ግን ነፍሳችን የሚያስፈልጋትን አዳኝ ባታውቅ ምን ይጠቅማል?! የተከማቸው ኃብት ከስጋም ሆነ ከነፍስ መሞት አያስጥልም::

ዉደ ነፍሳችን እረኛ ዞር እንድንልና እንድናውቀው የረዳን ጌታ ይባረክ! መዳን ብቻ ሳይሆን የሚጠበቅብን በቃሉ አለማፈርም ነው:: በእኔና በቃሌ የሚያፍር ሁሉ፥ የሰው ልጅ በክብሩ በአባቱና በቅዱሳን መላእክቱ ክብርም ሲመጣ በእርሱ ያፍርበታል ይላልና በጌታና በቃሉ እንዳናፍር ጌታ ይርዳን!

አባት ሆይ ዕለት ዕለት መስቀላችንን ተሸክመን እንድንከተልህ እንዲሁም በአንተ ላይ ዓይናችንን እንድናደርግና በሙሉ ልባችን እንድንከተልህ ጸጋህን አብዛልን! 

ሉቃስ 9: 28-29

29 ሲጸልይም የፊቱ መልክ ተለወጠ፤ ልብሱም ተብለጭልጮ ነጭ ሆነ።

እናንተስ ማን ትሉኛላችሁ ያለው ጌታ ማንነቱን በመጠኑ ሊያሳያቸው ወደ ተራራ ወሰዳቸው::  ደግሞም ጌታ እውነት እላችኋለሁ፥ በዚህ ከሚቆሙት ሰዎች የእግዚአብሔርን መንግሥት እስኪያዩ ድረስ ሞትን የማይቀምሱ አንዳንድ አሉ እንዳለው ክብሩን አሳያቸው::  

አብሯቸው ቢበላና ቢጠጣ ቢመላለስም እርሱ ግን የተፈራውና የተከበረው ጌታና አምላካችን ነው::  ስለዚህም ያየነውንና ከገናና ክብሩ የሰማነውን የዳሰስነውን እናወራለን እንመሰክራለን ብለው ጻፉልን::  ሃሌሉያ! 

በዚያ ተራራ ላይ እየጸለየ ፊቱ ተለወጠ ይህንንም በሙሴ እናያለን አርባ ቀንና ለሊት ከጌታ ጋር ቆይቶ ሲወርድ ፊትህን ሸፍን እስኪሉት ደረሰ::  የእየሱስ ግን የፊቱ መለወጥ ብቻ ሳይሆን ልብሱም ተብለጨለጨ ወይም አጣቢ ሊያነፃው እስከማይችል የምድር ያልሆነ መዋብ ሆነባቸው:: ይህ ጌታ ዛሬ ከእኛ ጋር ነው የምናጋፋ ሳይሆን ክብሩን የምናይ ያድርገን::  አሜን!!!

ሉቃስ 9: 30-31

30 እነሆም፥ ሁለት ሰዎች እነርሱም ሙሴና ኤልያስ ከእርሱ ጋር ይነጋገሩ ነበር፤

ጌታ ክብሩን ሊያሳይ ይዟቸው በወጣበት ሁለት ሰዎች ማለትም ሙሴና ኤልያስ ከእርሱ ጋር ይነጋገሩ ነበር::  የእነዚህ ሰዎች ተጽዕኖ በእስራኤሎች ላይ ቀላል አይደለም::  ለምን እነዚህ ታዩ?  ለምን አዳም፤ ዳዊት ወይም ደግሞ አብርሃም አልታዩም? 

በጥቂቱ ለመጥቀስ ሙሴ ህግን ወክሎ ኤልያስ ደግሞ ነብያትን ወክሎ ቆመዋል::  ቃል እንደገባው አምላክ ሰው ሆኖ አዩ::  ይህ ተአምር  ነው!!!  በሙሴ ዘመን እስራኤላውያን እግዚአብሔር አይናገረን እንሞታለን አሉ::  ዛሬ እንደዛ የተንቀጠቀጡለት ጌታ በመካከላቸው ቆሞ አላወቁትም::  ክብሩ ሰማያትን ሸፍኗል!!  ይህ ትልቅ ጌታ ተላልፎ በሰው እጅ ለመሞት መጣ?!!!  እንዴት ጥልቅ ነው ደህንነታችን::  ከእነርሱም ጋር የተነጋገረው በኢየሩሳሌም ሊፈጽም ስላለው ስለ መውጣቱ ይናገሩ ነበር። ይደንቃል!  የተዋጀሁት በእንሰሳ ደም ሳይሆን ክብሩን ጥሎ በመጣውና እጅግ በወደደኝ ቅዱስና ኃያል አምላክ ነው!  መዳኔ ውድ ነውና ተመስገን!!

ሉቃስ 9: 32-33

33 ከእርሱም ሲለዩ ጴጥሮስ ኢየሱስን፡— “አቤቱ፥ በዚህ መሆን ለእኛ መልካም ነውና አንድ ለአንተ አንድም ለሙሴ አንድም ለኤልያስ ሦስት ዳሶች እንሥራ፡” አለው፤ የሚለውንም አያውቅም ነበር።

ጴጥሮስ የሚለውንም አያውቅም ነበረና ሶስት ዳስ ማቆም ፈለገ:: በእውኑ ኢየሱስ ከሙሴና ከኤልያስ መደዳ ነውን? ጌታም አልወቀሰውም ታገሰው:: የእኛ አምላክ በላይ በሰማይ በዙፋኑ ላይ የሚቀመጥ ጌታ ነው የሰው እጅ በሰራው ዳስ አይኖርም::

የእግዚአብሔር ዓላማ ምንድነው ይህንን ክብር ሲያሳያቸው? ክብሩን አይተው ምስክር ይሆኑ ዘንድ ነው:: ሶስቱን ብቻ መርጦ ነው ይዞ ወደ ተራራው የወጣው:: እነርሱም እንቅልፍ የከብዶባቸው ያለ ቢሆንም ግን ነቅተው ክብሩን አዩ:: የሚነጋገሩትንም ሰሙ ስለሚመጣው መከራውና በእየሩሳሌም ስለሚፈጸመው የሰው ልጆችን ነፃ የማውጣት ተልዕኮና ስለኢየሱስ ተላልፎ መሰጠት ነበር::

ክብሩን እንዳናይ ከሚከለክል ድካም ጌታ ያውጣንና ክብሩን እንይ:: ሐዋርያቱ አብረውት በጸሎት ተግተው ቢሆን ኖሮ ይህ ባልሆነ ነበር:: ዛሬም በጸሎት እንድንተጋና ክብሩን እንድናይ ጸጋው ይብዛልን:: አሜን!

ሉቃስ 9: 34-36

35 ከደመናውም፡— “የመረጥሁት ልጄ ይህ ነው፥ እርሱን ስሙት፡” የሚል ድምፅ መጣ።
የሚለውን የማያውቀው ጴጥሮስ ሲናገር ሳለ ደመና መጣና ጋረዳቸው::  ከደመናውም ድምጽ መጣ ልጄን ስሙት የሚል::  ድምጹ ልጅነቱን አውጆ እርሱን ስሙት የዳሱንም አሳብ ተውት በዚህ ተራራ ላይ ለመኖር  ማቀዱን ተውትና እርሱን ስሙት እርሱ የመጣው የሰውን ልጅ ታድጎ ወደ ክብሩ ሊመለስ ነው! በዝች በጥንጥዬዋ አእምሯችን የጌታን ነገር ማወቅና መረዳት አንችልም መንፈስ ብቻ ይገልጥልናል::
ብዙ ጊዜ ኢየሱስ የሚያደርገውን ተአምራት  ለማንም አትናገሩ ብሎ ሰዎችን ያዛል::  እዚህ ቦታ ላይ ምንም አላላቸውም እነርሱ እራሳቸው በዚያ ወራት ለማንም አላወሩም::  ቢያወሩስ ማን ሊያምናቸው ሙሴንና ኤልያስን አየን ቢሉ ሰው እንዴት እንደሚያያቸው ማሰብ ነው:: ደመና በላያችን መጣና ድምጽ ከደመና ውስጥ ሰማን ብለው ቢያክሉማ ለየላቸው ነው የሚባሉት::  የምድርን ምናምንቴ ሰብስቦ ልጁን እንድናውቅ ላደረገ ለጌታ ክብር ይሁንለት::  ህይወት ተገልጧል ጌታችን ጸጋንና እውነትን ተሞልቶ በእኛ አድሯል!
ዛሬም የእግዚአብሔርን ልጅ የሆነውን የእየሱስን ድምጽ እንስማ!  በራሳችን ከመሮጥና የማናውቀውን ከማውራት እንቆጠብ!  ጌታ ሆይ ድምጽህን ልስማ ክብርህንም ልየው!  አሜን! 

ሉቃስ 9: 37
37 በነገውም ከተራራ ሲወርዱ ብዙ ሕዝብ ተገናኙት።
ወደ ተራራው ሲወጣ ሶስቱን ሐዋርያት ብቻ ይዞ ነበር የወጣው::  እነርሱም ሲጽፉልን ስለዚህ ልምዳቸው ከገናናው ክብሩ ሰምተናል አይተነዋል ዳስሰነዋል እያሉ አሉን::  በክብሩ ተገለጠላቸው!  ከክብሩ የተነሳ ምን እንደሚል ጴጥሮስ አያውቅም ነበረ::
እዛው ተራራ ላይ አድረው ነበረ የወረዱት::  ለእኛም ዛሬ ከእርሱ ጋር መዋል ማደር ይብዛልን::  
አባት ሆይ ዛሬ ጸሎቴ ክብርህን አሳየኝ ከአንተ ጋር መሰንበት ይሁንልኝ: ይብዛልኝ::  በጸጋህ ይቻላልና ከስጋ ድካም ወጥቼ በፊትህ መትጋት  ለእኔም ለህዝብህም ይሁንልን!  በኢየሱስ ስም አሜን! 

ሉቃስ 9: 38-42
41 ኢየሱስም መልሶ፡— “እናንተ የማታምን ጠማማ ትውልድ፥ እስከ መቼ ከእናንተ ጋር እኖራለሁ? እስከ መቼስ እታገሣችኋለሁ? ልጅህን ወደዚህ አምጣው፡” አለ።
ጴጥሮስ የሚለውን ሳያውቅ ስለሶስቱ ዳስ ሲያወራ ጌታ አልወቀሰውም እዚህ ጋር ግን እስከ መቼስ እታገሣችኋለሁ? ይላቸዋል::  ጌታ እምነትን ይፈልጋል ያለ እምነት እርሱን ደስ ማሰኘት አይቻልም::
ይህ የሆነው አንድ አባት ያለውን አንድ ልጁን ጋኔን እያሰቃየው አምጥቶት ሳለ ዘጠኙ ደቀ መዛሙርት ሊያወጡት አልቻሉም ነበረ::  የጌታ ክብር ተገልጦ ሶስቱ ሐዋርያት ከአእምሮ በላይ የሆነ ሚስጥር አይተው ሲወርዱ ጠላት ሽንፈትን እያስወራ ጠበቀው:  በዚህም ምክንያት ጌታ የማታምን ጠማማ ትውልድ ብሎ ጠራቸው::  ዛሬ ምን እንባል ይሆን?  እንደው በስንት ጊዜ አንዴ የጌታን ኃይል እያየን ላለን? እርሱ ግን አልተለወጠም ዛሬም ይሰራል:: 
ልጅህን አምጣው አለውና ሲቀርብም ጋኔኑ ጣለውና አንፈራገጠው፤ ኢየሱስ ግን ርኵሱን መንፈስ ገሥጾ ብላቴናውን ፈወሰው ለአባቱም መለሰው። ይህንን እንድናደርግ ስልጣንና ኃይል ተሰቶናል በምድር አምባሳደሮቹ እኛ ነን:: አባት ሆይ የተጨነች ነፍስ ነፃ ትውጣ ዛሬ:: አሜን! 

ሉቃስ 9: 43-45
44 ለደቀ መዛሙርቱ፡— “የሰው ልጅ በሰው እጅ ይሰጥ ዘንድ አለውና እናንተ ይህን ቃል በጆሮአችሁ አኑሩ፡” አለ።
ሐዋርያቱ ያቃታቸውን አጋንንት አውጥቶ የታመመውን ልጅ ለአባቱ በጤና ሲሰጥ ያዮ ሁሉ ከእግዚአብሔር ታላቅነት የተነሣ ተገረሙ። እርሱ ግን የሰው ልጅ በሰው እጅ ይሰጥ ዘንድ አለውና የመጣሁበት ዓላማ አልተለወጠም ብሎ ለደቀ መዛሙርቱ ነገራቸው:: እነርሱ ግን ይህን ነገር አላስተዋሉም፥ እንዳይገባቸውም ተሰውሮባቸው ነበር፤ ስለዚህ ነገርም እንዳይጠይቁት ፈሩ ይላል ቃሉ።
ክብሩ ተገልጦ አይተው በፊቱ የሚመጣውን ደዌ ሁሉ እየፈወሰ ሲርባቸው እየመገበ ያለ ምንም እንቆቅልሽ እየተመላለሱ ታድያ ከዚህ በላይ ሌላ መሪ ምን ያስፈልጋል?! ተላልፌ እሰጣለሁ: እሞታለሁ ቢልም ትነግሳለህ ነውና በእነርሱ አእምሮ ውስጥ ያለው መስማና ማስተዋል አልቻሉም:: እኛም በራሳችን ነገር ተይዘን የሚለንን እንዳንሰማ እንዳያደርገን ጌታ ይርዳን!
አባት ሆይ ተላልፈህ የተሰጠኸው ስለእኛ ነውና ተመስገን:: 

ሉቃስ 9: 46

46 ከእነርሱም ማን እንዲበልጥ ክርክር ተነሣባቸው።
የሰው ልጅ በሰው እጅ ይሰጣልና ይህንን በጆሮአችሁ አኑሩ  እያላቸው እርሱን ችላ ብለው በእራሳቸው ነገር ላይ ተጠምደዋል::  ምናልባትም ሶስቱን ብቻ ይዞ ወደ ተራራ ወጥቶ ስለነበረም ይሁን በሌላ ምክንያት ብቻ ማወቅ ፈልገዋል ማን ትልቅ እንደሆነ::  ከመጣበትና ከተጠሩለት  ዓላማ ጋር ሲተያይ የሚሉትና የሚሰሩት ይገርማል ጌታ ግን ይታገሳቸው ነበር::  አሁን ምን አልኳችሁና ይህንን ትጠይቃላችሁ አላለም ወይንም ደግሞ እኔ ነኝ ትልቅ አላለም እውነታው እርሱ ቢሆንም::  መንፈስ ቅዱስ ሆይ የመንግስት ሚስጥር ይገለጥልን የምትናገረንንም ማስተዋል ይሁንልን::
ዛሬም የቤተክርስቲያን ችግር ይህ ነው:: የትኛውም የአካል ብልት ትልቅነት አይገባውም ትልቅ ኢየሱስ ብቻ ነው:: የጫማውን ጠፍር መፍታት አይገባኝም እንዳለው መጥምቁ ዮሃንሰ እንደዛ ነው ማለት የሚገባን:: በተቃራኒውም እኔ አልረባም ብሎ ማለትም ትክክል አይደለም በክርስቶስ ውስጥ መሆናችንን እናስተውል:: 


ሉቃስ 9: 47-50
48 “ማንም ይህን ሕፃን በስሜ የሚቀበል እኔን ይቀበላል፤ የሚቀበለኝም ሁሉ የላከኝን ይቀበላል፤ ከሁላችሁ የሚያንስ እርሱ ታላቅ ነውና፡” አላቸው።
ከሁላችሁ የሚያንስ እርሱ ታላቅ ነውና የሚለው አባባል በየትኛውም የዓለም ቀመር አይሰራም በእግዚአብሔር ቤት እንጂ::  እንደ ህፃናት ካልሆንን በቤቱ ማገልገል አይቻልም::  ህፃንን መቀበል ማለት በየትኛውም ማኅበረሰብ ትንሽ ነው ማዕረግም የለውም ስለዚህ ሁሉን መቀበል አለብን::  እንዴት ትንሹ ትልቅ ይሆናል?  ማነስን የሚፈልግ ማንም የለም:: አሁንም እያስቸገረን ያለው እርሱ ነው::  ዝቅ ማለት አንወድም!  ጌታ ግን ክብሩን ሁሉ ጥሎ መጣና ዝቅ አለ ልያውም የዝቅታ ሁሉ ጥግን ዝቅ ብሎ በግርግም ተኛ::  እኔ ማነኝ ዝቅታን የምጠላ? እኔ ማነኝ ወንድሜና እህቴ ከእኔ ይሻላሉ የማልል?! ጌታ ሆይ አስበኝ!! ተመዝኜ ቀልዬ እንዳልገኝ!
ሌላውን ስለመቀበል ሲናገራቸው ዮሐንስም ትዝ አለውና አንድ ሰው በስምህ አጋንንትን ሲያወጣ አየነው፥ ከእኛ ጋርም ስለማይከተል ከለከልነው አለው። የጌታም መልስ ጎሽ ልክ ነህ አላለውም የማይቃወማችሁ ከእናንተ ጋር ነውና አትከልክሉት ነበረ::  አጋንንትን ማውጣት ጌታን በማያውቅ ሰው እንደማይቻል ሰባቱ የአስቄዋ ልጆች ምሳሌ አሉን:: ዛሬ በድርጅት ስም ተይዘን ስንቱን ገፍተን ይሆን?  እኛ ቤተክርስትያን እንደዛ አይደለም በሚል ልምድ ላይ በተደገፈ አስተያየት ስንቱን ወደኃላ መልሰን ይሆን?!  አቤቱ እኛንም አስበን በማስተዋል መመላለስ  ይሁንልን! አሜን 

ሉቃስ 9: 51-56
55 እርሱ ግን ዘወር ብሎ ገሠጻቸውና፡— “ምን ዓይነት መንፈስ እንደ ሆነላችሁ አታውቁም፤
ወደ እየሩሳሌም ለበዓል ሲሄዱ በእግር ነውና መንገዱም እሩቅ ስለሆነ እየታረፈ ነው የሚኬደው::  እዚህ ስፍራ ላይ ለማረፍ ፈልጎ ሳምራውያን አልተቀበሉትም:: በዚህ የተነሳ ክብሩን ያዩት ሐዋርያት እሳት ከሰማይ ይውረድ እንበል አሉት::  ያሉበትን የአዲስ ኪዳን ጅማሬ ብዙም አልተረዱትምና ይህንን አሉ::  
አምላክ እራሱን ከሰው ልጅ ጋር ሊያስታርቅና ህግን ሁሉ ሊፈጽም መጥቶ ሳለ ጥፋትማ አይታሰብም::  ህግ በሙሴ ተሰጠ ኢየሱስ ግን ጸጋንና እውነትን ተሞልቶ በእኛ አደረ:: ስለዚህም ገሰጻቸው:: ዓላማውንም እንዲህ ሲል ገለጸ:- የሰው ልጅ የሰውን ነፍስ ሊያድን እንጂ ሊያጠፋ አልመጣም፡” አለ። ወደ ሌላ መንደርም ሄዱ። እኛም ዛሬ ከመጣላትና የኃይልን ቃል ከመነጋገር ዞር እንበልና እንሂድ ለሚበድሉንና ለሚያሳድዱን  እንጸልይ:: ይህ መንፈስ ይብዛልን! 

ሉቃስ 9: 57-62
62 ኢየሱስ ግን፡— “ማንም ዕርፍ በእጁ ይዞ ወደ ኋላ የሚመለከት ለእግዚአብሔር መንግሥት የተገባ አይደለም፡” አለው።
ጌታ ኢየሱስ እዚህ ስፍራ ላይ ሶስት አይነት ሰዎች ገጠሙት:- አንዱ ልከተልህ አለው ሁለቱ ደግሞ ተከተሉኝ እያላቸው መከተም ፈልገው ምክንያት እየደረደሩ ያሉ ናቸው:: 
ጠጋ ብለን ስናይ ልከተልህ ያለው ድንቅና ተአምር አይቶ ብዙዎችን ሲመግብና ሲፈውስ ተመልክቶ ነው::  ጌታም ለኔም ማረፍያ የለኝም አለው::  
ሁለተኛውና ሶስተኛው ተጠርተው ሳሉ አንዱ አባት ታሞበታል ላስታምም አለ ለመከተል መቼ እንደሚመጣም አያውቀውም::  ከሁለት ትክክለኛ ምርጫዎች መካከል ነበረ ለመምረጥ የተቸገረው::  ጌታም ግን አንተስ ሄደህ የእግዚአብሔርን መንግሥት ስበክ አለው። የጌታን ነገር እናስቀድም::
ሶስተኛው ልሰናበት አለው አጭር ጊዜ ቢሆንም እንኳን  ተጠርቶ ወደ ኋላ የሚመለከት ለእግዚአብሔር መንግሥት የተገባ አይደለም አለው።
አስቀድመን መንግስቱን እንፈልግ እግዚአብሔርንም በሙሉ ኃይላችን አሳባችንና ጉልበታችን እንውደደው:: ምንም ነገር ከጌታችን አይብለጥብን በየዕለቱ ውሳኔያችንም እናስቀድመው:: 
አባት ሆይ ከአንተ ጥሪ ይልቅ በፊትህ ከመሆን ይልቅ ቅዱሳንህን ከማገልገል ይልቅ ብቻ በፈለከኝ ቦታ ከመሆን ይልቅ ሌላ ነገር አስቀድሜ ቢሆን ይቅር በለኝ ከተሰወረም ኃጥያት አንፃኝ በከበረ ደምህም እጠበኝ እንዳስቀድምህም ማስተዋልና ጸጋን ስጠኝ::  አሜን! 



ሉቃስ 10: 1-3
2 አላቸውም፡— “መከሩስ ብዙ ነው፥ ሠራተኞች ግን ጥቂቶች ናቸው፤ እንግዴህ የመከሩን ጌታ ለመከሩ ሠራተኞች እንዲልክ ለምኑት 3 ሂዱ፤ እነሆ፥ እንደ በጎች በተኵላዎች መካከል እልካችኋለሁ።
ከዚህ በፊት በነበረው ምዕራፍ ላይ ሐዋርያቱን ኃይልና ስልጣን ስጥቶ ላካቸው::  እዚህ ስፍራ ላይ እንደምናየው ሰባ ሰዎችን ሁለት ሁለት አድርጎ ላከ::  ለምን ሌሎችን ላከ? ምክንያቱም መከሩ ብዙ ስለሆነነው::  ሁለት ደግሞ ለህብረት መጀመርያ ነው::  ሁለት ሆነው በምድር ተስማምተው ሲጸልዩ  እኔ ከሰማይ እሰማለሁ ይላልና ጌታ::  ሌላው ጌታ ጊዜ የለውም ከምድር የሚሄድበት ጊዜ እየደረሰ ነበረ በሌላ በኩል ደግሞ መድረስ የነበረበት ሁሉ አልደረሰምና ነው:: አሁንም መምጫው በደጅ ነው ጊዜ የለም ጌታ ብዙዎች ይድኑ ዘንድ ታግሶ እየጠበቀ ነው ሙሽራውን ለመውሰድ በቅርብ ይመጣልና ወገኖቼ በርትተን ወንጌልን ለፍጥረት ሁሉ እናድርስ::  ጌታ ሆይ ላከን ደግሞም እርዳን::
እንዲሁም ለምኑ ብሎ እነሱኑ ላከ ዛሬም ጸሎታችን የመከሩን ጌታ ሰራተኞች እንዲልክ መሆን አለበት::  ይህ ጸሎት በእኛም ውስጥ ለመላክ ያዘጋጀናል እንደፈቃዱ የሆነ ጸሎት ደግሞ ይመለሳል:: የሚገርመው ወንጌልን ለማድረስ ስንሄድ እንደበግና ተኩላ ነው የምንተያየው ህይወቱን በዚህ ውስጥ የሚያጣ ይኖራል እያለን ነው:: ተኩላ አሳቡ ሁሉ በግዋን መብላት ነው::  የጌታ ጥበቃ በዝቶልን ነው የኖርነው ጠላት ሁልጊዜ ዓላማው መግደል ነው አልሆንለት ብሎ እንጂ!
ጌታ ሆይ የልብህን አሳብ እንዳገለግል እራሴን በፊትህ አኖራለሁ!  እኔን ላከኝ እላለሁ አባ!  መምጣትህን ወንጌል በመስበክ ላስቸኩል::  አሜን 

ሉቃስ 10:4-12
9 በእርስዋም ያሉትን ድውዮችን ፈውሱና፡— ‘የእግዚአብሔር መንግሥት ወደ እናንተ ቀረበች፡’ በሉአቸው።
እነዚህን ሰባ ሰዎች ሲልካቸው- እርሱን ቀድመው ተላኩ እርሱም    ከኃላቸው ነው- ሂዱ አላቸው- ጸልዮ ሰራተኛ እንዲጨመር  አላቸው- መመሪያን ሰጣቸው    –  በምንም አትጨናነቁ ፍላጎታችሁን         እሞላለሁ     –  ሰላም ለዚህ ቤት በሉ     – የሚሰጧችሁን ብሉ     –  የእግዚአብሔር መንግስት          ቀርባለች በሉ      – ድዊዎችን ፈውሱ     – ባይቀበሏችሁም መንግስቴ          መቅረብዋን ንገሩይህንን ጥሪ የማይቀበል ከተማ ትቢያቸውን አራግፈው የሚወጡበት የሚጠብቃቸው ከሰዶም የከፋ ነው::  እንዴት ያስፈራል? 
እኛ የመንግስት መልክተኞች ነን ንጉሳችን ያለንን እንናገራለን:- የእግዚአብሔር መንግስት ቀርባለች!  የመንግስቱ መቅረብ አንዱ ምልክት የበሽተኞች መዳን ነው:: ጌታ ኢየሱስ ያስተምርና ይፈውስ በአጋንንትም የተያዙትን ሁሉ ነፃ ያወጣ ነበረ::  ለእኛም ይህንኑ ነው የተወልን:: ተነስተን የመንግስቱን መቅረብ እናውጅ!


ሉቃስ 10: 13-16
16 የሚሰማችሁ እኔን ይሰማል፥ እናንተንም የጣለ እኔን ይጥላል፤ እኔንም የጣለ የላከኝን ይጥላል።”
ወንጌልን ይዘን ስንወጣ የሚሰማን የላከንን ይሰማል የማይሰማንም የላከንንይጥላል::  ወንጌል ባለቤት አለው እኛ መልክት አድራሾች ነን::  ወደ እግዚአብሔር እየተጠጋን ክብሩን እያየን ስንመጣ ብዙ ይጠበቅብናል::
እዚህ ክፍል ላይ ወዮላችሁ የተባሉት ከተሞች ኮራዚን፥ ቤተ ሳይዳ፤ እና ቅፍረናሆም ምክንያቱ አምላክ በስጋ ተመላልሶ ባላስተማረና ተአምራትን ባላደረገ ለእነርሱም የፍርድ ምክንያት ባልሆነባቸው ነበር:: ሰምተውት መመለስ ሲገባቸው አንዳንዶቹ ይህ የዮሴፍ ልጅ አይደለምን ብለው ተሰናከሉበት::  
ወንጌልን ሰምተው ያሾፉትን ሁሉ እግዚአብሔር ይቅር ብሎ እድልን ይሰጣቸው ዘንድ በፊቱ እናስባቸው:: እኛን ሳይሆን እርሱን ገፍተዋልና!
አባት ሆይ ምድራችንም ቤተሰቦቻችንም ወንጌልን በገፉበት ይቅር እንድትልና ልባቸውን እንደሊድያ እንድትከፍት እጸልያለሁ::  በኢየሱስ ስም አሜን! 

ሉቃስ 10: 17
17 ሰብዓውም በደስታ ተመልሰው፡— “ጌታ ሆይ፥ አጋንንት ስንኳ በስምህ ተገዝተውልናል፡” አሉት።
እነዚህን ሰባ ሰዎች ሁለት ሁለት አድርጎ እርሱ ሊሄድበት ወዳለው ከተማና ስፍራ ሁሉ በፊቱ ሲልካቸው ያዘዛቸው ድዊዎችን ፈውሱና የእግዚአብሔር መንግስት ቀርባለች በሉ ነው::  ከፊቱ የምንላክ ነን ቀርባለች መንግስቱ ብለን ስናውጅ እርሱ እራሱን ይገልጣል ምክንያቱም ወደሚሄድበት ነውና የላከን::  ጆሮ ያለው ይስማ!
ሰባውም በተኩላ መካከል እንደ በግ ቢላኩም በሰላም ተመልሰው እንዲያውም አጋንንት በስምህ ተገዙልን ብለው ተጨማሪ ነገርም እንደሆነላቸው ነገሩት::
በእርግጥ አጋንንት የተገዛላቸው በስሙ ነውና ክብሩን ወደ እርሱ አመጡ:: በአገልግሎታችንም ይሁን በህይወታችን  ምንም ቢደረግ ክብሩን ወደ ጌታ እናምጣ እንጂ በጸሎታችን ወይም በትጋታችን እንደሆነልን አንቁጠር ሁሉ ከእርሱ በእርሱ ለእርሱ  ነውና:: አሜን!

ሉቃስ 10: 18-19
18 እንዲህም አላቸው፡— “ሰይጣንን እንደ መብረቅ ከሰማይ ሲወድቅ አየሁ። 19 እነሆ፥ እባቡንና ጊንጡን ትረግጡ ዘንድ፥ በጠላትም ኃይል ሁሉ ላይ ሥልጣን ሰጥቻችኋለሁ፥ የሚጐዳችሁም ምንም የለም።
የሰይጣንን መውደቅ የነገራቸው አጋንንት በስምህ ተገዛልን ሲሉት ነው::  ሰይጣን የወደቀው እንደ መብረቅ ነው ማለትም ከየት መጣ ሳይባል ድንገት ተጣለ::  ባለስልጣን የእኛ አምላክ ነው ድንገት ጣለው!  
በመምጣቱም በአገዛዙ ስር ያሉትን ነፃ ለማውጣት በስጋ መጣ::  የወደቀው ግን ለእኛ በክርስቶስ ውስጥ ላለነው ነው::  ያልሆኑትማ ሊያዙት ሲሞክሩ ኢየሱስን አውቃለሁ እናንተ እነማን ናችሁ እንዳለው ነው::  የሰይጣን መውደቅ ወይም ስንፀልይ ቢወጣ አይደንቅም ስልጣኑን የገፈፈው የእግዚአብሔር ልጅ ኢየሱስ እንጂ እኛን የሚያስተብተን መሆን  የለበትም::  
የተባልነው:እባቡንና ጊንጡን ርገጡ፥ በጠላትም ኃይል ሁሉ ላይ ሥልጣን ሰጥቻችኋለሁ፥ የሚጐዳችሁም ምንም የለም።
ምን አይነት መተማመኛ ቃል ነው?! ጠላት ኃይል አለው በእኛ ላይ ግን አይደለም::  እድሉን ቢያገኝ ምን ያደርገን ይሆን?!  የተሰጠን ዋስትና የሚጐዳችሁም ምንም የለም ነው!  አሜን!ሊጎዳን አይችልምና የሚያስፈራን ምንድነው?  የጠላታችንን ደጅ እንውረስ!  አሜን!


ሉቃስ 10: 20
20 ነገር ግን መናፍስት ስለ ተገዙላችሁ በዚህ ደስ አይበላችሁ፥ ስማችሁ ግን በሰማያት ሰለ ተጻፈ ደስ ይበላችሁ።”
ዛሬ ደስ ሊለን የሚገባው ስማችን በሰማያት በህይወት መጽሐፍ ላይ ስለተፃፈ ነው:: አገር በሰማይ አለን!
ራእይ 21:27 ለበጉም በሆነው በሕይወት መጽሐፍ ከተጻፉት በቀር፥ ጸያፍ ነገር ሁሉ ርኵሰትና ውሸትም የሚያደርግ ወደ እርስዋ ከቶ አይገባም።
ተመስገን ጌታ ሆይ  ምን እንላለን!


ሉቃስ 10: 21
21 በዚያን ሰዓት ኢየሱስ በመንፈስ ቅዱስ ሐሤት አደረገና፡— “የሰማይና የምድር ጌታ አባት ሆይ፥ ይህን ከጥበበኞችና ከአስተዋዮች ሰውረህ ለሕፃናት ስለ ገለጥህላቸው አመሰግናለሁ፤ አዎን አባት ሆይ፥ ፈቃድህ በፊትህ እንዲህ ሆኖአልና።
ጌታ ኢየሱስን ሃሴትእንዲያደርግ ያደረገው እርሱን በማወቃቸውና ስማቸውም በህይወት መጽሐፍ በመፃፉ እንዲሁም ወጥተው የመንግስቱን ስራ ስለሰሩ ፍሬውንም ማየት ስለጀመረ ነው:: አባቱንም በመስገን የቀጠለው:: 
በአንድ ሰው መዳን በሰማይ ደስታና ምስጋና አለ::  የእያንዳንዳችን መዳን ይህንን አድርጏል በስብከት ሞኝነት አምነን ስለዳንን ዛሬም ይደነቃል:: ደህንነት ለእኛ ተገለጠልን ፈቃዱ እንዲህ ሆንዋልና የጌታ ስም ይባረክ:: በሄድንበት ስፍራ ሁሉ መንግስቱ መቅረብዋን የምናውጅ ያድርገን ደስታውንም እንደዚህ እንፈጽም::  አሜን!

ሉቃስ 10: 22-23
22 ሁሉ ከአባቴ ዘንድ ተሰጥቶኛል፥ ወልድንም ማን እንደ ሆነ ከአብ በቀር የሚያውቅ የለም፥ አብንም ማን እንደ ሆነ ከወልድ በቀር ወልድም ሊገልጥለት ከሚፈቅድ በቀር የሚያውቅ የለም፡” አለ።
አብን ወልድ ገልጦልን በቤቱ ላለን ምስጋና እናብዛ:: የአብንና የወልድን ህብረትና አንድነት እያሳየን ነው በቃሉ:: ሌላው ሁሉ ከአባቴ ተሰጥቶኛል እንዳለን እናስተውል::  በዚሁ ስልጣን ነው እኛንም የላከን የራሳችን የሆነ አንዳችም የለም::  በዚህ በመጨረሻ ዘመን በልጁ ተናገረን እኛም ሰማነው እንዴት ያለ መታደል ነው?!  አብን አውቃለሁ ብሎ ወልድን ግን የማይቀበል ወደ አብ አይደርስም ምክንያቱም መንገዱ ኢየሱስ ነውና::
እርሱን በማወቅና በመገለጥ መንፈስ ይሞላን ዘንድ እንጸልይ::  አወቅነው ብለን የምንጨርሰው አይደለም ጌታችን ከመታወቅ ያልፋልና!  እራሱን ይግለጥልን እንጂ በዝች ትንሽ ጭንቅላታችን አውቀነው የምንደርስበት አምላክ አይደለም እርሱ ከፍጥረት ውጪ ከጊዜ ውጪ የሆነ አምላክ ነው::  በሞኝነት ስንከት አወቅነው እንጂ ድረሱብኝ ተመራምራችሁ ቢለን ጠፍተን ነበረ ዓለም አሁን እንደጠፋችው:: 
ጌታ ሆይ የእግዚአብሔርን ሚስጥር ኢየሱስን ማወቅ ስለሆነልኝ ተመስገን:: አብ አባት ሆይ ወደ ልጅህ ስለሳብከኝ ተመስገን:: ተመስገን! ተመስገን!

ሉቃስ 10: 24
24 እላችኋለሁና፥ እናንተ የምታዩትን ብዙዎች ነቢያትና ነገሥታት ሊያዩ ወደዱ አላዩምም፥ የምትሰሙትንም ሊሰሙ ወድደው አልሰሙም፡” አለ።
ይህንን እውነት አውቆ በጌታ ታውቆ መኖር እንዴት መታደል ነው?  ብዙዎች በደጅ አሉና ስለእነርሱ የሚያስብ ማንነት ይኑረን::  እኛስ አወቅነው አረፍን ያላወቁት የሚጠብቃቸው ምን እንደሆነም እናውቃለን እርሱም ሲዖል ነውና ስለሌሎች እንጸልይ እንዲድኑም እንመስክር::
ጌታ ሆይ እኛ ብቻችንን ተሟሙቀን እንድንኖር ብቻ አይደለምና የጠራኸን ሌሎችን እንደርስና ወደ አንተ እንድናመጣ እርዳን::   በመክሊታችን አትርፈን እንደ አምስቱ ቆነጃጅት ተዘጋጅተን ዘይታችን ሞልቶ እንድንጠብቅህ እርዳን::  አሜን!


ሉቃስ 10: 25-37
27 እርሱም መልሶ፡— “ጌታ አምላክህን በፍጹም ልብህ በፍጹም ነፍስህም በፍጹም ኃይልህም በፍጹም አሳብህም ውደድ፥ ባልንጀራህንም እንደ ራስህ ውደድ፡” አለው።
ይህ ህግ አዋቂ ጌታን ሊፈትን ነበር የዘላለም ህይወት እንዳገኝ ምን ላድርግ ያለው ዘመኑ ብሉይ ኪዳን ነውና ኢየሱስም የጠየቀው ህጉ ምን እንደሚል ነው::  እግዚአብሔርን መውደድና ባልንጀራን መውደድ ብሎ መመለስ ብቻ ሳይሆን ሌላ ጥያቄ ጨመረ ትክክል መልሰሃል ሲባል::  እርሱ ግን ራሱን ሊያጸድቅ ወድዶ ኢየሱስን፡— “ባልንጀራዬስ ማን ነው?” አለው። ባልንጀራማ ብሎ ስለ ካህኑ: ስለሌዋዊዉ እንዲሁም ሳምራዊው ነገረው::  እግዚአብሔርን እናገለግላለን ቃሉን እናውቃለን የሚሉት (እንዳንተ አይነቶቹ) እንደራሳቸው በወንበዴዎች እጅ ለወደቀው አልራሩም ወይም አልወደዱትም ዘወር ብለው  አለፉ ባልንጀራዬ የማይባለው በእርሱ መስፈርት ባልንጀራ ሆኖ ተገኘ::
በየዕለቱ ባለው ኑሮአችን ሰውን ከሰው ሳንለይ የምንረዳና ሰውን እንደራሳችን ከዛም ሲያልፍ ጌታ እንደወደደ የምንወድ እንሁን::  በተግባር እንዋደድ!



ሉቃስ 10: 38-42
41 ኢየሱስም መልሶ አላት፡— “ማርታ፥ ማርታ፥ በብዙ ነገር ትጨነቂአለሽ ትታወኪማለሽ፥ 42 የሚያስፈልገው ግን ጥቂት ወይም አንድ ነገር ነው፤ ማርያምም መልካም ዕድልን መርጣለች ከእርስዋም አይወሰድባትም።”
ኢየሱስ በእንግድነት በቤታቸው ተገኘ!  የአምላክ እንግዳ!  በሁለት መልኩ ተቀበሉት እህትማማቾቹ:- ማርታ እርሱን ለማስተናገድ ባከነች፥ ተጨነቀች እንዲሁም ታወከች::  በተቃራኒው ማርያም በእግሩ ስር ቁጭ አለች፥ አልባከነችም ፥ አልተጨነቀችም ፥ እርፍ አለች እረፍትዋም ሰላምዋም ከእርስዋ አይወሰድም::  የመረጠችው ጌታ ዕድል ፋንታዋ ነውና እርሱን ከማውቅና በፊቱ ጊዜ ከማሳለፍ የሚበልጥ ነገር የለም::  እኛንም እርዳን ጌታሆይ በዓለም ከመባዘን በፊትህ መሆን ይብዛልን!!
ማርታ ያላወቀችው አምስት ሺ ሰዎችን በአምስት እንጀራና በሁለት ዓሳ  ማጥገቡንና ተርፎ መነሳቱን ነው::  ጌታ ሆይ ሩጫችን ለመንግስትህ ይሁን!


ሉቃስ 11: 1

1 እርሱም በአንድ ስፍራ ይጸልይ ነበር፥ በጨረሰም ጊዜ ከደቀ መዛሙርቱ አንዱ፡— “ጌታ ሆይ፥ ዮሐንስ ደቀ መዛሙርቱን እንዳስተማረ እንጸልይ ዘንድ አስተምረን፡” አለው።
ቀላል ጥያቄ ይመስላል ጸሎት አስተምረን ማለት:: ከኢየሱስ  ያዩት ነገር ለየት የሚያደርገው  ቢኖር ጸሎት ነው::   እስኪጨርስ ጠበቁት እንጂ አብረውት አልጸለዮም ምክንያቱም አልቻሉምና በጸጋ እንጂ በስጋ ትጋት አይሆንም::
ዛሬ ይህንን እንጠይቅ ጸሎትን ጌታ ያስተምረን::  ጸሎት ህብረት ማድረግ ነው ከሚወደን አባታችን ጋር እንጂ ይህንና ያንን ስጠን ብለን የምንነሳው አይደለም::
አባት ሆይ ጸሎትን አስተምረኝ?  አሜን! 


ሉቃስ 11:2 አላቸውም፡— “ስትጸልዩ እንዲህ በሉ፦ ‘በሰማያት የምትኖር አባታችን ሆይ፤ ስምህ ይቀደስ፤ 
አባት አለን በሰማይ የሚኖር ስለዚህ ጸሎት ከእርሱ ጋር ህብረት ማድረጊያ ነው ::  ምናልባት ጸሎት ጥያቄያችንን ይዘን ብቻ የምንቀርብበት ይመስለን ይሆናል::  ልክ ነው ጥያቄያችንን በፊቱ እናቀርባለን ነገር ግን ይህ ጊዜ ህብረት የምናደርግበት ነውና ጌታንና ፍቅሩን እንጥገበው::
በሰማይ የምትኖር አባት ሆይ ክበር ተመስገን ስምህንም እቀድሳለሁኝ!  እያልን ስናመልከው በጸሎት መንፈስ እንዋል!

ሉቃስ 11:2 አላቸውም፡— “ስትጸልዩ እንዲህ በሉ፦ ‘በሰማያት የምትኖር አባታችን ሆይ፤ ስምህ ይቀደስ፤ መንግሥትህ ትምጣ፤ ፈቃድህ በሰማይ እንደ ሆነች እንዲሁ በምድር ትሁን፤
ይህ ጸሎት በአንደበት ብቻ የምንናገረው ሳይሆን በማስተዋል የምንጸልየው መሆን አለበት:: እንዲሁም የጸሎት ህይወታችንን የሚቃኝና የሚመራ መርህ መሆኑን ነው  እዚህ ቁጥር ላይ ሊያሳየን የፈለገው:– 
በሰማያት የምትኖር አባታችን ሆይ፤ ጸሎታችንን ይዘን በፊቱ የምንቀርበው ጌታ ከሁሉ በላይ ከፍ ብሎ ዙፋኑን በሰማይ ያዘጋጀና ምንም ሳይቀናቀነው ሁሉን ተቆጣጥሮና ገዝቶ እንደሚኖር ለእኛም አባታችን መሆኑን እንወቅ::
ስምህ ይቀደስ፤  በብዙ ስሞች የሚገለጥ ጌታ ነው:: ከስም ሁሉ በላይ የተቀባ ስም ያለው እንድንበትም ዘንድ ስሙን የሰጠን ጌታ::  ልክ እንደ ስሙ የሆነ ጌታ ነውና ስሙን እናወድስ:
መንግሥትህ ትምጣ፤ ይህ ጌታ መንግስትና አገዛዝ ስርአት ያለው ነው::  መላእክቱን/ሰራዊቱን ይልካል ፈቃዱንም ያደርጋሉ::  የምናየውንና የማናየውን ሁሉ የፈጠረ  እነርሱም የሚሰሙትና የሚታዘዙት ንጉስ ነው::  መንግስቱ ትጋፋለች በኃይልም ትመሰረታለች:: ትምጣልን!
ፈቃድህ በሰማይ እንደ ሆነች እንዲሁ በምድር ትሁን፤ ይህ ንጉስ ፈጠረን ሲፈጥረንም ፈቃዱን እንድንፈጽም ነውና በየዕለቱ በላይ በሰማይ ያለችው ፍቃዱ ታግኘንና ቀናችንን ይምራ::
እኔን ያገኘኝ የጸሎት መንፈስ ያግኛችሁ! በማስተዋል እንጸልየው!


ሉቃስ 11:2  . . . ፈቃድህ በሰማይ እንደ ሆነች እንዲሁ በምድር ትሁን፤
ለህይወታችን ጌታ ፈቃድ አለው ይህም ፈቃድ በጎ የሆነ ፍፃሜ ያለው ነው::  ፈቃዱም በሰማይ ነውና በእርሱ ዘንድ ያለው ፈቃዱ ያግኘን:: በሰማይ ካለው አሳቡ ጋር እንስማማና በምድር ትፈጸም::
እኛ የራሳችን አይደለንም በበጉ ደም ተገዘተናል:: የሚገርመው በደሙ የገዛን የእርሱ ብንሆንም እንኳን ፈቃድህ ትሁን ብላችሁ ተስማሙ ብሎ ፈቃዳችንን ይጠይቃል እንጂ ፈቃዱን አያስገድደንም::  ብንቀበል መልካም ይሆንልናል አለበለዚያም ዋጋ ከፍለን እንማራለን ያኔም ቢሆን ዋጋሽን አገኘሽ ሳይሆን የሚለው እጁን ዘርግቶ ይቀበለናል ደግሞም ያጽናናናል:: በነገር ሁሉ ከእርሱ ጋር መስማማት ይሁንልን ማትረፍ ነውና:: ሞኝነት ቢመስልም ቀላል በሆነው ነገር ሁሉ ፈቃዱን እንጋብዝ:: እርሱ ታማኝ ነውና እንመነው!  ባናምነውም ታማኝ ሆኖ ይኖራል!  አሜን!  በማስተዋል እንጸልይ!


ሉቃስ 11:3 የዕለት እንጀራችንን ዕለት ዕለት ስጠን፤ጌታ ጸሎትን ሲያስተምር የጀመረው ስለታላቅነቱ እንድናስብ፤ ዙፋኑን በሰማይ ያዘጋጀ ሁሉን የሚገዛ ጌታ እንደሆነ እንድናስብ ፤ ደግሞም ፈቃድ እንዳለው ያንን እንድንጠይቅ እንጂ አስገድዶ እንደማይሰጠን አስተማረ::  ጌታ እየሱስ በምድር ሲመላለስ ፈቃዱን ማድረግ እንደምግቡ ነበረና እኛም ፈቃዱን እንፈልግና በእርሱ እንርካ::
በመቀጠልም ይኽንን የሚያሮጠንን የምድርን እንጀራ እንድንለምን ተነገረን::  መቼም እንጀራ ሲባል የሚበላውን ብቻ ሳይሆን በዓለት ውስጥ የሚያስፈልገንን ሁሉ ማለት ነው::  የምንጠይቀውም የዛሬን ነው ነገማ ክፋቱ  ይበቃዋል አታስቡና አትጨነቁ ተብለናል::  እኛን ግን የሚያስጨንቀን የነገው ነው በዚህም የሚደሰተው ጠላት ነው ዛሬን እንደሚገባ እንዳንኖር ሳናውቀው ሰርቆናልና::  እስራኤሎች መና ሲሰጣቸው ለየዕለቱ ሰብስቡ አያድርም አላቸው ስላላመኑት ነገ ምን እንሆናለን ብለው ሰበሰቡ መናውም ተላ::  የመታመን ችግር ይመስለኛል አለማመኔን እርዳው::
ጌታ ሆይ በፊትህ ንስሃ እገባለሁ በአንተ ላይ ባልታመንኩበት ይቅር በለኝ:: አሜን!

ሉቃስ 11:4 ኃጢአታችንንም ይቅር በለን፥ እኛ ደግሞ የበደሉንን ሁሉ ይቅር ብለናልና፤
ለቃሉ ትኩረት እንስጥ!!!!
የበደሉንን ሁሉ እንደሚል እናስተውል ይህንን ይቅር ብለን ይሄኛው ጎድቶኛልና ይቅር ማለት ከበደኝ አይሰራም ጸጋን ብንጠይቅ ይሰጠናል::  ይቅር እንዳልነው መሰረት ነው ይቅር የምንባለው::  ይቅርታ ምርጫ ነውና ፈልገን እስረኞችን በልባችን ዘግተን የያዝናቸውን ሁሉ እንልቀቅ!  ይቅር ከማለት የሚያግደንና የሚያግደረድረን ምን ይሆን?  እኔነት? ምንም አይጠቅመንም ዝቅ ብለን ይቅርታም እንጠይቅ ደግሞም ይቅርታን እንስጥ::   መርዝ እየጠጡ ሌላው ሰው እንዲሞት መጠበቅ ማለት ነው::  እውነታው ግን እየሞትን ያለነው ይቅር ያላልነው እኛው ነን!   እግዚአብሔር ማንንም አያሰቃይም አንሰማ ካልን ግን ያ ክፉ መጥቶ ያሰቃየናል ህጋዊ መንገድ አግኝቷልና ተላልፈንም ለአሰቃዮች እንሰጣለን በምርጫችን::  ያልተመለሱ ጸሎቶች አሉ? እንግድያውስ እራሳችንን እንመርምር ከዚህ ጋር በተያያዘ ጉዳይ እንዳይሆን:: 
ልናመልክና ልንጸልይ ስንነሳ አንዳች ከሰው ጋር ካለን ጊዜ ማጥፋት እንጂ  በፊቱ የምናደርገው ያ መስዋዕት ተሰሚነት የለውም አምልኮህን ትተህ ይቅርታን ጠይቅ ይቅርታንም ስጥ ነው የሚለን::  የውቅያኖስ ያህልን ኃጥያት ተትቶልን የሲኒዋን ይቅር ማለት አቃተን::  ጌታ ሆይ አስበን ምህረት ማድረግን በእኛ ውስጥ አብዛልን::

ሉቃስ 11:4  . . .  ከክፉ አድነን እንጂ ወደ ፈተና አታግባን’።
በጌቴ ሰማኒ በመጨረሻዋ ሰዓት ላይ ኃዋርያቱ የመጣውን ሳያውቁ እንቅልፍ እንቅልፍ ብሏቸው ሳለ እርሱ ግን አንድ ሰዓት እንኳን ከእኔ ጋር ልትተጉ አልቻላችሁም? እንደገናም ሉቃስ 22:46 “ስለ ምን ትተኛላችሁ? ወደ ፈተና እንዳትገቡ ተነሥታችሁ ጸልዩ፡” አላቸው። አልጸለዩምና እርሱ ስለእነርሱ ማለደ::  ጌታ በሚያመለክተን ሰዓት ፊቱን መፈለግ መልካም ነው:: 
ሲያንኳኳ ሳንከፍትለት ቀርተን ጥሎ ከሄደ በኃላ እንደ ሱናማይቱ ሴት ብንከፍትና ብንፈልገው ጥፋቱ ከደጃፋችን ደርሷልና ዋጋ  ያስከፍላል::  ጥቂት እንቅልፍ አጥቶ ከክፉ ለመዳንና ወደ ፈተና እንዳንገባ መጸለይ ይሻላል::  ምርጫችን የእኛ ነው ምርጫችን ምንድነው ከፈተና ማምለጥ ወይስ ወጥመድ ውስጥ ወድቆ ዋጋ መክፈል? እርሱ እንደሆነ ነግሮናል ቃሉ እውነት ነው መታዘዝ የእኛ ድርሻ ነው:: 
ጌታ ሆይ  ስትቀሰቅሰን የነቃና እሺ የሚል መንፈስን እንዲሁም የሚያስፈልገንንም ጸጋ ስጠን::  አሜን!

ሉቃስ 11: 5-7
ሉቃስ 11:6 አንድ ወዳጄ ከመንገድ ወደ እኔ መጥቶ የማቀርብለት የለኝምና፡’ ይላልን?  7 “ያም ከውስጥ መልሶ፡— ‘አታድክመኝ፤ አሁን ደጁ ተቈልፎአል ልጆቼም ከእኔ ጋር በአልጋ ላይ አሉ፤ ተነሥቼ ልሰጥህ አልችልም፡’ ይላልን?
ጸሎት አስተምረን ብለው የጠየቁት እነ ዮሃንስ ስለሚያስተምሩ ነበረ::  የሐዋርያቱን ለየት የሚያደርገው ተጠያቂው ነው::  እርሱ የጸሎቱ ተቀባይ መሆኑ እናም ግምት ሳይሆን ትክክለኛውን አስተማራቸው::  እንዲያውም ምሳሌ ነገራቸው እወዳጁ ጋር ሄዶ እንጀራን ለእንግዳ ለመበደር የሚል ምሳሌ::  ወዳጅየው ስለንዝነዛው ነው የጠየቀውን የሚሰጠው? አይደለም ወዳጅ ስለሆነ እንጂ::  ተነስቶ የሚሰጠውም ምክንያት ሳይደረድር ከአልጋው ተጣድፎ  ወርዶ ማባያም እንዳለው ሁሉ ይጠይቃል ወይም ሌላስ የምትፈልገው አለ ወይ ብሎ መጠየቁ አይቀርም የጠየቀውን ከመስጠትም አልፎ ማለት ነው::  የምድር ወዳጅነት እንኳን እንደዚህ ከሆነ  የሰማዮ ወዳጃችንማ እንዴት?! ከምንጠይቀው አብልጦ ይሰጠናል::
ጌታም እራሱን ወዳጅ አድርጎ ነው የጠራው በቀን ይሁን በለሊት ስናንኳኳ ከፍቶ ይሰጠናል::  እራሱ ነው የነገረን ስናኳኳ ይከፈታል የምናኳኳው እወዳጃችን ቤት ነው::  ጸሎትን እሩቅ አድርገን ትግልና ስራ ሆኖ አንየው በጣም የምንወደውን ወዳጃችንን እንደመጠየቅ እንየው::  ጌታ ወደፊቱ እንደዚህ ባለ ነፃነት እንድንመጣ ነው የሚፈልገው::  እርሱ ከሁሉ አብልጦ የሚጠጋጋ ወዳጅ ነው::
ስንጸልይ እንድንቀበል እንወቅ በሩን እናኳኳ ይከፈታል ወዳጃችንም ጥያቄያችንን ይመልሳል!  አሜን!

ሉቃስ 11: 8-10
9 እኔም እላችኋለሁ፦ ለምኑ፥ ይሰጣችሁማል፤ ፈልጉ፥ ታገኙማላችሁ፤ መዝጊያን አንኳኩ፥ ይከፍትላችሁማል።10 የሚለምን ሁሉ ይቀበላልና፥ የሚፈልግም ያገኛል፥ መዝጊያውንም ለሚያንኳኳው ይከፈትለታል።
ቸል የማይል ወዳጅ የማንንም ጸሎትየማይንቅ ጌታ እኔም እላችኋለሁ፦ ለምኑ፥ የሚለምን ሁሉ ይቀበላልና፤ ፈልጉ፥ ታገኙማላችሁ፤ መዝጊያን አንኳኩ፥ ለሚያንኳኳው ይከፈትለታል ብሎ የልብ ልብ ሰጠን! ጸሎት ቀጣይነት ያለው በዘመናችን ሁሉ የምናደርገው ነው::  ወዳጅ ያልሆነ እንዲነዘነዝ ይፈልግ ይሆናል የእኛ ጌታ ግን ገና ልባችንን ወደ እርሱ ስናነሳ ይሰማናል እኛም እስኪመልስ እንጠብቃለን::
ትቀበላላችሁ፥ ታግኛላችሁ፥ ይከፈታል በሩ እራሱ ጌታ ካለን የማንንም ማረጋገጫ ሳንፈልግ በፊቱ እንቀርባለን እንዳለውም እንደቃሉ ይሆንልናል:: በእምነት ፊቱን ከመፈለግ ቸል እንዳንል ጌታ ይርዳን!

ሉቃስ 11:11-13
13 “እንኪያስ እናንተ ክፉዎች ስትሆኑ ለልጆቻችሁ መልካም ስጦታ መስጠት ካወቃችሁ፥ በሰማይ ያለው አባት ለሚለምኑት እንዴት አብልጦ መንፈስ ቅዱስን ይሰጣቸው?”
ስለጸሎት እያስተማረ በቀጠለበት እራሱን ከወዳጅ ጋር እያስተያየ ምን ያህል የተሻለ ወዳጅ እንደሆነ አስተማራቸው::  እዚህ ክፍል ላይ ደግሞ እራሱን ከምድር አባት ጋር አወዳድሮ የተሻለ መልካም አባት እንደሆነና የምድር አባት ክፉ ቢሆንም እንኳን የምንጠይቀውን ተቃራኒ ሳይሆን የምንፈልገውን ይሰጠናል::  የሰማዮ አባትማ እንዴት እንዲያው  በበለጠ እራሱን ይሰጠን? አሁንም እያለን ያለው እንደጸሎቱ መግቢያ አባት እንደሆነ ነው::  አባታችን ሆይ ተመስገን!
ልጅ እንጀራና አሳ የሚለምነው ሲራብ ነው:: እንደምግብ የተመሰለውን መንፈስ ቅዱስን እንራብ  ጸሎታችንም ከምድሩ ባለፈ እርሱን የሚጠማና የሚራብ ይሁን!  መንፈስ ቅዱስን መሞላት አጥብቀን እንፈልግ ያለ እርሱ ክርስትና የትም አይደርስምና እንጠይቅ ከጠየቅን እንቀበላለን::  ማንም የተጠማ ቢኖር ወደ እኔ ይምጣና በነፃ ይጠጣ የሚለው ግብዣ እስከአሁን ክፍት ነው እንዲሁም  መንፈሱን  ሳይሰፍር በልግስና ይሰጠናል!  አሜን!
አባት ሆይ መንፈስህን ሙላኝ!

ሉቃስ 11: 14-23
20 እኔ ግን በእግዚአብሔር ጣት አጋንንትን የማወጣ ከሆንሁ፥ እንግዲህ የእግዚአብሔር መንግሥት ወደ እናንተ ደርሳለች።   .  .  .  23 ከእኔ ጋር ያልሆነ ይቃወመኛል፥ ከእኔ ጋርም የማያከማች ይበትናል።”
ይህ ስፍራ ዲዳውን ጋኔን ካወጣው በኃላ ድዳው ሲናገር አይተው ህዝቡ ሁሉ የተደነቁበት ነው::  በዚህም ጊዜ ነው በአጋንንት አለቃ ነው ያወጣው ብለው ሌሎችንም ጥርጣሬ ውስጥ ከተቷቸውና እንግዲያውስ ተጨማሪ ተአምራትና ምልክት አሳየን አሉት::  እርሱ ግን አሳባቸውን አውቆ የተለያየች መንግስት ትፈርሳለች ብሎ በትህትና መለሰ::  ኢየሱስ የመጣው የሰውን ልጅ ከዲያብሎስ ቀንበር ነፃ ሊያወጣ ሆኖ ሳለ ነፃ የሚወጣው የሰው ልጅ ግን  ነፃ አውጪያችንን ከጠላቱ ጋር መድቦት ቁጭ! 
ኢየሱስ በእግዚአብሔር ጣት አጋንንትን አወጣ፥ መንግሥቱም  ቀርባለች። ዛሬም መንግስቱ ቀርባለች በስሙ  አጋንንት ታዘው ይወጣሉ::  ይህንን ስልጣን ለቤተክርስትያን ሰጥቷል ጣቱ ትሰራለች::  ኃይለኛ ነኝ ብሎ የሰውን ህይወት የሚያጎሳቁለው ከእርሱ የበለጠው የይሁዳ አንበሳ ሲገለጥ  ታምኖበት ያለውን ጋሻና ጦር ይዞ ሲጠብቅና ሲያሰቃይ፥ ያለውን ሰው ይለቃል ሳይወድ ምርኮውንም ያካፍላል! 
ምርጫ ለሰው ልጆች ተሰቷል ኃይለኛ ነኝ ብሎ ከተሸነፈው  ወይንም በጣም ኃያል ከሆነው ጋር መወገን መሃል ላይ ሌላ አማራጭ የለም::  ጌታም ከእኔ ጋር ያልሆነ ይቃወመኛል፥ ከእኔ ጋርም የማያከማች ይበትናል። ምርጫችን ሁሌም ኢየሱስ ነው!!! የኃያላን ኃያል የጌቶችም ጌታ ስምህ ይባረክ! የእግዚአብሔር ወገን መሆኔን አውጃለሁ!  ከአንተ ጋር እወግናለሁ! ከአንተም ጋር አከማቻለሁ!

ሉቃስ 11: 24-28
28 እርሱ ግን፡— አዎን፥ ብፁዓንስ የእግዚአብሔርን ቃል ሰምተው የሚጠብቁት ናቸው፡” አለ።
ዲዳውን አጋንንት ካስወጣ በኃላ ሲያስተምር ኃይለኛው በኃይለኛ ከተባረረ በኃላ ስፍራ ፈልጎ ሲያጣ ወደ ወጣሀበት ቤቴ ልመለስ ብሎ ይመጣል::  ሲመጣም ብቻውን ሳይሆን ከእርሱ የከፉ ሰባት ይዞ ይመጣል የዛም ሰው መጨረሻ የባሰ ይሆናል::  እንኳን መንግስቱ ሊከፋፈል እነርሱ እንደሚሉት እንዲያውም ኃይላቸውን ጨምረው እየተረዳዱ ሰውን ያሰቃያሉ::  የመንግስታቸው ዓላማ መስረቅ ማጥፋትና መግደል ስለሆነ ተግተው ይሰራሉ:: ይህ ሊያስቆጨንና እንድንዘምትበት ሊያነሳሳን ይገባል::  እኛም መንግስት አለን መንግስታችንም የሚፈታና ህይወትን የሚሰጥ ነውና እንደ አንድ አካል ተነስተን እንሰራለን ጌታም ያከናውንልናል::  ከጌታ ጋር ሆነን እናሸንፋለን!
በዚህ ጊዜ ነበር አንዲት ሴት ድምፅዋን ከፍ አድርጋ፡— “የተሸከመችህ ማኅፀንና የጠባሃቸው ጡቶች ብፁዓን ናቸው፡” ያለችው።  እርሱ ግን ብፁዓንስ  የእግዚአብሔርን ቃል ሰምተው የሚጠብቁት ናቸው አላት::  ቃሉን መስማት ብቻ ሳይሆን በቀንና በለሊት ማሰላሰል እናም መኖር ይሁንልን:: 

ሉቃስ 11: 29-32
29 ብዙ ሕዝብም በተሰበሰቡ ጊዜ እንዲህ ይል ጀመር፡— “ይህ ትውልድ ክፉ ነው፤ ምልክት ይፈልጋል፥ ከነቢዩም ከዮናስ ምልክት በቀር ምልክት አይሰጠውም።
ብዙ ህዝብ ባለበት ነው ጌታ ይህ ትውልድ ምልክት ይፈልጋል የሚለው::  እርሱንና ዮናስን ምን ያመሳስላቸዋል?  ዮናስ ንስሃን ሰበከ የነነዌ ሰዎች ንስሃ ገቡና ከጥፋትአመለጡ ኢየሱስም ንስሃን እየሰበከ መጣ ምላሽ ባያገኝም::  ሌላው ዮናስ በአሳ ነባሪው ሆድ ውስጥ ለሶስት ቀን ቆየ እንዲሁ ኢየሱስ በመሬት ውስጥ ሞቶ ለሶስት ቀን ቆየ:: 
ልዮነቱስ የነነዌ ህዝብ ይህንን ተአምር ሲያዮ በዮናስ ስብከት ንስሃ በመግባት ተመለሱ::  ይህ ትውልድ ግን በኢየሱስ አገልግሎት አልተመለሱም በመካከላቸው ሲሰብክም ልባቸው ተሰብሮ አልተመለሱም::  ስለዚህ ኢየሱስ  ከዮናስ የሚበልጥ በዚህ አለ ብሎ ቢልም ሰሚ አልነበረም::  ከትንሳኤ በኃላ እንዲያውም በትምህታችሁ እየሩሳሌምን ሞላችሁ ሁለተኛ በዚህ ስም እንዳታስተምሩ ብለው ገረፏቸው እንጂ ምላሽ አልሰጡም:: ዮናስ የጌታ መልክተኛ ነው፤  ኢየሱስ ግን እራሱ ጌታና አምላክ ነብያቶችን ሁሉ የላከ ነው::  የተላከውን ሲያደንቁ እራሱ ላኪው  መጥቶ በመካከላቸው ቆሞ አላወቁትምና ገና ምልክትን ይፈልጋሉ:: ፍርድን በላያቸው አከማቹ!
ጥበበኛውንም ሰለሞንን ጥበበኛ ያደረገው ጌታ በዛ እያለ አላወቁትም:: ከሰለሞን የሚበልጥ በዚህ አለ ቢልም የሰማው አልነበረም::  
አሜን ኢየሱስ አንተ ከዮናስም ከሰለሞንም ትበልጣለህ::  ንስሃ በስምህ ይሰበካል የጥበብ ሁሉ ምንጭ እንደሆንክም እኛ አውቀናልና እናውጃለን::  አንተን ማወቅ ተሰቶናልና ተመስገን!  


ሉቃስ 11: 33-36
35 እንግዲህ በአንተ ያለው ብርሃን ጨለማ እንዳይሆን ተመልከት።
ለሰው ሁሉ የሚያበራው እውነተኛው ብርሃን ወደ ዓለም ይመጣ ነበር። (ዮሐንስ 1:9 ) ይህ ብርሃን በድብቅ አልመጣም በግልጥ መጣ::  በመካከላቸውም ማንም የማይክደውን ድንቅ እያደረገ ማስተዋል አልቻሉም:: እናውቃለን ያሉት ቃሉን የመረመሩ አዋቂዎች የህይወትን ራስና ብርሃን የሆነውን ኢየሱስን  ከማወቅ ሳቱ::  በውስጣቸው ያለውን ጨለማ ሊያበራ የሚችለውን  ብርሃን አልተመለከቱምና ጨለማ ውስጥ ቀሩ::
እራስን መመርመር እንዴት ትልቅ ነገር ነው?  በውስጣችን የያዝነው ብርሃን ጨለማ እንዳይሆን ብለው እነዚህ ሰዎች መመርመርን ትተው ጨለማው ወረሳቸው::  ይህ ብርሃን ዝግጁ ነበር ሊረዳቸው::  ማስተዋል! አባት ሆይ አውቀናል ብለው በጨለማ የሚመላለሱትን እርዳቸው::  አሜን!
እንግዲህ ሰውነትህ ሁሉ የጨለማ ቍራጭ የሌለበት ብሩህ ቢሆን፥ መብራት በደመቀ ብርሃን እንደሚያበራልህ በጭራሽ ብሩህ ይሆናል። ይህም የሚሆነው ብርሃን የሆነውን ክርስቶስን ሲያውቅና ዓይኑም በብርሃን ሲሞላ ጨለማው ይጠፋል:: 
ለእኛ ግን ይህንን ብርሃን ማየት ሆነልንና በጨለማችን ላይ ብርሃን ይብራ ያለውን እርሱን አውቀን ብርሃናችን ቀትር እስኪሆን እየደመቀልን እየሄደ ነው:: ሃሌሉያ!  አሜን!


ሉቃስ 11: 38-54
41 ነገር ግን በውስጥ ያለውን ምጽዋት አድርጋችሁ ስጡ፥ እነሆም፥ ሁሉ ንጹሕ ይሆንላችኋል። 42 ነገር ግን እናንተ ፈሪሳውያን፥ ከአዝሙድና ከጤና አዳም ከአትክልትም ሁሉ አሥራት ስለምታወጡ፥ ፍርድንና እግዚአብሔርን መውደድ ስለምትተላለፉ፥ ወዮላችሁ፤ ነገር ግን ሌላውን ሳትተዉ ይህን ልታደርጉት ይገባችሁ ነበር።
ጌታ ግብዣን ከፈሪሳዊም ተቀብሎ ወደ ቤቱም ሄዶ እጁን ሳይታጠብ ምግብ ስለበላ ፈሪሳዊዉ ተደነቀ::  ኢየሱስም የጽዋውንና የወጭቱን ውጭ ታጠራላችሁ፥ ውስጣችሁ ግን ቅሚያና ክፋት ሞልቶበታል አለው::  እነሱን የሚጨንቃቸው የውጪው ጌታን ግድ የሚለው የውስጡ::  ስለዚህም ውስጣችሁን ወይም ልባችሁን ምጽዋት አድርጉና ስጡ እንጂ አዝሙድና ጤና አዳም አትክልት ብትሰጡ ምን ይጠቅማል::  ምጽዋት አንዴ ከተሰጠ አይመለስም እራሳችሁን ስጡ አላቸው:: እነርሱ ግን የሚያስቡት ይህንን ሁሉ አድርጌ እግዚአብሔር እኔን እንዴት አይቀበልም ብለው እራሳቸውን እያደነቁ ነው::  ስለዚህም እግዚአብሔር የሰጠውን የመዳንን መንገድ ኢየሱስን ችላ ብለው ከህይወታቸው አውጥተው ጣሉ:: ውጭው የሚነፃው ውስጡ ሲነፃ ነው::
ጌታ የወቀሰባቸው:-  ፍርድንና እግዚአብሔርን መውደድ ስለምትተላለፉ፥ ወዮላችሁ፤ ነገር ግን ሌላውን ሳትተዉ ይህን ልታደርጉት ይገባችሁ ነበር። የተውት ዋናውን ትእዛዝ እግዚአብሔርን መውደድ ነው:: 
ህግ አዋቂዎችንም አባቶቻችሁ ያፈሰሱትን የነብያት ደም ከእናንተ ይፈለጋል አላቸው::  እነርሱ አልገደሉም አባቶቻቸው ናቸው ነገር ግን  በዚህ ውስጥ አቋማቸው አልተለወጠም እንደአባቶቻቸው ሊገድሉት ይማከራሉና ያንኑ የመግደል መንገድና መቃብሩን አሳብ እያጸኑት ነው:: አልተጸጸቱም  ንስሃም አልገቡም እግዚአብሔር የላካቸው መልክተኞች መገደላቸው ትክክል አይደለም አላሉምና ይኸው በዛው መንፈስ ቀጥለዋል::  እራሱ ጌታ መጥቶ ትክክል አይደላችሁም እያላቸው ግግም ብለው ልክ ነን እያሉ ነው::
ህይወታችን ምጽዋት ሆኖ ተሰጥቷልና የእኛ አይደለም::  ውስጣችን እንዲሰራ አሁንም እራሳችንን በትህትና ወደፊቱ እናቅርብ::  አሜን!

ሉቃስ 12: 1-3
1 በዚያን ጊዜ የሕዝብ አእላፍ እርስ በርሳቸው እስኪረጋገጡ ድረስ ተሰብስበው ሳሉ፥ ለደቀ መዛሙርቱ እንዲህ ይል ጀመር፡— “አስቀድማችሁ ከፈሪሳውያን እርሾ ተጠበቁ፥ እርሱም ግብዝነት ነው።
አእላፍ ህዝብበዙሪያው ቢኖርም እርሱ ግን ለደቀ መዛሙርቱ እርሾ ብሎ ከጠራው ከግብዝነት እንዲጠበቁ ነገራቸው::  ግብዝነት ልክ እርሾ ሊጡን እንደሚነፋው ያልሆነውን እንደሚያደርገው እንዲሁ በሰውም ህይወት ያልሆኑትን ያደርጋል:: እብጠቱን  ያመጣው ከውጪ የሆነው እርሾ ነውና ጊዜው ሲያልቅና ሲተነፍስ ሊጡ እዛው ቦታው ይመለሳል ምክንያቱም  ይህንን ውጤት ያመጣው እርሾው እንጂ ሊጡ አይደለምና በአደባባይ አዋርዶ ይሄዳል::  ግብዝነት ማለት ውጪን ሸላልሞ ያልሆኑትን መሆን ማለት ነው::  ጌታ ሲቀጥል እንዳለው መሸፋፈኑና መደበቁ አንድ ቀን ይገለጣል በጏዳ የተደረገው በአደባባይ ይወጣል በሹክሹክታ በጆሮ የተነገረው በአደባባይ ይሰበካል::  መንፈሳዊዉ ዓለም ግድግዳና ሽፋን የለውም ሁሉ በአደባባይ የተደረገ ነውና ይገለጣል ሲገለጥ ጌታን አይገርመውም በፊትም ያውቀው ነበረና:: 
የላይኛይቱ ጥበብ ግን ግብዝነት የላትም ስለዚህም ያለግብዝነት እንመላለስ::  ፍቅራችን ይሁን አገልግሎታችን ያለግብዝነት በእውነት ይሁን ያልሆነውን ለመሆን አንጣር መንፈሳዊ ነገር ከውስጥ ይበቅላልና:: ለታይታ ምንም አናድርግ!  ጌታ ዓይናችንን ይክፈተውና መጣል ያለብንን እንጣል::


ሉቃስ 12: 4-12
5 እኔ ግን የምትፈሩትን አሳያችኋለሁ፤ ከገደለ በኋላ ወደ ገሃነም ለመጣል ሥልጣን ያለውን ፍሩ። አዎን እላችኋለሁ፥ እርሱን ፍሩ።
ጌታም ለእናንተ ለወዳጆቼ እላችኃለሁ እግዚአብሔርን ፍሩ ሌላውን አትፍሩ አለን::  በኢሳይያስ 11:2 የእግዚአብሔር መንፈስ፥ የጥበብና የማስተዋል መንፈስ፥ የምክርና የኃይል መንፈስ፥ የእውቀትና እግዚአብሔርን የመፍራት መንፈስ ያርፍበታል። እግዚአብሔርንም ከመፍራቱ የተነሳ ጸሎቱ ተሰማለት:: ይህንኑ እንድንቀበል ብሎ ለእኛ  ለወዳጆቹ ተናገረ:: ሊያሳስበን የፈለገውም ሰው ስጋን ብቻ ነው የሚገድለው ለእርሱም  ቢሆን የጌታ ጥበቃ አለልን::  የእናንተ የራሳችሁ ጠጕር ሁሉ እንኳ የተቈጠረ ነው፤ እንግዲያስ አትፍሩ ከብዙ ድንቢጦች ትበልጣላችሁ።” ተብለናል:: አንዲቷ ድንቢጥ አትረሳምና እኛማ በአምሳሉ የተፈጠርን በልጁ ሞት የተዋጀን እንዴት አንታሰብ!
በወንጌል ምክንያት መንገላታት ሲመጣ ማተኮር ያለብን በጌታ ላይ ነው::  መንፈስ ቅዱስ በዚያች ሰዓት ልትናገሩ የሚገባችሁን ያስተምራችኋልና።” እንደተባልን በጌታ ሳናፍር ለእርሱ መቆምና መመስከር አለብን::  የምንናገርበትን ጸጋና ጥበብ እርሱ ይስጠን! ወደ መከሩም ይላከን በዚህ ዘመን ጦርነትን እየሰማን ባለንበት በመምጣቱ ዋዜማ ላይ ቆመን የሚጠፋውን የሰው ልጅ እናስብና መመስከርን እንቀጥል::  
አባት ሆይ ልትመጣ በደጅ ነህና ፍሬዬን አንዥርግጌ ልገኝ!  አሜን!


ሉቃስ 12: 13-15
15 “የሰው ሕይወት በገንዘቡ ብዛት አይደለምና ተጠንቀቁ፥ ከመጐምጀትም ሁሉ ተጠበቁ፡” አላቸው።
ጌታ እያስተማረ አቋርጦት ጥያቄን ጠየቀ የሚገርመው ጌታ አታስቡ ከብዙ ድንቢጦች ትበልጣላችሁ የሚያስብላችሁና የሚጠብቃችሁ አለ ያለውን የሰማ አይመስልም::  የከበረውን ሰማያዊውን የህይወትም መርህ የሆነውን እያስተማረ ቢሆንም እንኳን እርሱን የከነከነው የራሱ አጀንዳ እንጂ ጌታ የሚለው አይደለም::
የወንድሙን እርስት እንዲያካፍለው ጌታን ጠየቀው:: የገረመኝ ርስቱ የወንድምየው ከሆነ እንዴት ሆኖ ነው ርስት ወደ ጎን ለወንድም የሚካፈለው? የአባቴን እርስት ከወንድሜ ጋር አካፍለኝ ሌላ ነገር ነው ይህ ግን የማይሆን ጥያቄ ነው:: ጌታም እንደ ህጉ ተካፈሉ ማለት ይችላል እርሱ ህግን ሊሽር አልመጣምና::  የብሉይ ህግ ወደ የሌላ ሰውን ሚስት: ንብረት ወይም ሎሌ እንኳን አትመኝ ሲለው እርሱ አልፎ ሄዶ መጐምጀት ውስጥ ገባ::  ሄዋንንም የጣለው ይኸው ችግር ነው::  
ከመጐምጀት እራሳችንን እንጠብቅ ምክንያቱም የራሳችን ያልሆነውን ነው የምንጐመጀው::  ለገንዘብና ለጌታ መገዛት አይቻልም ዓይናችንን ከጌታ ላይ አድርገን ያለኝ ይበቃኛል ብለን የጌታን መምጣት በዝግጅት እንጠባበቅ!

ሉቃስ 12: 16-21
21 ለራሱ ገንዘብ የሚያከማች፥ በእግዚአብሔር ዘንድም ባለ ጠጋ ያልሆነ እንዲህ ነው።”
በዚህ ምሳሌ ላይ ያለው ሰው እርሻው በዝቶለት ነፍሱን እረፊ ብይ ጠጪ እያለ ሊያንደላቅቃት ፈለገ::  ገንዘቡ አምላኩ ሆንዋልና እያመለከው ባለበት ጊዜ ከማያስጥለው ጥግ ደረሰ ገንዘብ የተባለው አምላክ ነፍስን ማዳን አይችልም ከሲኦል::  ስለዚህ ‘አንተ ሰነፍ፥ በዚች ሌሊት ነፍስህን ከአንተ ሊወስዱአት ይፈልጓታል፤ ይህስ የሰበሰብኸው ለማን ይሆናል?’ አለው። ጌታ የሚለንን እናስተውል:-  እኔ ግን የምትፈሩትን አሳያችኋለሁ፤ ከገደለ በኋላ ወደ ገሃነም ለመጣል ሥልጣን ያለውን ፍሩ። አዎን እላችኋለሁ፥ እርሱን ፍሩ።
ጌታ ኃብታም መሆናችንን አይቃወምም ነገር ግን በእግዚአብሔር ዘንድም ባለ ጠጋ እንድንሆን ይፈልጋል::  በእርሱ ላይ የተደገፈ ባለጠጋ ነው::  በማቴዎስ 10:39 “ነፍሱን የሚያገኝ ያጠፋታል፥ ነፍሱንም ስለ እኔ የሚያጠፋ ያገኛታል” ብሏልና እራሳችንን እንመርምር ምንም አይደለም ብለን የያዝነው አስተሳሰብ እንዳይኖር:: በራእይ 2:9 መከራህንና ድህነትህን አውቃለሁ፥ ነገር ግን ባለ ጠጋ ነህ እስከሞትም ታመን የህይወትን አክሊል እሰጥኃለሁ ይላል ለሰርምኔስ ቤተክርስቲያን:: ጆሮ ያለው ይስማ! በጌታ ፊት ሰው በገንዘቡ ብዛት አይበለጽግም::
መ ር ም ረ ኝ!! በደልንም ብታይ መጎምጀትም ቢገኝብኝ ወይም ደግሞ በገንዘቤና ባለኝ ነገር ላይ ተንተርሼ ቢሆን እንዲሁም ገንዘብ ገዝቶኝ ቢሆን ይቅር በለኝ ልቤንም እይ መርምር!  ማረኝ ጌታዬ በዚህ ውስጥ መገኘት አልፈልግም::  ሁሉ ከንቱ እራቁቴን እንደመጣሁ እራቁቴን እመለሳለሁና::  ማስተዋልን ስጠኝ!  አሜን!

ሉቃስ 12: 22-31
26 እንግዲህ ትንሹን ነገር ስንኳ የማትችሉ ከሆናችሁ፥ ስለ ምን በሌላ ትጨነቃላችሁ?   .  .  .    31 ዳሩ ግን መንግሥቱን ፈልጉ ይህም ሁሉ ይጨመርላችኋል።”
ይህንን ቃል ስናነብ ቃሉ ህያው ነውና ይመረምረናል::  ከመንፈስ ቅዱስ ጋር እንተባበርና እራሳችንን እናስመርምር::  ችግርም ካየን በጌታ ላይ ያልታመንበትን ነገር ካየን ንስሃ እንግባ እርሱ ይቅር ይለናል ጸጋንም ይሰጠናል::  አንወድቅም አይደለም እንፈተናለን ነገር ግን በቃሉ መብራት ስንፈተሽና ስናየው ከእጁ በታች መውደቅ ምመልካም ነው::  በዚህ ምድር ስንኖር ብዙ የሚያስጨንቅ ነገር አለ ተጨንቀን ምንም አለመቀየራችንን ስናውቅ በእርሱ መታመን መፍትሄው ነውና እንንቃ!  ሁሉም እንዲጨመርልን አባታችን ይፈልጋል ቀድሞ ግን መንግስቱን እንፈልግ::  አናሽቀዳድመው::
ምንም ላንለውጥ ልባችንን በጌታ ላይ እንጂ በዙሪያችን በከበበን መጣሁ መጣሁ እያለ በሚያስፈራራው ላይ አይሁን:: ማስፈራራቱ ሁሉ ከንቱ ይሆናል ዓይናችንን በጌታ ላይ እናድርገው::

ሉቃስ 12: 32-34
32 “አንተ ታናሽ መንጋ፥ መንግሥትን ሊሰጣችሁ የአባታችሁ በጎ ፈቃድ ነውና አትፍሩ።
ፈልጉ የተባልነው መንግስቱን ሌላው ደግሞ ይጨመራል ተብለናል::  በዚህ ላይም ጨምሮ መንግስትን እሰጣችኃለሁ አለን:: ሐዋርያቱም ሆኑ እስራኤሎች መሲህ ይመጣል ብለው የሚጠብቁት የነበረው ከሮም መንግስት ነፃ አውጥቷቸው መንግስቱን እንዲመሰርት ነበረ::  አንዳንዶችም በቀኝና በግራ ለመቀመጥ ጠይቀው ነበር:: እርሱ ግን መንግስቱ ከዚህ ዓለም አይደለም::  ያለንን በማከማቸት የምንወርሰው ወይም የምናገለግለው ሳይሆን በላይ በሰማይ ያለውን መንግስት በልጁ ተዋጅቶ መውረስ ነው::   የእርሱ በጎ ፈቃድ ሆነልን ምንም ያላደረግነውን መንግስት በጸጋው መውረስ ሆነልን::  አገር አለን በሰማይ ልባችን በእርሱ ይያዝ በላይ በሰማይም እናከማች::  ከፍቅር በቀር እዳ አይኑርብን!  መንግስቱን እንፈልግ!
እግዚአብሔር ዙፋኑን በሰማይ አዘጋጀ መንግስቱም ሁሉን  ትገዛለች::  አሜን!

ሉቃስ 12: 35-40
40 እናንተ ደግሞ ተዘጋጅታችሁ ኑሩ፥ የሰው ልጅ በማታስቡበት ሰዓት ይመጣልና።”
ያለንን እናስተውል “ወገባችሁ የታጠቀ መብራታችሁም የበራ ይሁን::  ለምን?  ምክንያቱም እናንተ ጌታቸው መጥቶ ደጁን ሲያንኳኳ ወዲያው እንዲከፍቱለት ከሰርግ እስኪመለስ ድረስ የሚጠብቁ ሰዎችን ምሰሉ። ተብለናልና::  ጌታ እንደተናገረው ድንገት በማናስብበትሰዓት  ይመጣል::   
እንዴት እንዘጋጅ? ወገባችንን ታጥቀንና መብራታችንንም አብርተን መጠበቅ::  ይህ ዓለም አይገባንምና ጌታን በጽድቅ እየጠበቅን ክርስቶስንም እያብለጨለጭን እንጠብቅ::  በቃሉና በመንፈሱ እየበረታን በደሙም እየታጠብን እንጠብቅ::  ወንጌልን ለሌሎች እየነገርን መምጣቱን እያፈጠንን እንጠብቅ:: ጌታ ሆይጌታ ሆይ ብቻ በማለት ሳይሆን የሚለንንም በመታዘዝ እንጠብቀው:: መምጣቱን ስንጠባበቅ ጸጋን ይሰጠናል:- በቲቶ 2:12—13 ይህም ጸጋ፥ ኃጢአተኝነትንና ዓለማዊን ምኞት ክደን፥ የተባረከውን ተስፋችንን እርሱም የታላቁን የአምላካችንንና የመድኃኒታችንን የኢየሱስ ክርስቶስን ክብር መገለጥ እየጠበቅን፥ ራሳችንን በመግዛትና በጽድቅ እግዚአብሔርንም በመምሰል በአሁኑ ዘመን እንድንኖር ያስተምረናል፤
ምንን እናገኛለን ተግተን ከጠበቅን በኃላ? ጌታቸው በመጣ ጊዜ ሲተጉ የሚያገኛቸው እነዚያ ባሪያዎች ብፁዓን ናቸው፤ እውነት እላችኋለሁ፥ ታጥቆ በማዕድ ያስቀምጣቸዋል ቀርቦም ያገለግላቸዋል።


ሉቃስ 12:41-48
42 ጌታም አለ፡— “እንኪያስ ምግባቸውን በጊዜው ይሰጣቸው ዘንድ ጌታው በቤተ ሰዎቹ ላይ የሚሾመው ታማኝና ልባም መጋቢ ማን ነው?
ጌታን ማገልገል መልካም ነው::  ጸጋን ስጠን ብለን ጠዋት ማታ እንጠይቃለን እርሱም መልካም ነው::  ማወቅ ያለብን እንደተቀበልነው መጠን ጌታ ይጠብቅብናል::  ፈቃዱን አውቆ አለማገልገል ኃጥያት ነው::  ብዙ  ከተቀበለ ብዙ ይጠበቃል::  የጌታውንም ፈቃድ አውቆ ያልተዘጋጀ እንደ ፈቃዱም ያላደረገ ያ ባሪያ እጅግ ይገረፋል ይላልና:: ማድረግ ሲገባው ያላወቀ ጥቂት ይገረፋል ይላል::  የምንቀበለው ለመስጠት መሆኑን እንወቅ::  ይህ ማለት ጸጋ ብቻ ሳይሆን ያለን ነገር በሙሉ ማለት ነው::  የተሰጠን ሁሉ የተሰጠን ለመንግስቱ ነው::  ለመምጣቱ ስንዘጋጅ ይህንንም መታዘዙን እንጨምርበት አለዚያ አገልግሎታችን በእሳት ውስጥ ሲያልፍ ውጤቱ ከተበላ ከስረናል:: በወርቅና በብር እንጂ በሳርና በእንጨት አይሁን አገልግሎታችን::
ጌታ ሆይ ዛሬ ቀን ሳለ ማስተዋል ይሁንልን እርዳን!  አሜን!

ሉቃስ 12: 49-59
50 ነገር ግን የምጠመቃት ጥምቀት አለችኝ፥ እስክትፈጸምም ድረስ እንዴት እጨነቃለሁ?
ይህ ያስጨነቀው ጥምቀት እኛን የዋጀበት የመስቀል ስራ ነው::  የመስቀሉ ስራ ሲጠናቀቅና እየሱስ ሲከብር መንፈስ ቅዱስ ወረደልን::  ይህንንም እሳት ሲገልጸው “በምድር ላይ እሳት ልጥል መጣሁ፥ አሁንም የነደደ ከሆነ ዘንድ ምን እፈልጋለሁ?” አለ::  ይህ የመንፈስ ቅዱስ ኃይል ነው መለየትን የሚያደርግ እንዲሁም መንግስቱን በስልጣን የሚመሰርተውና በሰዎችም እንዲሁም በቤተሰብ መካከልም ቢሆን መለያየትን የሚያመጣው:: ከጨለማው ወደሚደነቅ ብርሃን ዘወር ያለ ከጨለማው ስራ ጋር አይተባበርም ህይወቱን ለጌታው ሰቷል::
ጌታ የወቀሳቸው ጊዜውን ስላላወቁም ነው::  እናንት ግብዞች፥ የምድሩንና የሰማዩን ፊት ልትመረምሩ ታውቃላችሁ፥ ነገር ግን ይህን ዘመን የማትመረምሩ እንዴት ነው?” እኛስ? ጌታ ሊመጣ በደጅ ባለበት በዚህ ጊዜ እየተዘጋጀንና የልቡን አሳብ እያገለገልን ነው? 
ወደ ፍርድ ከመወሰድህ በፊት ከባለጋራህ ጋር ታረቅ እንደሚል በእግዚአብሔር የፍርድ ወንበር ፊት ከመቆም በፊት ከእግዚአብሔር ጋር በልጁ በማመንና በንስሃ መታረቅ ለሁሉ ነው::

ሉቃስ 13: 1-9
5 ነገር ግን ንስሐ ባትገቡ ሁላችሁ እንደዚሁ ትጠፋላችሁ።”
የሰው አእምሮ ቶሎ ብሎ የሚያስበው ለምን ይህ ነገር ደረሰ ኃጥያተኞች ስለሆኑ ወይም እንደዚህና እንደዚያ ማለትን ይወዳል::  ጌታ ግን ሲጠየቅ ጲላጦስ ደማቸውን ከመስዋእታቸው ጋር ስለቀላቀለው እንዲሆም በእየሩሳሌም ውስጥ በሰሊሆም ግንብ ስለገደላቸው ሲናገር የእነርሱ ኃጥያት ከሌላው በዝቶ እንዳይደለ ይናገራል::  መፍረድንና ጣትን መቀሰርን እናቁም!
ሰው ሲያይ ንስሃ ነው መግባት ያለበት እንጂ ወደ መፍረድ መሄድ የለበትምና ማስተዋል ይስጠን::  የእግዚአብሔር ምህረት እንዳንጠፋ እንደራራልን እናስተው::  ንስሐ ባትገቡ ሁላችሁ እንደዚሁ ትጠፋላችሁ ሲላቸው ሰምተው ብቻ አለፉት::  በምሳሌም ነገራቸው በወይኑ አትክልት ውስጥ ስላለችው በለስ::  እየሱስ ማለደላቸው ጊዜ እንዲጨመር እስራኤል ግን አልተመለሰችም::  በለስ በእስራኤል ይመሰላልና::  እስራኤል ካልተመለሰና ንስሃ ካልገባ ይጠፋል ነበረ መልክቱ::  የሰማው የለም እየሩሳሌም ሆይ ልሰበስብሽ መጣሁ መጎብኛሽን እንቢ አልሽ ብሎ አለቀስላት::  ምህረቱን ቸል ብለዋልና በ70 ዓ.ም ግንቦችዋ ሁሉ ፈርሰው ተነቀለች::  እስከዛሬ ችግር ውስጥ ናት ስፍራዋን ለማስከበር በማያቋርጥ ጦርነት ውስጥ ትገኛለች::
እራስን መመርመር እንዲሁም ሌሎችም ወደ ንስሃ እንዲመጡ መጸለይም  መልካም ነውና ጌታ ማስተዋልን ይስጠን:: የመጎብኛን ጊዜ ከማሳለፍ ጌታ ይጠብቀን::ሉቃስ 13: 10-17
16 ይህችም የአብርሃም ልጅ ሆና ከአሥራ ስምንት ዓመት ጀምሮ ሰይጣን ያሰራት በሰንበት ቀን ከዚህ እስራት ልትፈታ አይገባምን?” አለው።
ይህች ሴት 18 ዓመት ሙሉ በሰይጣን ነበረ የታሰረችው እንጂ በእግዚአብሔር አይደለም::  ጌታ አስሮ አያስቀምጥም እንድንፈታና በሰላም እንድንኖር ነው የሚፈልገው::  በሐዋ. ሥራ 10:38 እግዚአብሔር የናዝሬቱን ኢየሱስን በመንፈስ ቅዱስ በኃይልም ቀባው፥ እርሱም መልካም እያደረገ ለዲያብሎስም የተገዙትን ሁሉ እየፈወሰ ዞረ፥ እግዚአብሔር ከእርሱ ጋር ነበረና:: ሊፈውስ እንጂ ሊያስር አልመጣም! 
ይህች ሴት ፈውሰኝ ብላ ወደእርሱ አልመጣችም እርሱ እራሱ ነው የጠራትና “አንቺ ሴት፥ ከድካምሽ ተፈትተሻል” ብሎ እጁንም ጭኖ ፈወሳት::  አሜን!  የአብርሃም ኪዳን አለና እርሱን አሰበ ጌታ::  
መፈወስዋን ያየው የምኩራብ አለቃ ይህ ለምን በሰንበት ሆነ ብሎ ተቆጣ::  ጉዱን ሲገልጠው ግን አፍሮ ዝም አለ ሰንበትን እርሱም በጏዳው አያከብርምና::  ሲሆን ሲሆን እንደመሪነቱ ከእርስዋ ጋር እግዚአብሔርን ማመስገን  ነበረ::  እግዚአብሔር ለሌሎች በሚያደርገው አብረናቸው እንደሰት እንጂ ቅናት አይገኝብን ይህ ዝንባሌ  ካለ ጌታ ከእኛ ያስወግደው:: በደስታቸው ደስ ይበለን! 
ዛሬም ጌታ ይፈውሳል አላረጀም ወይም አሳቡን አልቀየረም የአብርሃም በረከት በክርስቶስ ለእኛ ደርሷል:: እንፈውስ ዘንድ እኛን ልኮናልና ለተጨነቁትና ለታሰሩት መዘርጋት ይሁንልን::ሉቃስ 13: 18-21 
18 እርሱም፡— “የእግዚአብሔር መንግሥት ምን ትመስላለች፥ በምንስ አስመስላታለሁ?
የእግዚአብሔር መንግስት በጥቂት ነው የምትጀምረው::  ከ12 ሐዋርያት ለዓለም ሁሉ ወንጌልን ማድረስ::  ከአንዱ አብርሃም አገርን  ማውጣት::  በብዙም ይሁን በጥቂት ማዳን አይሳነውም::  እንዲሁ እዚህ ስፍራ ላይ ጌታ በሰናፍጭ ቅንጣትና በእርሾ መሰላት::  መንግስቱ የምትሰፋ ናት::  ጌታ የሚጠይቀው በእጅ ምን እንዳለ ነው::  እንጥፍጣፊ ዘይት በቂ ነው ለጌታ::  ለአንድ ጊዜ ብቻ የሚጋገር ዱቄት?  በቂ ነው ረሀብ እስኪወጣ ሶስት ሰው መመገብ ይችላል::  አምስት እንጀራና ሁለት አሳ በቂ ነው ለሺዎች:: አንዱ ለሺ ሁለቱ ለአስር ሺ ይበቃሉ::  ጌታ ሲሰራ ቀመር ቦታ የለውም::
መንግስቱ ሁሉን ትገዛለችና ዛሬ የጠበበብን ምንድነው? መንግስቱ ትጋፋለች ደግሞም ትሰፋለች:: በዙሪያችን ያለውን ሁሉ ታስወርሰናለች::  ጥቂት የዘራነው ቃል ህይወትን ሞልቶ ወደጌታ ያመጣል::  ቀመሩ ይግባንና በተሰማራንበት ሁሉ እንጠባበቃት::
አቤቱ ዓይናችንን ክፈትልንና ታላቅነትህ ላይ እንጂ በምናየው በከበበን ላይ እንዳናተኩር እርዳን::  አሜን!

ሉቃስ 13: 22-30
29 ከምሥራቅና ከምዕራብም ከሰሜንና ከደቡብም ይመጣሉ፥ በእግዚአብሔርም መንግሥት በማዕድ ይቀመጣሉ።
“ጌታ ሆይ፥ የሚድኑ ጥቂቶች ናቸውን?” ለሚለው ጥያቄ ጌታ ኢየሱስ ሲመልስ “በጠበበው በር ለመግባት ተጋደሉ፤ እላችኋለሁና፥ ብዙዎች ሊገቡ ይፈልጋሉ አይችሉምም። እንዴ መጋደል ማለት ለመዳን ነው? ወይንስ ከተዳነ በኃላ?  ለምንድነው ብዙዎች መግባት የማይችሉት? እስኪ እናስበው ማን እራሱን ማዳን ቻለ?  መልሱም ማንም አልቻለም ነው::  ለመዳንማ ማናችንም  ምንም አላደረግንም::  ጌታ  በመስቀል ከፈለልን::  በአንዱ ኃጥያት ብዙዎች ሞቱ በአንዱ መታዘዝ ደግሞ መዳን ተገኘ::   ከእግዚአብሔር በኩል የተከለከለ ነገር የለም እራሱን ሰጠን::  ሰው ግን ወደ እግዚአብሔር መቅረብን አልወደደምና ብዙዎች በውጪ ከራሳቸው ጽድቅ ጋር ቀሩ:: ሰዎች ጽድቅን አልተራቡምና አልጠግቡም 
ጽድቅን ተርበው ለገቡት ደግሞ መጋደል ግድ ይላል በ1 ጢሞቴዎስ 6:12 መልካሙን የእምነት ገድል ተጋደል፥ የተጠራህለትንም በብዙም ምስክሮች ፊት በመልካም መታመን የታመንህለትን የዘላለምን ሕይወት ያዝ። ጸጋው ዓለማዊ ምኞትን ሁሉ ያስጥለናልና ስሙ ይባረክ! ጸጋህን ስጠን ጌታሆይ!ሉቃስ 13:31-35
34 ኢየሩሳሌም፥ ኢየሩሳሌም፥ ነቢያትን የምትገድል ወደ እርስዋ የተላኩትንም የምትወግር፥ ዶሮ ጫጩቶችዋን በክንፎችዋ በታች እንደምትሰበስብ ልጆችሽን እሰበስብ ዘንድ ስንት ጊዜ ወደድሁ፥ እናንተም አልወደዳችሁም።
የጊዜውን ጉብኝት ያላወቀችው እስራኤል እስከ ዛሬ ድረስ ቤታችሁ የተፈታ ይሆንላችኃል እንዳላቸው ይኸው እንደምናየው ተፈቶ  በማያቋርጥ ጦርነት ውስጥ ነው የሚኖሩት::  ይህ የሚያበቃው በጌታ ስም የሚመጣ የተባረከ ነው እስክትሉ ድረስነው ብሏል:: የእግዚአብሔርን ጉብኝት በተለያየ ነገር ላይ ዓይናችንን አድርገን እንዳናሳልፍ ማስተዋልን ይስጠን:: እርሱ መኖርያችን ነውና::
ሄሮድስ ሊገድልህ ይፈልጋልና ከዚህ አምልጥ ብለው መረጃ ያቀበሉት አንዳንድ ፈሪሳውያን መሆናቸው ይገርማል::  ሁሉም አይቃወሙትም ነበረ ማለት ነው::  መረጃውን ሰምቶ ከዚህ ልሂድ አይደለም ያለው እርሱ ከሰማይ ባለው ዕቅድ መሰረት ነውና የሚንቀሳቀሰው::  ለዛች ቀበሮ ብሎ አቃሎ ጠርቶ ዕቅዱን የነገራቸውና ንገሩት አላቸው ከእርሱ የተደበቀ አዲስ ነገር የለም::  የዚህ ዓለም መንግስት እርሱን መግደል አይችልም ወዶና ፈቅዶ እራሱን ለመስቀል ሞት ሰጠ እንጂ:: ስጋ ለባሽ በፊቱ ምንድነውና ይገድለዋል? 
ሊመጣ ባለበት በዚህ ጊዜ ስራችንን ቶሎ ቶሎ እንድንሰራና መንግስቱ እንዲሰፋ ጌታ ይርዳን::ሉቃስ 14: 1-14
11 ራሱን ከፍ የሚያደርግ ሁሉ ይዋረዳልና፥ ራሱንም የሚያዋርድ ከፍ ይላል።”
በሰንበት ጌታ ኢየሱስ በአንድ የፈሪሳውያን አለቃ ቤት አብረውትም ፈሪሳውያንና የሕግ አዋቂዎች በተገኙበት ግብዣ ላይ ተጠርቶ ባለበት ሆዱ ያበጠበትን ሰው ፈወሰው::  ሰንበት መሆኑ አልጠፋውም በሰንበትም መልካም ማድረግ ይቻል ነበረና ነው::  እንደልማዳቸው ደስተኞች አልነበሩምና በሰንበት የሚያደርጉትን ግን ሲነግራቸው:- “ከእናንተ አህያው ወይስ በሬው በጕድጓድ ቢወድቅ በሰንበት ወዲያው የማያወጣው ማን ነው?” አላቸው። እነርሱም ዝም አሉ::
እኛም ወደ ሰንበት እረፍት የገባን ነንና መልካሙንም ለማድረግ በክርስቶስ ተፈጥረናልና መልካም በማድረግ እንትጋ:: 
ሌላው ጌታ የታዘበው በዚህ ግብዣ ላይ የታደሙት የከበሬታ ስፍራ እንደ መረጡ አየና ምሳሌ ነግሮ መከራቸው:- “ራሱን ከፍ የሚያደርግ ሁሉ ይዋረዳልና፥ ራሱንም የሚያዋርድ ከፍ ይላል።”  እኛም እራስን ከፍ ከማድረግ ትህትናን ከጌታ ተምረን እራሳችንን ከኃይለኛው ከእግዚአብሔር እጅ በታች እናዋርድ:: 
አባት ሆይ እንዳስተውል እርዳኝ ልቤን መርምርና ይህ መራራ ስር የሆነው ትእቢት ካለ ይቅር ብለህ አስወግደው በደምህም እጠበኝ አልፈልገውም የአንተን ትህትና ልላበስ::  አሜን!

ሉቃስ 14:15-24
23 ጌታውም ባሪያውን፡— ‘ቤቴ እንዲሞላ ወደ መንገድና ወደ ቅጥር ውጣና ይገቡ ዘንድ ግድ በላቸው፤
በዚሁ ግብዣ ላይ እያሉ  ከተቀመጡትም አንዱ ይህን ሰምቶ፡— “በእግዚአብሔር መንግሥት እንጀራ የሚበላ ብፁዕ ነው፡” አለው። ግብዣውን የሚያዘጋጀውና ወደ በጉ ሰርግ የሚጠራው ጋባዥ ከፊቱ ያለው የሚያወራው መሆኑን ማን በነገረው?! 
ምሳሌውንም ጌታ ሲናገር አንድ ሰው ታላቅ ግብዣ ጠራ::  ብዙ ደክሞ ትልቅ ግብዣን አዘጋጅቶ ሳለ ተጋባዦቹ ግን እያመካኙ ይቅርታ ጠይቀው ቀሩ::  እነዚህ ተጋባዦች የሚገርሙ ናቸው መሬትን ሳያዩ የሚገዙ ከብትንም ሲገዙ ሳያዩ ገዝተው በኃላ የሚፈትሹ ኑሮን አገላብጠው የሚኖሩ ናቸው::  ሙሽራውም ቤተሰብን ከእግዚአብሔር ያስቀደመ ነገሩን ያገላበጠ ነው:: ጌታ ማስተዋልን ይስጠን!  ዛሬ ማቄን ጨርቄን የሚያስብለን ሰበብ ሁሉ ከእኛ ይውደቅ!
እንግዲህ ግብዣው ተዘጋጅቷልና ባለቤቱ ተቆጥቶ ባርያውን  ወደ ከተማ ጎዳናና ወደ ስላች ፈጥነህ ውጣ ድሆችንና ጕንድሾችን አንካሶችንና ዕውሮችንም ወደዚህ አግባ አለው:: የተጋበዙት የተገባቸው ቀርተው ያልታሰቡ በግብዣው ላይ ይቀመጣሉ:: እንግዲህ እኛ ከዚህ ዝርዝር ውስጥ ነው የምንገኘው ታውረን የነበርን ጠላት አቁስሎ ሲደቁሰን የነበርን አንካሶች ድሆች በወንጌል ምክንያት ወደ ግብዣው መጣን::
ባርያው እንዳደረገው  ወደ ከተማ ሁሉ እንድንወጣና ወዳሉበት ሁሉ ሄደን እኛ በነበርንበት ሁኔታ ላይ ያሉትን የሰው ልጅ ሁሉ ወደ ቤቱ አምጥተን ቤቱን እንድንሞላ ይፈልጋል – በአባቴ ቤት ብዙ መኖርያ አል ብሎን የለ::  ተጋባዥ ብቻ አይደለንም የተላክን ነን ጌታችን የደገሰውን ድግስ ኑና ተጋበዙለት የምንል::  ጌታ ሆይ የመከሩ ሰራተኛ ስላደረከን ተመስገን መከሩ መሰብሰብያው ነውና ልትመጣም በደጅ ነህና ወጥተን መሰብሰብ ይሁንልን:: አሜን!ሉቃስ 14: 25-35
33 እንግዲህ እንደዚሁ ማንም ከእናንተ ያለውን ሁሉ የማይተው ደቀ መዝሙሬ ሊሆን አይችልም።”
ያልተጋበዙት ሁሉ ቤቱን ከየስፍራው መተው እንደሞሉት ከተናገረው ምሳሌ ጋር አያይዞ ስለሚጠበቅባቸው ህይወት አስተማረ::  ይህንንም የተናገረው ለደቀ መዛሙርቱ ነበር:: የሚከተለኝ አይደለም ቤተሰቡን እራሱንም ይካድ አለ::  ቤተሰብን መተው ዛሬ የጀመረው አይደለም አብርሃምንም ሲጠራው ይህንኑ ነበር ያደረገው::  
ዓለምንና ቤተሰብን እራሳችንንም እንድንጠላና እርሱን በመከተል ታማኝነታችንን እንድናሳይ ይፈልጋል:: እያንዳንዳችን የራሳችንን መስቀል ይዘን እንድንከተል ተጠርተናል:: ቁጭ ብለን ደቀመዝሙር መሆን የሚጠይቀውን አውቀን እንከተል::  ይህ ህይወት መሞት ነውና ይሻላል እኔ ስሞት እርሱ መኖር ይጀምራል በሞራል ተነስቼ እችላለሁ የምለው አይደለም::  እርሱ በይህወቴ ከሌለ ጨውነቴም ይጠፋል እንዲህ ያለው ጨው ጠአም ስለሌለው ከድንጋይ ተመድቦ ከመጣል ብቻ ነው እጣ ክፍሉ::  ታድያ ለእኔነት ሞቼ መስቀሉን ተሸክሜ ጨው ጨው ብዬ ብኖር አይሻልም?
አባት ሆይ እይኸው ህይወቴ አንተው ብቻ ኑርበት ለአንተ እሰጥሃለሁ::  አሜን!

ሉቃስ 15:1-7
7 እላችኋለሁ፥ እንዲሁ ንስሐ ከማያስፈልጋቸው ከዘጠና ዘጠኝ ጻድቃን ይልቅ ንስሐ በሚገባ በአንድ ኃጢአተኛ በሰማይ ደስታ ይሆናል።”
ቀራጮችና ኃጢአተኞችም ሁሉ ሊሰሙት ወደ እርሱ ይቀርቡ ነበር እንጂ አይሸሹትም::  በዙርያው ይገኛሉ አይሳቀቁም::  እርሱም ይቀርባቸዋል አያንቋሽሽም አይሸሽም ደዌያቸውንም ይፈውሳል:: ይህንን ያዩ የዘመኑ አገልጋዮች እውነት ለመናገር ማንን ይሆን የሚያገለግሉት? አንጎራጎሩበት ኃጥያተኞችን ይቀበላል አብሮም ይበላል ብለው እንደሳተ ደመደሙ::  ወይ መተላለፍ!  
እውነተኛ እረኛ ነፍሱን ስለበጎቹ ይሰጣል::  በጎቹ ግን ከጠፉበት መመለስ ወይም እራሳቸውን መጠበቅና ከነጣቂም ማስጣል አይችሉም::  ስለዚህ እረኛው የተቀሩትን አስቀምጦ (እነዚህንም በአደጋ ላይ አድርጎ ሳይሆን)  የጠፋውን ፍለጋ ይሄድና ተሸክሞት ይመለሳል ምክንያቱም ይህ በግ ደክሟል ያለ እረኛ ተንገላቷል አልበላም በአግባቡ ሲቅበዘበዝ ቆይቷልና ተሸክሞ ያመጣዋል:: 
እኛንም ፈልጎ ባያመጣን ኖሮ በራሳችን ወደ እርሱ ባልመጣን ነበር:: ከጠላት መንጋጋ ውስጥ አውጥቶ  ተሸክሞ አመጣን!! በሮሜ 5:6 ገና ደካሞች ሳለን ክርስቶስ ዘመኑ ሲደርስ ስለ ኃጢአተኞች ሞቶአልና። አሜን የማይገባንን ሰጠን!  ሲያገኘንም የጠፋውን በጌን (ልጄን) አግኝቼዋለሁና ከእኔ ጋር ደስ ይበላችሁ ይላል በሰማይም ከመላእክቱ ጋር ታላቅ ደስታ ይሆናል:: እርሱ ሃሴት የሚያደርግበትን ነገር አገልጋዮቹ የተባሉት የሚያጉረመርሙበት መሆኑ ይገርማል:: ዛሬስ የጠፋውን የሚፈልግ ልብ አለን?! የእግዚአብሔር ልብና ዓይን በጠፉት ላይ ነውና ደስታውን እንፈጽምለት!
አባት ሆይ በእኔ መገኘት (ንስሃ መግባት) ደስ ብሎህ ሃሴት አድርገህ ነበረና ተመስገን ተከታትለህ አግኝተኸኝ ተሸክመህ ወደቤትህ ያመጣኸኝ ጌታዬ ክበርልኝ::  ልብህ ባለበት የኔም ልብ ይሁን የጠፉትን  በቅን ልብና በፍቅር መፈለግ ይብዛልኝ:: አሜን!

ሉቃስ 15:8-10
10 እላችኋለሁ፥ እንዲሁ ንስሐ በሚገባ በአንድ ኃጢአተኛ በእግዚአብሔር መላእክት ፊት ደስታ ይሆናል።”
በግም የጠፋው ሰው ድሪምም የጠፋት ሴት ያላቸውን ቁጭ አድርገው የጠፋውን ፍለጋ ነው የሄዱት:: ለጠፋው ቅድሚያ ሰጡ እንጂ ቸል አላሉም:: ጠፍቶ የቀረ ነገር እንዴት ይከነክናል? በተገኘው አጋጣሚ ሁሉ ለማግኘት መፈለግ አይቀርም:: እንዲሁ ፈልጎ ፈልጎ ያገኘኝ ልጁ ነኝ እኔ!  ተመስገን!
ድሪሙን ለማግኘት ይህች ሴት የወሰደችው እርምጃ አለ ይኼውም በመጀመርያ መብራት ማብራት ከዛም በጥንቃቄ መጥረግ ነው::  እግዚአብሔርም እንዲሁ  ብርሃኑን አብርቶ በደሙ ቀድሶ የራሱ አድርጎን በውስጣችንም ሆኖ የጠፋውን ፍለጋ ቀጥሏል::   በእኛ ውስጥ ሆኖ እየፈለገ ያለው እራሱ ጌታ ነው:: ይህች ሴት ስታገኘው የጠፋብኝን ድሪሜን አግኝቻለሁና  ከእኔ ጋር ደስ ይበላችሁ እንዳለችው ጌታም አንድ ኃጥያተኛ ንስሃ ሲገባ በሰማይ ከመልአክቱ ጋርና እንዲሁም ከልጆቹ ጋር ደስስስስ ይለዋል:: አጋንንት በስምህ ተገዙልን ሲሉት እርሱ ግን በመንፈስ ሃሴት አደረገ በህይወት መጽሐፍ ላይ ስማቸው ስለተፃፈ::
በእኔ ውስጥ ሆነህ ፍለጋ ላይ ያለህ ጌታዬ ሆይ ደስታህ እንዲፈጸም በደምህ አጥበህ ያነፃኸውን ማንነቴን በፊትህ ቅዱስና ህያው መስዋእት አድርጌ አቀርባለሁ እንደ ሊድያ የሰዎችን ልብ ከፍተህ ወደቤትህ አምጣ::  አሜን!

ሉቃስ 15: 11-32
20 “ተነሥቶም ወደ አባቱ መጣ። እርሱም ገና ሩቅ ሳለ አባቱ አየውና አዘነለት፥ ሮጦም አንገቱን አቀፈውና ሳመው።  . . .  24 ይህ ልጄ ሞቶ ነበርና ደግሞም ሕያው ሆኖአል፤ ጠፍቶም ነበር ተገኝቶአልም’። ደስም ይላቸው ጀመር።
ይህንን አባት ሳይ በጣም ልቤን ይነካዋል::  ፍቅሩ አልተቀየረም ልጅየው  እስክትሞት አልጠብቅም አሁኑኑ ድርሻዬን ስጠኝ ብሎ ወሰደ ከአባቱም ርቆ ሄደ::  አባትየው ግን ይህንን ሁሉ ቢያደርገውም ልጄ ሲመጣ የሚያደርገውን ልብስ ቀለበት ጫማ ብሎ ተዘጋጅቶ መንገድ መንገዱን እያየ ይጠብቀው ነበረ::  እኔንም እንደዚህ ጠብቀህ ስላገኘኸኝ ተመስገን::
ይህ ልጅ ወደ ልቡ ተመልሶ ያጠፋው ገብቶት በአባቴ ቤት ባርያ ልሁን ብሎ መጣ::  አባትየው ልጁን ገና ሩቅ ሲያይ ከነቁሻሻውና ከነጉስቁልናው ቢሆንም አዘነለት፥ ሮጦም አንገቱን አቀፈውና ሳመው እንጂ አልተጠየፈውም::  ጌታዬ እኔንም ሲያየኝ አልተጠየፈኝም እየሱስን አልብሶ አዲስ ፍጥረት አድርጎ ልጄ ነሽ ወዳጄም ነሽ እንጂ ባርያ አይደለሽም አለኝ!!!!  ሃሌሉያ!! ምን አይነት ፍቅር ነው?!
ወንድምየው ግን በዚህ ደስ አላለውም አሁን ፈሪሳውያን እያደረጉ እንዳሉት ማለት ነው::  ምሳሌውን የጀመረው ከኃጥያተኞች ጋር ይበላል ስላሉት ነበረና::ትልቁ ልጅ  እንዳለው  እንደባርያ አገለገልኩህ አለ በቤት ነን ብለው የጠፉ አሉ::  የአባቱ የሆነው ሁሉ የእርሱ እንደሆነ አልገባውም ገና በባርያነት ልብ ውስጥ ነው ያለው:: እንደነዚህ ያሉት ንስሃ መግባትና ወደ አባታቸው መመለስ ይሁንላቸው::  በራሳቸው ጽድቅ የሚመኩትን ጌታ ያስብ::  እኛም የጌታ ልብና ፍቅር ለጠፉት ይኑረን እንጂ ኃጥያተኛን ከኃጥያተኛ የምናወዳድርና ፍርድን የምንሰጥ እንዳንሆን እንጠንቀቅ::  የዚህ አባት ደስታ በጠፋው ልጅ መመለስ ነውና የጠፋውን ለመፈለግ ሰፊ ልብ ይኑሩን::ሉቃስ 16: 1-14
13 “ለሁለት ጌቶች መገዛት የሚቻለው ባርያ ማንም የለም፤ ወይም አንዱን ይጠላልና ሁለተኛውንም ይወዳል፥ ወይም ወደ አንዱ ይጠጋል ሁለተኛውንም ይንቃል። ለእግዚአብሔርና ለገንዘብ መገዛት አትችሉም።”
ስላልታመነው መጋቢ ምሳሌ ነገራቸው ይህ ሰው የጌታውን ገንዘብ አባክኖ ለራሱ የወደፊት ህይወት አደላደለ::  ጌታውም ይህንን ክህደቱን በልባምነት አድርገሃል አለው በአመፃውም ገንዘብ ወደፊት የሚቀበሉትን አዘጋጀ::  ይህ ለዓለም ልባምነት ነው::  ለጌታቸው ለገንዘብ ተገዝተዋል::  
ልጆቹ ልባም እንድንሆንና የሚሰጠንን በአግባቡ እንድንጠቀምበት አንድ ቀን እንደቀረው እንድንዘጋጅ አንድ ሺ አመትም እንደቀረው እንድናቅድ ይፈልጋልና ልናስተዳድረው በተሰጠን ንብረትና ገንዘብ መልካምን እናድርግ:: ይህም ምሳሌ ገንዘብ የሚወዱትን ፈሪሳውያንን አስቆጣ እንጂ አልመለሳቸውም።  የሚሰማ ጆሮ ያለው ይስማ!  እውነተኛ አምልኮ ወላጅ የሌላቸውን ልጆችና መበለቶችን መርዳት ይጨምራልና የጌታ ዓይን በሆነበት በዚያ የእኛም ይሁን::  በልግስና እንዘርጋ::

ሉቃስ 16: 15-18
15 እንዲህም አላቸው፡— “ራሳችሁን በሰው ፊት የምታጸድቁ እናንተ ናችሁ፥ ነገር ግን እግዚአብሔር ልባችሁን ያውቃል፤ በሰው ዘንድ የከበረ በእግዚአብሔር ፊት ርኵሰት ነውና።
ስለአመጸኛው መጋቢ ምሳሌ ሲነግራቸው ገንዘብን የሚወዱት ፈሪሳውያን አሾፉበት::  ምክንያቱም ህጉን እንደሚመቻቸው አድርገው ይለምጡት ነበርና ነው::  ስለዚህም ምክንያት ራሳቸውን በሰው ፊት ማጽደቅ በደንብ ችለው ነበር:: እግዚአብሔር ግን ልብን ይመረምራልና እንደሰው ፊትን አይቶ አይታለልም:: ህግ ሁሉ ይፈጸማል ህጉ ከሚያልፍ/ከሚሻር ሰማይና ምድር ቢያልፍ ይቀላል::  ጌታ አሳቡን የሚቀያይር ጌታ አይደለም::
እንደወደዱ የሚለምጡት የህግ ዘመን ዮሃንስ ላይ አበቃና የጸጋ ዘመን በአዲሱ ኪዳን በኢየሱስ ተጀመረ::  እያንዳንዷን ህግ ፈጽሞ ኖረ!  አንዱ እንዲመቻቸው የለመጡት ህግ ስለትዳር ነበረና እርሱን አነሳላቸው::  ሚስቱንም የሚፈታ ሁሉ ሌላይቱንም የሚያገባ ያመነዝራል፥ ከባልዋም የተፈታችውን የሚያገባ ያመነዝራል አላቸው:: እነሱ ግን ትንሽ ምክንያት ፈልገው አንዷን ፈተው ሌላኛይቱን ያገቡ ነበረ::  ልብን የሚያውቀው ጌታ ግን ይህ ማመንዘር ይባላል አላቸው::  ከዝሙት በቀርና የማያምን መለየት ከፈለገ ነው (1ቆሮ 7:15) ፍቺ የሚፈጸመው:: የልባቸው እልከኝነት ግን ይህንን እንዳይቀበሉ አደረጋቸው::
የልብ እልኸኝነት እንዴት ከባድ ጠላት ነው?!  ከልባችን ይልቅ አንተ ታላቅ ነህና ጌታ ሆይ ልባችንን መርምር ፈትሽ አለመታዘዝን በመታዘዝ ተካልን:  እንደቃልህ እንድናስብ በአእምሯችንም  መታደስ እንድለወጥ እርዳን ይህንንም ዓለም ከመምሰል አድነን::  አንተን ማብለጭለጭ ይሁንልን::  አሜን!

ሉቃስ 16: 19-31
31 ‘ሙሴንና ነቢያትንም የማይሰሙ ከሆነ፥ ከሙታንም እንኳ አንድ ቢነሣ አያምኑም፡’ አለው።”

ተመችቶት በዓለም የኖረው ሐብታም ሰው ተቀበረ ነው የሚለው መቼም በምድር ድብልቅልቅ ያለ ነበረ ቀብሩ በብዙ አጀብ ነበረ የተፈፀመው:: ከሰማይ ግን መልአክት የተላከው ለአላዛር ነበረ::  ከዛም አሻቅቦ አይቶ ነው አብርሃምን የሚያናግረው እርሱ ከታች እነአብርሃም ከላይ::  አላዛርን እንዲልክለትና በጥማት ስለደረቀ ውሃ ምላሴ ላይ ያድርግልኝ በማለት ይጠይቃል::   መሞቱን አላወቀም እንዴ?  ዛሬም አላዛር ለእርሱ ጥሪ የሚመልስ ነው የመሰለው እንደለመደው:: ውሃ አይሰጥህም ሲባል እሺ ወደ ወንድሞቼ ላከው ይህንኑ የፈረደበትን አላዛርን አዛም ሆኖ የእርሱን ስራ ሊያሰራ ይፈልጋል::  ነገር ግን አላዛር ለእርሱ የሚታዘዝበት ጊዜ አብቅቷል::  በህይወት ላሉት ከቃሉ ውጪ ሌላ የሚላክ የለም::  
ከሞት በኃላ ህይወት አለ በዛ በእሳት ውስጥ መኖር ለማንም የማይመረጥ ነው በእግዚአብሔር ዓይን::  ስቃይ አለው እረፍትም የለውም!  ስሜት አለ መጠማት አለ መቃጠል አለ መሰቃየት አለ ማወቅ አለ (በበሩ ይተኛ የነበረውን አላዛርን አውቆት ነበረ)::   እውቀቱም ሙሉ ነው ያላየውን አብርሃምንም አውቋል::  የትኛው የዓለም ነገር የሚማርክ ቢሆን ነው ወደዚህ ስፍራ ሰው የሚያመራው?!  ሰው ነፍሱን አጉድሎ ዓለምን ሁሉ ቢያተርፍ ምን ይጠቅመዋል?! ዛሬ ወደነፍሱ እረኛና ወደሞተለት ጌታ ዞር ማለና ንስሃ መግባት አይሻልም?!! ከዚህ ስቃይ አመለጡ ብሎ ነው ጌታ ሃሴት ያደረገው:: ስማችን በሰማይ ስለተፃፈ ደስ ይበለን::
ውሳኔ ወደ ክርስቶስ ለመምጣት ዛሬ ነው እንጂ ይህ ሐብታም ባለበት ሁኔታ ከሆነ ዘግይቷል::  በ2 ቆሮንቶስ 6:2 በተወደደ ሰዓት ሰማሁህ፡ በመዳንም ቀን ረዳሁህ፡ ይላልና፤ እነሆ፥ የተወደደው ሰዓት አሁን ነው፤ እነሆ፥ የመዳን ቀን አሁን ነው።
ዛሬ ዙሪያ ገባችንን እንመልከት እርዳታችንን የሚፈልጉ ሰዎችን እበራችን ድረስ ልኮ አላስተዋልን እንዳይሆን::  ኤልሳዕ የግያዝ ዓይኖች እንዲከፈቱ ጸልዮ እንደተከፈቱ የእኛንም መንፈሳዊ ዓይኖች ጌታ ይክፈት የማያውቁት የት እንደሚሄዱ እያወቅን ዝም አንበል::  አሜን

ሉቃስ 17: 1-2
ከእነዚህ ከታናናሾች አንዱን ከማሰናከል ይልቅ የወፍጮ ድንጋይ በአንገቱ ታስሮ ወደ ባሕር ቢጣል ይጠቅመው ነበር።
ጌታ ለደቀ መዛሙርቱም እንዲህ አለ፡— “መሰናክል ግድ ሳይመጣ አይቀርም፥ ነገር ግን መሰናክሉን ለሚያመጣው ወዮለት::  ፈተና የለም ክርስትና አልጋ በአልጋ ነው ብሎ አልዋሸንም መሰናክል በብዙ መንገድ ይመጣል ጥቂቱን ለማየት እንሞክር:: መሰናክል ሁለት ተዋንያን አሉት ተሰናካይና አሰናካይ::  ተሰናካይ ጌታን የሚከተል ወይም ወደ ጌታ ሊመጣ ያለ እጩ ሰው ሲሆን አሰናካይ ብለን የምንላቸውን በሁለት መክፈል እንችላለን: – ከውስጥ እና ከውጪ:: 
የውጪው  እንደ ጳውሎስ አይነቱ ነው:: ቅዱሳንን እያሳደደ ለእስር የሚያበቃ የነበረ ሰው ነበረ ዛሬም እነዚህ አሉ ቅዱሳን ተዘርግተው ወተው እንዳያገለግሉ እንቅፋት የሚያደርጉ:: ጌታ ለምን ታሳድደኛለህ አለው እንጂ ህዝቤን አታሳድ አይደለም ያለው በህዝቡ ውስጥ የሚገፋው ኢየሱስ ነው:: 
ሌሎቹ ደግሞ አውቀናል ብለው የገላትያን ቅዱሳን ያሰናከሉ ህግን እንዲጨምሩ አስተማሯቸው በመንፈስ የጀመሩትን በስጋ እንዲጨርሱ ያደረጉ በፊታቸው የተሳለውን ጌታ አደበዘዙት::  
ሁለተኞቹ ከውስጥ ያሉ ናቸው በጌታ ቤት ያሉ ለብ ያለ ህይወት ያላቸው:: የእነዚህ ደግሞ አይጣል ነው የመዳንን በር ይዘው አያስገቡም::  የእነርሱን ህይወት እያዩ አዳዲስ ሰዎች ለመምጣት ይቸገራሉ:: ሁለቱም አይነቶች ወዮላቸው የሚባሉ ናቸው ለጌታ መልስ ይሰጣሉ::

አቤቱ መሰናክልን እንዳላስቀምጥ እርዳኝ::  ማንም በእኔ እንዳይሰናከል እንዲያውም ቃልህ እንደሚል አንተን የማብለጨልጭ ዝቅ ብዬ በትህትናና በፍቅር የምመላለስ ሰው አድርገኝ::  ከአንተ አጀንዳ ጋር እስማማለሁ ልጅህን አስመስለህ ስራኝ!  አሜን!

ሉቃስ 17: 3-4
3 ለራሳችሁ ተጠንቀቁ። ወንድምህ ቢበድልህ ገሥጸው፥ ቢጸጸትም ይቅር በለው።
ወንድማችንን ይቅር ማለት ለራስ መጠንቀቅ ነው::  ልብ ብለን ካሰብነው በደልን የሚበድለን የቅብ ወይስ የሩቅ ሰው?  መልሱ ቀላል ነው የቅርብ ሰዋችን ነው::  ስለዚህ ወንድማችንን መገሰጽ ያስፈልጋል እኛ ግን ብዙ ጊዜ በውስጣችን ይዘን እንመላለሳለን::  ነገራችንን ገልጸን መነጋገር አለብን ወንድማችንም ቢጸጸት ይቅር እንበለው እንጂ አሁን እውነቱን ነው እንደገና ሊበድለኝም አይደል ብለን ማሰብን ትተን ይቅር እንበል::  ወደኃላም እየተመለስን የተዘጋ ፋይል አናገላብጥ ወደፊት እንዘርጋ ጠላት በትላንትና ሊያስረን ይፈልጋልና እንንቃ::  መጸጸት ትልቅ የንስሃ ደረጃ ነው:: ጌታም ያለን ኑ እና እንዋቀስ ነው:: አለበለዚያ እንዴት ሆነን በፊቱ ልንጸልይ ነው?  የምናቀርበውን መስዋእት ጥለን ሄደን ከወንድማችን እንድንታረቅ ይፈልጋል ጌታ::
አባታችን ይቅር ባይ አባት ነው:: ስንት ጊዜ ነው ይቅር ያለን? እይኽው በቤቱ ያኖረን?! እርሱን መምሰል ይሁንልን ሰባት ጊዜ ሰባ ይቅር ማለት ይሁንልን::  ይህንን የይቅርታ ልብ ከጌታ እንማር::  ጌታ ለመቱት ለሰደቡት ላሾፉበትና ለሰቀሉት ይቅር በላቸው ብሎ ነው የጸለየላቸው::  
አባት ሆይ እርዳኝ !

ሉቃስ 17: 5-10
6 ጌታም አለ፡— “የሰናፍጭ ቅንጣት የሚያህል እምነት ቢኖራችሁ፥ ይህን ሾላ፡— ‘ተነቅለህ ወደ ባሕር ተተከል፡’ ብትሉት፥ ይታዘዝላችሁ ነበር።
ሐዋርያቱ እምነት ስጠን ብለው የጠየቁት ስለይቅርታ ሲያስተምራቸው ነው::  ሰባት ጊዜ በድሎ ተጸጽቶ ቢመጣ ይቅር ማለት የሚለው አሳብ በሰው የሚቻል አይደለም ብለው አስበው ይመስላል::  የእርሱም ምላሽ ጥቂቱ በቂ ነው አላቸው::  
እምነት ደረጃም አለው:- ትልቅ እምነት ብሎ ጌታ የተደነቀበት የመቶ አለቃው ነው እምነት ነው ቃል ብቻ ተናገር ይሆናል ብሎ አመነ::  ሐዋርያቱ ደግሞ ብዙ ጊዜ እምነትየጎደላችሁ ብሎ ይነቅፋቸዋል::  ከዛ በፊት ያደረገውን በተመሳሳይ ነገር ያለፉበትን ይነግራቸዋል::  ለምሳሌ ማዕበል ተነስቶ ጠፋን ሲሉ ነፋሳትን ገስጾ ማዕበሉ ጸጥ ሲል አይተው ተመልሰው ይፈራሉ: ጴጥሮስም በውሃ ላይ ሲራመድ ፈራ በውሃ ላይ ስልጣን እንዳለው ቢያዩም እምነትን ፈጥሮላቸው አላለፈም::  
ትላንትና በህይወታችን የተደረገው ነገር ለዛሬ እምነትን ፈጥሮልን ልናምን እንጂ ልንፈራ አይገባም::  ጥቂቱ ይበቃል::  የምናምነው ነገሩ ይሆናል በማለት ሳይሆን እርሱ ይችላል ብለን መሆን አለበት::  ይህ እምነት በልመና አይመጣም ቃሉን ከመስማት የሚወለደው ነውና::  የእግዚአብሔርን ቃል እንስማ እናሰላስል በዚህ ውስጥ በደንብ ጌታን እንደሚገባ እያወቅነው ስንመጣ እምነትም ይፈጠራል::  ልባችንም ያምነዋል::  እምነት የመንፈስ ፍሬ ነው::  እኛ አምጠን የምናመጣው አይደለምና  ማስተዋል ይሁንልን ለቃሉም ጊዜ መስጠት ይሁንልን የትላንቱም አይጥፋን አቤኔዘር ይሁንልን:: ይህንን በማድረጋችን ደግሞ ጎሽ ጎሽ አንፈልግ ሁሉ በእርሱ ለእርሱ ከእርሱ ነውና በእኛ የሰራ ጌታ ይባረክ እኛ የማንጠቅም ባርያ ነን! 

ሉቃስ 17: 11-19
19 እርሱንም፡— “ተነሣና ሂድ፤ እምነትህ አድኖሃል፡” አለው።
እነዚህን ለምፃሞች ጌታ ያገኛቸው ገሊላና ሰማርያ መካከል ነው ከከተማ ተባረው አትገቡም እስክትነጹ ተብለው ተገልለውና ተትተው እያሉ አገኛቸው::  እነርሱም እየጮኹ፡— “ኢየሱስ ሆይ፥ አቤቱ፥ ማረን፡” አሉ። አይቶም፡— “ሂዱ፥ ራሳችሁን ለካህናት አሳዩ፡” አላቸው። እነሆም፥ ሲሄዱ ነጹ። አይቶም ሲል እንደው ማየት ብቻ ሳይሆን ያሉበትን ሁኔታ እንደእነርሱ ሆኖ ተረድቶ ራራላቸው::  መገፋታቸውን መተዋቸውን ግራ መጋባታቸውን ጭንቀታቸውን ቤተሰብና ዘመድ ጏደኛ መናፈቃቸውን እስከመቼ እንደሚቆዮ አለማወቃቸውን ሁሉ አየ!
ቃልን ጌታ አወጣ ሂዱ! እነሆም፥ ሲሄዱ ነጹ። ይገርማል ከነለምፃቸው ወደ ከተማ ለመግባት አቀኑ?!  እንዴት ቃሉን እንዳመኑ ምክንያቱም ወድያው አልነፁም ሲሄዱ እንጂ!!  አረ ይሄ እምነት የሚባል ነገር የሚገርም ነው::  እንመነው ጌታን ምንም ሳናይ እርሱ የታመነ ነው!!!!
ጌታም ሲመሰክር እምነትህ አድኖሃል፡” አለው:: ከአንዱ ሳምራዊ በቀርም የተደረገላቸውን አይተው ሊያመሰግኑ አልመጡም::  የጸሎታችን ብዛት ለመለመን ከጌታ የምስጋናችን ማነስ ከተቀበልን በኃላ ይገርመኛል:: ምስጋና ይብዛልህ አምላኬ! 

የምስጋና ቀን ነው ጌታዬ ስላደረክልኝ ነገር ሁሉ::

ሉቃስ 17: 20-37
ሉቃስ 17:20 . . .— “የእግዚአብሔር መንግሥት በመጠባበቅ አትመጣም፤ 21 ደግሞም፡— ‘እንኋት በዚህ፡’ ወይም፡— ‘እንኋት በዚያ፡’ አይሉአትም። እነሆ፥ የእግዚአብሔር መንግሥት በመካከላችሁ ናትና፡” አላቸው።
ይህንን ምላሽ የሰጠው ፈሪሳውያንም፡— “የእግዚአብሔር መንግሥት መቼ ትመጣለች፡” ብለው ሲጠይቁት ነው::  መጥምቁ ዮሃንስ ሲላቸው የነበረው የእግዚአብሔር መንግስት ቀርባለችና ንስሃ ግቡ ነበረ::  በመካከላቸው ያለውን ንጉስ ማወቅ አልቻሉም!  በመካከላችሁ ናት ቢላቸውም አልሰሙትም:: የእግዚአብሔር መንግስት በህዝቡ መካከል ናት ህዝቡ ሲወሰድ ግን አብሮ ይሄዳል::
አሁንም በኖኅና በሎጥ ዘመን እንደነበረው ጥፋቱ መጥቶ እስኪያገኛቸው እንዳልነቁ ይህም ዘመን እንደዛው ነው::  የጌታ መምጣት ሹልክ ብሎ ሳይሆን ከዓለም ጥግ እስከ ጥግ የሚታይ ነው የሚሆነው::  ማራናታ!
“ነፍሱን ሊያድን የሚፈልግ ሁሉ ያጠፋታል፥ ነፍሱንም የሚያጠፋ ሁሉ በሕይወት ይጠብቃታል እንደሚል በዛች ለሊት የሚወሰድ አለ የሚውቀርም አለ:: እግዚአብሔር ግን ህዝቡ ይወሰዳል::  የሚገርመኝ ነገር ለዚህ ጥያቄ የተሰጠው መልስ ነው::  መልሰውም፡— “ጌታ ሆይ፥ ወዴት ነው?” አሉት። እርሱም፡— “ሥጋ ወዳለበት በዚያ አሞራዎች ይሰበሰባሉ፡” አላቸው። ስለመጨረሻው ጦርነት እየተናገረ ነው በማቴ 24:28 በጥልቅ ያብራራዋል:: ራእይ 19:21 የቀሩትም በፈረስ ላይ ከተቀመጠው ከአፉ በሚወጣው ሰይፍ ተገደሉ፤ ወፎችም ሁሉ ከሥጋቸው ጠገቡ።

ሉቃስ 18:1 -8
ሳይታክቱም ዘወትር ሊጸልዩ እንዲገባቸው የሚል ምሳሌን ነገራቸው፥
መታከትን ምን አመጣው ካልን ጠላታችን ጸሎትን ስራ ሊያደርግብንና ጸሎትሽ አልተሰማም እያለ ሊያደክመን ስለሚመጣ ነው::  ጌታን እንደዛ አመጸኛ ዳኛ እንድናየው ነው የሚፈልገው:: ጌታችን ግን የሚለን ቀንና ሌሊት ወደ እርሱ ለምንጮህ ለእኛ ለሚታገሰን ለምርጦቹ አይፈርድልንምን?  ፈጥኖ ይፈርድልናል። የእርሱ ጥያቄ የሰው ልጅ በመጣ ጊዜ በምድር እምነትን ያገኝ ይሆንን?
ጌታ የሚጠራን ምርጦቼ ብሎ ነው ደስ አይልም?! ለሚታገሰን ምርጦቹ ዛሬም ጌታ ይፈርዳል:: እርሱ ሲመጣ እምነትን ተሞልተን እንጠብቅ::  ያለ እምነት እግዚአብሔርን ደስ ማሰኘት አይቻልም::  ከጸሎት አንዘናጋ ፊቱን መፈለግ ይብዛልን!! እርሱ ይፈርዳልና!!ሉቃስ 18: 9-14
9 ጻድቃን እንደ ሆኑ በራሳቸው ለሚታመኑና ሌሎቹን ሁሉ በጣም ለሚንቁ ይህን ምሳሌ ነገራቸው፥ 
ይህንን አባባል ልብ ብዬ አይቼው አላውቅም ነበረ ምሳሌውን እንጂ::  ጣትን ወደ ሌላ ከመጠቆም በፊት እኔስ እንዴት ነኝ?! ብሎ ማለት መልካም ነው::  የተሻለ እጸልያለሁ?  ቃሉን አነባለሁ? በጽድቅ እመላለሳለሁ?  ሌላም ሌላም?  ብዬ ጠይቄ ልቤ አበጥ ካለ ትልቅ ችግር አለ::  ይህንን ማድረግ የቻልኩት በእርሱ ጸጋ መሆኑ ካልገባኝ አወይ አወዳደቅ ከጸጋው ከኢየሱስ እጅ ወድቄአለሁና ማስተዋል ይሁንልኝ::  ይህንን ምሳሌ ሳስብ የሚመጣልኝ በመኪና  እሩቅ መንገድ ሄደን ልክ ስንደርስ እያለከለክን ያዙኝ ልቀቁኝ እንደማለት ነው::  ያደረሰን መኪናው እንጂ በእግራችን አልሮጥን የምን ማለክለክ ነው?!  እንዲሁ ክርስቶስ ተሸክሞን እየተመላለስን ደርሶ መኮፈስ አይሁንብን::  ጌታ ማስተዋልን ይስጠን::
ዕለት ዕለት የምንለማመደውና ብዙም የማናስተውለው ወጥመድ ነው የፉክክር ህይወት!   እራስን ከሌላው ማወዳደር ወይም በዙሪያችን ያሉትን ማወዳደር::  ስለበረቱት ወገኖች አመስግነን ስለደከሙት ደግሞ ሳንፈርድ መጸለይ ይሁንልን::  ማንም በራሱ አልቆመምና::  
ይህ ፈሪሳዊ በልቡ እግዚአብሔርንም አብሮ ከእርሱ ጋር ጥፋተኛ እያደረገ  እንደ ሌላ ሰው ሁሉ፥ ቀማኞችና ዓመፀኞች አመንዝሮችም፥ ወይም እንደዚህ ቀራጭ ስላልሆንሁ አመሰግንሃለሁ፤ እያለ በአመጹ ጌታን ይጨምርል እንዲሁም በጾሙና በአስራቱ ተመክቶ ተናገረ ጌታ ግን የሚለው ነፍስህን ምጽዋት አድርገህ ስጥ ነው::  በሌላ አባባል ምንም ለአንተ ከአንተነትህ አይቅርልህ ነው::  እራሱን ሚዛን ላይ አውጥቶ መዝኖ እበልጣለሁ ብሎ ሚዛኑን ገልብጦ አንብቦ ሄደ::  ሌላው ሚዛኑንም ለማየት ሳይደፍር አልቅሶ ጸድቆ ተመለሰ:: 
አባት ሆይ እራሴን በፈቃዴ መባ አድርጌ እጥላለሁ በእጅህ!  አሜን!

ሉቃስ 18: 15-17
17 እውነት እላችኋለሁ፥ የእግዚአብሔርን መንግሥት እንደ ሕፃን የማይቀበላት ሁሉ ከቶ አይገባባትም፡” አለ።
ህፃናትን ወደእኔ ይመጡ ዘንድ አትከልክሏቸው ብሎ ጋበዛቸው::  ህፃናት ህግ አያውቁም መቼ ማልቀስና መብላት እንዳለባቸውም ስለማያውቁ የሆነ ነገር ሲፈልጉ እረብሻለሁ ሰው ምን ይለኛል ሳይሉ ያለቅሳሉ:: በአጠቃላይ በዙሪያቸው ያለውን ቃኝተውና አገናዝበው አይደለም የሚኖሩት::  የተባሉትን ሁሉ ያምናሉ ያለ ጠባቂ ለጥቂት ደቂቃ ቢተው ችግር ውስጥ ይገባሉ:: ልጆች ይሉኝታ አያውቁም እንደመጣ ያወራሉ ያደርጋሉ::  እንደዚህ አይነት ደረጃ ላይ እንዳሉ ቢያውቅም አትከልክሏቸው ቢረብሹም ይምጡ ብሎ ተቀበላቸው::  ታድያ ለምን መንግስቱን እንደ ህፃን የማይቀበላት አይገባባትም አለን? 
ይህንን ጥያቄ በሁለት አቅጣጫ አየዋለሁ::  አንደኛ:- ሳንጠራጠር የምናምን  ሁለተኛው:- ያለ እርሱ ምንም ማድረግ የማንችል መሆናችንን እንወቅ::
የማንጠራጠር የምናምንና በእርሱ የምንደገፍ እንሁን:: 
ልክ እንደህፃናቱ እኛም ያለእረኛችን ለጥቂት ደቂቃ ብንተው ችግር ውስጥ እንገባለን::  ያለእርሱ እርዳታ ምንም ማድረግ አንችልም:: እራሳችንን እንደ ህፃናት ማየት አለብን!  አውቃለሁን ወደጎን አድርገን በእርሱ መታመን ይሁንልን::  በቃሉና በመንፈሱ እንድናድግ ይጠበቅብናል ::  እምነትና መደገፋችን ግን ያው መሆን አለበት::

ሉቃስ 18: 18-30
27 እርሱ ግን፡— “በሰው ዘንድ የማይቻል በእግዚአብሔር ዘንድ ይቻላል፡” አለ።
ቸር መምህር፥ የዘላለምን ሕይወት እንድወርስ ምን ላድርግ?” ብሎ አንድ ኃብታም ጠየቀው:: ጌታም ህጉን ነገረው ከመጀመርያው ህግ በቀር – አምላክህን በፍጹም ልብህ ውደድ የምትለውን አስቀርቶ ምክንያቱም ይህ ሰው ያለህን ሁሉ ሸጠህ ተከተለኝ ሲለው አልቻለም:: ሌላውን ግን  ከልጅነቱ ጀምሮ አድርጎት ነበር በአንዱ የጎደለ በሁሉ ወደቀ ነውና ይህ ሰው ወድቋል::  ጌታም ግመል በመርፌ ቀዳዳ ቢያልፍ ይቀላል ለኃብታም ወደ እግዚአብሔር መንግስት ከሚገባ ብሎ አለ:: ኃብታም መሆንን ሳይሆን የተቃወመው ገንዘብን እንደ አምላክ መቁጠርን ነው::
ሌሎችም ሰምተው ታድያ ማን ይድናል አሉ?  እዚህ ጋር ነው የእግዚአብሔር የማዳን ስራ የሚታየው ለሰው የማይቻል ለእግዚአብሔር ተችሏል::  አንድያ ልጁን ልኮ መዳንን ፈጽሞታልና በእርሱ በኩል መዳን ሆነልን::  ሐዋርያቱም ሁሉን ትተን ተከተልንህ አሉት –  እርሱም፡— “እውነት እላችኋለሁ፥ ስለ እግዚአብሔር መንግሥት ቤትን ወይም ወላጆችን ወይም ወንድሞችን ወይም ሚስትን ወይም ልጆችን የተወ፥ በዚህ ዘመን ብዙ እጥፍ በሚመጣውም ዓለም የዘላለምን ሕይወት የማይቀበል ማንም የለም” አላቸው:: የዘላለምን ህይወት ተቀብለናል! በዚህም ዓለም አይጎድልብንም::  አሜን!


ሉቃስ 18: 31-34
31 አሥራ ሁለቱንም ወደ እርሱ አቅርቦ እንዲህ አላቸው፡— “እነሆ፥ ወደ ኢየሩሳሌም እንወጣለን፥ ስለ ሰው ልጅም በነቢያት የተጻፈው ሁሉ ይፈጸማል። ለአሕዛብ አሳልፈው ይሰጡታልና፥ ይዘብቱበትማል ያንገላቱትማል ይተፉበትማል፤ ከገረፉትም በኋላ ይገድሉታል፥ በሦስተኛውም ቀን ይነሣል።”
በትንቢት የተነገረው ሁሉ ምንም ሳይቀር በእርሱ ላይ ተፈጸመ::  ምን አይነት ፍቅር ነው ለእኛ ያለው?!  ይህ ታላቅ ጌታ የሰማይና የምድር ፈጣሪ ሰውንም ከአፈር ሰርቶ እስትንፋሱን የጨመረበት ጌታ በፍጥረቱ እንደዚህ ተንገላታ ብሎም ተገደለ::  እርሱ ግን የሞትንና የሲኦልን ቁልፍ ተቀብሎ በሶስተኛው ቀን ከሙታን ተነሳ!!  ህያው አምላክ እናመልካለን!!  የሚታመኑበትም ሞት አይዛቸውም::
አባት ሆይ ይህንን ሁሉ የሆንክልኝ እኔ ከሲኦል  እንዳመልጥና ከአንተ ጋር ለዘላለም እንድኖር ብለህ  ነውና ተመስገን::  ሌሎችን ማስመለጥ ይሁንልኝ::ሉቃስ 18: 35-43
41 “ምን ላደርግልህ ትወዳለህ?” ብሎ ጠየቀው። እርሱም፡— “ጌታ ሆይ፥ አይ ዘንድ ነው፡” አለው።
በእያሪኮ መንገድ ላይ ተቀምጦ ይለምን የነበረው ሰው ግርግር ሲሰማ ምንድነው ብሎ ጠየቀ::  የተጠየቁትም “የናዝሬቱ ኢየሱስ ያልፋል፡” ብለው አወሩለት። ልብ እንበል ያሉት የናዝሬቱ ኢየሱስ ነው እርሱ ግን የጠራው፡— “የዳዊት ልጅ፥ ኢየሱስ ሆይ፥ ማረኝ፡” እያለ አብዝቶ ጮኸ ተው ቢሉትም አልሰማም::  ምን አይነት መገለጥ ነው?!  ሌላው እያጋፋ ነው ይህ ሰው ግን ተገልጦለት ነበረ:: አንተ ንጉስ ነህ ደግሞም ምህረትን የምትሰጥ አምላክም ነህ እያለው ነው::  እግዚአብሔር  ለዳዊት ቃል እንደገባለት:- በኢሳይያስ 9:6. ሕፃን ተወልዶልናልና፥ ወንድ ልጅም ተሰጥቶናልና፤ አለቅነትም በጫንቃው ላይ ይሆናል፤ . . . በዳዊት ዙፋንና በመንግሥቱ ላይ አለቅነቱ ይበዛል፥::  በራእይ 22:16 . . .  እኔ የዳዊት ሥርና ዘር ነኝ፥ የሚያበራም የንጋት ኮከብ ነኝ።”
ኢየሱስ ለዘላለም ንጉስ ነው ኃጥያትንም ይቅር የሚልና የሚፈውስ አምላክ ነው::  ይህ ሰው አይ ዘንድ ነው የምፈልገው ብሎ ሲለው ኢየሱስም፡— “እይ፤ እምነትህ አድኖሃል፡” አለው። ወድያውም አየ!  
ዛሬ ምንድነው የምትፈልጉት ቢለን ምንድነው የምንጠይቀው?  ጌታዬ ንጉሴና አምላኬ ሆይ:- ክብርህን መንፈስህን ሙላኝና ብዙዎች በመንፈሳዊ እውርነትና በብዙ እንቆቅልሽ  እየተመላለሱ ነውና በኃይልህ አስታጥቀህ የመከሩ ሰራተኛ አድርገህ ላከኝ ነው ልመናዬ:: ክብሩም በዚህ ውስጥ ለአንተ ይምጣ ምክንያቱም የተንገላታህ ዋጋን የከፈልክ በመስቀል የዋልከው አንተ ነህና!  የሚያስተውል ልብ ስጠኝ!

ሉቃስ 19: 1-10
10 የሰው ልጅ የጠፋውን ሊፈልግና ሊያድን መጥቶአለና።
ከአጭርነቱ የተነሳ በዛፍ ላይ ተንጠላጥሎ ጌታን ለማየት የተጠማውን ሰው ጌታ አይቶ በስሙ ጠራውና በቤትህ እውል ዘንድ ይገባኛልና ፈጥነህ  ውረድ አለው::  ዘኬዎስ ቀራጭ ብቻ ሳይሆን የቀራጮች አለቃና ባለ ጠጋም ነበረ።  በዛ ስፍራ የነበሩት ሰዎች ግን እንደተለመደው፡— “ከኃጢአተኛ ሰው ጋር ሊውል ገባ፡” ብለው አንጐራጐሩ። አወይ የዛሬውን የእኔን የአህዛብዋን መጎብኘትና በእኔ ውስጥ መኖር ቢያዩ ምን ይሉ ነበረ?! 
የዚህ ሰው ነገር የሚገርመው ጌታ ምንም ሳይለው “ጌታ ሆይ፥ ካለኝ ሁሉ እኵሌታውን ለድሆች እሰጣለሁ፤ ማንንም በሐሰት ከስሼ እንደ ሆንሁ አራት እጥፍ እመልሳለሁ፡” ብሎ አለ::  ያ ኃብታም ሰው ግን ህግን ሁሉ ጠብቄያለሁ ብሎ ሲመካ አንድ ነገር ቀርቶሃል ያለህን ለድሆች ስጥና ተከተለኝ ባለው ጊዜ ከበደው::  ኃብታም ወደ እግዚአብሔር መንግስት ከሚገባ ግመል በመርፌ ቀዳዳ ቢያልፍ ይቀላል ብሎት ነበረ::  እዚህ ስፍራ ላይ ግን “እርሱ ደግሞ የአብርሃም ልጅ ነውና ዛሬ ለዚህ ቤት መዳን ሆኖለታል ተባለለት::  ጉዳዩ ኃብታም ከመሆን ጋር የተያያዘ ሳይሆን የልብ ጉዳይ ነው:: ልዩነቱም ምንም ሳይባል ገንዘቡን እንደሚሰጥ ተናዘዘ::  ገንዘብ ጌታው አልነበረም ስለዚህ ጌታ ኃብት ከማፍራት ጋር ችግር የለበትም ከአያያዙ ጋር እንጂ!
አባት ሆይ በስሜ የምታውቀኝ ፈልገህ ያገኘኸኝ ጌታ አመሰግንሃለሁ::  የሰጠኸኝን ሁሉ እንዴት መጠቀም እንዳለብኝ እንዳስተውል እርዳኝ!  በዙሪያዬ ያሉትንም የተቸገሩትን ማሰብ ይሁንልኝ የገንዘብ ፍቅር ሳይሆን አንተን መውደድ ይብዛልኝ! አሜን! 

ሉቃስ 19: 11-27
26 ‘እላችኋለሁ፥ ላለው ሁሉ ይሰጠዋል፥ ከሌለው ግን ያው ያለው ስንኳ ይወሰድበታል።
ጌታ የጠፋውን ልፈልግ መጥቻለሁ አለ እነርሱም ይህን ሲሰሙ፥ ወደ ኢየሩሳሌም መቅረቡ ስለ ሆነ የእግዚአብሔርም መንግሥት ፈጥኖ ሊገለጥ እንዳለው ስለ መሰላቸው ጌታም የመንግስቱ መምጫ ገና መሆኑን በምሳሌ ተናገረ። ይህም ምሳሌ ስለ አንድ መኰንን ለራሱ መንግሥትን ይዞ ሊመለሰ ወደ ሩቅ አገር እንደሄደና ለአስር  (10) ባርያዎቹ አስር አስር ምናን እንደሰጣቸው ተናገረ::
መንግስትንም ይዞ ሲመለስ መጀመርያ ያስጠራው ባርያዎቹን ነው ከዛም በእርሱ በማያምኑት ላይ ፍርድን በየነ::  እነርሱም ሰርተው ያተረፉትን በፊቱ አቀረቡ ከአንዱ ባርያ በቀር::  ሁሉም እኩል አስር መክሊትን ተቀብለው ነበረ::  አንዱ አስር ሌላው ደግሞ አምስት አትርፈው ነበረ::  ጌታም እንደየስራቸው ሾማቸው እንጂ እርሱ አስር አትርፎ አንተ እንዴት አምስት አላለውም::  ምንም ሳይሰራ የመለሰውን ግን ምናኑን ውሰዱበትና አሥሩ ምናን ላለውም ስጡት፡ አላቸው። ለታመነና ለሚሰራ ይጨመራል::  ጌታ በሰጠን ጸጋ እናገልግል አንድ ቀን የታለ ትርፉ መባላችን አይቀርምና::
ሌላው ይህ ሰው ምንም እንኳን ያላተረፈ ቢሆንም ከመንግስቱ አልተባረረም::  መንግስቱን ግን ያልተቀበሉት ይታረዱ ብሎ በየነ:: ስንት የምንወዳቸው ሰዎች ስም ዝርዝር በዚህ ውስጥ ይሆን?  ዛሬ መዳን ወደ ቤተሰባችን ወደ ጏደኞቻችን አብረውን ወደሚሰሩት ወደ ጎረቤቶቻችን ይድረስ ጨለማቸውም በጌታ በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ይገፈፍ:: 

ሉቃስ 19: 28-44
38 “በጌታ ስም የሚመጣ ንጉሥ የተባረከ ነው፤ በሰማይ ሰላም በአርያምም ክብር፡” አሉ።
እዚህ ስፍራ ላይ የተከናወነው:-
1.  ወደ እየሩሳሌም ጉዞ – እራሱን ለመስጠት
2.  ሆስዕና – ወደ ደብረ ዘይት ቍልቍለትም አሁን በቀረበ ጊዜ፥ ደቀ መዛሙርቱ ሁላቸው ደስ እያላቸው ተአምራትን ሁሉ ስላዩ በታላቅ ድምፅ እግዚአብሔርን አመሰገኑ::  አንዳንዶች ግን ዝም አሰኛቸው አሉት እርሱ ግን፡— ‘እላችኋለሁ፥ እነዚህ ዝም ቢሉ ድንጋዮች ይጮኻሉ።’  እንደዚህ ሆኖ ንጉስዋ በትህትና እንደትንቢቱ ሲመጣ እየሩሳሌም ግን አላወቀችምና ለመቀበል ዝግጁ አልነበረችም:: አለማወቅዋም ዋጋ አስከፈላት::
3.  ጉብኝትዋን ባለማወቅዋ ለእየሩሳሌም ማልቀሱ::  ለምን አለቀሰ?  “ለሰላምሽ የሚሆነውን በዚህ ቀን አንቺስ ስንኳ ብታውቂ፤ አሁን ግን ከዓይንሽ ተሰውሮአል። ጠላቶችዋ ከበው እንደሚያፈርስዋት ተናገረ::  ይህ ደግሞ ስንት ጊዜ ሆነ?  አሁንም ተከበው ያሉ አይደሉም ዘመናቸው ሁሉ በጦርነት የተሞላ ነው::  በእግዚአብሔር ስም የሚመጣ የተባረከ ነው ብለው እስኪጠሩት ድረስ ነው ሲጣሩ ግን ሊዋጋላቸው ይወርዳል::
አባት ሆይ የጉብኝቴን ወራት ከዓይኔ ተሰውሮ ወይንም በቸልታ ሳይገባኝ እንዳላሳልፍ እርዳኝ::  አሜን!

ሉቃስ 19: 46-48
46 እርሱም፡— “ቤቴ የጸሎት ቤት ይሆናል ተብሎ ተጽፎአል፤ እናንተ ግን የወንበዴዎች ዋሻ አደረጋችሁት፡” አላቸው።
የጸሎት ቤት በአዲስ ኪዳን እኛ ነን ቤተ መቅደሶቹ::  ዛሬም የማይሆን ነገር ሲያይ በመንፈሱና በቃሉ ይገለብጣል ይነቅላል ያጠፋል::  በኤፌሶን 3: 16-18 በመንፈሱ በውስጥ ሰውነታችሁ በኃይል እንድትጠነክሩ ክርስቶስም በልባችሁ በእምነት እንዲኖር እንደ ክብሩ ባለ ጠግነት መጠን ይስጣችሁ፤ የእናንተ ሥርና መሠረት በፍቅር ይጸና ዘንድ፥ እንዲሁም የክርስቶስን ፍቅር ለማወቅ ትበረቱ ዘንድ፥ እስከ እግዚአብሔርም ፍጹም ሙላት ደርሳችሁ ትሞሉ ዘንድ እንደሚል ውስጣችን በኃይል ይጠንክር ፍቅርን ትህትናን የመንፈስ ፍሬን ሞልቶ ያጊጥለት::   የምናስበውን እንኳን ነግሮናልና ፍቅር ያለበትን ሰላም የሆነውን እርሱን የሚያገነውን እናስብ!  ቤቱ እንደሆንን የመንፈስ ቅዱስም መኖርያ እንደሆንን እያሰብን ጌታን እናመስግን::  በእኛ ውስጥ ሌላ አይኖርም ኮምፓተብል አይደለንም ለሌላ::  አንዴ በደሙ ለእርሱ ተቀድሰናልና እኛ የጌታ ነን! ሃሌሉያ!!!

ሉቃስ 20: 1-8
1 አንድ ቀንም ሕዝቡን በመቅደስ ሲያስተምር ወንጌልንም ሲሰብክላቸው . . .
ጌታ የሚያደርገው ወንጌልን ማስተማርና መስበክ ነው በዛ ውስጥም ፈውስን ያደርግ ነበር:: የካህናት አለቆችና ጻፎች ከሽማግሌዎች ጋር ወደ እርሱ ቀርበው ጥያቄ ጠየቁት ለመማር ሳይሆን ሊያጠምዱት ነበር:: እነዚህን በምን ሥልጣን ታደርጋለህ ወይስ ይህን ሥልጣን የሰጠህ ማን ነው?” ብለው ስልጣን ሰጪውን ማንም ምንም ሊሰጠው የማያስፈልገውን ንጉስ ጠየቁት::  አለማወቅ ሆኖባቸው በፊታቸው ያለውን ጌታ ማወቅ አልቻሉም::  እርሱም የዮሐንስ ጥምቀት ከሰማይ ነበረችን ወይስ ከሰው? ብሎ ጠየቃቸው በፊቱ እንዲሄድና ልብን እንዲያዘጋጅ የተላከውን ነብይ ሰምተው ቢሆን ኖሮ እንደዚህ ባልሆኑ ነበር ኃጥያተኞች ግን ሰምተው ተዘጋጅተው ሲጠብቁት እነዚህ ግንበኞች ናቁት:: አሁንም መልስን ሳያገኙ ቀሩ:- “እኔም በምን ሥልጣን እነዚህን እንዳደርግ አልነግራችሁም፡” አላቸው።
እዚህ ላይ ቆም ብዬ እንዳስብ ያደረገኝ ነገር ቢኖር ጌታ ከአመጣጣቸው ያውቅ ነበረናግን በትዕግስትና በትህትና ይጠይቅና ይመልስ ነበረ::  ይህ መረጃ ቢኖረኝ እኔ እንዴት ይሆን የማናግራቸው?  የምጀምረው አውቅሻለሁ እያንዳንድሽን ምን መክራችሁ እንደመጣችሁ ብዬ የራሴንም የጌታንም የህዝቡን ሁሉ ጊዜ አባክን ነበር::  ጸጋ የተሰጠን በጥበብ እንድናገለግልበት እንጂ አወኩሽ ናኩሽ እንዲሆን አይደለምና የተሰጠንን ጸጋ በአግባቡ እናገልግልበት:: እነዚህ ሰዎች በራሳቸው መልሳቸውን መልሰው ተመለሱ ማጥመድም አልቻሉም::  እርሱም ወደ ማስተማሩ ተመለሰ::  
አቤቱ ጌታዬ ሆይ ትህትናን ከአንተ ልማር በትዕግስትም በተሰጠኝ ጸጋ ስሜቴን ሳይሆን የልብህን አሳብና ፈቃድ ማገልገል ይሁንልኝ!  አሜን!

ሉቃስ 20: 9-19
17 እርሱ ግን ወደ እነርሱ ተመልክቶ እንዲህ አለ፡— “እንግዲህ፦ ‘ግንበኞች የናቁት ድንጋይ እርሱ የማዕዘን ራስ ሆነ፡’ ተብሎ የተጻፈው ይህ ምንድር ነው? 18 በዚያም ድንጋይ ላይ የሚወድቅ ሁሉ ይቀጠቀጣል፤ የሚወድቅበትን ሁሉ ግን ይፈጨዋል።”
ይህንም ምሳሌ ለሕዝቡ ይላቸው ጀመር፡— “አንድ ሰው የወይን አትክልት ተከለ፡ ለገበሬዎችም አከራይቶ ለብዙ ዘመን ወደ ሌላ አገር ሄደ። በዚህ ምሳሌ መሰረት ይህ ገበሬ እግዚአብሔር አብ ሲሆን ባርያዎች ተብለው የተላኩት ደግሞ ነብያት ናቸው ልጅየተባለውም ኢየሱስ ነው::  ጊዜው ሲደርስ ፍሬ ፍለጋ ባርያዎቹን ላከ እስራኤል ግን እግዚአብሔርን ከመስማት ይልቅ እነርሱን ማሰቃየትና መግደልን መረጠች:: 
የማዕዘን ራስ የሆነውን ልጁን አደራ የተሰጣቸው ገበሬዎች ናቁት:: ልጁንም ገደሉ ስለዚህ እግዚአብሔር ይመጣል፡ እነዚህንም ገበሬዎች ያጠፋል፥ የወይኑንም አትክልት ለሌሎች ይሰጣል።” ይህንም በሰሙ ጊዜ፡— “ይህስ አይሁን፡” አሉ። ነገር ግን ሆነ መንግስቱ በቤተክርስትያን ላይ ተመሰረተ ኢየሱስም  ከፍ አለ እርሱንም በቤተክርስትያን  ብቻ ሳይሆን በሚመጣውም መንግስት ላይ ራስ አድርጎ ሾመው::  እርሱን ለሚቃወሙ መጨረሻቸው መቀጥቀጥ ሲሆን (ምሳሌ ጳውሎስን ለምን ታሳድደኛለህ ለአንተ ይብስብሃል ነበር ያለው) የሚነሳበት መንግስት ደግሞ  ይፈጫል::  እግዚአብሔር ዙፋኑን  በሰማይ አዘጋጀ መንግስቱም ሁሉን ትገዛለች!  አሜን!

ሉቃስ 20: 20-40
37 ሙታን እንዲነሡ ግን ሙሴ ደግሞ በቍጥቋጦው ዘንድ ጌታን፡— ‘የአብርሃም አምላክ የይስሐቅም አምላክ የያዕቆብም አምላክ’ በማለቱ አስታወቀ፤ 38 ሁሉ ለእርሱ ሕያዋን ስለ ሆኑ፥ የሕያዋን አምላክ ነው እንጂ የሙታን አይደለም።”
የወይን ተክል ተክሎ አከራይቶ ስለሄደው ሰውና ተከራዮቹ ስላደረጉት ሲነግራቸው ስለእነርሱ መሆኑ ገብቷቸው እንዴት አድርገው ወደ ገዢ ግዛትና ሥልጣን አሳልፈው እንዲሰጡት ጻድቃን መስለው በቃሉ የሚያጠምዱትን ሸማቂዎች ሰደዱበት።  ይህ ሞኝነት ይገርማል ከማን ጋር እንደሆነ የሚወዳደሩት አላወቁም ሁሉን የሚያውቅ ጌታ::  እርሱም ምንም እንኳን ቢያውቅም አልገለጣቸውም ጥያቄያቸውን መለሰላቸው::  ይህ ትህትናና ትዕግስት ለኔም ይሁንልኝ ጌታዬ!
ስለግብር ጠየቁት የቄሳርን ለቄሳር አላቸው::  ሌሎቹ ደግሞ ስለአንዲት ሴት አለመውለድና ወንድማማቾች አገብዋት ሳይወልዱ ሞቱ የማን ሚስት ልትሆን ነው በሰማይ? ብለው ግራ ሊያጋቡት ሞከሩ::  ምናልባት በሰው መካከል ይህ ጥያቄ ፐ የተባለለትና ዋናው ማንም ያልመለሰው ሊሆን ይችላል ወይም ከባዱ ጥያቄ ተብሎም የሚፈራ ሊሆን ይችላል የጠየቁት::  ያለ እውቀት የሆነ ጥያቄ ተብሎ የሚመደብ ቢሆንም ይህንንም መለሰ::  አምላካችን ህያው ብቻ ሳይሆን የህያዋንም አምላክ ነው::  እንዴት ከሞት በኃላ ህይወት የለም ይላሉ?! በክርስቶስ ስለተዋጀነው ጌታ እንዳለው ሊሞቱም ወደ ፊት አይቻላቸውም፥ የትንሣኤም ልጆች ስለ ሆኑ የእግዚአብሔር ልጆች ናቸው አለ!  ሃሌሉያ እኔ የትንሳኤ ልጅ ነኝ!  የእግዚአብሔርም ልጅ!  አሜን! 

ሉቃስ 20: 41-47
42—43 ዳዊትም ራሱ በመዝሙራት መጽሐፍ እንዲህ ይላል፦ ‘ጌታ ጌታዬን፡— ጠላቶችህን ለእግርህ መርገጫ እስካደርግልህ ድረስ በቀኜ ተቀመጥ፡’ አለው።
ምዕራፉ የጀመረው እስኪ ንገረን፤ እነዚህን በምን ሥልጣን ታደርጋለህ ወይስ ይህን ሥልጣን የሰጠህ ማን ነው?”  ብለው ነበረ::  እርሱም ስልጣኑን ማን እንደሰጠው ከመመለሱ በፊት ጥያቄውን በጥያቄ መለሰና ስለ መጥምቁ ዮሃንስ አገልግሎት ጠየቀ እነሱም አናውቅም አሉት እርሱም የኔንም አልነግራችሁም አላቸው::  ለጥያቄአቸው ዮሃንስ ቁልፉ ነበረ ምክንያቱም የሚመጣ አለ ተዘጋጁ እያለ ነበረና እነርሱ ግን ሁሉንን እናውቃለን ብለው አልሰሙትም::
በምን ስልጣን ነው? ለሚለው ጥያቄ መልስ እየሰጠ ይመስላል በዚህ ክፍል ላይ:- ዮሃንስን አልሰማችሁም እስኪ ዳዊትን ስሙት እርሱ ጌታ ብሎ ነው የሚጠራኝ እያላቸው ነበረ::  የዳዊት ልጅ ተብሎ ተጠርቶ ያውቃል ትውልዱም ሲቆጠር ዳዊት ይገኝበታል::  ነገር ግን የዳዊት ልጅ ብቻ ሳይሆን የእግዚአብሔር ልጅም ነው::  እርሱ አልፋና ኦሜጋ መጀመርያና መጨረሻ የሆነ ጌታ ነው::
ሐዋርያቱን ከነዚህ ከጻፎች ተጠንቀቁ አላቸው ምክንያቱም ሁሉን የሚያደርጉት ለራሳቸው ክብር እንጂ ለእርሱ ክብር አይደለምና ደሃንም ይበዘብዛሉ::  ስለዚህም የባሰ ፍርድ ይቀበላሉ አለ::  አልገባቸውም እንጂ ይግባኝ የሌለው ፍርድ  እዛው ጋር ባሉበት ተፈርዶባቸዋል ::  
አባት ሆይ አንተን አውቃለሁ እያልኩኝ ለራሴ እንዳልኖር በህይወቴ ሁሉ አንተው ክበርልኝ! ጸጋህ ይብዛልኝ:  በመንፈስህም ሙላኝ! አሜን!ሉቃስ 21: 1-4
3 እንዲህ አለ፡— “እውነት እላችኋለሁ፥ ይህች ድሀ መበለት ከሁሉ ይልቅ አብልጣ ጣለች፤ 4 እነዚህ ሁሉ ከትርፋቸው ወደ እግዚአብሔር መዝገብ ጥለዋልና፤ ይህች ግን ከጕድለትዋ የነበራትን ትዳርዋን ሁሉ ጣለች።”
ጌታ ያየው ባለጠጎችና ደሃዋ ሴት  መባን ሲሰጡ ልዮነቱን ነው::  እርሱ የሚያየው ስንት እንደቀረ እንጂ ስንት እንደሰጡ አለመሆኑ ገርሞኛል::  ስለእኔ ብሎ ሁሉን የማይተው የእኔ ሊሆን አይገባውም እንዳለ በልግስና ያለንን ሳንሰስት መስጠት ይሁንልን::  እኛም ያለንም ገንዘባችን ሁሉ የእርሱ ነውና::
አቤቱ እርዳኝ!  


ሉቃስ 21: 5-38
36 እንግዲህ ሊመጣ ካለው ከዚህ ሁሉ ለማምለጥ፥ በሰው ልጅም ፊት ለመቆም እንድትችሉ ስትጸልዩ ሁል ጊዜ ትጉ።”
ስለመጨረሻው ዘመንና ስለመምጣቱ በዚህ ክፍል ላይ ይናገራል::   ጦርንና ሁከትንም በሰማችሁ ጊዜ አትደንግጡ፤ ይህ አስቀድሞ ይሆን ዘንድ ግድ ነውና፥ ነገር ግን መጨረሻው ወዲያው አይሆንም። ሕዝብ በሕዝብ ላይ፥ መንግሥትም በመንግሥት ላይ ይነሣል፤ ታላቅም የምድር መናወጥና በልዩ ልዩ ስፍራ ቸነፈር ራብም ይሆናል፤ የሚያስፈራም ነገር ከሰማይም ታላቅ ምልክት ይሆናል:: ኢየሩሳሌም ግን በጭፍራ ተከባ ስታዩ በዚያን ጊዜ ጥፋትዋ እንደ ቀረበ እወቁ። የጌታም መምጣት  በምድር ሁሉ ላይ በሚቀመጡ ሁሉ እንደ ወጥመድ ይደርስባቸዋልና::
የጌታ ጥያቄ ስመጣ እምነትን አገኝ ይሆንን? ነው ምክንያቱም የዓለም ነገር እንደምናየው አድካሚ ነውና ልባችሁ በመጠጥ ብዛትና በስካር ስለ ትዳርም በማሰብ እንዳይከብድ፥ ያ ቀንም በድንገት እንዳይመጣባችሁ ለራሳችሁ ተጠንቀቁ ተብለናልና:: የተዘረዘረው ሁሉ መሆን ሲጀምር ቤዛችሁ ቀርቦአልና አሻቅባችሁ ራሳችሁን አንሱ እንዲሁም ስትጸልዩ ሁል ጊዜ ትጉ ተብለናል::  በጸጋ ተሞልተን በፊቱ እየተጋን እንጠብቀው:: መሰባሰባችንና መፈላለጋችንን እናብዛ:: 
ሰማይና ምድር ያልፋሉ ቃሌ ግን አያልፍም ብሎናል!  አባት ሆይ እርዳን ተግተን ሌላውን የምናተጋ እንድንሆን::

ሉቃስ 22: 1-13
13 ሄደውም እንዳላቸው አገኙና ፋሲካን አሰናዱ።
ይህ በምድር የመጨረሻው ፋሲካ ነው ምክንያቱም ሰይጣን በይሁዳ ውስጥ አሳልፎ ለመስጠት አሳብን አገባበት ከዛም እርሱ እራሱ ገባበት ይላል::  ዮሃንስንና ጴጥሮስን የፋሲካን በዓል እንዲያዘጋጁ  ላካቸው::  ጌታ በስራ ላይ ነው ጠላትም ለማጥፋት እየተጋ ነው::  ጌታ ህይወቱን ሊሰጥ የሰውን ልጅ ሁሉ ሊታደግ ተዘጋጅቷል ሰይጣን ደግሞ ሊከስርና የያዘውን ሁሉ ሊለቅ ሰዓቱ ደርሷል::  ሰይጣን ውድቀቱ እየቀረበ መምጣቱን አላወቀ እርሱው ባዘጋጀው ወጥመድ እራሱ ተረታ::  ጌታስ ለዚህ መቷል ዱብ እዳ አይደለም እየሆነ ያለው የመጣው እኛን ለመታደግ ህይወቱንም ለመስጠት ነውና! 
ሲልካቸው እንዳላቸው አዳራሹ ተዘጋጅቶ አገኙት::  የላካቸው በተዘጋጀ ነገር ላይ ነው::  እርሱ ነገሮችን አቀነባብሮ የተደነቅንባቸውን ጊዜያት አስቡና ጌታን ባርኩ::  ዛሬም ነገሮችን ያቀናብራል አሁንም በስራ ላይ ነው:: 
አባት ሆይ እጅህን አይቻለሁ በዘመኔ ስለዚህም አመሰግንሃለሁ:: 


ሉቃስ 22: 14-23
15 እርሱም እንዲህ አላቸው፡— “ከመከራዬ በፊት ከእናንተ ጋር ይህን ፋሲካ ልበላ እጅግ እመኝ ነበር፤16 እላችኋለሁና፥ በእግዚአብሔር መንግሥት እስኪፈጸም ድረስ፥ ወደ ፊት ከዚህ አልበላም።”
ጌታ ይህንን ሲናገር የመጣበትን የማዳን ስራ በመስቀል ለመፈጸም የቀረው ወደ 24 ሰዓት ያህል ነበር::  በእግዚአብሔር መንግሥት እስኪፈጸም ድረስ፥ ወደ ፊት ከዚህ አልበላም እንዳለውም በምድር ላይ ሳለ ይህ የመጨረሻው መአድ ነበረ::
ከመከራዬ በፊት ከእናንተ ጋር ይህን ፋሲካ ልበላ እጅግ እመኝ ነበር የሚለው ገርሞኛል::  ተላልፎ ለመሰጠት ሰዓታት ነው የሚቀሩት የሚጠብቀውንም መከራ ጠንቅቆ ያውቀዋል ከእኔ ትለፍ ብሎ እስኪል ድረስ ግን ደግሞ ይህን ፋሲካ ልበላ እጅግ እመኝ ነበር ይላል::  እዚህ ክፍል ላይ እንደምናየው:-እንጀራንም አንሥቶ አመሰገነ ቆርሶም ሰጣቸውና፡— “ስለ እናንተ የሚሰጠው ሥጋዬ ይህ ነው፤ ይህን ለመታሰቢያዬ አድርጉት፡” አለ። እንዲሁም ከእራት በኋላ ጽዋውን አንሥቶ እንዲህ አለ፡— “ይህ ጽዋ ስለ እናንተ በሚፈሰው በደሜ የሚሆን አዲስ ኪዳን ነው። አሜን! 
በደሙ አዲስ ኪዳን ሆነ! የመጣበትን ትልቁ ዓላማ ይሄውም ሰውን መታደጉን አወጀው ለሰው ልጅ መፈታት ደሙን እንደሚያፈስ ይህ ንጹ የእግዚአብሔር በግ አወጀ! ከዚህ በኃላ ይህ በዓል በምሳሌነት አይከበርም በእርግጥም ፋሲካ ሆነ! ሞትና ሲኦል ተዋጡ!  እየሱስ ከበረ!  ምርኮንም ተካፈለ!  የሰይጣን መንግስት ተሸነፈ ከዚህ ድል በኃላ በክርስቶስ ያሉትን መያዝ አይችልም! በክርስቶስ የህይወት መንፈስ ህግ በእኛ ይሰራልና እኛም አብረን ሞተን ከእርሱ ጋር ተነስተናል!!  ፋሲካችን ኢየሱስ ክበር ተመስገን!  የሞቱና የትንሳኤው ምስክር ነኝ !  አሜን!!!!


ሉቃስ 22: 24-30
26 እናንተ ግን እንዲህ አትሁኑ፤ ነገር ግን ከእናንተ ታላቅ የሆነ በመካከላችሁ እንደ ታናሽ፥ የሚገዛም እንደሚያገለግል ይሁን።
ተላልፎ ስለመሰጠቱ ደሙን ስለማፍሰሱ እየተነገራቸው እነርሱ ግን ማን እንደሚበልጥ ክርክር ላይ ናቸው:: እግር አጥቦም ቢያሳያቸው በፍቅራችሁ ታወቁ ቢላቸውም እነርሱ ግን እንደአህዛብ የገዢና ተገዢ ስርአት ላይ ነበር ልባቸው መንግስትን ለእስራኤል መልሶ እነርሱም ምን አይነት ስልጣን እንደሚይዙ ነበር የሚያስቡት:: መቼም በእነርሱ መፍረድ ይቀላል::  እኛስ? 
በእግዚአብሔር መንግስት ታላቅ የሆነ እንደ ኢየሱስ ዝቅ ብሎ ያገልግል::  ኢየሱስ እንዳለው እኔ ግን በመካከላችሁ እንደሚያገለግል ነኝ አላቸው። ጸጋውን እንጠይቅ!
አባት ሆይ ዝቅ ብዬ በቤትህ የማገለግልበትን የአንተን  አይነት ልብና ጸጋ ስጠኝ!  አሜን!

ሉቃስ 22: 31-38

31 ጌታም አለ፡— “ስምዖን ስምዖን ሆይ፥ እነሆ፥ ሰይጣን እንደ ስንዴ ሊያበጥራችሁ ለመነ፤ 32 እኔ ግን እምነትህ እንዳይጠፋ ስለ አንተ አማለድሁ፤ አንተም በተመለስህ ጊዜ ወንድሞችህን አጽና።”

ጌታ ኢየሱስ ስለነ ጴጥሮስ ማለደ ምክንያቱም ወደ ፈተና እንዳትገቡ ትጉና ጸልዮ ቢላቸውም እነርሱ ግን እንቅልፍ ከብዶባቸው ነበረ:: ጌታም ነግሬአችኃለሁ ብሎ አልተወውም ሊቀ ካህንነቱን ተወጣ:: ዛሬም በአብ ፊት ስለእኛ የሚማልድ ሊቀ ካህን አለን!! ስምህ ይባረክ ጌታዬ ጥሎ ማለፍ በአንተ ዘንድ ስለሌለ::

የጌታ ምልጃ የተሰማ እስከማይመስል ጠላት ሊያበጥር ሲመጣ ምንም እንኳን ጴጥሮስ የተነገረው ቢሆንም ሶስት ጊዜ ካደ:: የጊዜውን ነገር መመርመርና ማወቅ ይሁንልን:: ጌታ ሰይፍ አያስፈልገውም ነገር ግን ከአመጸኞች ጋር ይቆጠር ዘንድ ሊይዙት ሲመጡ የሚገዳደሩበትን ሁለት ሰይፍ አዘጋጅተው ነበር:: ከሰማይ ሰማያት የመጣለት እራሱን የመሰዋት ዓላማ አልተለወጠም ግን ትንቢት ይፈጸም ዘንድ ይህ ሆነ::

ስለእኛ የሚያስብ ዓይኑን ከእኛ ላይ የማይነቅል እኛን ይዞ በአብ ፊት የሚታይ ሊቀ ካህናት አለን:: ለምርጦቹ የሚራራና የሚታገስ ጌታ ስሙ ይባረክ!!

Published by Betty & Abera

We’re dedicated to share God’s goodness and mercy through His word!

Leave a comment