መግቢያ
የዮሐንስ ወንጌል ከሌሎቹ ወንጌሎች ለየት ይላል:: መለየቱም በጣም መንፈሳዊ ነው ማለትም አዲስ ኪዳናዊነቱ በጣም የጎላና የመንፈስ ቅዱስ እርዳታና መገለጥ ያለበት ጥልቅ እይታ ያለው ነው:: አንዳንዶች ስለዚህ ክፍል ሲናገሩ ሌሎቹን አንብቦ የጎደለውን ለመሙላት የተፃፈ ነው ይላሉ:: ከተደረጉት ተአምራት ሰባቱን ብቻ ነው የፃፈልን:: ሌሎቹ የተደረጉትን ነገሮች እንደሪፖርት ሲጽፉ እሱ ግን በእየሱስ አምላክነትና ሰው መሆንን ሊያሳየን ፃፈ:: የፍቅር ሰው ነው ምክንያቱም እራሱን ጌታ የሚወደው እያለ ይጠራል በሌሎቹ ወንጌላት አናገኘውም ይህም አልበቃውም በሌሎቹ መልእክቶቹም ፍቅርን በደንብ ገልጾ ጽፎልናል:: ስለእየሱስ አምላክነት ሲጽፍ ከስጋ ከትውልዱ አይደለም የጀመረው ከእግዚአብሔርነቱ ቃል እንደነበረ ቃልም በእግዚአብሔር ዘንድ እንደነበረና ቃልም እግዚአብሔር እንደሆነ ይነግረናል:: ስለእየሱስ ሰው መሆን ደግሞ በተለያየ ታሪክ ውስጥ እናገኘዋለን:: ሳምራይቱን ሴት ሲያገኝ በምዕራፍ 4 ላይ ደክሞት እንደነበረ፤ ለአላዛር እንዳዘነና እንዳለቀሰ እንዲሁም በቤተመቅደስ ውስጥ ሲነግዱ ባገኛቸው ሰዎች እንደተናደደና ዱላ እንዳነሳም አሳይቶናል:: ጌታ ይረዳንና ይህንን ክፍል እናጠናለን::
ጸሎት:-አባት ሆይ አስተምረን ቃልህን በልባችን አትመው ውሃ የሌለው ደመና አይሁን ወደ ልባችን ወርዶ ያረስርሰን:: አሜን!
ዮሐንስ 1: 1-21፤
በመጀመሪያው ቃል ነበረ፥ ቃልም በእግዚአብሔር ዘንድ ነበረ፥ ቃልም እግዚአብሔር ነበረ።2፤ ይህ በመጀመሪያው በእግዚአብሔር ዘንድ ነበረ።
ዮሃንስ የሚጀምረው ከዘፍ 1:1 ነው:: በመጀመሪያ እግዚአብሔር ሰማይንና ምድርን ፈጠረ። ይህም ማለት የምጽፈውን ለመረዳት አዳም ጋር ወይም አብረሃም ጋር አይደለም የምጀምረው (የተቀሩት ወንጌላት ያንን አሳይተዋልና) ከዛ በፊት ምንም ፍጥረት ሳይኖር ዓለም ሳትሰራ መኖርያም ሳትሆን ማለቱ ነው:: ወንጌልን ሲጽፉ ሶስት ዓመት ሙሉ ከሰራውና ከኖረው መርጠው ነው የፃፉት ሁሉ ቢፃፍ እንደማይቻልም ነግሮናል ዮሃንስ:: ከፍጥረት መጀመሪያ በፊት ይህ ቃል የተባለው በእግዚአብሔር ዘንድ ነበረ:: በፍጥረት አፈጣጠር ጥያቄ ካለ ይህም ቃል ተብሎ እየተጠራ ያለው ወልድ ተጠያቂ ነው:: ምክንያቱም ከእግዚአብሔር ጋር አብሮ ነበረና:: ይህም ቃል እራሱ እግዚአብሔር ነው ይለናል:: እኔን ያየ አብን አየ ብሎ የለም ጌታ እየሱስ:: በእቅፉ ያለ አንድያ ልጁ ተረከው እንደሚል አብሮ ስለነበረ መተረክ ይችላል ማሳየትና መናገርም ይችላል:: ሌላው አብርሃም ቀኔን ሊያይ ተመኘም ብሎ ነበር – አብርሃም ወንጌል ተሰብኮለታል በራሱ በጌታ:: እርሱ የነበረና ያለ ነው:: የእየሱስን ፍጥረት አለመሆንና ፈጣሪ መሆኑን የሚያሳይ ነው:: አልፋና ኦሜጋ! ሃሌሉያ!
ዮሐንስ 1: 3-53፤ ሁሉ በእርሱ ሆነ፥ ከሆነውም አንዳች ስንኳ ያለ እርሱ አልሆነም።4፤ በእርሱ ሕይወት ነበረች፥ ሕይወትም የሰው ብርሃን ነበረች።5፤ ብርሃንም በጨለማ ይበራል፥ ጨለማም አላሸነፈውም።
ይህ የሁሉ መገኛ የሆነው ጌታ ሁሉን አደረገ ሁሉን ፈጠረ:: ምንም ነገር ያለ እርሱ የሆነ የለም የፍጥረት ሁሉ መገኛ ነው እርሱ:: አምላክ መሆኑን ይገልፃል::ይህንን የህይወት ራስ ነው የሰው ልጅ አንገላቶ የሰቀለው እርሱም እንዳለ ነፍሴን በፈቃዴ አኖራታለሁ አለ:: አለበለዚያ ማንም ህይወትን ከእርሱ መንጠቅ አይችልም:: ወዶ ስለእኛ ዋጋ ከፈለ:: በጨለማችን ላይ ብርሃን ይብራ ያለ እርሱ ነው:: ጨለማውን አስወግዶ በብርሃን ተካው:: ጨለማም ብርሃንን አላሸነፈውም:: ለዘላለምም አያቨንፈውምም:: ዮሃንስ በእርሱ ህይወት ነበረች ሲለን የሚያወራው እስከሞት ያለውን በስጋ መኖርን አይደለም:: ስለዘላለም ህይወት ስለማይቋረጠው ህይወት ነው:: ይህ ህይወት የሆነው ጌታ በእኛ ውስጥ እየኖረ ነው ይህ ህይወት ደግሞ አይቋረጥም ለዘላለም ያኖረናል::
አባት ሆይ: አንተ የህይወት ምንጭ ነህ ይህንን ህይወት ስለሰጠኸኝ አመሰግንሃለሁ ማንም ከእጅህ መዳፍ አይነጥቀኝም ለዘላለም ልጅ ብለህ ተቀበልከኝ እኔም አባ ተመስገን እላለሁ::
ዮሐንስ 1: 6-10
6፤ ከእግዚአብሔር የተላከ ስሙ ዮሐንስ የሚባል አንድ ሰው ነበረ፤7፤ ሁሉ በእርሱ በኩል እንዲያምኑ ይህ ስለ ብርሃን ይመሰክር ዘንድ ለምስክር መጣ።8፤ ስለ ብርሃን ሊመሰክር መጣ እንጂ፥ እርሱ ብርሃን አልነበረም።9፤ ለሰው ሁሉ የሚያበራው እውነተኛው ብርሃን ወደ ዓለም ይመጣ ነበር።10፤ በዓለም ነበረ፥ ዓለሙም በእርሱ ሆነ፥ ዓለሙም አላወቀውም።
መጥምቁ ዮሃንስ ማን ይሆን የተባለ ህፃን ከውልደቱ ጀምሮ የሚጠብቁት አኗኗሩ በምድረ በዳ፤ ልብሱ ለምድ፤ ነገሩ ሁሉ ለየት ያለ ነበረ:: ድንገት መቶ ጥምቀት ማጥመቅ ሲጀምር ብዙዎች መጡ ለንስሃ:: ጥምቀት ብሉይ ኪዳናዊ ባይሆንም እንኳን ሰው ንስሃ እየገባ ለሚመጣው መሲህ ለመዘጋጀት እየተጠመቀ ነበረ:: እርሱንም ማነህ ሲባል እኔ እርሱ አይደለሁም ብሎ ስለ ብርሃን ይመሰክር ነበር:: እንደጌታ ደቀ መዛሙርት ስለነበሩት አንድ እንዳይመስሏችሁ ነው የወንጌሉ መልክት:: ይህ ጠቋሚ ነው ሊመጣ ያለው ግን ለሰው ሁሉ የሚያበራው እውነተኛው ብርሃንና በግ መሲሁ እየሱስ ነው። አሜን መጥምቁ ዮሃንስ በእግዚአብሔር የተላከ ሰው ነበረ:: ስራውም ይህንን ብርሃንና ህይወት የሆነውን ጌታ ሰዎች ያምኑ ዘንድ እንዲጠቁም እንጂ እርሱ አዳኝ አልነበረም:: ዛሬም እኛ ከእግዚአብሔር ጋር ታረቁ የሚል አገልግሎት ተሰቶናል ወደዚህ ህይወት ወደሆነው ጌታ እንድንጠቁም::
አባት ሆይ እራስህን ገልጠህልኝ አንተን አውቄ በቤትህ ተክለኸኛልና ተመስገን:: ሌሎችን ከአንተ ጋር የማስታረቅንም ጸጋ ስለሰጠኸኝ ተመስገን ሰዎች ስነግራቸው አንተን ማወቅ ይሁንላቸው:: አሜን!
ዮሐንስ 1: 11-13
11፤ የእርሱ ወደ ሆነው መጣ፥ የገዛ ወገኖቹም አልተቀበሉትም።12፤ ለተቀበሉት ሁሉ ግን፥ በስሙ ለሚያምኑት ለእነርሱ የእግዚአብሔር ልጆች ይሆኑ ዘንድ ሥልጣንን ሰጣቸው፤13፤ እነርሱም ከእግዚአብሔር ተወለዱ እንጂ ከደም ወይም ከሥጋ ፈቃድ ወይም ከወንድ ፈቃድ አልተወለዱም።
ጌታ ዋጋ ለመክፈል መምጣት ነበረበት ከአብርሃምም በቀር የታዘዘ አልነበረምና ለአዳም እንደገባው ቃል ወደ ሰው ልጅ ሁሉ በእስራኤል በኩል መጣ:: የፈጠረውና እንዲኖር ያደረገው ይህንን ዓለም እርሱ ሆኖ ሳለ ሲመጣ ግን ማንም አላወቀውም:: የሰው ልጅ ፈጣሪውን አለማወቁ ደግሞ አለመቀበልን አስከተለ:: ባወቁትስ ኖሮ የህይወትን ራስ ባልገደሉት ነበረ እንደሚል ነው ቃሉ:: እርሱ ግን ለመሞት ቆርጦ መጣ:: ልጅነት በመቀበል የሚገኝ እንጂ ለሁሉ እንደራሽን የሚታደል አይደለም:: እርሱን ማወቅ የእግዚአብሔር ልጅ እንደሆነና ከዛም ጌታዬ ነህ ስንለው ልጅነትን እናገኛለን:: ሌላ ነገር አድርጉም አልተባልንም:: ስለዚህም ከእግዚአብሔር ተወለዱ እንጂ ከደም ወይም ከሥጋ ፈቃድ ወይም ከወንድ ፈቃድ አልተወለዱም።
አሜን
አባት ሆይ እንዳውቅህ ስለረዳኸኝ አመሰግንሃለሁ:: ከአንተ ተወልጃለሁኝ ይህንን ልጅነት ማንም አይነጥቀኝም:: ተመስገን!
ዮሐንስ 1: 14-18
14፤ ቃልም ሥጋ ሆነ፤ ጸጋንና እውነትንም ተመልቶ በእኛ አደረ፥ አንድ ልጅም ከአባቱ ዘንድ እንዳለው ክብር የሆነው ክብሩን አየን።15፤ ዮሐንስ ስለ እርሱ መሰከረ እንዲህም ብሎ ጮኸ፦ “ ‘ከእኔ በኋላ የሚመጣው እርሱ ከእኔ በፊት ነበረና ከእኔ ይልቅ የከበረ ሆኖአል፤’ ስለ እርሱ ያልሁት ይህ ነበረ።”16፤ እኛ ሁላችን ከሙላቱ ተቀብለን በጸጋ ላይ ጸጋ ተሰጥቶናልና፤ 17፤ ሕግ በሙሴ ተሰጥቶ ነበርና ጸጋና እውነት ግን በኢየሱስ ክርስቶስ ሆነ።18፤ መቼም ቢሆን እግዚአብሔርን ያየው አንድ ስንኳ የለም፤ በአባቱ እቅፍ ያለ አንድ ልጁ እርሱ ተረከው።
ይህ ቃል እግዚአብሔር ነው የተባልነው ቃል ያለ እርሱ ምንም አልሆነው የተባለው ቃል ምን ሆነ ይለናል? በእኛ መካከል እደረ ወይም ተወለደ ስጋን ለብሶ መጣ:: ሲመጣ ደግሞ ጸጋንና እውነትን ተሞልቶ ነው ምክንያቱም እርሱን አይቶ በህይወት የሚኖር የለምና – ጸጋ ተሞልቶ እውነትንም ሳይጥል አብሮ ይዞ መጣ:: የእርሱ ፍርድ ጽድቅና እውነት ነው አልተዛነፈም ሊያመቻምችም አልመጣም የሐጥያት ደሞዙ ሞት ነው:: እንድንኖር ጸጋን ሰጠን ይህ ቅዱስ ጌታ:: ዮሃንስ ግን መሰከረ ከእኔ በኋላ የሚመጣው እርሱ ከእኔ በፊት ነበረና ከእኔ ይልቅ የከበረ ሆኖአል፤’ ስለ እርሱ ያልሁት ይህ ነበረ።” ዋዉ እርሱ ትልቅ ነው ከሁሉ የከበረ:: እኛ ሁላችን ከሙላቱ ተቀብለን በጸጋ ላይ ጸጋ ተሰጥቶናልና፤ በጸጋ ላይ ጸጋ እንጂ እንደገና በሙሴ የተሰጠውን ህግ አይደለም ይዞልን የመጣው:: እግዚአብሔር ለእኛ ያለውን ፍቅር በዚህ አሳየ ጸጋን ሰቶ እውነትንም ሳያዛንፍ ዋጋ ከፍሎ አዳነን:: አሜን! ስለዚህም እየሱስ ጸጋንና እውነትን ተሞልቶ መቶ የአባቱን ማንነት አሳየን:: መቼም ቢሆን እግዚአብሔርን ያየው አንድ ስንኳ የለም፤ በአባቱ እቅፍ ያለ አንድ ልጁ እርሱ ተረከው። አሜን
አባት ሆይ ተመስገን ከሙላትህ ስለሞላኸን ዛሬም በጸጋ ላይ ጸጋ ስለሰጠኸን ክበር:: በእኔ ዛሬ ማንነትህ ሰውን መውደድህ ይታይ:: አሜን
ዮሐንስ 1: 19-28
19፤ አይሁድም፦ “አንተ ማን ነህ?” ብለው ይጠይቁት ዘንድ ከኢየሩሳሌም ካህናትንና ሌዋውያንን በላኩበት ጊዜ፥ የዮሐንስ ምስክርነት ይህ ነው።20፤ መሰከረም አልካደምም፤ “እኔ ክርስቶስ አይደለሁም” ብሎ መሰከረ።21፤ “እንኪያስ ማን ነህ? ኤልያስ ነህን?” ብለው ጠየቁት። “አይደለሁም፡” አለ። “ነቢዩ ነህን?” “አይደለሁም፡” ብሎ መለሰ።22፤ “እንኪያስ፦ ማን ነህ? ለላኩን መልስ እንድንሰጥ፤ ስለራስህ ምን ትላለህ?” አሉት።23፤ እርሱም፦ “ነቢዩ ኢሳይያስ እንዳለ፦ ‘የጌታን መንገድ አቅኑ፡ ብሎ በምድረ በዳ የሚጮኽ ሰው ድምፅ፡’ እኔ ነኝ፡” አለ።
አይሁድ የዮሐንስ ዝና ስለወጣ ማንነቱን ለማጣራት መልክተኞችን ላኩ:: የተላኩትም ካህናትንና ሌዋውያን ነበሩ ላኪዎቹም አይሁድ ናቸው:: ማነህ ነው? ብለው ሶስት ምርጫ ነው ይዘው የመጡት:- መሲህ ፤ ኤልያስ ወይስ ነብዮ ነበር ጥያቄው:: ሌዋዉያን የተላኩት የህጉን ክፍል ጠንቅቀው ስለሚያውቁም ይሆናል:: መጽሐፍት ትመረምራላችሁ እነርሱም ስለእኔ ይናገራሉ ግን ትስታላችሁ እንዳለ ጌታ እንደዛው ሆነባቸው:: ያልጠቀሱት ወይም ቸል ያሉት እውነት ቢኖር የጌታን መንገድ አቅኑ፡ ብሎ በምድረ በዳ የሚጮኽ ሰው ድምፅ፡ ነበረ ዮሃንስ:: መሲህ ከመገለጡ በፊት ኤልያስ ይመጣል ብለው ይጠባበቁ ነበር:: ነገር ግን ኤልያስን ኤልያስ ያደረገው መንፈስ በዮሐንስ መገለጡን አላወቁም:: ስለዚህም ሳቱ! ዮሃንስ የተገለጠው በኤልያስ ኃይልና መንፈስ ነው:: መሲሁን እየጠበቁ እንደሆነ ያሳያል ግን ዮሃንስ እንዳለ እናንተ የማታውቁት በመካከላችሁ ቆሟል! ዋዉ እኛ ግን ረድቶን አወቅነው ስሙ ይባረክ:: ዮሃንስም መሰከረ ነብዮም አይደለሁም አለ:: ይህ ነብይ የሚሉት ማንን ነው? ሙሴ በመካከላችሁ እንደእኔ ያለ ነብይ ያስነሳል ያለውን ነው የሚጠብቁት::ዮሐንስ ግን ስለእየሱስ መሰከረ አልሸሸገምም የጊዜውም ዝና ከእውነት አላራቀውም ሊሸፍነውም አልደፈረ በግልጥ፦ “እኔ በውኃ አጠምቃለሁ፤ ዳሩ ግን እናንተ የማታውቁት በመካከላችሁ ቆሞአል፤ እኔ የጫማውን ጠፍር ልፈታ የማይገባኝ፥ ከእኔ በኋላ የሚመጣው ከእኔ ይልቅ የሚከብር ይህ ነው፡” አላቸው። አሜን የከበረ ጌታ ነው ስሙ ይባረክ! አዋቂዎች ያላወቁት/የናቁት የማእዘን ራስ እየሱስ ለዓለም ምናምንቴ እራሱን ገለጠ ይገርማል:: ምን እላለሁ ጌታዬ ክበር::
ዮሐንስ 1: 29-31
29፤ በነገው ዮሐንስ ኢየሱስን ወደ እርሱ ሲመጣ አይቶ እንዲህ አለ፦ “እነሆ የዓለምን ኃጢአት የሚያስወግድ የእግዚአብሔር በግ።30፤ ‘አንድ ሰው ከእኔ በኋላ ይመጣል፥ ከእኔም በፊት ነበርና ከእኔ ይልቅ የከበረ ሆኖአል፡’ ብዬ ስለ እርሱ ያልሁት ይህ ነው።31፤ እኔም አላውቀውም ነበር፥ ዳሩ ግን ለእስራኤል ይገለጥ ዘንድ ስለዚህ በውኃ እያጠመቅሁ እኔ መጣሁ።”32፤ ዮሐንስም እንዲህ ብሎ መሰከረ፦ “መንፈስ ከሰማይ እንደ ርግብ ሆኖ ሲወርድ አየሁ፤ በእርሱ ላይም ኖረ።33፤ እኔም አላውቀውም ነበር፥ ዳሩ ግን በውኃ አጠምቅ ዘንድ የላከኝ እርሱ፦ ‘መንፈስ ሲወርድበትና ሲኖርበት የምታየው፥ በመንፈስ ቅዱስ የሚያጠምቅ እርሱ ነው፡’ አለኝ።34፤ እኔም አይቻለሁ እርሱም የእግዚአብሔር ልጅ እንደ ሆነ መስክሬአለሁ።”ምን አይነት ምስክርነት ነው?! እነሆ አለ ዮሃንስ እየሱስን ሲያስተዋውቅ:1. የእግዚአብሔር በግ – የዓለምን ኃጢአት የሚያስወግድ:: 2. ከእኔም በፊት ነበርና ከእኔ ይልቅ የከበረ ሆኖአል – ያለና የነበረ 3. መንፈስ ከሰማይ እንደ ርግብ ሆኖ ሲወርድ አየሁ – በመንፈስ ቅዱስ የሚያጠምቅ እርሱ ነው፡4. የእግዚአብሔር ልጅ እንደ ሆነ መስክሬአለሁይህንን ምስክርነት ዮሃንስ እየሰጠ ያለው እየሱስ ከመጠመቁ በፊት ሳይሆን ተጠምቆ በመንፈስ ቅዱስ ተሞልቶ በምድረ በዳ 40 ቀናትን ጾሞና ጸልዮ በሰይጣንም ተፈትኖ ሲመለስ ነው:: አያይዞም እኔም አላውቀውም ነበር አለ እርሱ ብቻ ሳይሆን መጽሐፉን እናውቃለን የሚሉትም እስከመጨረሻው አላወቁትም፥:: ዳሩ ግን ለእስራኤል ይገለጥ ዘንድ ስለዚህ በውኃ እያጠመቅሁ እኔ መጣሁ። ዋናው ስራ የዮሐንስ ሲመጣ መሲሁ መግለጥ ነበረና ገለጠው ክብርንም አልወሰደም ይኸው እናንተ የማታውቁት በመካከላችሁ ቆሟል አለ::ይህ በግ ንጹ የሆነ በምንም ያልተበከለ የዓለምን ኃጥያቶች ሳይሆን ኃጥያት ተብሎ በነጠላ ቁጥር ተጠቅልሎ እንደቀላል የተሰጠው ነው:: ይህ በግ በሸላቶቹ ፊት ዝም አለ፤ የደም ላብ አላበው በጌቴሰማኒ የመጣበትን ጽዋ ለመጠጣት አባት ሆይ ከእኔ ይህ ጽዋ ይለፍ እስኪልና በመስቀልም ከፍሎ እስኪጨርስ ድረስ አብ አባት ተወው:: ዋው የእግዚአብሔር በግ!!! ተመስገን ጌታዬ!ከእኔም በፊት ነበርና ከእኔ ይልቅ የከበረ ሆኖአል ሲል ዮሃንስ አንዳንዱ አንተ በወራት ትበልጠዋለህ ብሎ ሊያርም ይነሳ ይሆናል:: ነገር ግን እርሱ ከሁሉ በፊት የኖረ የሁሉ መገኛ እንዲሁም እንደከበረ የሚኖር አልፋና ኦሜጋ ነው::እዚህ በግ ላይ መንፈስ ከሰማይ እንደ ርግብ ሆኖ ሲወርድ አየሁ በመንፈስ ቅዱስ የሚያጠምቅ እርሱ ነው አለኝ ብሎ አላበቃም የእግዚአብሔር ልጅ እንደ ሆነ መስክሬአለሁ አለን ዮሃንስ:: ይህ የእግዚአብሔር ልጅና በግ የሆነው እየሱስ እኛን ፍለጋ መጣ ዋጋንም ከፍሎ ዋጀን:: በምስጋና ላይ ምስጋና ይብዛልህ አሜን
ዮሐንስ 1: 36-42
36፤ ኢየሱስም ሲሄድ ተመልክቶ፦ “እነሆ የእግዚአብሔር በግ፡” አለ።37፤ ሁለቱም ደቀ መዛሙርት ሲናገር ሰምተው ኢየሱስን ተከተሉት።38፤ ኢየሱስም ዘወር ብሎ ሲከተሉትም አይቶ፦ “ምን ትፈልጋላችሁ?” አላቸው። እነርሱም፦ “ረቢ፥ ወዴት ትኖራለህ?” አሉት፤ ትርጓሜው፡ “መምህር ሆይ፡” ማለት ነው።39፤ “መጥታችሁ እዩ፡” አላቸው። መጥተው የሚኖርበትን አዩ፥ በዚያም ቀን በእርሱ ዘንድ ዋሉ፤ አሥር ሰዓት ያህል ነበረ።41፤ እርሱ አስቀድሞ የራሱን ወንድም ስምዖንን አገኘውና፦ “መሢሕን አግኝተናል” አለው፤ ትርጓሜውም “ክርስቶስ” ማለት ነው።መጥምቁ ዮሃንስ እየሱስን ባየው ቁጥር የሚጠራው የእግዚአብሔር በግ እያለ ነው:: ተከታዮቹም እየሱስን ሲከተሉ አልተቃወመም:: ሁልጊዜ የሚያመለክተው ወደ እየሱስ ነው:: የእኛም ህይወት ወደዚህ ጌታ የሚጠቁም መሆን አለበት::እየሱስ ሲከተሉት አይቶ ፦ “ምን ትፈልጋላችሁ?” አላቸው:: ለእኛም ዛሬ ጥያቄው ምን ትፈልጋላችሁ ነው:: ምንድነው የምንፈልገው? እየሱስ እራሱን ወይስ ስጦታውን? ምቾትን? የዚህን ዓለም ብልጽግና ወዘተ:: መልስ እንስጥ:: እኛስ የተሰቀለውን እየሱስን እንሰብካለን አሜን:: የምድር ነገር ይዞ አያንገላታንም ዓይናችን በንጉሱ ላይ ይጽኑ:: እየሱስን ስንፈልገው ሌላው እኛን እየፈለገ ይመጣል:: አስቀድመን መንግስትና ጽድቁን እንፈልግ:: ጌታም ወዴት ትኖራለህ ሲሉት ወታችሁ እዩ አላቸው እነርሱም ከእሱ ጋር ዋሉ ይላል:: የጌታ መሆን ከጌታ ጋር መዋልን ይጠይቃል:: ጊዜያችን እንዳይባክን በፊቱ የምንሆንበትን ያብዛልን::እንድርያስ ወድያው ስራውን ጀመረ ሰውን ወደ እየሱስ ማምጣት የመጀመርያው ጴጥሮስ ነበረ መሲሁን አግኝተናል ብሎ ይዞት መጣ:: የቤተክርስቲያን መሪ የሆነውን ደቀ መዝሙር ጌታም ስሙንም ቀየረው:: ለእኛም መልእክቱ ከቤተሰባችን ጀምረን ዙሪያችን ላሉት ሁሉ ወንጌልን ማድረስ ነው:: መቀየርና ገንዘቡ ማድረግ ግን የጌታ ስራ ነው:: ጌታ ድፍረትንና ተደማጭነትን ይስጠን:: አሜን!
ዮሐንስ 1: 43-51
43፤ በነገው ኢየሱስ ወደ ገሊላ ሊወጣ ወደደ፥ ፊልጶስንም አገኘና፦ “ተከተለኝ፡” አለው።47፤ ኢየሱስ ናትናኤልን ወደ እርሱ ሲመጣ አይቶ ስለ እርሱ፦ “ተንኰል የሌለበት በእውነት የእስራኤል ሰው እነሆ፡” አለ።49፤ ናትናኤልም መልሶ፦ “መምህር ሆይ፥ አንተ የእግዚአብሔር ልጅ ነህ፤ አንተ የእስራኤል ንጉሥ ነህ፡” አለው።51፤ “እውነት እውነት እላችኋለሁ፥ ሰማይ ሲከፈት የእግዚአብሔርም መላእክት በሰው ልጅ ላይ ሲወጡና ሲወርዱ ታያላችሁ፡” አለው።በዝች አንድ ምዕራፍ ውስጥ ዮሃንስ ለእየሱስ ሰባት ስሞች እንደተሰጡት ያሳየናል:: 1. ዮሃንስ: የእግዚአብሔር በግ 2. የዮሃንስ ደቀመዛሙርት: መምህር (ቁ 38)3. እንድርያስ: መሲህ (ቁ 41)4. እንድርያስ: የናዝሬቱ እየሱስ (ቁ 45)5. እንድርያስ: የሰው (የዮሴፍ) ልጅ (ቁ 45)6. ናትናኤል: የእግዚአብሔር ልጅ (ቁ 49)7. ናትናኤል: የእስራኤል ንጉስ (ቁ 49)ጌታ እየሱስ ሶስተኛውን ደቀ መዝሙር ፊልጶስን ከቤተ ሳይዳ መረጠና ተከተለኝ አለው:: ጴጥሮስምና ወንድሙ እንድርያስም ከቤተሳይዳ ነበሩ:: እርሱም መከተል ብቻ ሳይሆን ስለእየሱስ መመስከር ጀመረ::ፊልጶስም የመሰከረው ለናትናኤል ነበረ:: ናትናኤል ግን የመለሰው የሚገርም ነው ከናዝሬት “ከናዝሬት መልካም ነገር ሊወጣ ይችላልን?” አለው። ፊልጶስ፦ “መጥተህ እይ፡” አለው። ስለየሱስ ሰዎች እራሳቸው መተው የሚያዩት ነው እኛ ማድረግ ያለብን ማመልከት እራሱን ግን የሚገልጥ እራሱ ነው:: ናትናኤል ብዙም ሳያምንበት ነበረ የመጣው ሲመጣ ግን የገጠመው ያልጠበቀው ነው ናትናኤል ብቻ ነው የሚያውቀው ከበለሱ በታች ምን እንደነበረ:: ስለዚህም ተነክቶ የእግዚአብሔር ልጅ ነህ ንጉስም ነህ አለው:: የናትናኤል ልብ ግን ደስ ይላል ተንኮል የሌለበት እንደሆነ ጌታ መስክሯልና:: በዝችው የረካውን ናትናኤልን “ከዚህ የሚበልጥ ነገር ታያለህ፡” አለው። የሚያየውም “እውነት እውነት እላችኋለሁ፥ ሰማይ ሲከፈት የእግዚአብሔርም መላእክት በሰው ልጅ ላይ ሲወጡና ሲወርዱ ታያላችሁ፡” አለው።አሜን የከበረ ተስፋ ያለን ነን ጌታ እራሱን ይግለጥልን::
ዮሐንስ 2: 1-12
1፤ በሦስተኛውም ቀን በገሊላ ቃና ሰርግ ነበረ፥ የኢየሱስም እናት በዚያ ነበረች፤3፤ የወይን ጠጅም ባለቀ ጊዜ የኢየሱስ እናት፦ “የወይን ጠጅ እኮ የላቸውም፡” አለችው።4፤ ኢየሱስም፦ “አንቺ ሴት፥ ከአንቺ ጋር ምን አለኝ? ጊዜዬ ገና አልደረሰም፡” አላት።5፤ እናቱም ለአገልጋዮቹ፦ “የሚላችሁን ሁሉ አድርጉ፡” አለቻቸው።7፤ ኢየሱስም፦ “ጋኖቹን ውኃ ሙሉአቸው፡” አላቸው። እስከ አፋቸውም ሞሉአቸው።8፤ “አሁን ቀድታችሁ ለአሳዳሪው ስጡት፡” አላቸው፤ ሰጡትም።ኢየሱስ ይህን የምልክቶች መጀመሪያ በገሊላ ቃና አደረገ፤ ክብሩንም ገለጠ፥ ደቀ መዛሙርቱም በእርሱ አመኑ። ይህ ሰርግ የገጠመው ችግር በዘመኑ በጣም አሳፋሪ የሆነ ነገር ነው:: እንደው የምታደርገውን ነገር ብታጣነው ማርያም ወደ እርሱ የመጣችው:: ይህ መቼም ለእርስዋ የመጀመርያ ነው ብዬ ባይፃፍም ለማመን ይቸግረኛል:: ብትለማመደው ነው ችግሩን ነግራው ብቻ የሄደችው ከተፈጸመም በኃላ አሳላፊው ከየት እንደመጣ አላወቀም የመሰከረው ግን እነሱ የለፉበትን መናኛ ጌታ የፈጠረውን ግን ምርጥ አለው ባይገባውም እንኳን:: ባህርይዋም ስለእርሱ ሲነገር በልብዋ ትጠብቀው ነበረ ነው የሚለን ቃሉ እንጂ እወቁኝ እወቁኝ የምትልም አይደለችም:: አስቸጋሪ ነገር ስለሆነባት ወይን አልቆባቸዋል እንጂ ያለችው ምን ማድረግ እንዳለበት አልነገረችውም:: ከዛም በመቀጠል የሚላችሁን አድርጉ ወይም አንዳች ጥያቄ አትጠይቁ ምክንያቱም የሚያደርገው ነገር ከተፈጥሮ አሰራር ውጪ እንደሆነ ተረድታለችና:: የእኛ የጸሎት ርእስ እንዴት ነው? እንዴት እንደሚያደርገው ሁሉ የሱን ስራ ለማቅለል ይመስል መመሪያ ያለው ነው:: የታመነ ሰው ልመና ግን ለየት ይላል ነገሩን ማሳየትና ቻሌንጅ ሲመጣም ቆሞ መጠበቅ ነው:: ይህን እንደዚህ ወይም እንደዛ አድርግ አይባልም እርሱ ፈጣሪ ነው::ሰዎቹም ይገርማሉ ውሃ ሙሏቸው ጋሎኖቹን ሲባሉ እሺ ብለው ሞሉ መቼም የተዋጠላቸው አይመስለኝም:: አሁን ይባስ አትሉም ቀድታችሁ ስጡ! ምን?!! አሁን አይደል እንዴ ውሃውን የሞላንበት?! የጌታ አሰራር ይገርማል ዛሬም አልደከመም አልተቀየረምም!! ልመናችንን በፊቱ ከምስጋና ጋር እናስታውቅ እንጂ በአንዳች አንጨነቅ እርሱ መልስን ሲመልስ ነገሩ ቀላል ነው ለእኛ የሚቀረው ውሃውን መቅዳት ብቻ ይሆናል:: ስናስበው ይህንን ወይን ለሰርጉ ለመጥመቅ ስንት ጊዜ ጉልበትና ገንዘብ አፍሰው ይሆን? ለዛውም እንደዚህ አንሶ ሊያሳፍራቸውና መናኛ ተብሎ ሊፈረጅ:: ለጌታ ግን የደቂቃዎች ጉዳይ ነው አትረፍርፎና አሳምሮ ለመስጠት:: አሜን!አባት ሆይ አንተ የታመንክ አምላክ ነህ ዛሬም ክንድህ አልደከመም ትሰራለህ!! በአንተ እታመናለሁ ይህ ጎደለ ብቻ ማለት ሲገባኝ እንዴት እንድታደርገው በነገርኩህ ይቅር በለኝ:: አባቴ ሆይ ተ መ ስ ገ ን!! አሜን!
ዮሐንስ 2: 13-25
13፤ የአይሁድ ፋሲካም ቀርቦ ነበር፥ ኢየሱስም ወደ ኢየሩሳሌም ወጣ።14፤ በመቅደስም በሬዎችንና በጎችን ርግቦችንም የሚሸጡትን ገንዘብ ለዋጮችንም ተቀምጠው አገኘ፤16፤ ርግብ ሻጪዎችንም፦ “ይህን ከዚህ ውሰዱ፤ የአባቴን ቤት የንግድ ቤት አታድርጉት፡” አላቸው።19፤ ኢየሱስም መልሶ፦ “ይህን ቤተ መቅደስ አፍርሱት፥ በሦስት ቀንም አነሣዋለሁ፡” አላቸው።ይህ የፋሲካ በዓል ለ7 ቀን የሚከበር ከግብጽ የወጡበትን ድንቅ የሚያስቡበትና ወንዶች ሁሉ በእግዚአብሔር ፊት የሚታዩበት ነው:: በግብጽ ምድር ቀሳፊው ሲያልፍ የሚያየው የበጉን ምልክት ነበረ ነገር ግን ማንም ከቤቱ ውጪ ቢገኝ በራሱ ላይ ነበረ እግዚአብሔር አይጠየቅም:: ዘጸአት 12:27፤ እናንተ፦ ‘በግብፅ አገር በእስራኤል ልጆች ቤቶች ላይ አልፎ ግብፃዊያንን በመታ ጊዜ፥ ቤቶቻችንን ያዳነ የእግዚአብሔር የማለፉ መሥዋዕት ይህች ናት፡’ ትሉአቸዋላችሁ።” ሕዝቡም ተጎነበሰ ሰገደም።ይህንንም በዓል ማክበር ቀጠሉ ለልጆቻቸውም አስተላለፉ:: በዓሉ ግን ለሚመጣው እውነተኛ በግ ስፍራውን የሚለቅ ጥላ ሆኖ ሳለ እነርሱግን አላወቁትም::በዓሉ በደረሰ ጊዜ ነው ወደ እየሩሳሌም የወጣው ሰው ሁሉ ያንን በግ እየፈለገ ነው ለበዓሉ:: የእግዚአብሔር በግ ግን በመካከላቸው ቆሞ ነበረ! ወይ መተላለፍ! የቤትህ ቅናት ይበላኛል ብሎ እነዚህን ነጋዴዎች እየገረፈ አባረረ:: ማንም ቆሞ ንብረቱ ሲወድም ወፎቹንም ሲለቅ ገበታውንም ሲገለባብጥ አንድ ሰው ነው ተሰብስበው እንኳን ሊመጡበት አልቻሉም:: አምላካዊ ቁጣ መሆን አለበት:: ዮሃንስ ይህንን የዘገበው ገና አገልግሎት ሲጀምር የመጀመርያው ቤቱን ማፅዳት እንደሆነ ሲሆን ሎሌቹ ግን የዘገቡት በስተመጨረሻ ነው ከአንድ ጊዜ በላይ አድርጎት ይሆን? አንድ ጥያቄ አይሁድ ጠየቁት፦ “ይህን ስለምታደርግ ምን ምልክት ታሳየናለህ?” አሉት። የምን ምልክት ነው የሚፈልጉት መሆን የሌለበትን ነገር ስላስወጣ? እርሱ ግን ይህን ቤተ መቅደስ አፍርሱት፥ በሦስት ቀንም አነሣዋለሁ፡” አላቸው። የፈጀው እኮ 46 ዓመት ነው እንዴት በ3 ቀን ታነሳዋለህ ብለው በዓለቱ እንደገና ተደናቀፉበት:: እርሱ ግን ስለትንሳኤው ተናገረ::ዛሬም ጌታ ይናገራል መንፈስ ቅዱስ ያብራልን እኛም ስንስት እንዳንገኝ:: ውስጣችን ነው የጌታ መቅደስ ኮተት ሞልቶት እንዳይሆንም እናጽዳው:: ቤቱ የፀሎት ቤት ነው:: በቃሉና በመንፈሱ ነው ሊሞላ የሚገባው::አባት ሆይ እየኝ ፈትሸኝ የዓለምን አመለካከት ከቃልህ በላይ በውስጤ አከማችቼ እንዳይሆን መርምረኝ የልቤንም ጉርጆ አገላብጠው ይቅርም በለኝ ከንቱ የሆነውን ሁሉ ከእኔ አውጣውና በመንፈስህና በቃልህ ሙላኝ:: መራራ ስር በእኔ እንዳያድግ ንቀልልኝ! እየኝ አባ: ማረኝም በእየሱስ ደም እጠበኝ! አሜን!
ዮሐንስ 3: 1-31፤ ከፈሪሳውያንም ወገን የአይሁድ አለቃ የሆነ ኒቆዲሞስ የሚባል አንድ ሰው ነበረ፤2፤ እርሱም በሌሊት ወደ ኢየሱስ መጥቶ፦ “መምህር ሆይ፥ እግዚአብሔር ከእርሱ ጋር ከሆነ በቀር አንተ የምታደርጋቸውን እነዚህን ምልክቶች ሊያደርግ የሚችል የለምና፡ መምህር ሆነህ ከእግዚአብሔር ዘንድ እንደ መጣህ እናውቃለን፡” አለው።3፤ ኢየሱስም መልሶ፦ “እውነት እውነት እልሃለሁ፥ ሰው ዳግመኛ ካልተወለደ በቀር የእግዚአብሔርን መንግሥት ሊያይ አይችልም፡” አለው።ይህ ሰው ፈሪሳዊ እንደዚሁም የአይሁድ አለቃ ነው:: ከእየሱስ ጋር በግል ጊዜ ለማሳለፍና ጥያቄ ለመጠየቅ ነው የመጣው:: ፈሪሳውያን ለእግዚአብሔር የቀኑ ሰውን ሁሉ የሚያስጨንቁ በተለያየ እራሳቸው ባመጡት ህግ የተተበተቡ ናቸው:: ምክንያታቸውም እስራኤል እግዚአብሔርን እያሳዘነ ነው ለምርኮ ተላልፎ የሚሰጠው ስለዚህ ሁሉምያለ ኃጥያት መኖር አለበት የሚሉ እስራኤል ከስደት ሲመለሱ የተፈጠሩ ግሩፖች ናቸው:: በብሉይ ኪዳን ላይ አናያቸውም::ኒቆዲሞስ ግን ለየሱስ ያለው ነገር እግዚአብሔር ከአንተ ጋር ነው እንጂ ያለበለዚያ እንዴት ይህንን ሁሉ ተአምራት ማድረግ ትችላለህ? ይህ ተአምር የማድረጉ ጉዳይ ነው ወደ እየሱስ ያመጣው:: ምዕራፍ ሁለትን ሲዘጋ ዮሃንስ ያለን ነገር ቢኖር ዮሐንስ 2:23፤ በፋሲካ በዓልም በኢየሩሳሌም ሳለ፥ ያደረገውን ምልክት ባዩ ጊዜ ብዙ ሰዎች በስሙ አመኑ፤ 24-25፤ ነገር ግን ኢየሱስ ሰዎችን ሁሉ ያውቅ ነበር፤ ስለ ሰውም ማንም ሊመሰክር አያስፈልገውም ነበርና አይተማመናቸውም ነበር፤ ራሱ በሰው ያለውን ያውቅ ነበርና። ብዙዎች አመኑበት ተአምራትን ስላደረገ ምንም እንኳን ተአምራቶቹን ዮሃንስ ባይዘግበውም:: እነዚህ ተአምራት የሳቡት የነኒቆዲሞስንም ቀልብ ነው:: እየሱስ ግን አይተማመንባቸውም ነበር ምክንያቱም በመስቀል ላይ ብቻውን እንደሚሆንና ስቀለው ስቀለው የሚሉ እንደሚሆኑ ያውቃል:: የጊዜውን ተአምር ግን አግኝተው ወደ ቤታቸው ተመልሰዋል::እየሱስን የምንከተለው ይህንና ያንን አድርግልን ለማለት ለምድር ነገር ከሆነ እናሳዝናለን:: እርሱ የዘላለምን ህይወት ሊሰጠን መጣ ከጥፋት ሊያድነን በደሙ ገዛን:: እኛ የእርሱ ነን በከፍታም በዝቅታም ጌታ ጌታ ነው በህይወታችን:: እንድናስተውል ይርዳን:: አሜን!
ዮሐንስ 3: 3-8
3፤ ኢየሱስም መልሶ፦ “እውነት እውነት እልሃለሁ፥ ሰው ዳግመኛ ካልተወለደ በቀር የእግዚአብሔርን መንግሥት ሊያይ አይችልም፡” አለው።4፤ ኒቆዲሞስም፦ “ሰው ከሸመገለ በኋላ እንዴት ሊወለድ ይችላል? ሁለተኛ ወደ እናቱ ማኅፀን ገብቶ ይወለድ ዘንድ ይችላልን?” አለው።5፤ ኢየሱስም መለሰ፥ እንዲህ ሲል፦ “እውነት እውነት እልሃለሁ፥ ሰው ከውኃና ከመንፈስ ካልተወለደ በቀር ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ሊገባ አይችልም።6፤ ከሥጋ የተወለደ ሥጋ ነው፥ ከመንፈስም የተወለደ መንፈስ ነው።7፤ ‘ዳግመኛ ልትወለዱ ያስፈልጋችኋል’ ስላልሁህ አታድንቅ።8፤ ነፋስ ወደሚወደው ይነፍሳል፥ ድምፁንም ትሰማለህ፥ ነገር ግን ከወዴት እንደ መጣ ወዴትም እንዲሄድ አታውቅም፤ ከመንፈስ የተወለደ ሁሉ እንዲሁ ነው።”ኒቆዲሞስ ስለእግዚአብሔር አብሮነት ለእየሱስ መሰከረ:: እየሱስ ግን ልክ ነህ አንተ ልባም ወይም እንደዚህ አይነት ነገር አይደለም ያለው ዳግመኛ ተወለድ ብሎ ነው የነገረው:: ኒቆዲሞስ የሚያወራው ሌላ እየሱስ የሚያወራው ሌላ! ማስተዋል ይስጠን ጉድለታችንን አይቶ ሲናገር የነቃ መንፈስ ይስጠን:: የእስራኤል መምህር የተባለው ሰው ጭራሽ ግራ ገባው ዳግም ስለመወለድና እንደገና እናቴ ማህፀን ልመለስ ነው? ብሎ ጠየቀ:: እርሱ የሚያውቀው መወለድ ይኼኛው ብቻ ነውና:: ስለአዲስ መወለድ በመንፈስ ስለመወለድ ምንም አያውቅም:: ምናልባትም ከማውቀው እውቀት ምን የተለየ ይነግረኛል ብሎ ይሆናል የመጣው:: ነገር ግን የማያውቀው እውቀት ተገናኘው::እየሱስ ያስረዳው ጀመረ እውነት እውነት እልሃለሁ፥ ሰው ከውኃና ከመንፈስ ካልተወለደ በቀር ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ሊገባ አይችልም። ከሥጋ የተወለደ ሥጋ ነው፥ ከመንፈስም የተወለደ መንፈስ ነው።ዳግመኛ ልትወለዱ ያስፈልጋችኋል’ ስላልሁህ አታድንቅ። ይህ ሰው የሚያውቀው አንድ አይነት መወለድ ነው እርሱም ወደዚህ ዓለም መምጫውን እንጂ ወደ እግዚአብሔር መንግስት መግቢያውን አይደለም:: ግራ ግብት ብሎ ከብዶታል ለዚህም ነው ጌታ አታድንቅ የሚለው:: ዳግም መወለድ ልክ ንስር እራስዋን እንደምታድሰው ለብቻዋ ሄዳ ጥፍርዋን መብያ አፍዋን ሁሉ እያደቀቀች ከላይዋ በወራት ውስጥ እንደምታራግፈው አይነት ቢሆን ሳይቀለው አይቀርም:: ዛሬም ሰዎች ይህ ነው የሚከብዳቸው ስራ ቢኖረው ግን ሁሉ ሮጦ አድርጎት ነበረ:: ለተቀበሉት ግን በስሙ ለሚያምኑት ለእነርሱ የልጅነት ስልጣንን ሰጣቸው ከእግዚአብሔር ተወልደዋል:: አጭርና ግልጽ!!! ስሙ ይባረክ ደካሞችን ያሰበና በስብከት ሞኝነት በማመን መዳንን ያደረገው ጌታ ስሙ ይባረክ::ለዚህ አእምሮ አይመችም ጌታም እንዳለው ነፋስ ወደሚወደው ይነፍሳል፥ ድምፁንም ትሰማለህ፥ ነገር ግን ከወዴት እንደ መጣ ወዴትም እንዲሄድ አታውቅም፤ ከመንፈስ የተወለደ ሁሉ እንዲሁ ነው። አሜን! ስራው በእኛ ላይ ተሰርቶ ተለውጠን እራሳችንን አግኝተናል:: እንዴት ቢባውል ከየት ወዴት እንደነፈሰ የማናውቀው ያ የእግዚአብሔር መንፈስ ወለደንና ለወጠን!! ክብር ይሁንለት! አሜን
ዮሐንስ 3: 9-13
9፤ ኒቆዲሞስ መልሶ፦ “ይህ እንዴት ሊሆን ይችላል?” አለው።10፤ ኢየሱስም መልሶ እንዲህ አለው፦ “አንተ የእስራኤል መምህር ስትሆን ይህን አታውቅምን?11፤ እውነት እውነት እልሃለሁ፥ የምናውቀውን እንናገራለን ያየነውንም እንመሰክራለን፥ ምስክራችንንም አትቀበሉትም።12፤ ስለ ምድራዊ ነገር በነገርኋችሁ ጊዜ ካላመናችሁ፥ ስለ ሰማያዊ ነገር ብነግራችሁ እንዴት ታምናላችሁ?13፤ ከሰማይም ከወረደ በቀር ወደ ሰማይ የወጣ ማንም የለም፥ እርሱም በሰማይ የሚኖረው የሰው ልጅ ነው።እንደዚህ እያስረዳውም ኒቆዲሞስ ሊገባው አልቻለም የዳግም መወለድ ሚስጥር: : ጌታም አንተ የእስራኤል መምህር ስትሆን ይህን አታውቅምን? ይህ ሰው የአይሁድ ሁሉ አለቃና መምህር ነው ከመምህራን አንዱ ሳይሆን ዋናው ነው ማወቅ ነበረበት:: ጌታ በቃሉ ላይ ያለውን ሊፈጽም መጣ እንጂ ዱብ እዳ አይደለም የሆነው ቀድሞ በነብያቱ ተነግሯል:: እንደሚመጣ እየተጠባበቁት ነበር ነገር ግን ተሸዋወዱ ዮሃንስ መጥምቁ እንዳለው እናንተ የማታውቁት በመካከላችሁ ቆሟል አላቸው ግን አላወቁትም! ግንበኞች የናቁት የማዕዘን ራስ እየሱስ!!ይህ ዋና የእስራኤል መምህር ሕዝቅኤል 36:26፤ አዲስም ልብ እሰጣችኋለሁ አዲስም መንፈስ በውስጣችሁ አኖራለሁ፤ የድንጋዩንም ልብ ከሥጋችሁ አወጣለሁ፤ የሥጋንም ልብ እሰጣችኋለሁ። የሚለውን አንብቧል ግን አልገባውም እፊቱ የእግዚአብሔር በግ ቆሞ በብዙ የዮሐንስ ምስክር እየፀና አዋቂ ነን የሚሉት ግን በእውቀት ተኮፍሰው ከእኛ ምን ያመልጣል ብለው ተላለፉ:: ጌታ ይጠብቅ በዝች ትንሽ ጭንቅላታችን ይህንን ፈጣሪ ለማወቅ መነሳት የማይሆን ነው በመንፈሱ ግንማንነቱን ይገልጥልናል::ይህ ከሰማይ የመጣው ጌታ እውነት እውነት እልሃለሁ፥ የምናውቀውን እንናገራለን ያየነውንም እንመሰክራለን፥ ምስክራችንንም አትቀበሉትም። እርሱ የሚለንን እንስማ! ስለ ምድራዊ ነገር በነገርኋችሁ ጊዜ ካላመናችሁ፥ ስለ ሰማያዊ ነገር ብነግራችሁ እንዴት ታምናላችሁ? መንፈስ ቅዱስ ነው አስተማሪው ስለምናውቅ አንናገር ይህ የከበረ ህያው የሆነ ቃል ነው:: እርሱ ሲያስተምረን እንደነቃለን:: ይህ ንጉስ ክብሩን ገለጠልን ማንም ከምድር ወደ ሰማይ የሄደ የለምና እርሱ ግን ሁሉን ነገረን:: የመንፈስ ነገር በመንፈስ ይታወቃል አሁንም ጳውሎስ የፀለየውን እንፀልይ:- እርሱን በማወቅና በመገለጥ መንፈስ ይሙላን:: አሜን!! ለመማርም የቀናን በትህትና የምንመላለስና ዝቅ ያለ መንፈስን ይዘን ወደፊቱ እንቅረብ:: ለትሁታን ፀጋን ይሰጣል:: አሜን አባት ሆይ እርዳን!
ዮሐንስ 3: 8-9 ይህንን ክፍል እንደገና እንድናተኩርበት በሚል ደግሜዋለሁ:: ጌታ እየሱስ የሚናገረው ስለሰማያዊዉ አሰራር ኒቆዲሞስ የሚያወራው ስለምድራዊዉ:: በዚህ ምክንያት ተላለፉ:: ኒቆዲሞስ እውቀት አላነሰውም መጽሐፍትን ጥጥት አድርጎ ነው ያጠናውና የሚያውቀው:: ያው የጭንቅላት እውቀት ማለት ነው:: ጌታ የሚለው ነፋስ ወደሚወደው ይነፍሳል፥ ድምፁንም ትሰማለህ፥ ነገር ግን ከወዴት እንደ መጣ ወዴትም እንዲሄድ አታውቅም፤ ከመንፈስ የተወለደ ሁሉ እንዲሁ ነው።” ሲለውኒቆዲሞስ ደግሞ የሚለው፦ “ይህ እንዴት ሊሆን ይችላል?” አለው።የመንፈስ አሰራር ሊገባን ይገባል አለበለዚያ ግን ጸሎታችን ሁሉ እንዴት ይሆናል በሚል ልባችን ተሞልቶ አፋችን ግን እየለመነ ይሆናል: ያለማመን ጠንቅ! ውስጣችንና አንደበታችን በአንድ አሳብ ይስማማ:: ይህ እንዲሆን የመንፈስ እርዳታ ያስፈልገናል:: ማነኝ ሲል አንተ የእግዚአብሔር ልጅ ነህ ብሎ መመለስ የሚቻለው በመንፈስ ብቻ ነው::ባጭሩ በጌታ ፊት እንጸልይ ዛሬን እራሳችንን በፊቱ እናቅርብ በመንፈሱ ማንነቱን ያሳውቀን ቃሉንም ያብራልን! አባት ሆይ እራሳችንን በፊትህ ለማሳየት መተናል ሩጫችን በስጋ ይሆን? መርምረን ያለ አንተ አንዳች ማድረግ አንችልም የምንለው በአፋችን ብቻ ይሆንን? መርምረን:: አንተን በማወቅና በመገለጥ ሙላን አለዚያ የማያምን ጠማማ ትውልድ እንዳንሆን አስበን:: በፊትህ ዛሬ የመንፈስ ቅዱስ እርዳታ በዳከርንበት ላይ ሁሉ ይምጣና ያብራልን:: መገለጥ ያስፈልገናል ጌታዬ ሆይ:: የሰው ልጅ ሲመጣ እምነትን ያገኝ ይሆንን ነበረ ጥያቄህ:: አባት ሆይ ዛሬ እርዳን እምነት ከመስማት ነውና የምንሰማውን ይህንን የምትሰጠንን ቃል አብራልን በመንፈስ እንረዳውና ከእኛ ጋር ይዋሃድ:: በእየሱስ ስም አሜን!
ዮሐንስ 3: 14-15
14-15፤ ሙሴም በምድረ በዳ እባብን እንደ ሰቀለ እንዲሁ በእርሱ የሚያምን ሁሉ የዘላለም ሕይወት እንዲኖረው እንጂ እንዳይጠፋ የሰው ልጅ ይሰቀል ይገባዋል።ጌታ እንዳለው ስለምድራዊው ነገር ስናገር ካልገባህ እንዴት ሰማያዊዉን ልንገርህ? በንፋስ ሊያስረዳው ሞከረ ብዙም አልገባውም ስለዚህ ይህንን ታሪክ ይነግረው ጀመረ ከራሱ ጋር እያያያዘ:: ከላይ የተናገረው ካልገባው የበለጠ የሚገርመው የመንፈስ አሰራር በዚህ የናስ እባብ ላይ ታይቷል:: እንደው ስለተፃፈ ነበብ አድርገን ባናልፈው መልካም ነው ቆም ብለን የሆነውን እናስብ:: የሆነው ነገር እስራኤል በእግዚአብሔር ላይ እንጎራጉሮ እባቦች መተው ነደፏቸው:: ድሮም የጌታ ጥበቃ ነው እንጂ እኮ እባቦቹማ ነበሩ ወይም ሄዳችሁ ይህንን ህዝብ ንደፉ ብሎ ለዚሁ ጥፋት የፈጠራቸው አይመስለኝም:: የሆነ ሆኖ እባቦቹ ህዝቡን ነድፈዋል:: ስለዚህ የህዝቡ ስቃይ ሲያሳዝነው ሙሴን የክፉ ምሳሌ የሆነውን እባብ ከብር ሰርተህ ስቀለው ተባለ:: የተሰቀለው አንድ እባብ ብቻ ሰውን የነደፉት ግን ብዙ እባቦች ለምን ታድያ ለእያንዳንዱ አንድ አልተሰቀለም? ይህ ሰውኛ አሰራር ነው መንፈስ ለሆነው ለጌታ ግን አንዱ በቂ ነበር:: እየተሰቃየ ያለው ሰው የሚጠበቅበት ካለበት እሩቅም ይሁን ቅርብ የተሰቀለውን እባብ ማየት ብቻ ነው የነደፈው እባብ እንደተሰቀለ ሲያይ መርዙ በእርሱ ላይ ጉልበት ያጣል እናም ነፃ ይሆናል:: የነደፈኝ እባብ ተሰቀለ ብሎ ማየት እንዴት ያድናል ሄዶ መተሻሸት ወይም ቁስሉን ቢነካልኝ እንደዛና እንደዚህ ባደርግ ለአእምሮ ይመች ነበር:: ነገር ግን ጌታ በማየትና በማመን አደረገው አለበለዚያማ እየሱስ በየጊዜው እንድንነካውና እንድንድን እየተመላለሰ መሰቀል ሊኖርበት ነበረ:: ከሁሉም በላይ እየሱስ መቶ በሁላችን ውስጥ ያለውን የእባቡን መርዝ አንድ ጊዜ ተሰቅሎ ባመነው ጊዜ ነቅሎታል :: ብሉይ ኪዳን የአዲስ ኪዳን ጥላው አይደለምን? ይህ የአይሁድ መምህር ግን የገባውም አይመስለኝም ተአምራትን እዩ አባቶቻችን ብሎ አልፎት ይሆናል እንጂ አዲስ ልብ የሚሰጠው የድንጋዩ ልብ የሚወጣው እንደ እባቡ ምሳሌ የሰው ልጅ የሆነው እየሱስ ተሰቅሎ ነው ብሎ ያገናዘበው አይመስልም:: ለእኛም ይህ የእግዚአብሔር መንፈስ ቃሎቹን እያገናኘ ሙሉ ስእሉን ይስጠን:: መቼም አሁንም ቢሆን ለኒቆዲሞስ ከባድ ነው ተፅፎ አነበበው እንጂ አልተለማመደውምና:: እኛ ግን ተለማምደነዋል በስብከት ሞኝነት አምነነው ከዚህ እባብ ነፃ ሆንን አዲስ ፍጥረት የእግዚአብሔር ወገን ለርስቱ የተለየን ካህናቱ አደረገን:: በእርሱ በማመን የዘላለም ህይወትን አግኝተናል!! አሜን!!! እኛም ዛሬ ወደተሰቀለው እየስስ የምናሳይ ቀስት ሆነናል በዚህ ሞኝነት ውስጥ ሕይወትን ማግኘት:: አባት ሆይ ተመስገን አሰራርህ ድንቅነው ዛሬም በአንተ ላይ እንታመናለን በህይወታችን ያልከው ሁሉ ይሁን:: አሜን!
ዮሐንስ 3:16-18
16፤ በእርሱ የሚያምን ሁሉ የዘላለም ሕይወት እንዲኖረው እንጂ እንዳይጠፋ እግዚአብሔር አንድያ ልጁን እስኪሰጥ ድረስ ዓለሙን እንዲሁ ወዶአልና።17፤ ዓለም በልጁ እንዲድን ነው እንጂ፥ በዓለም እንዲፈርድ እግዚአብሔር ወደ ዓለም አልላከውምና።18፤ በእርሱ በሚያምን አይፈረድበትም፤ በማያምን ግን በአንዱ በእግዚአብሔር ልጅ ስም ስላላመነ አሁን ተፈርዶበታል።በእርሱ ለሚያምን ሁሉ የተደረገለት:-1. ልጅ መሆን2. የዘላለም ህይወት ማግኘት4. አለመጥፋትና3. ከፍርድ ማምለጥ (አይፈረድብንም)ቀላል ይመስላል የሆነው ነገር ስናድግም ስንሰማው ስለሆነ መደነቃችንን ሳይቀንሰውአልቀረም:: ዓለምን አብ የወደደው እንዲያው ነው እንጂ እንደው ይሄ ነገሩ ተብሎ የሰው ልጅ የሚወደድበት ነገርም የለውም መልካም ብለን የምናደርገው እንኳን እንደመርገም ጨርቅ ነው:: አብ ወደደንና ልጁን ላከልን ሲልከውም ብዙ ክፉ ታያለህ አትፍረድባቸው ግን ሞተህ የዘላለምን ይህወት ስጥ ተባለ:: ሃሌሉያ!! በምድር ሲመላለስ ስለሰው ሊነገረው የማይፈልግ ጌታ ያችንም ሴት ከሞት አዳናት ሐጥያት ያላደረገ ይውገራት ብሎ እርሱም በመጨረሻ አልፈርድብሽም ደግመሽ ኃጥያትን አታድርጊ አላት:: እሱን ያላወቀች ነፍስ ግን አሁን በፍርድ ውስጥ አለች:: ፍርድ አሁን አይደለም የፍርድ ጊዜ ይመጣል ሰው እንደማገዶ ወደ እሳት የሚጣልበት ጊዜስለዚህ እንመስክር:: ወንጌልን እንድናደርስ የተጠራን ነንና በእግዚአብሔር ቁጣ ስር መገኘት እንዴት ከባድ ነው? እንራራላቸውና እንመስክር እንፀልይ!!ጌታ ሆይ እርዳን!
ዮሐንስ 3: 19-21
19፤ ብርሃንም ወደ ዓለም ስለ መጣ ሰዎችም ሥራቸው ክፉ ነበርና ከብርሃን ይልቅ ጨለማን ስለ ወደዱ ፍርዱ ይህ ነው።20፤ ክፉ የሚያደርግ ሁሉ ብርሃንን ይጠላልና፥ ሥራውም እንዳይገለጥ ወደ ብርሃን አይመጣም፤21፤ እውነትን የሚያደርግ ግን ሥራው በእግዚአብሔር ተደርጎ እንደ ሆነ ይገለጥ ዘንድ ወደ ብርሃን ይመጣል።”ይህ የዓለም ብርሃን ለእኛ ደግሞ የህይወት ብርሃን ከጨለማው ስልጣን እንደወደደ ሲያሽከረክረን ከነበረው ሊታደገን መጣ እርሱ ባይመጣና ባያወጣን በራሳችን አንድም ማድረግ አንችልም ነበረ:: ይህ ጌታ መቶም አልፈረደብንም ነገር ግን ህይወትን ሰጠን ይህም ህይወት የሰው ብርሃን ነው:: ደግሞም ጨለማ ብርሃንን አሸንፎ አያውቅም:: ዮሐንስ 1:4፤ በእርሱ ሕይወት ነበረች፥ ሕይወትም የሰው ብርሃን ነበረች።5፤ ብርሃንም በጨለማ ይበራል፥ ጨለማም አላሸነፈውም። አሜን!ሰው ስራው ክፉ ስለሆነ ወደዚህ ህይወት ወደሆነው ብርሃን መምጣትና ስራውን ማስመርመር አልፈለገም:: ክፉ ጨለማን ተገን አድርጎ ይሰራል እኛ ግን የብርሃን ልጆች ነን በብርሃን እንመላለሳለን የአምላካችንንም ስራ እንሰራለን:: ይህንን ህይወት ለሰጠን ብርሃኑን ላበራልን አዳኝ ክብር ይሁን:: ከጨለማ ጋር አልተባበርም በብርሃን እመላለሳለሁ::
ዮሐንስ 3: 22-30
27፤ ዮሐንስ መለሰ፥ እንዲህ ሲል፦ “ከሰማይ ካልተሰጠው ሰው እንዳች ሊቀበል አይችልም።ዮሐንስ 3:30፤ እርሱ ሊልቅ እኔ ግን ላንስ ያስፈልጋል።ዮሃንስ ስለራሱ ሲናገር እኔ ሚዜ እንጂ ሙሽራ አይደለሁም አለ:: ምንም አይነት ትኩረት አይስብም ስራውን ያውቆ ነበረ:: ወደ ከበረው ጌታ ብቻ መጠቆም ነበረ ስራው:: አገልግሎትህን ቀማህ ሰው ሁሉ ወደ እርሱ እየሄደ ነው ቢሉትም እናንተ ምስክር ናችሁ እኔ እርሱ አይደለሁም ብያለሁኝ እያለ እማኝ ይጠራል:: ምን አይነት ትኩረት ነው ያለው ለተሰጠው አገልግሎት? ቅናት በአገልግሎት ውስጥ መታየት የለበትም እህቴ በርቺ ወንድሜ በርታ ተባብለን ንጉሱን በይህወታችን ማክበር ነው ያለብን::ስለዚህም “ከሰማይ ካልተሰጠው ሰው እንዳች ሊቀበል አይችልም።” ይህ ቃል በጣም ነው የነካኝ በዚህ ማለዳ:: አንብቤው ብቻ ማለፍ አልቻልኩም የጌታ መንፈስ በኃይል በላዬ ይመጣል: እናንተንም ጌታ በመንፈሱ ይጎብኛችሁ:: ምን ተቀብለናል ከሰማይ?! ከሰማይ የተቀበልነው እኮ እርሱን ልናገንበትና ልናሳይበት ነው:: አንዱም ለእኛ አልተሰጠም ለእርሱ ክብር ነው:: ሃሌሉያ!ይህ ጌታ በልግስና መንፈሱን በየዕለቱ ያፈሳል ደግሞም በለመለመ መስክ ያሳድረኛል፤ በዕረፍት ውኃ ዘንድ ይመራኛል። ነፍሴን መለሳት፥ ስለ ስሙም በጽድቅ መንገድ መራኝ። መዝሙር 23:2-3 አሜን!!!አባት ሆይ አንተ ከሰማይ የሰጠኸንን ለክብርህ እናውለው :: ማስተዋልን ስጠን እርዳን!! አንተ ልትልቅ ይገባሃልና ልቀህ ታይ!
ዮሐንስ 3:31-33
31፤ ከላይ የሚመጣው ከሁሉ በላይ ነው፤ ከምድር የሚሆነው የምድር ነው የምድሩንም ይናገራል። ከሰማይ የሚመጣው ከሁሉ በላይ ነው።32፤ ያየውንና የሰማውንም ይህን ይመሰክራል፥ ምስክሩንም የሚቀበለው የለም።33፤ ምስክሩን የተቀበለ እግዚአብሔር እውነተኛ እንደ ሆነ አተመ።ወንጌላዊው ዮሃንስ እየሱስን ማሳየት የሚፈልገው ከላይ የመጣ አምላክ መሆኑን ነው:: መጥምቁ ዮሃንስ እየሱስን የእግዚአብሔር በግ እንዲሁም ሙሽራ እያለ ይጠራዋል:: ከላይ የመጣው እግዚአብሔር ነው አምላክነቱን እወቁ እያለ ነው:: ከሰማይ የሚመጣው ከሁሉ በላይ ነው ብሎ አወጀ። አሜን!እርሱም በላይ ያየውንና የሰማውን ተናገረ ያስተዋለ ወይም የተቀበለ ግን የለም:: ብዙዎች ያጋፉት ነበረ የዕለት ጥቅም ፍለጋ ፤ እንጀራን ፍለጋ ፤ ፈውስን ፍለጋ:: ያወቁት ደግሞ ጥቂቶች ያላቸውን ሁሉ ትተው ተከተሉት:: ምስክርነቱ እውነተኛ ነው ምስክሩን የተቀበለ እግዚአብሔር እውነተኛ እንደ ሆነ አተመ! ይህንን እውነት ያመንን አምላካችን እውነተኛ ነው ብለን አውጀናል! አሜን አትመናል!! ጌታችን እውነተኛ ነው መዳናችንም እውነት ነው ልጅ መሆናችንም እውነት ነው::አባት ሆይ ክብርንና ምስጋናን ወደ አንተ አመጣለሁ እውነተኛ እንደሆንክና እኛም በአንተ እንደተነካን እንመሰክራለን! አሜን!
ዮሐንስ 3: 34-36
34፤ እግዚአብሔር የላከው የእግዚአብሔርን ቃል ይናገራልና፤ እግዚአብሔር መንፈሱን ሰፍሮ አይሰጥምና።35፤ አባት ልጁን ይወዳል ሁሉንም በእጁ ሰጥቶታል።36፤ በልጁ የሚያምን የዘላለም ሕይወት አለው፤ በልጁ የማያምን ግን የእግዚአብሔር ቍጣ በእርሱ ላይ ይኖራል እንጂ ሕይወትን አያይም።”ያየውንና የሰማውን እየሱስ መሰከረ እኛም ምስክሩን እውነት ነው ብለን ተቀበልንና አተምን:: አሜን እግዚአብሔር እውነተኛ ነው:: እውነትተኛነቱንም ያወቅቅነው ቃሉን ስለነገረን ነው ሲናገርም በመንፈስ ሆኖ ነው:: የብሉይ ኪዳን ነብያት በልክና በጊዜ የተወሰነ ነገር በመንፈስ ቅዱስ አድርገዋል:: በአዲስ ኪዳን ግን መንፈስ ቅዱስ ስራ ሰርቶ መሄድ ብቻ ሳይሆን ከመለኮቱ ኃይል ተካፋይ አፍርጎንማንነቱን በእኛ ውስጥ አድርጎ እየኖረ ነው ስለዚህ ምኑን ሰፈረው ማንነቱ ሁሉ በእኛ ውስጥ እየኖረ እራሱን ነው የሰጠን:: ስሙ ይባረክ!አብ ሁሉን ለእየሱስ ሰቶታል በልጁ የሚያምን የዘላለም ሕይወት አለው፤ እንደሚል እኛ የዘላለም ህይወትን የምናገኘው ሞተን መንግስተ ሰማያት ስንገባ ሳይሆን አሁን ወደ ፍቅሩ መንግስት አፍልሶናል:: በልጁ የማያምን ግን የእግዚአብሔር ቍጣ በእርሱ ላይ ይኖራል እንጂ ሕይወትን አያይም:: ይህ ማለት በክርስቶስ ስራ ከማመን በህግ እንሄዳለን ለሚሉት ነው እርሱምመጨረሻው ህይወትን አለማየት ነው:: በራእይ 20:13፤ ባሕርም በእርሱ ውስጥ ያሉትን ሙታን ሰጠ፥ ሞትና ሲኦልም በእነርሱ ዘንድ ያሉትን ሙታን ሰጡ፥ እያንዳንዱም እንደ ሥራው መጠን ተከፈለ።አባት ሆይ ስለሰጠኸኝ ህይወት አመሰግንሃለሁ:: ስለሚጠፉት ደግሞ የምፀልይበትን ፀጋ ስጠኝ አንብቤ ብቻ እንዳላልፍ ጌታዬ ሆይ መራራትን ስጠኝ::አሜን!
ዮሐንስ 4: 1 – 6
እንግዲህ፦ “ኢየሱስ ከዮሐንስ ይልቅ ደቀ መዛሙርት ያደርጋል፡ ያጠምቅማል፡” ማለትን ፈሪሳውያን እንደ ሰሙ ጌታ ባወቀ ጊዜ፥ ይሁዳን ትቶ ወደ ገሊላ ደግሞ ሄደ፤ ዳሩ ግን ደቀ መዛሙርቱ እንጂ ኢየሱስ ራሱ አላጠመቀም። በሰማርያም ሊያልፍ ግድ ሆነበት።ስለዚህ ያዕቆብ ለልጁ ለዮሴፍ በሰጠው ስፍራ አጠገብ ወደምትሆን ሲካር ወደምትባል የሰማርያ ከተማ መጣ፤ በዚያም የያዕቆብ ጕድጓድ ነበረ። ኢየሱስም መንገድ ከመሄድ ደክሞ በጕድጓድ አጠገብ እንዲህ ተቀመጠ፤ ጊዜውም ስድስት ሰዓት ያህል ነበረ።ፈሪሳውያን እየሱስ ከዮሃንስ የበለጠ ደቀ መዛሙርት ያደርጋልን እንደሰሙ ባወቀ ጊዜ ይሁዳን ትቶ ወደ ገሊላ መሄድን መረጠ:: አሁን ጊዜው አልነበረም ከነዚህ ባለስልጣናት ጋር ለመጨቃጨቅ:: ስለዚህም ወደ ሌላ ስፍራ ሄዶ አገልግሎቱን መቀጠል ነበረበት:: ወደ ገሊላም ሲያቀና በሰማርያ ማለፍ ግድ ሆነበት ይላል:: ወደ ገሊላ ለመሄድ አጭሩ መንገድ ነበረ:: እስራኤሎች ግን ከሰማርያውያን ጋር ስለማይተባበሩ በከተማቸውም ማለፍን አይፈልጉምና በረጅም መንገድ ዙሪያውን ነበረ የሚሄዱት:: እየሱስ ደክሞት እንደነበረ ዮሃንስ ይነግረናል:: አምላክ እንደሆነ ሁሉ እንደሰውም ይደክመዋል:: እራሱን ዝቅ አድርጎ ነው የመጣው ስሙ ይባረክ::እየሱስን ግን ወደዚህ ስፍራ እንዲመጣ ግድ ያለው አንዱ ምክንያት ይህ ስፍራ አብርሃምንም ያዕቆብንም የተገናኘበትና እነርሱም መሰዊያን ሰርተው የሰውበትና ያመለኩበት ስፍራም ነው:: ሌላው አንዲትን ሴት ለማግኘትና ከተማዋን ሁሉ በአንድ ጊዜ መድረስ ነበረ:: የሰማርያ ህዝብ ከአህዛብ የተቀላቀለ ስለሆነ በእስራኤሎች ዘንድ ይገፋሉ:: ይህንንየተገፋና በተመረጡት ዘንድ ስፍራ ያልተሰጠውን ማህበረሰብ ፈልጎ መጣ:: አገልግሎታችን በፍቅር ያለ አድልዎ ለሰው ልጅ ሁሉ መሆን አለበት :: ጌታ ይርዳን::ዘፍጥረት 12:6፤ አብራምም እስከ ሴኬም ስፍራ እስከ ሞሬ የአድባር ዛፍ ድረስ በምድር አለፈ፤ የከነዓን ሰዎችም በዚያን ጊዜ በምድሩ ነበሩ። 7፤ እግዚአብሔርም ለአብራም ተገለጠለትና፦ “ይህችን ምድር ለዘርህ እሰጣለሁ፡” አለው። እርሱም ለተገለጠለት ለእግዚአብሔር በዚያ ስፍራ መሠውያን ሠራ።ዘፍጥረት 33:18፤ ያዕቆብም ከሁለት ወንዞች መካከል በተመለሰ ጊዜ በከነዓን ምድር ወዳለችው ወደ ሴኬም ከተማ በደኅንነት መጣ፤ በከተማይቱም ፊት ሰፈረ። 19፤ ድንኳኑን ተክሎበት የነበረውንም የእርሻውን ክፍል ከሴኬም አባት ከኤሞር ልጆች በመቶ በጎች ገዛው። 20፤ በዚያም መሠውያውን አቆመ፥ ያንም ኤል ኤሎሄ እስራኤል ብሎ ጠራው።
ዮሐንስ 4: 7-12
7፤ ከሰማርያ አንዲት ሴት ውኃ ልትቀዳ መጣች። ኢየሱስም፦ “ውኃ አጠጪኝ፡” አላት፤8፤ ደቀ መዛሙርቱ ምግብ ሊገዙ ወደ ከተማ ሄደው ነበርና።10፤ ኢየሱስ መልሶ፦ “የእግዚአብሔርን ስጦታና፦ ‘ውኃ አጠጪኝ፥’ የሚልሽ ማን መሆኑንስ ብታውቂ፥ አንቺ ትለምኚው ነበርሽ፡ የሕይወትም ውኃ ይሰጥሽ ነበር፡” አላት።እየሱስ በሰማርያ ለማለፍና ይህንን መሰዊያ የነበረበትን ስፍራ ለመጎብኘት የተገኘ ይመስላል:: አብርሃምም ያዕቆብም እዚሁ ስፍራ ላይ መሰዊያን አድርገው ነበረና:: በስፍራው ላይ ሲመጣ ግን የተገኘችው ይህች ምስኪን በጥያቄ የተሞላች ሳምራዊት ነበረች:: በዘመኑ እስራኤላውያንና ሳምራውያን አይተባበሩም ነበረ:: እየሱስ ግን የተናቀችውን ለመገናኘት ጊዜውንና ቦታውን አስተካክሎ ተገናኛት:: እኛንምበጨለማው ውስጥ ስንደናበር ተገናኝቶን እራሱን ገልጦልን ተከተልነው::ሴቲቱን ኢየሱስም፦ “ውኃ አጠጪኝ፡” አላት፤ ይህ የማይታመን ጥያቄ ነው አይሁዳዊ ሰማርያዊትን? እርሱ ግን የሚያደርገውን ያውቅ ነበረ:: እርስዋም ገርሟታል መልሶም እንድትለምነው ስለፈለገ መንገዱን እያሳያት ነበር:: ጥያቄ የሚፈጥርን ነገርም ተናገራት:- የእግዚአብሔርን ስጦታና፦ ‘ውኃ አጠጪኝ፥’ የሚልሽ ማን መሆኑንስ ብታውቂ፥ አንቺ ትለምኚው ነበርሽ፡ የሕይወትም ውኃ ይሰጥሽ ነበር፡” ሲላት ከውሃው አሳብ ወጣችና ማወዳደር ጀመረች:: ማን ቢሆን ነው ብላ ከያዕቆብ ጀመረች::እራሱንየጠራው የእግዚአብሔርን ስጦታ ብሎ ነው:: እየሱስ ለእኛ ስጦታ ነው:: የሕይወትም ውኃ ይሰጥሽ ነበር አላት እኛምተቀብለናል ይህንን የህይወት ውኃ ጥማችንን የሚያረካ ከእርሱ በቀር ሌላው ሁሉ እያለቀ ያስጠማናል እየሱስ ግን ጥማትን የሚያረካ ነው ለዘላለም:: ሃሌሉያ! ጥያቄያችንን ሁሉ የሚመልስ ጌታ በዙፋኑ ላይ ነው::
ዮሐንስ 4: 13-19
13፤ ኢየሱስም መልሶ እንዲህ አላት፦ “ከዚህ ውኃ የሚጠጣ ሁሉ እንደ ገና ይጠማል፤14፤ እኔ ከምሰጠው ውኃ የሚጠጣ ሁሉ ግን ለዘላለም አይጠማም፥ እኔ የምሰጠው ውኃ በእርሱ ውስጥ ለዘላለም ሕይወት የሚፈልቅ የውኃ ምንጭ ይሆናል እንጂ።”19፤ ሴቲቱ፦ “ጌታ ሆይ፥ አንተ ነቢይ እንደ ሆንህ አያለሁ።ይህች ሴት እየሱስን ከያዕቆብ ጋር እያወዳደረች ነበረ:: ኒቆዲሞስም ሆነ ይህች ሴት እየሱስ እያወራ ያለውን መንፈሳዊ ነገር አልተገለጠላቸውም:: ይህችም ሴት የደረሰችበት እውቀት ይህንን ውሃ ስጠኝና ደግሜ እዚህ እንዳልመጣ ገላግለኝ አለችው:: ይሄኔ የመሰላት ጏሮዋ የውሃ ምንጭ ሊያፈልቅልኝ ይሆናል ብላ ነው እንጂ ገና የእርሱ ትምህርት ጥልቀቱ አልገባትም:: እየሱስ:- እኔ ከምሰጠው ውኃ የሚጠጣ ሁሉ ግን ለዘላለም አይጠማም፥ አላት:: ውሃ ይሰጠናል ከእኛ የሚጠበቀው ግን መጠማትና መጠጣት ነው:: ዕለት ዕለት በመንፈስ ተሞሉ ነው የተባልነው እንድንጠጣ ይሰጠናል የሚሰጠንም በልግስና ሳይሰስት ያረካናል ከእርሱ ውጭ የሚያረካ የለም:: የምንፈልገውን ሁሉ ብናገኝና ቢትረፈረፍ የዓለም ነገር ይሰለቸንና ሌላ ፍለጋ እንሄዳለን:: እርሱ ግን ለዘላለም የሚያረካ የህይወት ምንጭ ነው ምንም በእርሱ ላይ መጨመር አያስፈልገንም ከእርሱስ ወዴት እንሄዳለን?!ሌላው:- እኔ የምሰጠው ውኃ በእርሱ ውስጥ ለዘላለም ሕይወት የሚፈልቅ የውኃ ምንጭ ይሆናል አለ:: በእኛ ውስጥ የማይቋረጥ ህይወት ይፈሳል:: ህይወት እንዲበዛልንና እንዲትረፈረፍልን መቷል! አሜን!ታላቅ መንፈሳዊ ነገር ሲነግራት ብዙም ያልገባት ሴት ህይወትዋን ግን ሲገልጠው “ጌታ ሆይ፥ አንተ ነቢይ እንደ ሆንህ አያለሁ አለች። ከያዕቆብ ያወዳደረችውን አሁን ደግሞ ነብይ ነህ አለችው:: የሚገርመኝ የዓለም ጌታና ንጉስ ቁጭ ብሎ ማኅበረሰብዋ እንኳን የማይፈልጋትን ሴት በትዕግስት ወደሚፈልገው አቅጣጫ እንድትደርስ ማስተማሩ:: እርሱ ማንንም አይንቅም አንዱንም ከአንዱ አያበላልጥም ለሁሉ እንደሚረዳው መጠን ዝቅ ብሎ ይገኛል:: እኛንም እንደዚሁ ታግሶ እዚህ አድርሶናል:: ፍቅሩ አይለወጥም ማንም ወደ እኔ ይምጣና ይጠጣ ብሎናል:: የጠራው ሁሉንም ነው:: እንጠጣ!!አባት ሆይ አንተ መልካም ነህ!! እናመሰግንሃለን አንተ አትለወጥም ዛሬ በመንፈስህ ሙላን:: ልክ እንደአንት የተጠሉትንና የማይፈለጉትን መፈለግና ወደ መንግስትህ ማምጣት ይሁንልን:: ዓይኖቻችን ይከፈቱና የምታሳየንን ማየትና መታዘዝ ይብዛልን:: አሜን!
ዮሐንስ 4: 20-27
20፤ አባቶቻችን በዚህ ተራራ ሰገዱ፤ እናንተም፦ ‘ሰው ሊሰግድበት የሚገባው ስፍራ በኢየሩሳሌም ነው፡’ ትላላችሁ፡” አለችው።21፤ ኢየሱስም እንዲህ አላት፦ “አንቺ ሴት፥ እመኚኝ፥ በዚህ ተራራ ወይም በኢየሩሳሌም ለአብ የማትሰግዱበት ጊዜ ይመጣል።22፤ እናንተስ ለማታውቁት ትሰግዳላችሁ፤ እኛ መዳን ከአይሁድ ነውና ለምናውቀው እንሰግዳለን።23፤ ነገር ግን በእውነት የሚሰግዱ ለአብ በመንፈስና በእውነት የሚሰግዱበት ጊዜ ይመጣል አሁንም ሆኖአል፤ አብ ሊሰግዱለት እንደ እነዚህ ያሉትን ይሻልና፤24፤ እግዚአብሔር መንፈስ ነው፥ የሚሰግዱለትም በመንፈስና በእውነት ሊሰግዱለት ያስፈልጋቸዋል።”25፤ ሴቲቱ፦ “ክርስቶስ የሚባል መሲሕ እንዲመጣ አውቃለሁ፤ እርሱ ሲመጣ ሁሉን ይነግረናል፡” አለችው።26፤ ኢየሱስ፦ “የምናገርሽ እኔ እርሱ ነኝ፡” አላት።ነብይ ነው ብላ ስላመነች በውስጥዋ የሚቃጠለውን እርሱም ሊመልስ የተገኘውን ጥያቄ ጠየቀች እርሱም ስለ አምልኮ ነበረ:: አባቶቻችን በዚህ ተራራ ሰገዱ፤ እናንተም፦ ‘ሰው ሊሰግድበት የሚገባው ስፍራ በኢየሩሳሌም ነው፡’ ትላላችሁ፡:: እውነቱን ንገረኝ የት ነው መመለክ ያለበት አለች? አዲስ ኪዳን አልነበረምና የሚመለከውና የሚሰገደው በእየሩሳሌም ብቻ ነበረና ሰማርያውያን መተው ማምለክ አይችሉም ነበር:: ኢየሱስም እንዲህ አላት፦ “አንቺ ሴት፥ እመኚኝ፥ በዚህ ተራራ ወይም በኢየሩሳሌም ለአብ የማትሰግዱበት ጊዜ ይመጣል አሁንም ሆኖአል አላት:: ስለዚህም ጌታ ሲመልስላት እናንተስ ለማታውቁት ትሰግዳላችሁ፤ እኛ መዳን ከአይሁድ ነውና ለምናውቀው እንሰግዳለን አላት:: በተወሰነ ስፍራ መመለክ ነበረበት:: ይህንን አሰራር ሊሽረው የመጣ ጌታ ስሙ ይባረክ:: በእየሩሳሌም ብቻ የነበረውን አምልኮ ወደ እያንዳንዳችን ልብ አምጥቶ እግዚአብሔር መንፈስ ነው፥ የሚሰግዱለትም በመንፈስና በእውነት ሊሰግዱለት ያስፈልጋቸዋል ብሎ ደመደመው ምክንያቱም አብ ሊሰግዱለት እንደ እነዚህ ያሉትን ይሻልና:: አሜን!ይህች ሴት ከውሃ ክርክር ወጥታ ከያዕቆብ ትበልጣለህ ወይ ስትለው ነበር ከዛም ደግሞ ነብይ ነህ አለችው በስተመጨረሻ ግን ተወው እንዲያውም ጥያቄዬን ሁሉ የሚመልስ የምጠብቀው አለኝ አለች:: እንዲህ ስትል፦ “ክርስቶስ የሚባል መሲሕ እንዲመጣ አውቃለሁ፤ እርሱ ሲመጣ ሁሉን ይነግረናል፡” አለችው። ይህየሚራራ ንጉስ ግን ለእርስዋ ብቻ የተናገረው ነገር ቢኖር “የምናገርሽ እኔ እርሱ ነኝ፡” አላት። ዋዉ! ለዝች ሴት ጊዜውን ሰጥቶ ማንነቱን ገለጠላት:: ጥያቄዋን ሁሉ መለሰ:: ጠብቃው ነበረና መሲህ ይመጣል ብላ ለራሱ ነገረችዉ ምን አይነት ትጋት ነው?! በተመረጡት እየተገፉ ተስፋ አድርገው እርሱን መጠበቅ?! እርሱም ስለሚያውቅ የውስጥዋን ቁጭት አይቶ ለብቻዋ እንድታመልከና ጥማትዋን እንድትወጣ አደረጋት:: መሲህ እንደሆነ ገለጠላት: አባት ሆይ ክብር ለአንተ ይሁን ይህንን እውነት ስለገለጥክልን:: አንተን በውስጣችን የትም ሳንሄድ በመንፈስና በእውነት እናመልክህ ዘንድ መቅደስህ ላደረከን ጌታ ክብር ይሁንልህ:: ለዘላለም ግዛን! የምናመልክበትን መንፈስ አፍስስልን! አሜን
ዮሐንስ 4: 28-30
28፤ ሴቲቱም እንስራዋን ትታ ወደ ከተማ ሄደች ለሰዎችም፦29፤ “ያደረግሁትን ሁሉ የነገረኝን ሰው ኑና እዩ፤ እንጃ እርሱ ክርስቶስ ይሆንን?” አለች።30፤ ከከተማ ወጥተው ወደ እርሱ ይመጡ ነበር።ኢየሱስ፦ “የምናገርሽ እኔ እርሱ ነኝ፡” ባላት ጊዜ እንስራዋን ትታ ወደ ከተማ ሄደች ስለ እየሱስ ለመመስከር:: ይህ ሰው ክርስቶስ ይሆንን? እያለች መሰከረች:: የመጣችበት በኃላ ላይ የሚያስፈልጋት ውሃም ትዝ አላላትም:: እየሱስ ሲመጣ ምን ይወዳደረዋል ይህንን ልጨምር በእርሱ ላይ አንልም ሁሉንም ጥለን ነው ተከትለነው የምንሮጠው:: በእውነት ዛሬ ተከትለን መሮጥ ይሁንልን እውቀታችን ልምዳችን ሳንል ህይወቴን የቀየረውን ኑና እዮ ማለት ይሁንልን::ጳውሎስም ምንም በገማልያ እግር ስር የተማረና ብዙ እውቀት የነበረው ቢሆንም ሁሉንም ጥሎ ባዶ እራሱን አድርጎ ነበረ:: 1 ቆሮንቶስ 2:1፤ እኔም፥ ወንድሞች ሆይ፥ ወደ እናንተ በመጣሁ ጊዜ በቃልና በጥበብ ብልጫ ለእግዚአብሔር ምስክርነቴን ለእናንተ እየነገርሁ አልመጣሁም። 2፤ በመካከላችሁ ሳለሁ ከኢየሱስ ክርስቶስ በቀር እርሱም እንደተሰቀለ ሌላ ነገር እንዳላውቅ ቆርጬ ነበርና።ዛሬ መጣል ያልቻልነው ምንድነው? ሃብት: መልክ: እውቀት: ወገን: ችሎታ: ገቢያችን . . . እየሱስ ሲመጣ ጥለን እንሮጣለን እርሱን እንጂ እራሳችንን አናሳይም:: እርሱን ያየ ያስታውቃል እየሱስን እዮ የሚል ቀስት ብቻ ይሆናል:: ጌታ ይገለጥልንና በእርሱ ላይ ጨምረን የያዝነውን አስጥሎ እርሱን ብቻ የምናሳይ ያድርገን:: አባት ሆይ እርዳን! እራስህን ግለጥልን እንወቅህ::አሜን
ዮሐንስ 4: 31-38
31፤ ይህም ሲሆን ሳለ ደቀ መዛሙርቱ፦ “መምህር ሆይ፥ ብላ፡” ብለው ለመኑት።32ግንድ34፤ ኢየሱስም እንዲህ አላቸው፦ “የእኔስ መብል የላከኝን ፈቃድ አደርግ ዘንድ ሥራውንም እፈጽም ዘንድ ነው።37፤ አንዱ ይዘራል አንዱም ያጭዳል የሚለው ቃል በዚህ እውነት ሆኖአልና።38፤ እኔም እናንተ ያልደከማችሁበትን ታጭዱ ዘንድ ሰደድኋችሁ፤ ሌሎች ደከሙ እናንተም በድካማቸው ገባችሁ።”ከሳምራዊትዋ ጋር መነጋገሩን ሲጨርስ ደቀመዛሙርቱ ከሄዱበት ተመለሱ ያመጡትንም ምግብ ጋበዙት:: እርሱ ግን፦ “እናንተ የማታውቁት የምበላው መብል ለእኔ አለኝ አላቸው:: እርሱ ምግብ የሚለውና እነሱ ምግብ የሚሉት የተለያየ ነገር ሆነ:: ስጋውያን ነበሩና መንፈሳዊዉን አሳብ መረዳት አልቻሉም:: የእግዚአብሔርን አሳብ የምንረዳው በመንፈሱ ነው እንጂ በእኛ በራሳችን አይደልም:: ለሴቲቱ እንዳለው እርሱ በመንፈስና በእውነት የሚመለክ ጌታ ነው::መብሉ ምን እንደሆነ ባያብራራልን ኖሮ እኛም እንደነርሱ የሆነ ምክንያት ሰተን እናልፍ ነበር:: እየሱስ ግን የእኔስ መብል የላከኝን ፈቃድ አደርግ ዘንድ ሥራውንም እፈጽም ዘንድ ነው።ይህ የመንግስቱ ስራ ነው እርሱን የሚያረካው:: ምግብን ስናስብ ጉልበት የሚሆነን: የሚያረካን: ስንጠግብም ሌላ እንዳንፈልግ የሚያደርግ ነው:: ይህንን ሁሉ ፈቃዱን በማድረግ ተካው:: ጀምሮም አልሄደ ብትወድ ይህች ጽዋ ከእኔ ትለፍ ብሎ ነበር ነገር ግን ለዚህ መጥቻለሁ ብሎ ፈቃድህ ይሁን እያለ እራሱን ስቶ የአባቱን ፈቃድ ፈጽሞ አከበረው:: በመስቀልም ላይ ተፈፀመ ብሎ አወጀ:: አሜን ተፈጸመ!በመስቀል ላይ ዋጋ መክፈሉ የሚያሳየው ያልደከማችሁበትን ታጭዱ ዘንድ ሰደድኋችሁ፤ ሌሎች ደከሙ እናንተም በድካማቸው ገባችሁ። እንዳለው እኛ ዛሬ የምናጭደው እርሱ የለፋበትን ስለእርሱ ሲናገሩና ሲመሰክሩ የነበሩት ነብያት የሞቱለትን ስራ ነው:: በዚህም ውስጥ የአካል ስራ ይታያል እርሱንም የሚሰራው በመንፈሱ ነው:: አንዱ ይዘራል አንዱም ያጭዳል የሚለው ቃል በዚህ እውነት ሆኖአልና። አባት ሆይ ፈቃድህን ማድረግና መታዘዝ ይብዛልን አንተን እንዳረካህ እኛም በዚህ እንርካ እንጂ ሌላ የሚያረካ ፍለጋ እንዳንባዝን የሚያስፈልገውን አንድ ነገር ስጠን በእግርህ ስር መገኘት! አሜን!
ዮሐንስ 4: 39-42
39፤ ሴቲቱም፦ “ያደረግሁትን ሁሉ ነገረኝ፡” ብላ ስለ መሰከረችው ቃል ከዚያች ከተማ የሰማርያ ሰዎች ብዙ አመኑበት።
40፤ የሰማርያ ሰዎችም ወደ እርሱ በመጡ ጊዜ በእነርሱ ዘንድ እንዲኖር ለመኑት፤ በዚያም ሁለት ቀን ያህል ኖረ።
41፤ ስለ ቃሉ ከፊተኞች ይልቅ ብዙ ሰዎች አመኑ፤
42፤ ሴቲቱንም፦ “አሁን የምናምን ስለ ቃልሽ አይደለም፥ እኛ ራሳችን ሰምተነዋልና፤ እርሱም በእውነት ክርስቶስ የዓለም መድኃኒት እንደ ሆነ እናውቃለን፡” ይሉአት ነበር።
ሳምራይትዋ ሴት እየሱስን አስተዋውቃዋለች ሳታፍርና ሳትደብቅ:: “ያደረግሁትን ሁሉ ነገረኝ፡” እያለች ስለእርሱ መሰከረች:: እኛም ስላደረገልን ነገር መመስከርና እርሱን ማሳየት አለብን::
የሰማርያ ሰዎች እርስዋን ሰምተው የመጡ ቢሆኑም ቅሉ እራሳቸው ቁጭ ብለው ተምረው ስለእርሱ መሰከሩ:: ሴቲቱንም፦ “አሁን የምናምን ስለ ቃልሽ አይደለም፥ እኛ ራሳችን ሰምተነዋልና፤ እርሱም በእውነት ክርስቶስ የዓለም መድኃኒት እንደ ሆነ እናውቃለን፡” ይሉአት ነበር። እራሱን የሚያሳይ ጌታ ነው::
ሳምራውያኑ የተረዱበት አረዳድ
1. በእውነት ክርስቶስ ነው
2. የዓለም መድኃኒትነው
ከመጥምቁ ዮሃንስ ቀጥሎ ለዓለም እንደመጣ አወቁ:: እነርሱም በእስራኤሎቹ ተቀባይነት አልነበራቸውምና:: ጌታ ግን በእኛ ዘንድ ቆይ ሲሉት ሁለት ቀን አደረ:: በዘመኑ የነበሩት እስራኤሎች ግን እንኳን ሁለት ቀን ሊያድሩ ይቅርና በዛ በኩል አያልፉም ነበር ተጠይፈው:: እርሱ ግን የጥልን ግድግዳ አፍርሶ አንድን ሰው ለመፍጠር መጣ:: ሁሉ በክርስቶስ አንድ ነው:: አሜን! ፊሊጶስም ሲያገለግላቸው ከተማይቱ ተገለባበጠች የእርሱን ማዳን የተቀበሉ ነበሩና::
አአባት ሆይ ውጫዊ ማንነትን ሳናይ ዓይንህና ልብህ ባለበት የእኛም እንዲሆን ያደረክልንን ሁሉ እንድንመሰክር በኃይልና በግልጥነት እንድንመሰክርና እንድናገለግልህ እርዳን:: አሜን
ዮሐንስ 4: 43-45
43፤ ከሁለቱ ቀኖችም በኋላ ከዚያ ወጥቶ ወደ ገሊላ ሄደ።
44፤ ነቢይ በገዛ አገሩ እንዳይከበር ኢየሱስ ራሱ መስክሮአልና።
45፤ ወደ ገሊላም በመጣ ጊዜ፥ የገሊላ ሰዎች ራሳቸው ደግሞ ለበዓል መጥተው ነበርና በበዓል በኢየሩሳሌም ያደረገውን ሁሉ ስላዩ ተቀበሉት።
ሁለት ቀን በሳምራውያን ዘንድ ከቆየ በኃላ ወደ ገሊላ መጣ:: የገሊላ ሰዎች እየሱስን እንደመቀበል አድርጉ ምክንያቱም በኢየሩሳሌም ያደረገውን ስላዩ:: ያደረገውም አንዱ ነገር ቤተመቅደሱን ማጥራት ነበር ቤቴን የወንበዴዎች ዋሻ አደረጋችሁ ብሎ በቁጣ አስወጥቶ ነበረ:: እንደዚሁም ደግሞ ያልተመዘገበ ተአምራትን አድርጎ ነበረና ነው:: በዮሐንስ 2:23፤ በፋሲካ በዓልም በኢየሩሳሌም ሳለ፥ ያደረገውን ምልክት ባዩ ጊዜ ብዙ ሰዎች በስሙ አመኑ::
በገሊላ ውሃውን የወይን ጠጅ አድርጎ ቀይሮ ነበረ ነገር ግን እንኳን ህዝቡ የድግሱ ባለቤት ሙሽራውም አላወቀም ነበር:: እዚህ ላይም ሰው የተቀበለው ከእየሩሳሌሙ ተአምራት የተነሳ እንጂ በመካከላቸው ያደረገውን አያውቁም ነበረ አይ መተላለፍ:: እርሱ ብዙ ግርግር ሳያስነሳ ማገልገል ነበረ የሚፈልገው ስለዚህም ከስፍራ ወደ ስፍራ ይንቀሳቀስ ነበረ:: የገሊላ ሰዎች እንደመሲህ ለመቀበል ይከብዳቸዋል ምክንያቱም እንደማንኛውም ልጅ ሲያድግ ስላዮት እናትና አባቱን የምናውቃቸው አይደሉም እንዴ ወደ ማለት ነው የሚመጡት:: ነቢይ በገዛ አገሩ እንዳይከበር ኢየሱስ ራሱ መስክሮአልና። ለእኛ ግን ይህ የከበረ ጌታ የሌለን እንዳለ አድርጎ የሚጠራ ጌታ ስለእኛ ዝቅ ብሎ ተዋርዶ እራሱን ባዶ አድርጎ እንደመጣ ያሳየናል:: እነርሱ ባይቀበሉት እኛ ግን የህይወታችን ጌታ ነው ብለን ይህንን መሲህና አዳኝ ሾመነዋል:: እንዳያረጅብን እርሱ ማለዳ ማለዳ አዲስ ነው ህይወት እንዲበዛልን መቷል::
አባት ሆይ እራስህን ባዶ አድርገህ የባርያን መልክ ይዘህ ስለመጣህና ስለታደገን ተመስገን!! ሃሌሉያ!!
ዮሐንስ 4: 46-54
46፤ ኢየሱስም ውኃውን የወይን ጠጅ ወዳደረገባት ወደ ገሊላ ቃና ዳግመኛ መጣ። በቅፍርናሆምም ልጁ የታመመበት ከንጉሥ ቤት አንድ ሹም ነበረ።
47፤ እርሱም ኢየሱስ ከይሁዳ ወደ ገሊላ እንደ መጣ ሰምቶ ልጁ ሊሞት ስላለው ወደ እርሱ ሄደ ወርዶም እንዲፈውስለት ለመነው።
48፤ ስለዚህም ኢየሱስ፦ “ምልክትና ድንቅ ነገር ካላያችሁ ከቶ አታምኑም፡” አለው።
49፤ ሹሙም፦ “ጌታ ሆይ፥ ብላቴናዬ ሳይሞት ውረድ፡” አለው።
50፤ ኢየሱስም፦ “ሂድ፤ ልጅህ በሕይወት አለ፡” አለው። ሰውዬውም ኢየሱስ የነገረውን ቃል አምኖ ሄደ።
53፤ አባቱም ኢየሱስ፦ “ልጅህ በሕይወት አለ፡” ባለው በዚያ ሰዓት እንደ ሆነ አወቀ፤ እርሱም ከቤተ ሰዎቹ ሁሉ ጋር አመነ።
54፤ ይህም ደግሞ ኢየሱስ ከይሁዳ ወደ ገሊላ መጥቶ ያደረገው ሁለተኛ ምልክት ነው።
እየሱስ በገሊላ መሆኑን ሲሰማ አንድ አህዛብ የሆነ የንጉስ ሹም ልጁ ስለታመመበት ወደ ጌታ መጣ:: ኢየሱስ፦ “ምልክትና ድንቅ ነገር ካላያችሁ ከቶ አታምኑም፡” አለው። ምክንያቱም ሰውየው የፈለገው እየሱስ አብሮት እንዲመጣ ነው:: የጨነቀው አባት ስልጣኑና ማዕረጉ ምንም የማይጠቅምበት አጣብቂኝ ሰዓት ላይ ነውና ደግሞ ለመነ ሊሞትብኝ ነውና እባክህ:: ያለን ነገር ገንዘብ ቢሆን ዝና ቢሆን ጤና ቢሆን ወገን ቢሆን ሌላም ሌላም የሚያስመካ አይደለም መታመን ያለብን በጌታ ብቻ ነው:: ዓይናችን በንጉሱ ላይ ይሁኑ::
በዚህ ስፍራ እንደምናየው ብዙዎች መተው ተአምራት ሆኖላቸዋል የተአምራቱን ጌታ ግን ሳይተዋወቁት ቀርተዋል:: ይህም ሰው የፈለገው የልጁን መዳን ብቻ ነው:: ነገር ግን እንደባለስልጣን ሆኖ አይደለም በጌታ ፊት የቀረበው እርዳታ እንደሚፈልግ የተጨነቀ አባት እንጂ:: የፈለገውም የልጁን መፈወስ ነው ጌታም በቃል ላይ ብቻ እንዲደገፍ ቃል ነው የሰጠው “ሂድ፤ ልጅህ በሕይወት አለ” አለው። ሞትን በህይወት የሚለውጥ ጌታ! ያለ እምነት እግዚአብሔርን ደስ ማሰኘት አይቻልም::
ሰውዬውም ኢየሱስ የነገረውን ቃል አምኖ ሄደ። ይህ ሰውአህዛብ ነው ግን አምኖ ሄደ?! ይገርማል መታመኑ እንደዘመናችን ስልክ የለ ደወል አድርጎ አጣርቶ አያውቅ የሚሄደውም መንገድ ረጅም ነው:: ነገር ግን የተነገረውን ቃል አምኖ ሄደ እርሱም አላፈረም:: አባቱም ፈውሱ የሆነው ኢየሱስ፦ “ልጅህ በሕይወት አለ፡” ባለው በዚያ ሰዓት እንደ ሆነ አወቀ፤ ሳይዘገይ ቃሉ ገና ከአፉ ሲወጣ ነው ፈውሱ የሆነው:: እርሱም ከቤተ ሰዎቹ ሁሉ ጋር አመነ። ይህ ተአምር የዚህን ሰውና የቤተሰቡን ሁሉ እምነት በእየሱስ ላይ እንዲያደርጉ አደረጋቸው::
በገሊላ ይህ ሁለተኛ ተአምር ነው ይላል ቃሉ ከዚህ የበለጠ ማየት ሲችሉ የገሊላ ሰዎች ግን ይህንን ንጉስ አላወቁትም:: አምላካችን በስራ ላይ ነው:: ተአምራትን ማድረግ ሰዎችን ወደ ክርስቶስ ያመጣልና የተለያዩ ጸጋዎች በቅዱሳን መካከል መገለጥ አለባቸው::
አባት ሆይ አንተ ዛሬም ትፈውሳለህ ወደ ቤትህ ሰዎችን በየምክንያቱ ትጠራለህና እያንዳንዳችንን ተጠቀምብን በእኛ ውስጥ ያስቀመጥከው ጸጋ ይውጣና አንተ የህይወት ራስ ብቻህን ታይ:: አሜን!
ዮሐንስ 5: 1-4
1፤ ከዚህ በኋላ የአይሁድ በዓል ነበረ፥ ኢየሱስም ወደ ኢየሩሳሌም ወጣ።
2፤ በኢየሩሳሌምም በበጎች በር አጠገብ በዕብራይስጥ ቤተ ሳይዳ የምትባል አንዲት መጠመቂያ ነበረች፤ አምስትም መመላለሻ ነበረባት።
3፤ በእነዚህ ውስጥ የውኃውን መንቀሳቀስ እየጠበቁ በሽተኞችና ዕውሮች አንካሶችም ሰውነታቸውም የሰለለ ብዙ ሕዝብ ይተኙ ነበር።
4፤ አንዳንድ ጊዜ የጌታ መልአክ ወደ መጠመቂያይቱ ወርዶ ውኃውን ያናውጥ ነበርና፤ እንግዲህ ከውኃው መናወጥ በኋላ በመጀመሪያ የገባ ከማናቸው ካለበት ደዌ ጤናማ ይሆን ነበር።
እየሩሳሌምን ስናስብ ጌታ የመሰረተው መንግስት የኖረበት፤ መስዋዕት የሚቀበልበትና የሚናገርበት ቤተመቅደሱ ያለበት፤ በስጋም የተወለደበት፤ የኖረበት፤ የተቀበረበትና ያረገበት ዳግምም የሚመጣበት ርንዲሁምቤተክርስትያን የተወለደችበት ስፍራ ነው::
በዓልን ለማክበር ሁሉም ወደ እየሩሳሌም ይሰበሰባል እየሱስም ለበዓል ወደ እየሩሳሌም ብቅ ይላል አብዛኛው እስራኤላዊ እንደሚያደርገው ሁሉ:: የእርሱ መምጣት ግን አንድም ቤተመቅደሱን ከወንበዴዎች ለማጽዳት ወይም ለማስተማርና ለመፈወስ ነው::
ይህ አምላክ ይገርማል በዚሁ በእየሩሳሌም ቤተ ሳይዳን አዘጋጅቷል:: ያዘጋጀበትም ምክንያት መፍትሄ ለህዝቡ ለመስጠት ነው እንዲፈወስ:: አምላካችን ፈዋሽ ነው:: መልአኩ መጥቶ ሲያናውጠው ፈውስ ይሆናል:: ይህንን መጠመቅያ ሳያዳላ ለሁሉ ሰጠ ማንምቀድሞ ከገባ ከማንኛውም ህመም ይፈወሳል::
አባት ሆይ አንተ ዛሬም ሳታዳላ የምትፈውስ የህዝህን ጭንቅ መገላገል የምትፈልግ ነህና ለዚህም ተገርፈሃል በመገረፍህም ቁስል ተፈውሰናል! ተመስገን!!
ዮሐንስ 5: 5-9
5፤ በዚያም ከሠላሳ ስምንት ዓመት ጀምሮ የታመመ አንድ ሰው ነበረ፤
6፤ ኢየሱስ ይህን ሰው ተኝቶ ባየ ጊዜ፥ እስከ አሁን ብዙ ዘመን እንዲሁ እንደ ነበረ አውቆ፦ “ልትድን ትወዳለህን?” አለው።
7፤ ሰውዩም፦ “ጌታ ሆይ፥ ውኃው በተናወጠ ጊዜ በመጠመቂያይቱ ውስጥ የሚያኖረኝ ሰው የለኝም ነገር ግን እኔ ስመጣ ሳለሁ ሌላው ቀድሞኝ ይወርዳል፡” ብሎ መለሰለት።
8፤ ኢየሱስ፦ “ተነሣና አልጋህን ተሸክመህ ሂድ፡” አለው።
9፤ ወዲያውም ሰውዬው ዳነ አልጋውንም ተሸክሞ ሄደ።
እየሱስ ወደዚህ መጠመቅያ ስፍራ ሲመጣ ቀጠሮው በዚያም ለሠላሳ ስምንት ዓመት ለታመመ አንድ ሰው ነበረ:: እስኪ ወደኃላ እናስበው ሰላሳ ስምንት ዓመት ምንምን አደረግንበት? ስንት ቦታ ደረስን ስንቱን አደረግን:: እርሱ ግን እዛው አንድ ቦታ ሆኖ ሌሎች ሲፈዉሱና እየተደሰቱ ሲሄዱ ነው የሚመለከተው:: እርሱ ገና ወደ ውሃው ለመሄድ ሲሞክር ሌሎች ገብተው ይፈወሳሉ:: እንዴት ተስፋ ቆርጦ ጥሎ አልሄደም? ምናልባትም መሄጃ የለው ይሆናል ማንም የሚረዳውም የሌለው ለዛም ይሆናል:: በጌታ ፊት ግን ታሰበ ይህ ማንም ምንም የሌለው ሰው::
ኢየሱስ ይህን ሰው ተኝቶ ባየ ጊዜ፥ እስከ አሁን ብዙ ዘመን እንዲሁ እንደ ነበረ አውቆ፦ “ልትድን ትወዳለህን?” አለው። ምን አይነት ጥያቄ ነው? መቼም እዚህ እየጠበቀ ያለው ፈውስ ነው:: እየሱስም ጠፍቶት አይደለም ከውሃው ላይ ዓይኑን አንስቶ በእርሱ ላይ እንዲያደርግ ቢሆንም ሰውየው ግን ዓይኑ በውሃው ላይ ነበረና ሰውዩም፦ “ጌታ ሆይ፥ ውኃው በተናወጠ ጊዜ በመጠመቂያይቱ ውስጥ የሚያኖረኝ ሰው የለኝም ነገር ግን እኔ ስመጣ ሳለሁ ሌላው ቀድሞኝ ይወርዳል፡” ብሎ መለሰለት።
ኢየሱስ፦ “ተነሣና አልጋህን ተሸክመህ ሂድ፡” አለው። ከውሃው ላይ ዓይንህን አንሳ ውሃውን እንዲያናውጥ መልአኩን የሚልከው በአጠገብህ ቆሟል!! ዛሬም እኛ ዓይናችን በምን ላይ ነው?! በእየሱስ ላይ ይሁን:: መምጣቱንም እንደዚህ እንጠባበቅ:: እየሱስ ይመጣል!!
ወዲያውም ሰውዬው ዳነ አልጋውንም ተሸክሞ ሄደ። ይህ ሰው ሲፈወስ ብዙዎች በዛ ነበሩ ዓይናቸው ግን በውሃ ላይ ሆኖ ይህንን የህይወት ጌታ አላዮትም! ያሳዝናል:: እኛ ከዝች ክፉ ዓለም ድነን ህይወትን ስናገኝ አጠገባችን ያሉት አላዮትም አሾፉብን አላገጡብን:: እኛስ የተገለጠልንን ይህንን የህይወት ራስ አወቅን ዳንን እርፍ አልን:: ስሙ ይባረክ! ለጠፉት እንፀልይ!
አባት ሆይ ስምህ ይባረክ እኔን ፈልገህ ስለመጣህ አንተንም ማወቅ ስለሆነልኝ አመሰግንሃለሁ:: በዙሪያዬ ያሉትን አስብ ወደ መዳንም ይመጡ ዘንድ አንተን ማወቅ ይሆንላቸው ዘንድ እፀልያለሁ::
ዮሐንስ 5: 10-18
10፤ ያም ቀን ሰንበት ነበረ። ስለዚህ አይሁድ የተፈወሰውን ሰው፦ “ሰንበት ነው አልጋህንም ልትሸከም አልተፈቀደልህም፡” አሉት።
ዮሐንስ 5:11፤ እርሱ ግን፦ “ያዳነኝ ያ ሰው፦ ‘አልጋህን ተሸክመህ ሂድ፥’ አለኝ” ብሎ መለሰላቸው።
ዮሐንስ 5:12፤ እነርሱም፦ “ ‘አልጋህን ተሸክመህ ሂድ፡’ ያለህ ሰው ማን ነው?” ብለው ጠየቁት።
ዮሐንስ 5:13፤ ዳሩ ግን በዚያ ስፍራ ሕዝብ ሰለ ነበሩ ኢየሱስ ፈቀቅ ብሎ ነበርና የተፈወሰው ሰው ማን እንደ ሆነ አላወቀም።
ዮሐንስ 5:14፤ ከዚህ በኋላ ኢየሱስ በመቅደስ አገኘውና፦ “እነሆ፥ ድነሃል፤ ከዚህ የሚብስ እንዳይደርስብህ ወደ ፊት ኃጢአት አትሥራ፡” አለው።
ዮሐንስ 5:17፤ ኢየሱስ ግን፦ “አባቴ እስከ ዛሬ ይሠራል፡ እኔም ደግሞ እሠራለሁ፡” ብሎ መለሰላቸው።
ይህ በመጥመቅያው አጠገብ ለመፈወስ ሰላሳ ስምንት ዓመት ሲጠብቅ የነበረው ሰው መፈወሱ የአይሁድን አለቆች አልገረማቸውም ወይም ከእርሱ ጋር ደስ አላላቸውም:: የፈወሰውን ግን ለማወቅ ፈለጉ ሊያደንቁትና አብረው ሊተባበሩ ሳይሆን ሊከሱት:: ህግ እንደዚህ ነው ርህራሄ የለውም እኛ ግን ከህግ ነፃ ወተን ከፀጋ በታች ሆነናል:: ህግ ይከሳል ያሳጣል እንጂ አይረዳም ስራው ሁሉ መክሰስ ነው:: እነዚህ ሰዎች በህግ ታጥረው የህጉን ባለቤት እንኳን ማወቅ አልቻሉም:: ዓይናቸው በማይሆን ነገር ተይዟል:: ይህ ርህሩህ ጌታ ግን ይህንን ሰው አይቶት መጣ አጠገቡ ያልሉት እግዚአብሔርን እናገለግላለን ያሉት ግን ምንም ግድ አላላቸውም በመፈወሱም ባለመፈወሱም:: ጌታ ይባረክ የሚያየን ዛሬም እኛን ተጠቅሞ ለሌሎች መድረስ የሚፈልግ ጌታ::
እየሱስ እየሸሸ ያለው እነዚህን የህግ መምህራን ነው አላሰራ ስላሉት ከአንዱ ቦታ ወደ ሌላ እየሄደ ነው የሚያስተምረው:: እዚህ ስፍራ ላይ ይህንን ሰው ሲያገኘው የነገረው ነገር በኃጥያት እንዳትመላለስና የከፋ እንዳይገጥምህ ነው:: በፀጋ ዘመን ነው የምኖረውና ምናለበት እንደፈለኩ ብመላለስ ብሎ ነገር የለም:: እራሳችንን ለጌታ አስገዝተን እርሱን እያከበርን ዓለምን ንቀን እንመላለሳለን::
አምላካችን በስራ ላይነው: ኢየሱስ ግን፦ “አባቴ እስከ ዛሬ ይሠራል፡ እኔም ደግሞ እሠራለሁ፡” ብሎ መለሰላቸው።
አባት ሆይ ስለምህረትህና ርህራሄህ ተመስገን የእኛ ነገር ግድ ስለሚልህ ተባረክ:: የአንት ዓይን ባለበት የእኛም ይሁን:: አንተ በምትሰራበት ሰዓት እኛንም ገንዘቦችህ አድርገን:: አሜን
ዮሐንስ 5: 18-19
18፤ እንግዲህ ሰንበትን ስለ ሻረ ብቻ አይደለም፥ ነገር ግን ደግሞ ራሱን ከእግዚአብሔር ጋር አስተካክሎ፦ “እግዚአብሔር አባቴ ነው፡” ስላለ፥ ስለዚህ አይሁድ ሊገድሉት አብዝተው ይፈልጉት ነበር።
19፤ ስለዚህ ኢየሱስ መለሰ፥ እንዲህም አላቸው፦ “እውነት እውነት እላችኋለሁ፥ አብ ሲያደርግ ያየውን ነው እንጂ ወልድ ከራሱ ሊያደርግ ምንም አይችልም፤ ያ የሚያደርገውን ሁሉ ወልድ ደግሞ ይህን እንዲሁ ያደርጋልና።
“እግዚአብሔር አባቴ ነው፡” ብሎ ስላለ አይሁድ ሊገድሉት አብዝተው ይፈልጉት ነበር ይላል:: ለምን ቢባል አስርቱ ትዕዛዛት ለእነርሱ ከባድ ነገር ነውና:: አምላክህን ብቻ አምልክ ወይም እርሱን በፍፁም ማንነትህ ውደድ በምንም ምስል እንዳትመስለው ተብለው እያለ ይህ ሰው እኔ የእግዚአብሔር ልጅ ነኝ ብሎ እራሱን ሲያቀራርብ አልዋጥላቸው አለ:: እንዲያውም ሊገድሉት ፈለጉ:: አይፈረድባቸውም በእነርሱ ቤት ለጌታቸው መቆማቸውን ነው የሚያዩት:: በመካከላቸው የቆመው ማን እንደሆነ አላወቁም::
ስለዚህ ኢየሱስ መለሰ፥ እንዲህም አላቸው፦ “እውነት እውነት እላችኋለሁ፥ አብ ሲያደርግ ያየውን ነው እንጂ ወልድ ከራሱ ሊያደርግ ምንም አይችልም:: ይህ ማለት ግን በዮሐንስ 15:5፤ እኔ የወይን ግንድ ነኝ እናንተም ቅርንጫፎች ናችሁ። ያለ እኔ ምንም ልታደርጉ አትችሉም ካለው ጋር እንዳናስተያየው ምክንያቱም በዮሐንስ 10:30፤ እኔና አብ አንድ ነን።” ብሏል:: ልጅ ነኝ በማለቱ የተቆጡት ሰዎች እርሱ እግዚአብሔር መሆኑን ባወቁ:: እግዚአብሔር መንፈስ ነው አብን ለብቻ ወልድን ለብቻ መንፈስ ቅዱስን ለብቻ እንዳናይ ምክንያቱም ለጭንቅላታችን ያ ይመቸዋል:: አምላካችን በሶስትነት የተገለጠ አንድ አምላክ ነውና:: ዛሬም በእኛ ውስጥ ያለው መንፈስ ቅዱስ እርሱ እግዚአብሔር ነው:: እርሱ በእኛ ውስጥ ሆኖ ተቀባይነትን እንዳገኘንና ልጅ እንደሆንን ይመሰክርልናል:: እርሱ ልጅ ካለን የሚሽር ማነው?! ግን ከአምላካችን ጋር አንስተያይም እንዳንዳንድ የስህተት ትምህርት:: የእርሱ በእኛ በመኖር ነው ለውጥን ያመጣው:: እርሱን እናብለጭልጨው! እየሱስ ይታይ መንፈስ ቅዱስም ይስራና ይግለጠው::
አባት ሆይ በዚህ ምድር ያለነው የአንተን ስራ ለመስራት ነውና መንፈስ ቅዱስ በሙላት የመንግስትህን ዓላማ በእኛ ፈጽም:: እየሱስንም አክብረው ያለ አንተ አንዳች ማድረግ አንችልምና::
ዮሐንስ 5: 20-23
20፤ አብ ወልድን ይወዳልና፥ የሚያደርገውንም ሁሉ ያሳየዋል፤ እናንተም ትደነቁ ዘንድ ከዚህ የሚበልጥ ሥራ ያሳየዋል።
21፤ አብ ሙታንን እንደሚያነሣ ሕይወትም እንደሚሰጣቸው፥ እንዲሁ ወልድ ደግሞ ለሚወዳቸው ሕይወትን ይሰጣቸዋል።
22-23፤ ሰዎች ሁሉ አብን እንደሚያከብሩት ወልድን ያከብሩት ዘንድ፥ ፍርድን ሁሉ ለወልድ ሰጠው እንጂ አብ በአንድ ሰው ስንኳ አይፈርድም። ወልድን የማያከብር የላከውን አብን አያከብርም።
አብ ወልድን ይወዳልና እንደሚል ወልድን በወደደበት ፍቅር እኛንም ወደደን! በዮሐንስ 17:26፤ እኔንም የወደድህባት ፍቅር በእነርሱ እንድትሆን እኔም በእነርሱ፥ ስምህን አስታወቅኋቸው አስታውቃቸውማለሁ።”
አብ ለወልድ የሚያደርገውንም ሁሉ ያሳየዋል፤ እናንተም ትደነቁ ዘንድ ከዚህ የሚበልጥ ሥራ ያሳየዋል። እኔና አብ አንድ ነን እኔን ያየ አብን አየ እያለን መልሶ ደግሞ እርሱ ነው የሚያሳየኝ ለምን ይላል? እየሱስ እራሱን ባዶ አድርጎና የባርያን መልክ ይዞ ክብሩን ሁሉ ጥሎ መጣና ሰው ሆነ ስለዚህም በእግዚአብሔርና በሰው ፊት አደገ እንደሚል:: ምን አይነት ፍቅር ነው ሁሉን አስጥሎ የሚያስመጣ? እየሱስ እግዚአብሔር ነው:: አብ የሚያደርገውን ሁሉ ወልድም ያደርጋል:: ህይወትን የሚሰጥ የህይወት ምንጭ ነውና::
ፍርድ ሁሉ ለወልድ ተሰጠው በሰው ልጅ ላይ የሚፈርድ እርሱ ነው:: ከዚህም ፍርድ በደሙ ዋጅቶ አተረፈን የእርሱ ፅድቅ ለእኛ ተቆጠረ!! በአጭሩ ወልድን የማያከብር የላከውን አብን አያከብርም። እርሱ ከአብ ተልኮ ወደእኛ መቷልና!
አባት ሆይ ተመስገን ስለእኛ ብለህ ክብርህን ጥለህ እራስህንም ባዶ አድርገህ በእንጨት ላይ ተሰቅለህ የእርግማንን ሞት ስለእኛ ሞተህ የታደከን ከፍርድ ያስመለጥከን እጅግ የወደድከን ጌታ ነህና ተባረክ!!!!!
ዮሐንስ 5: 24-29
24፤ እውነት እውነት እላችኋለሁ፥ ቃሌን የሚሰማ የላከኝንም የሚያምን የዘላለም ሕይወት አለው፥ ከሞትም ወደ ሕይወት ተሻገረ እንጂ ወደ ፍርድ አይመጣም።
25፤ እውነት እውነት እላችኋለሁ፥ ሙታን የእግዚአብሔርን ልጅ ድምፅ የሚሰሙበት ሰዓት ይመጣል እርሱም አሁን ነው፤ የሚሰሙትም በሕይወት ይኖራሉ።
26፤ አብ በራሱ ሕይወት እንዳለው እንዲሁ ደግሞ ለወልድ በራሱ ሕይወት እንዲኖረው ሰጥቶታልና።
27፤ የሰው ልጅም ስለ ሆነ ይፈርድ ዘንድ ሥልጣን ሰጠው።
28-29፤ በመቃብር ያሉቱ ሁሉ ድምፁን የሚሰሙበት ሰዓት ይመጣል፤ መልካምም ያደረጉ ለሕይወት ትንሣኤ ክፉም ያደረጉ ለፍርድ ትንሣኤ ይወጣሉና በዚህ አታድንቁ።”
ቃሉ የከበረ ነው:: ቃሌን የሚሰማ የላከኝንም የሚያምን
የዘላለም ሕይወት አለው፥
ከሞትም ወደ ሕይወት ተሻገረ
ወደ ፍርድ አይመጣም።
ይህ የሆነልን ነገር እንጂ ገና የሚህን ጊዜ የሚጠብቅ ነገር አይደለም:: ህይወት ተሰጠን ፍርድ ተነሳልን ሞትም ከእኛ ተለየ በስብከት ሞኝነት ቃሉን ሰምተን አምነን ተቀበልን! ስሙ ይባረክ!
በዚህ ምድር የሚኖሩ ሰዎች ክርስቶስን ካላወቁ የእግዚአብሔር ቃል ሙታን ነው የሚይላቸው:: ስለዚህም ሙታን የእግዚአብሔርን ልጅ ድምፅ የሚሰሙበት ሰዓት ይመጣል እርሱም አሁን ነው፤ የሚሰሙትም በሕይወት ይኖራሉ። እርሱ ወደ ምድር በመምጣቱ ይህ ለውጥ መጣ:: ሙታን ድምጹን ሰምተው በህይወት መኖር:: ይህም የሆነው አብ በራሱ ሕይወት እንዳለው እንዲሁ ደግሞ ለወልድ በራሱ ሕይወት እንዲኖረው ሰጥቶታልና። ስለዚህ እየሱስ ህይወትን ሰቶን ሙታንን ወደእኔ አምጡ በህይወት እንዲኖሩ አለን::
እየሱስ ወደዝች ምድር የመጣው ሊፈርድ ሳይሆን ሊያድን ነው በማይቀበሉትላይ ግን በስራቸው ይፈርዳል የእግዚአብሔርን ደረጃ የሚያሟላ ስለማይኖር ሁሉ ወደ ሁለተኛ ሞት ይሄዳል:: እየሱስ የሰው ልጅም ስለ ሆነ ይፈርድ ዘንድ ሥልጣን ሰጠው። በስተመጨረሻ ክርስቶስን ያላወቀ ይፈረድበታል አሁንም ተፈርዶበታል ይላል ቃሉ::
በዚህም ፍርድ በመቃብር ያሉቱ ሁሉ ድምፁን የሚሰሙበት ሰዓት ይመጣል፤ መልካምም ያደረጉ ለሕይወት ትንሣኤ ክፉም ያደረጉ ለፍርድ ትንሣኤ ይወጣሉና በዚህ አታድንቁ።”
አባት ሆይ ከፍርድ ስላዳንከን ህይወትን ስለሰጠኸን ተመስገን! ሙታን ለሆኑት ግን ላላወቁት አንተን ማሳየት ይሁንልን በአንድ ኃጥያተኛ መዳን አንተ ትደሰታለህና ምርኮን ስጠን:: የሚሰሙበትንም የተከፈተ ልብ ስጣቸው:: አሜን
ዮሐንስ 5: 30-32
30፤ “እኔ ከራሴ አንዳች ላደርግ አይቻለኝም፤ እንደ ሰማሁ እፈርዳለሁ ፍርዴም ቅን ነው፥ የላከኝን ፈቃድ እንጂ ፈቃዴን አልሻምና።
ዮሐንስ 5:31፤ እኔ ስለ እኔ ስለ ራሴ ብመሰክር ምስክሬ እውነት አይደለም፤
ዮሐንስ 5:32፤ ስለ እኔ የሚመሰክር ሌላ ነው፥ እርሱም ስለ እኔ የሚመሰክረው ምስክር እውነት እንደ ሆነ አውቃለሁ።
ጌታ የአብን ፈቃድ ነበረ ሲያደርግ የነበረው ከእኛም የሚጠበቀው አንዳች ማድረግ የማንችል መሆናችንን አውቀን በእርሱ ላይ እንደገፍና ፈቃዱን እናድርግ:: ፍርድም ለእየሱስ ተሰቶታል ምክንያቱም የሰው ልጅ ስለሆነ የሚፈርደውም እሰማ ነው:: ይህ ማለት ግን እየሱስ አምላክ መሆኑን እንወቅ!! እርሱ እግዚአብሔር ነው:: ሁሉን ማድረግ የሚችል ነው ሌሎች ኃይማኖቶች እየሱስ አምላክ አይደለም የሚሉት ከዚህ እየተነሱ ነው:: እኛም አስረግጠን ማወቅ ያለብን ስለእርሱ ስንመሰክር እራሱን ባዶ አድርጎ መምጣቱን ነው እንጂ እኔና አብ አንድ ነን ማለቱንም ማወቅ አለባቸው::
ስለራሱ ምንም አይመሰክርም አብ ስለወልድ ይመሰክራል ምስክሩም እውነተኛ ነው:: የሰው ምስክር እየሱስ አላስፈለገውም:: ማንም እንዲያጸድቅለት አገልግሎቱን አላስፈለገውም በ12 ሰዎች ዓለምን ገለባብጦ ሄደ:: የዘመኑ አገልጋዮች አልተቀበሉትም እርሱም አልጠበቀምም አላስፈለገውምም:: ዛሬም ሰዎች ባይቀበሉን የእነርሱን መስማማት ከመጠበቅ ከጌታ ጋር እንስማማ:: የማንም ምስክርነት አያስፈልገንም የሚያስፈልገን የሰማይ ምስክርነት ነው:: ከእርሱ ጋር ከተስማማንና ከታዘዝን በቂ ነው:: ለነገሩ ከሰራንም በራሳችን አንሰራ የሚሰራው መንፈስ ቅዱስ ነው:: በራሳችን አንዳች ማድረግ የማንችል በወይኑ ግንድ ላይ የተጣበቅን ቅርንጫፎች ነን::
አባት ሆይ ፈቃድህን በዘመኔ ሁሉ አደርግና እታዘዝ ዘንድ እርዳኝ:: የሰውን ምስክርነት ስፈልግ አንተ የሰጠኸኝን እንዳልጥል ጸጋ አብዛልኝ! አሜን
ዮሐንስ 5: 33-42
ይህንን ሁሉ እየነገራቸው ያለው በመጠመቅያው ስፍራ ከፈወሰው ሰው በተነሳ ነው:: እየሱስ የሰው ምስክርነትን አይፈልግም አብ መስክሮለታል:: እናንተ ወደ ዮሐንስ ልካችኋል እርሱም ለእውነት መስክሮአል። እኔ ግን ከሰው ምስክር አልቀበልም፥ እናንተ እንድትድኑ ይህን እላለሁ እንጂ አላቸው። ምንም እንኳን ዮሃንስ የመሰከረ ቢሆንም ምስክርነቱንም አልተቀበሉም:: ሌላው የሚመሰክርለት ቃሉ ነው:: ሙሴ ጽድፎላቸዋልና በዘዳ 31 :21
የአብ ምስክርነት የምወደው ልጄ በእርሱ ደስ የሚለምኝ ብሏል:: እየሱስ የመጣው ተልኮ አባቱን ደስ ለማሰኘትና እኛን ለመታደግ ነው:: የኖረው ሁሉ የአባቱን ፈቃድ በማድረግ ነው:: ይህች ጽዋ ከእኔ ትለፍ ብሎ ነበር ከፊቱ ያለው አስፈሪ ስለነበረ ነገር ግን የአንተ ፈቃድ ይሁን ብሎ ታዘዘ::
የሚገርመው እነዚህ ሰዎች ቃሉን ጥጥት አድርገዋል ነገር ግን ህይወት አልሆነላቸውም:: መጻሕፍትን ካላመናችሁ ግን ቃሌን እንዴት ታምናላችሁ?” ጌታም እንዳለው:- እናንተ በመጻሕፍት የዘላለም ሕይወት እንዳላችሁ ይመስላችኋልና እነርሱን ትመረምራላችሁ፤ እነርሱም ስለ እኔ የሚመሰክሩ ናቸው፤ ነገር ግን ሕይወት እንዲሆንላችሁ ወደ እኔ ልትመጡ አትወዱም። ህይወት እንዲሆነን ወደ ህይወታችን የጋበዝነው ጌታ ስሙ ይባረክ እንደቃሉ ህይወትን ሰቶናልና::
እራሱን ዝቅ አድርጎ ስለመጣ የህይወትን ጌታ ሊያውቁት አልቻሉም:: ህይወትንም ፍለጋ ወደ እርሱ አልመጡም:: ዝቅ ብሎ ቢመጣም እንኳን ዛሬ መንፈስ ቅዱስ ከፍ ከፍ እያደረገው ስለእርሱ ብቻ ያሳያል::
አባት ሆይ ክበር ተመስገን! ልትከብር የተገባህ ህይወትን የሰጠኸን ጌታ ዛሬም ክበር:: ጌታ የምትከበርበት ጊዜ ነውና ክበር::
ዮሐንስ 5:43 – 47
5:43፤ እኔ በአባቴ ስም መጥቻለሁ አልተቀበላችሁኝምም፤ ሌላው በራሱ ስም ቢመጣ እርሱን ትቀበሉታላችሁ።
5:44፤ እናንተ እርስ በርሳችሁ ክብር የምትቀባበሉ ከአንዱም ከእግዚአብሔር ያለውን ክብር የማትፈልጉ፥ እንዴት ልታምኑ ትችላላችሁ?
45፤ እኔ በአብ ዘንድ የምከሳችሁ አይምሰላችሁ፤ የሚከሳችሁ አለ፤ እርሱም ተስፋ የምታደርጉት ሙሴ ነው።
46፤ ሙሴንስ ብታምኑት እኔን ባመናችሁ ነበር፤ እርሱ ስለ እኔ ጽፎአ ልና።
47፤ መጻሕፍትን ካላመናችሁ ግን ቃሌን እንዴት ታምናላችሁ?”
ጌታ እየሱስ በምድር ሲመላለስ ያደረገው ሁሉ የአባቱን ፈቃድ ማድረግ ነበረ:: እኛም ከሁሉ በፊት ፈቃዱን መታዘዝ ይሁንልን:: ቃሉ ከእኛ ጋር በእምነት ይዋሃድ እንጂ እዚህ ክፍል ላይ እንደሚናገረው መጽሐፍትን ትመረምራላችሁ እነርሱም ስለእኔ ይናገራሉ ነገር ግን ሕይወት እንዲሆንላችሁ ወደ እኔ ልትመጡ አትወዱም አላቸው:: እንዲያውም እኔ በአብ ዘንድ የምከሳችሁ አይምሰላችሁ፤ የሚከሳችሁ አለ፤ እርሱም ተስፋ የምታደርጉት ሙሴ ነው አላቸው:: ምን አይነት መተላለፍ ነው:: ዛሬም ልባቸው እስኪጠፋ የተከተሉት መስሏቸው የተላለፉ ስንቶች አሉ? የእኛ ስራ ስለእነርሱ መፀለይ ነው:: መጋረጃው ይነሳላቸውና የክብርን ጌታ ይዮት::
ያልተላለፍን እኛ ወደ እርሱ በመጠጋት በቀንም በለሊትም ቃልና ህይወት ከሆነው ከእየሱስ ጋር ህብረትን ማድረግ ይሁንልን:: አለበለዝያ ግን ውሃ የሌለው ዳመና ከሆነብን ቃሉ ምን ያደርጋል? ቃሉ ዘንቦ የደረቀውን ካላጠጣና ህይወት ካላበበ? ካለንበት ካላወጣን? ወይም ከመከራችን ካላዳነን? ከእኛ ጋር አልተዋሃደም ማለት ነው:: ስለዚህ ከወይኑ ግንድ ጋር እንጣበቅ እርሱ የሚሰጠውን ውሃ እንጠጣ ዳግመኛም አንጠማም:: አሜን!
አባት ሆይ ጸጋን ስጠን ለሳቱት የምንማልድበትንና ፈቃድህን ማድረግ!
ዮሐንስ 6:1 -15
የፋሲካ በዓል ደርሶ እያለ ኢየሱስ ወደ ገሊላ ባሕር ማዶ ተሻገረ በዚያም ብዙ ህዝብ ተሰበሰቡ:: እርሱም አስተማራቸው ፈወሳቸውና ሊመግባቸው ፈለገ:: ፊልጶስን፦ “እነዚህ እንዲበሉ እንጀራ ከወዴት እንገዛለን?” አለው።
ፊልጶስም የተጠየቀው ከወዴት እንግዛ ነበረና ዋጋውን ማስላት ጀመረ:: ነገር ግን በቃና ዘገሊላ እብረውት ነበሩ ውሃውን ወይንጠጅ ሲያደርገው:: ቢያንስ አንተ ታውቃለህ ጥሩ መልስ ነበረ እርሱ ግን ያለውን ነገር የምድሩን ካልኩሌሽን ቀጠለና፦ “እያንዳንዳቸው ትንሽ ትንሽ እንኳ እንዲቀበሉ የሁለት መቶ ዲናር እንጀራ አይበቃቸውም፡” ብሎ መለሰለት። እየሱስ ግን ሊያደርግ ያለውን ያውቅ ነበርና ሊፈትነው ይህን ተናገረ።
የእኛስ መልስ ምን ይሆን? ፈተናውን እናልፍ ይሆን? ጌታ አንዳች አጥቶ ከእኛ እርዳታ አይፈልግም አብረነው እንድንሰራ እንጂ:: ትላንትና ስንቱን አሻገረን?! እርሱ አይለወጥም ዛሬም በስራ ላይ ነው::
ሰይጣን እየሱስን ፈትኖት ይህንን ድንጋይ ዳቦ አድርግ ብሎት ነበረ እርቦት እያለ ለራሱ አላደረገም:: እዚህ ጋር ግን ህዝቡን ለመርዳት ተአምራትን አደረገ:: እጁ የገባው ዳቦና አሳ ነው:: ዳቦን ስናስበው እህሉ ወደ ዱቄትነት ተለውጧል ብንዘራው አይበቅልም አሳውም እንደዛው ከውሃ ወቶ ሞቷል:: ከህግ ውጪ ነው ይህንን ማብዛት:: ለእየሱስ ግን የተፈጥሮ ህግ ምንም አይደለምና ዳቦውንና አሳውን ቆርሶ አመስግኖ ሰጣቸው:: ልክ ሲሰጣቸው ተቆለለ አይልም ቃሉ ታድያ እንዴት በዛ?! እራሳችንን እንጠይቅ: እያንዳንዱ ደቀ መዝሙር ቁራሽ ዳቦና ቁራሽ አሳ ነበረ የደረሰው ለህዝቡ ለማደል:: አምነው ግን መስጠት ሲጀምሩ አላለቀም ለሁሉም አዳረሱ:: የእኛ አምላክ ህግ አይዘውም!!!! እርሱ ዛሬም ድንቅንና ተአምራትን ያደርጋል ያለ እምነት ግን እግዚአብሔር ደስ ማሰኘት አይቻልም! አሜን!
የተከተልነው አምላክ ትልቅ ነው በዝች ትንሽ አእምሯችን አናሳንሰው ሊያደርግ ያለውን ሁሉ ያድርግ!
አባት ሆይ እንዳትሰራ ባላመንኩትና ባገድኩህ ሁሉ ይቅር በለኝ:: አንተ ያሰብከው ብቻ ይሁን ከአንተ ጋር እስማማለሁ:: ጸጋን ስጠን!
ዮሐንስ 6: 16-21
ዮሐንስ 6:18፤ ብርቱ ነፋስም ስለ ነፈሰ ባሕሩ ተናወጠ።
ዮሐንስ 6:19፤ ሀያ አምስት ወይም ሠላሳ ምዕራፍ ከቀዘፉ በኋላም፥ ኢየሱስ በባሕር ላይ እየሄደ ወደ ታንኳይቱ ሲቀርብ አይተው ፈሩ።
20፤ እርሱ ግን፦ “እኔ ነኝ፤ አትፍሩ፡” አላቸው።
ወደ ባህርማዶ ተሻገሩ ብሎ እርሱ ግን ለፀሎት ወደኃላ ቀረ:: አብዛኛው ደቀመዛሙርቱ አሳ አጥማጅ ስለነበሩ ብዙም አላሳሰባቸው ወደ ማዶ መሻገሩ:: ብዙ ጊዜ ያጠመዱበት ባህር ነው ምን ይሆናልና ብሉው ይስጉ:: ትንሽ እንደቀዘፉ ማዕበል አስቸገራቸው:: ይህንንም ያይ ነበር ጌታእየሱስ እንዲያውም ማርቆስ እንደሚነግረን አልፎ የሚሄድ መሰለ ነው ያለው ምክንያቱም ተሻገሩ ብሏቸዋልና ይህ ማዕበል ግን ሲታገላቸው አደረ:: በምናልፍበት ሁሉ ጌታ በዛ አለ:: ከዚህ በፊት በጀልባው ውስጥ ተኝቶ ማዕበል ገጥሟቸው ነበረ ነገር ግን ንፋሱን ሲገስጽ ቆመ:: እዚህ ስፍራ ላይ ግን የተለየ ነው ያደረገው “እኔ ነኝ፤ አትፍሩ፡” ነው ያላቸው። ያን ጊዜም ማዕበሉ ቆመ::
ሲመጣም ወደእነርሱ በባህር ላይ እየተራመደ ነው የመጣው እኛን የሚያስቸግር እርሱን አያስቸግረውም:: እኛን የሚቋቋም እርሱን አይቋቋምም:: እኔ ነኝ ሲል ሁሉ ይስተካከላል:: አንዳንዴ ፈቃዱን እያደረግን በመንገድ መዘግየት አለ:: ጠላት ይዋጋል ፈቃዱን ማድረግ መንገዳችንን አልጋ ባልጋ አያደርገውም:: ጳውሎስና ሲላስ ተገርፈው ከግንድም ተጠርቀው ያደሩት በፈቃዱ እየሄዱ ሳለ ነው:: ምን ጠላት ቢጠበብና ቢበረታ ድሉ የጌታ ነው ወዳለው ፈቃድ መድረሳችን አይቀርምና እንበርታ:: እርሱ ከአሸናፊዎች በላይ አድርጎናል::
አባት ሆይ በማልፍበት ሁሉ አንተ ከእኔ ጋር ስላለህ ተመስገን:: ስጋቴን ሁሉ በአንተ ላይ እጥላለሁ! እሻገራለሁ ያየኸውንም እወርሳለሁ!
ዮሐንስ 6: 22-29
26፤ ኢየሱስም መልሶ፦ “እውነት እውነት እላችኋለሁ፥ የምትፈልጉኝ እንጀራን ስለ በላችሁና ስለ ጠገባችሁ ነው እንጂ ምልክቶችን ስላያችሁ አይደለም።
27፤ ለሚጠፋ መብል አትሥሩ፤ ነገር ግን ለዘላለም ሕይወት ለሚኖር መብል የሰው ልጅ ለሚሰጣችሁ ሥሩ፤ እርሱን እግዚአብሔር አብ አትሞታልና።”
29፤ ኢየሱስ መልሶ፦ “ይህ የእግዚአብሔር ሥራ እርሱ በላከው እንድታምኑ ነው፡” አላቸው።
በትናንትናው አገልግሎቱ እንጀራ ስላበላቸው ሁሉም ይፈልጉት ጀመር:: ፈልገው ፈልገው ሲያገኙት መቼ ወደዚህ መጣህ አሉት በጀልባ እንዳልተሳፈረ አውቀው ነበረና:: መልሱም መሆን የነበረበት ልክ ነው እዛው ነበርኩኝ ኃዋርያት በማዕበል ሲጨነቁ አይቼ ልታደጋቸው በውሃው/ በማዕበሉ ላይ እየተራመድኩ ነው የመጣሁት ማለት ነበረበት:: እርሱ ግን የመለሰላቸው የምትፈልጉኝ እንጀራን ስለ በላችሁና ስለ ጠገባችሁ ነው እንጂ ምልክቶችን ስላያችሁ አይደለም። እንዲያውቁ የፈለገውን ሙሉ ቀን ሲያስተምር የዋለውን ትተው የያዙት የሆዳቸውን ብቻ ነበረ:: ያ ሁሉ ፈውስና ተአምራት ሲደረግ የዋለውን መሲህ ብቻ የሚያደርገውን አላስተዋሉም:: ለእኛም ማስተዋልን ይስጠን በተደረገው ነገር ላይ ሳይሆን በአድራጊው ላይ አይናችን እንዲሆን::
ሌላው ጌታ እንዲያውቁ የፈለገው ለሚጠፋ መብል እንዳይሰሩ ነው:: አይናቸውን ወደ አዳኙ አድርገው ለዘላለም ሕይወት ለሚኖር መብል የሰው ልጅ ለሚሰጣችሁ ሥሩ፤ እርሱን እግዚአብሔር አብ አትሞታልና።” አላቸው:: ስራ ብሎ ስላለ ምን እንስራ አሉ ቶሎ ምክንያቱም ሰርቶ መፅደቅ ነው ሰው ሁሉ የሚፈልገው:: እርሱ ግን “ይህ የእግዚአብሔር ሥራ እርሱ በላከው እንድታምኑ ነው፡” አላቸው። እኛም የዳነው እርሱ በላከው በማመን ነው::
አባት ሆይ በአንተ በማመን መዳንን አገኘን በጨለማ ላሉት ሳንፈርድ ወንጌልን እናደርስ ዘንድ እርዳን! አሜን
ዮሐንስ 6: 30-34
30፤ እንግዲህ፦ “እንኪያ አይተን እንድናምንህ፡ አንተ ምን ምልክት ታደርጋለህ? ምንስ ትሠራለህ?
31፤ ‘ይበሉ ዘንድ ከሰማይ እንጀራ ሰጣቸው፡’ ተብሎ እንደ ተጻፈ፡ አባቶቻችን በምድረ በዳ መና በሉ፡” አሉት።
32፤ ኢየሱስም አላቸው፦ “እውነት እውነት እላችኋለሁ፥ እውነተኛ እንጀራ ከሰማይ የሚሰጣችሁ አባቴ ነው እንጂ ከሰማይ እንጀራ የሰጣችሁ ሙሴ አይደለም፤
33፤ የእግዚአብሔር እንጀራ ከሰማይ የሚወርድ ለዓለምም ሕይወትን የሚሰጥ ነውና።”
35፤ ኢየሱስም እንዲህ አላቸው፦ “የሕይወት እንጀራ እኔ ነኝ፤ ወደ እኔ የሚመጣ ከቶ አይራብም፡ በእኔ የሚያምንም ሁልጊዜ ከቶ አይጠማም።
ይህ የእግዚአብሔር ሥራ እርሱ በላከው እንድታምኑ ነው፡” ስላላቸው ምልክትን አሳየን? ይበሉ ዘንድ ከሰማይ እንጀራ ሰጣቸው፡’ ተብሎ እንደ ተጻፈ፡ አባቶቻችን በምድረ በዳ መና በሉ፡” አሉት:: እየሱስን በማወዳደር ሳምራይቱም ጠይቃ ነበር አንተ ይህንን ውሃ ከሰጠን ከያዕቆብ ትበለጣለህን? እዚህ ክፍል ላይ ደግሞ ከሙሴ ትበልጣለህን? እርሱ መናን ሰጠ ለአባቶቻችን አሉት:: እንጀራን በልተው ስለነበረ የተከተሉት ዛሬም በመገበን ብለው ይመስላል:: የሚያነሱትም ምሳሌ ምግብ ነው (መና) ነው::
እየሱስም ሲመልስ የጠየቁት ስለእንጀራ ነውና እውነት እውነት እላችኋለሁ፥ እውነተኛ እንጀራ ከሰማይ የሚሰጣችሁ አባቴ ነው እንጂ ከሰማይ እንጀራ የሰጣችሁ ሙሴ አይደለም፤ ያወዳደሩት ከሙሴ ጋር ነበረ:: ሙሴ ምንም አላደረገም ያንን መና በየጠዋቱ ይሰጣቸው የነበረው እግዚአብሔር ነው አላቸው:: ዛሬም በእኛ ህይወት አምላካችን ብቻ ነው ረድኤታችን::
እንዲያውም ስለእንጀራ ካነሳችሁማ ይህንን እወቁ ብሎ:- የእግዚአብሔር እንጀራ ከሰማይ የሚወርድ ለዓለምም ሕይወትን የሚሰጥ ነው። አሜን! ሙሴ የሰጠው እንጀራ ለነገ አይሆንም ነገም ይርባል ይኼኛው ግን የህይወት እንጀራ ለዘላለም ነው:: ሁልጊዜ የሚያረካ! ሃሌሉያ!
ይህንን እንጀራ ስጠን አሉት:: ሳምራይቱም ይህንኑ ብላለች ይህንን ውሃ ስጠኝ:: የሕይወት እንጀራ እኔ ነኝ፤ ወደ እኔ የሚመጣ ከቶ አይራብም፡ በእኔ የሚያምንም ሁልጊዜ ከቶ አይጠማም። አሜን እየሱሴ! የህይወት እንጀራ ነው የምትፈልጉት እይኸው እኔ ነኝ አላቸው:: ስለማንነቱ ነገራቸው ስለመሲህነቱ የገባው ግን የለም:: እኔም ያወኩህ በራሴ ጥበብ ሳይሆን በመንፈስ ቅዱስ እርዳታ ነውና ተመስገንልኝ! ላልገባቸው የማስታረቅን አገልግሎት ሰተኸኛልና የምመሰክርበት ጸጋ ይብዛልኝ!
አባት ሆይ አንተ የህይወት እንጀራዬ የህይወትም ውሃዬ ሆነሃል ተመስገን! ከቶም አልራብም አልጠማምም!! ጽድቄ ፤ ቅድስናዬ፤ የለበስኩህ ልብሴ በአብ ፊት መታያዬ ፤ ህይወቴ ፤ ሁሉ በሁሉዬ ሆንክልኝ!! እባርክሃለሁ!
ሃሌሉያ አሜን!!!
ዮሐንስ 6: 41-51
41፤ እንግዲህ አይሁድ፦ “ከሰማይ የወረደ እንጀራ እኔ ነኝ፡” ስላለ ስለ እርሱ አንጐራጐሩና፦
42፤ “አባቱንና እናቱን የምናውቃቸው ይህ የዮሴፍ ልጅ ኢየሱስ አይደለምን? እንግዲህ፦ ከሰማይ ወርጃለሁ፡ እንዴት ይላል?” አሉ።
43፤ ኢየሱስ መለሰ አላቸውም፦ “እርስ በርሳችሁ አታንጐራጕሩ።
44፤ የላከኝ አብ ከሳበው በቀር ወደ እኔ ሊመጣ የሚችል የለም፥ እኔም በመጨረሻው ቀን አስነሣዋለሁ።
ጌታ እየሱስ ደግሞ ደጋግሞ የሚነግራቸው እውነት እዚህ ስፍራ ላይ እርሱ የህይወት እንጀራ እንደሆነ በእርሱም የሚሆን የዘላለም ህይወት እንደሚኖረው እንደማይጠፋና ለዘላለም እንደሚኖር ነው:: ይህም የአባቴ ፈቃድ ነው አላቸው የሰው ልጅ ሁሉ በእርሱ እንዲያምን ስለዚህም ይህንን የአብን ፈቃድ እያደረኩኝ ነው አላቸው:: እነርሱ ግን ይሰናከሉበት ጀመር:: አባቱንና እናቱን የምናውቃቸው ይህ የዮሴፍ ልጅ ኢየሱስ አይደለምን? እንግዲህ፦ ከሰማይ ወርጃለሁ፡ እንዴት ይላል?” አሉ። ተሰናከሉ:: በመካከላቸው የቆመው ማን እንደሆነም አላወቁም! ሁሉም ከእግዚአብሔር የተማሩ ይሆናሉ ተብሎ በነቢያት ተጽፎአል እንደሚክል ይህንን እውነት በራሳችን አላወቅንም በጌታ ጸጋ እንጂ! ከእግዚአብሔር ከሆነ በቀር፥ እርሱ አብን አይቶአል። ይላል ቃሉ በክርስቶስ ወደ አብ ቀረብን::
አብ ምን አደረገ ወልድስ?
አብ:-
የላከኝ አብ ከሳበው በቀር ወደ እኔ ሊመጣ የሚችል የለም፥- ወደ እየሱስ የሳበን አብ ይባረክ!!
ከአብ የሰማ የተማረም ሁሉ ወደ እኔ ይመጣል:- ወደ ህይወት ራስ የደረስነው ከአብ መስማት ስለቻልን ነው! ከእኛ የሆነ ምንም የለም!
ወልድ:-
እኔም በመጨረሻው ቀን አስነሣዋለሁ።
በእኔ የሚያምን የዘላለም ሕይወት አለው።
የሕይወት እንጀራ እኔ ነኝ
ሰው ከእርሱ በልቶ እንዳይሞት ከሰማይ አሁን የወረደ እንጀራ ይህ ነው።
ከሰማይ የወረደ ሕያው እንጀራ እኔ ነኝ፤
የሚበላ እንጀራ
ሰው ከዚህ እንጀራ ቢበላ ለዘላለም ይኖራል፤ እኔም ስለ ዓለም ሕይወት የምሰጠው እንጀራ ሥጋዬ ነው።”
አሜን!
አባቴ ሆይ የዘላለምን ህይወት ስለሰጠኸኝ አመሰግንሃለሁ! የህይወት እንጀራ አንተ ነህ አንተን ወደ ህይወቴ አስገብቻለሁና ለዘላለም አልራብም አልጠማምም!
ዮሐንስ 6: 52-59
ስለዚህ ኢየሱስ እንዲህ አላቸው፦ “እውነት እውነት እላችኋለሁ፥
* የሰውን ልጅ ሥጋ ካልበላችሁ
ደሙንም ካልጠጣችሁ በራሳችሁ
ሕይወት የላችሁም።
* ሥጋዬ እውነተኛ መብል፡ ደሜም
እውነተኛ መጠጥ፡ ነውና።
* ሕያው አብ እንደ ላከኝ እኔም ከአብ
የተነሣ ሕያው ነኝ፥ እኛም ከእርሱ
የተነሳ ህያዋን ሆንን
ሥጋዬን የሚበላ ደሜንም የሚጠጣ :-
– የዘላለም ሕይወት አለው፥
– እኔም በመጨረሻው ቀን አስነሣዋለሁ
– በእኔ ይኖራል፡
– እኔም በእርሱ እኖራለሁ።
– የሚበላኝ ደግሞ ከእኔ የተነሣ ሕያው
ይሆናል።
– ይህን እንጀራ የሚበላ ለዘላለም
ይኖራል።
ይህንን ከሰማይ የወረደ እንጀራ መብላት እንደእስራኤሎቹ ያለ መና አይደለም እነርሱ በልተው ሞቱ ይኼኛው ግን ህይወትን የሚሰጥ ነው::፤
የቀረልኝ:-
1. በራሴ ህይወት የለኝም
2. እውነተኛ መብልና መጠጥ ለህይወቴ
እየሱስ ነው
3. ለዘላለም እንድኖር ይፈልጋል
4. በእርሱ እኖራለሁ
5. ህያው ነኝ
6. ትንሳኤን ይሰጠኛል
አብ አባት ሆይ አመሰግንሃለሁ! ልጅህን ልከህ ሞቴን ሞተልኝ:: የዘላለምንም ህይወት አገኘሁ! ተባረክ!!
ዮሐንስ 6: 60-71
62፤ እንግዲህ የሰው ልጅ አስቀድሞ ወደ ነበረበት ሲወጣ ብታዩ እንዴት ይሆናል?
63፤ ሕይወትን የሚሰጥ መንፈስ ነው፤ ሥጋ ምንም አይጠቅምም፤ እኔ የነገርኋችሁ ቃል መንፈስ ነው ሕይወትም ነው።
64፤ ነገር ግን ከእናንተ የማያምኑ አሉ።” ኢየሱስ የማያምኑት እነማን እንደ ሆኑ አሳልፎ የሚሰጠውም ማን እንደ ሆነ ከመጀመሪያ ያውቅ ነበርና።
65፤ ደግሞ አለ፦ “ስለዚህ አልኋችሁ፥ ከአብ የተሰጠው ካልሆነ ወደ እኔ ሊመጣ የሚችል የለም።”
ሕያው አብ እንደ ላከኝ እኔም ከአብ የተነሣ ሕያው እንደምሆን፥ እንዲሁ የሚበላኝ ደግሞ ከእኔ የተነሣ ሕያው ይሆናል ሲላቸው ብዙዎች ተሰናከሉና ተመለሱ:: ጌታም ይህ ያሰናክላችኃል አላቸውና ይባስ ብሎ ወደ ሰማይ ሳርግ ብታዩ ምን ልትሉ ነው:: ማረጉንም ቢሆን አይተዋል ከትንሳኤው በኃላ ነገር ግን ምንም ጭብጥ ያደረጉት ነገር አልነበረም::
ግራ የገባቸው ምክንያት መንፈሳዊዉን በስጋ ለመረዳት በመሞከራቸው ነው:: ስለዚህም ነው ጌታ ሕይወትን የሚሰጥ መንፈስ ነው፤ ሥጋ ምንም አይጠቅምም፤ እኔ የነገርኋችሁ ቃል መንፈስ ነው ሕይወትም ነው አላቸው:: ብዙዎች ግን ተሰናክለው ተመለሱ:: ዛሬም ሰዎች ይህንን እውነት መረዳት በስጋ ይሞክራሉ ይከብዳቸዋል:: እኛም ወደዛ እንዳንዳዳ በመንፈስ እንመላለስ – መንፈስ ህይወትን ይሰጣል::
ጴጥሮስም በመንፈስ ስምዖን “ጌታ ሆይ፥ ወደ ማን እንሄዳለን? አንተ የዘላለም ሕይወት ቃል አለህ፤ እኛስ አንተ ክርስቶስ የሕያው የእግዚአብሔር ልጅ እንደ ሆንህ አምነናል አውቀናልም፡” ብሎ መለሰለት። ሃሌሉያ! በመንፈስ ትክክለኛውን ማንነቱን እናውቃለን አለበለዚያ ግን ግምት ነው የሚሆነው ከዚህ ደግሞ ያውጣን:: መንፈስ ዝግጁ ነው!
ስለዚህ አልኋችሁ፥ ከአብ የተሰጠው ካልሆነ ወደ እኔ ሊመጣ የሚችል የለም።” እኛ ከአብ ዘንድ ቸርነት ተደርጎልን በመንፈስ ማንነቱን ተረድተን ወደ እየሱስ መጣን እንጂ የተሻለ ማንነት ስላለን ወይም በሌላ ምክንያት አይደለም እርሱ ከሰማይ ቸርነትን ስላደረገልን ብቻ ነው::
ዮሐንስ 7: 1-9
6፤ ኢየሱስም እንዲህ አላቸው፦ “ጊዜዬ ገና አልደረሰም፥ ጊዜያችሁ ግን ዘወትር የተመቸ ነው።
ዮሐንስ 7:7፤ ዓለም እናንተን ሊጠላ አይቻለውም፤ እኔ ግን ሥራው ክፉ መሆኑን እመሰክርበታለሁና እኔን ይጠላኛል።
ዮሐንስ 7:8፤ እናንተ ወደዚህ በዓል ውጡ፤ እኔስ ጊዜዬ ገና ስላልተፈጸመ ወደዚህ በዓል ገና አልወጣም።”
የእየሱስ ወንድሞች አላመኑበትም ነበረና ለበዓሉ ውጣና ለዓለም እራስህን ግለጥ አሉት:: ግን እንዴት ከእየሱስ ጋር በአንድ ቤት አድጎ እርሱን አለማወቅ ይቻላል?! ማርያም ግን የተነገራትን ሁሉ በልብዋ ትጠብቀው ነበር እንደሚል ለማንም አላካፈለችም ማለት ነው:: ይህ የሚያሳየው አብ ወደ ልጁ ካልሳበና መንፈስ ቅዱስ ካልገለጠልን በራሳችን እየሱስን ማወቅ አንችልም::
ለወንድሞቹም ዓለም እናንተን ሊጠላ አይቻለውም፤ እኔ ግን ሥራው ክፉ መሆኑን እመሰክርበታለሁና እኔን ይጠላኛል። ይህ ነው የእኛም ስራ የዓለምን ክፉ ስራ መግለጥ ነው:: እኛ የዓለም ብርሃን ነን ከእየሱስ የተነሳ:: በዝች ጨለማ በወረሳት ዓለም ውስጥ ስንመላለስ ብርሃናችንን ከፍ አድርገን እያሳየን እንሂድ:: ብርሃንን አብርቶ ከአልጋ ስር ማድረግ የለም ጽድቅን እየገለጥን እንመላለስ:: በዚህ ምድር የመቆየታችን ሚስጥሩ ይግባን ይኸውም ብርሃኑን እንድናበራና የጨለማውን ስራ እንድንገልጥ ነው:: እንደ ቁጫጭዋ እንዳንሆን እኔና ዝሆን ድልድዮን ነቀነቅነው እንዳለችው:: እየሱስ ነው በእኛ ብርሃን ይብራ ብሎ እያበራ ያለው እርሱኑ እናሳይ::
አባት ሆይ
ተመስገን በእኔ ውስጥ የምታበራ ብርሃን ነህና:: አሁንም አንተን ለማብለጭለጭ ጸጋህን ለኔና ለህዝብህ አብዛልን::
ዮሐንስ 7: 10-24
15፤ አይሁድም፦ “ይህ ሰው ሳይማር መጻሕፍትን እንዴት ያውቃል?” ብለው ይደነቁ ነበር።
16፤ ስለዚህ ኢየሱስ መለሰ፥ እንዲህም አላቸው፦ “ትምህርቴስ ከላከኝ ነው እንጂ ከእኔ አይደለም፤
23፤ የሙሴ ሕግ እንዳይሻር ሰው በሰንበት መገረዝን የሚቀበል ከሆነስ ሰውን ሁለንተናውን በሰንበት ጤናማ ስላደረግሁ ትቈጡኛላችሁን?
24፤ ቅን ፍርድ ፍረዱ እንጂ በመልክ አትፍረዱ።”
ወንድሞቹ ግን ወደ በዓሉ ከወጡ በኋላ በዚያን ጊዜ እርሱ ደግሞ በግልጥ ሳይሆን ተሰውሮ ወጣ ምክንያቱም አይሁድ ሊገድሉት ይፈልጉ ነበረና:: እየሱስ በራሱ ጊዜ ወደ በዓሉ ታደመ:: በዛም ተገኝቶ ዝም ማለትና እንደሌላው መሆን አይችልምና ማስተማሩን ቀጠለ::
አይሁድም፦ “ይህ ሰው ሳይማር መጻሕፍትን እንዴት ያውቃል?” ብለው ይደነቁ ነበር። ያላወቁት እውነትቢኖር ቃሉን የሰጣቸው አምላኬ የሚሉት ጌታ በፊታቸው መቆሙን ነው:: ኢየሱስ መለሰ፥ እንዲህም አላቸው፦ “ትምህርቴስ ከላከኝ ነው እንጂ ከእኔ አይደለም:: ጌታ አያችሁ እኔ ከእናንተ የተሻለ አውቃለሁ እያለ አልሸለለም አብን አከበረ:: እኛም በህይወታችን የፈለገውን አይነት መገለጥ ቢኖረን ትንሽም ሽርፍ ሳናደርግ እየተደነቅን መንፈስ ቅዱስ ነው እንበል እንጂ ኮፈስ እንዳንል ጌታ ይርዳን!!!! የዘመኑ ችግር ይህ ነውና በእውነት ይርዳን በባዶ ሜዳ እንዳንኮፈስ:: ጸጋው የእርሱ ህይወቱ የእርሱ ከቶ ምን ልሁን ብዬ ቀና ቀና እላለሁ?!
እነሱ ጥብቅና የቆሙት ለሙሴ ህግ ነው:: ህጉን የሰጠው ባለቤቱ እዛው ቆሞ ሊያርሙት ፈለጉ:: የቆሙለትንም ህግ ማድረግ በትክክል እንዳልቻሉ ነገራቸው:: እነርሱ ማሻሻያ አድርገው ነበረና በሰንበት ግዝረትን ማድረግ እንግዲያውስ ፈውስ ምን ችግር አለው አላቸው?! እንደው የመቃወም አባዜና ቅናት ይዟቸው እንጂ አንዳችም እንከን የማይገኝበት ጌታ ነው እርሱ:: ቅንን ፍርድ መፍረድ አልቻሉም እርሱም የአባቱን ፈቃድ ከማድረግ ወደኃላ አላለም::
አባት ሆይ ፍቃድህን አደርግ ዘንድና ሁልጊዜም አንተን ማሳየት ክብርህንም ወደ አንተ ማምጣት ይሆንልኝ ዘንድ እርዳኝ! አሜን!
ዮሐንስ 7: 25-31
28፤ እንግዲህ ኢየሱስ በመቅደስ ሲያስተምር እንዲህ ብሎ ጮኸ፦ “እኔንም ታውቁኛላችሁ፡ ከወዴትም እንደ ሆንሁ ታውቃላችሁ፤ እኔም በራሴ አልመጣሁም፡ ነገር ግን እናንተ የማታውቁት የላከኝ እውነተኛ ነው፤
29፤ እኔ ግን ከእርሱ ዘንድ ነኝ እርሱም ልኮኛልና አውቀዋለሁ።”
30፤ ስለዚህ ሊይዙት ይፈልጉ ነበር፤ ነገር ግን ጊዜው ገና ስላልደረሰ ማንም እጁን አልጫነበትም።
ወንድሞቹ ለዓለም እራስህን ግለጥ ቢሉትም እርሱ ግን እንዲህ አላቸው፦ “ጊዜዬ ገና አልደረሰም፥ ጊዜያችሁ ግን ዘወትር የተመቸ ነው አላቸውና እርሱ ግን በራሱ ጊዜና ሁኔታ ወደ በዓሉ ወጣ:: ሰው ባሰመረለት ሳይሆን በአባቱ ፈቃድ ይመላለስ ነበረና::
ህዝቡም ይህን ሰው እየፈለጉት አልነበረም በግልጥ እየሰበከ ነው ተቀበሉት እንዴ? እየተባባሉ ይነጋገሩ ነበር:: ይባስ ብለውም ይህን ከወዴት እንደ ሆነ አውቀናል አሉ ማለትም የዮሴፍና የማርያም ልጅ ብለው ነው አውቀነዋል የሚሉት:: ሲቀጥሉም ክርስቶስ ሲመጣ ግን ከወዴት እንደ ሆነ ማንም አያውቅም።” ብለው ደመደሙ:: ነገርግን መጽሐፍት ሁሉ ስለእርሱ ይናገራሉ:: በቃላቸው የሸመደዱት ብዙ ቃል አልገባቸውም:: መሲህ ከዳዊት ዘር በቤተልሔም እንደሚወለድ ተጽፎላቸዋል ይህንኑም እውነት ለሄሮድስ ነግረውህፃናትም አልቀዋል:: እዚህ ጋር ግን ህዝቡ አያውቁም?! እኛም ያወቅነው በእውቀት ብዛት ወይም ፃድቅ ስለሆንን ሳይሆን እርሱ ስለገለጠልን ብቻ ነው!!!
ኢየሱስም በመቅደስ ሲያስተምር እንዲህ ብሎ ጮኸ፦ “እኔንም ታውቁኛላችሁ፡ ከወዴትም እንደ ሆንሁ ታውቃላችሁ፤ እኔም በራሴ አልመጣሁም፡ ነገር ግን እናንተ የማታውቁት የላከኝ እውነተኛ ነው:: በሌላ አባባል የምታውቁኝ መሰላችሁ እንጂ አታውቁኝም የላከኝንም አታውቁትም:: እያላቸው ቢሆንም እነርሱ ግን የማንም ባርያ አይደለንም “እኛስ ከዝሙት አልተወለድንም አንድ አባት አለን እርሱም እግዚአብሔር ነው፡” ይላሉ በባዶ ሜዳ ነገር ግን አባት ብለው የሚጠሩትን አያውቁትም:: ቃሉ አልጠቀማቸውም ስላልተዋሃደ:: ለእኛ እርሱን ማወቅ ሆነልን አባ አባት ብለን የምንጠራበት መንፈስ ተሰጠን::
ስለዚህ ሊይዙት ይፈልጉ ነበር፤ ነገር ግን ጊዜው ገና ስላልደረሰ ማንም እጁን አልጫነበትም። አሜን! እርሱ ወዶ እንጂ ፍጥረት አስገድዶት አያውቅም አይችልምም!! ነፍሱንም በፈቃዱ ሰጠን ይህ ጌታ ስሙ ይባረክ!!! በዚህ ሁሉ መገፋትና ስድብ መንገላታት ውስጥ የገባው እኔን ለመታደግ ነው::
አባት ሆይ ምን እላለሁ ተባረክ!! እራስህን ስለገለጥክልኝ አንተንም የሚያውቅ ማንነት ስለሰጠኸኝ ክበር ተመስገን:: ማንም ሳያስገድድህ ነፍስህን መስዋእት አድርገህም ስለታደከኝ ተመስገን! ይህንን እውነት የማሳይበትንና የምመሰክርበትን ጸጋ ስጠኝ ! አሜን!!!
ዮሐንስ 7: 32-39
36፤ እርሱ፦ ‘ትፈልጉኛላችሁ አታገኙኝምም፡ እኔም ወዳለሁበት እናንተ ልትመጡ አትችሉም፡’ የሚለው ይህ ቃል ምንድር ነው?” ብለው እርስ በርሳቸው ተነጋገሩ።
37፤ ከበዓሉም በታላቁ በኋለኛው ቀን ኢየሱስ ቆሞ እንዲህ ብሎ ጮኸ፦ “ማንም የተጠማ ቢኖር ወደ እኔ ይምጣና ይጠጣ።
38፤ በእኔ የሚያምን መጽሐፍ እንዳለ፥ የሕይወት ውኃ ወንዝ ከሆዱ ይፈልቃል።”
ምንም እንኳን የካህናት አለቆችና ፈሪሳውያን ሊይዙት ሎሌዎችን ቢልኩም ኢየሱስ ግን “ገና ጥቂት ጊዜ ከእናንተ ጋር እቆያለሁ፡ ወደ ላከኝም እሄዳለሁ። ትፈልጉኛላችሁ፡ አታገኙኝምም፤ እኔም ወዳለሁበት እናንተ ልትመጡ አትችሉም።” ቢላቸውም አልገባቸውም:: እርሱ ከዚች ምድር አይደለምና ስለመጣበትና ተመልሶም ስለሚሄድበት ቢነግራቸውም እነርሱ ግን ሌላ ከተማ ወይም አገር ከእየሩሳሌም ወቶ የሚሄድ ነው የመሰላቸው:: ያላቸውን ኃይል ሁሉ አሰባስበው ቢመጡምያለ ጊዜው አይዙትም::
በነብዮ እዩኤል ሲነገርየነበረውን አሁን ደግሞ ባለቤቱ እየሱስ ከበዓሉም በታላቁ በኋለኛው ቀን ቆሞ እንዲህ ብሎ ጮኸ፦ “ማንም የተጠማ ቢኖር ወደ እኔ ይምጣና ይጠጣ። ግብዣው ለማንም ወይም ለሰው ልጆች በሙሉ ነው:: የተጠማ ሌላው መስፈርት ነው ስለዚህ የሚያስፈልገው ሰው መሆንና መጠማት ወደ እርሱም መቶ መጠጣት ነው ማለት ነው:: ዛሬም ግብዣው አልተለወጠም እየሱስ ከብሯልና መንፈስ ቅዱስ ወርዷል:: ወደ እርሱ መተን እንጠጣ!
በእኔ የሚያምን መጽሐፍ እንዳለ፥ የሕይወት ውኃ ወንዝ ከሆዱ ይፈልቃል።” አሜን! ማንም በእርሱ ቢያምን ወደእርሱ ተጠምቶ ቢመጣ እንደቃሉ የሕይወት ውኃ ወንዝ ከሆዱ ይፈልቃል:: አሜን
አባት ሆይ የህይወት ውሃ ወንዝ ከሆዴ ይፈልቃልና ተመስገን እኔን አረስርሶ ለሌላውም የሚደርስ ነውና ማንነትህ ቅዱሱ የእግዚአብሔር መንፈስ ክበር:: በልግስና ሳትሰስት ትሰጣለህና ተባረክ:: አሜን!
ዮሐንስ 7: 40-53
ዮሐንስ 7:50፤ ከእነርሱ አንዱ በሌሊት ቀድሞ ወደ እርሱ መጥቶ የነበረ ኒቆዲሞስ፦
ዮሐንስ 7:51፤ “ሕጋችን አስቀድሞ ከእርሱ ሳይሰማ ምንስ እንዳደረገ ሳያውቅ በሰው ይፈርዳልን?” አላቸው።
ዮሐንስ 7:52፤ እነርሱም መለሱና፦ “አንተም ደግሞ ከገሊላ ነህን? ነቢይ ከገሊላ እንዳይነሣ መርምርና እይ፡” አሉት።
ከበዓሉም በታላቁ በኋለኛው ቀን ኢየሱስ ቆሞ እንዲህ ብሎ ጮኸ፦ “ማንም የተጠማ ቢኖር ወደ እኔ ይምጣና ይጠጣ። በእኔ የሚያምን መጽሐፍ እንዳለ፥ የሕይወት ውኃ ወንዝ ከሆዱ ይፈልቃል።” ሲላቸው በመካከላቸው ክርክር ሆነ::
የመከራከርያ ነጥባቸው ይህ ክርስቶስ ነው፡” አሉ፤ ሌሎች ግን፦ “ክርስቶስ በእውኑ ከገሊላ ይመጣልን? ክርስቶስ ከዳዊት ዘር ዳዊትም ከነበረባት መንደር ከቤተ ልሔም እንዲመጣ መጽሐፍ አላለምን?” አሉ። አይሁድም ግራ ገብቷቸዋል ‘ትፈልጉኛላችሁ አታገኙኝምም፡ እኔም ወዳለሁበት እናንተ ልትመጡ አትችሉም፡’ ብሏቸው ነበረና:: እርሱ ስለምድር አልተናገረም:: በዚህ ውስጥ ግን ያመኑበትም ነበሩ::
ቃሉ እንደሚለን ከእነርሱም አንዳንዶቹ ሊይዙት ወደዱ ነገር ግን እጁን ማንም አልጫነበትም። አለቆችም ልከው ሎሌዎቹ ለመያዝ አልፈለጉም:: ያለ እርሱ ፈቃድ አንዳች አይሆንም:: በዚህም ጊዜ አለቆች ሕግን የማያውቀው ይህ ሕዝብ ርጉም ነው፡” ብለው ህዝቡን ረገሙ:: ምን አይነት ድፍረት ነው? ምክንያታቸው ከአለቆች ወይስ ከፈሪሳውያን በእርሱ ያመነ አለን? ነበር:: እነርሱ ካላፀደቁ ህዝቡ ምንም ማድረግ አይችልም ማለት ነው?!
በዚህ መሀል ግን ከእነርሱ አንዱ በሌሊት ቀድሞ ወደ እርሱ መጥቶ የነበረ ኒቆዲሞስ፦ “ሕጋችን አስቀድሞ ከእርሱ ሳይሰማ ምንስ እንዳደረገ ሳያውቅ በሰው ይፈርዳልን?” አላቸው። ቢነቅፉትም እንኳን በዚህ ንግግር ነገሩን አበረደው:: ይህ ሰው ከጌታ ጋር ጊዜ አሳልፏል በጥቂቱም ቢሆን ገብቶታል::
በመካከላቸው የቆመው ይህ ጌታ እየጠበቁት ያለ መሲህ ሆኖ ሳለ አላወቁትም እርሱ ግን በነብያት የተናገረውን እያደረገ ነው የተገለጠው ምንም ያላሟላው ነገር የለም:: እናውቃለን ያሉት ግንበኞች የማዕዘኑን ራስ ናቁት:: ለእኔ ግን መዳኛዬ ሆነልኝ አልተደናቀፍኩበትም::
አባት ሆይ ከዓለም ጥበበኞች ይልቅ እኔን ምንም እውቀት የሌለኝን መንግስትህን መረዳት ስለሰጠኸኝ አመሰግንሃለሁ! ከእኔ የሆነ ምንም የለም ሁሉ በአንተ ነውና ተመስገን:: አሁንም የክብር አባት ሆይ የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ አምላክ ሆይ አንተን በማወቅ የጥበብንና የመገለጥን መንፈስ ስጠኝ። አሜን!
ዮሐንስ 8: 1-11
10፤ ኢየሱስም ቀና ብሎ ከሴቲቱ በቀር ማንንም ባላየ ጊዜ፦ “አንቺ ሴት፥ እነዚያ ከሳሾችሽ ወዴት አሉ? የፈረደብሽ የለምን?” አላት።
ዮሐንስ 8:11፤ እርስዋም፦ “ጌታ ሆይ፥ አንድ ስንኳ” አለች። ኢየሱስም፦ “እኔም አልፈርድብሽም፤ ሂጂ ከአሁንም ጀምሮ ደግመሽ ኃጢአት አትሥሪ፡” አላት።
በደብረ ዘይት ጌታን የገጠመው ወጥመድ በዝሙት የተያዘችን ሴት አምጥተው መወገር አለባት አንተ ግን ምን ትላለህ የሚል ነበረ:: ውገርዋት ቢል በሮም ሊያሲዙት አትወገር ቢል ህግን ይሽራል ሊሉ ተጠብበው ነበረ የመጡት ከአንድም ሁለት አማራጭ ይዘው:: እርሱ ግን አልተያዘም ሴቲቱንም ነፃ አደረጋት:: የሚገርመው ግን ሴቲቱ ከማን ጋር ነው ያመነዘረችው? ህጉ የሚለው ሁለቱንም በድንጋይ መውገር ነው:: ታድያ የታለ ሰውየው? በዘዳግም 22:22፤ ማናቸውም ሰው ከሌላ ሰው ሚስት ጋር ተኝቶ ቢገኝ፥ አመንዝራውና አመንዝራይቱ ሁለታቸው ይሙቱ፤ እንዲሁም ክፉውን ነገር ከእስራኤል ታስወግዳለህ።
ሁሉን በሚመረምርና ቅዱስ በሆነው ጌታ ፊት ከነኃጥያታቸው መቆም አልቻሉም:: ኃጥያት የሌለበት ይውገራት ሲላቸው ሁሉም እየተወቀሱ ጥለው ሄዱ:: በመሬት ላይ የፃፈው ምን ይሆን? ከዚህስ በፊት ጽፎ የነበረው መቼ ነበር? በዘጸአት 31:18፤ እግዚአብሔርም ከሙሴ ጋር በሲና ተራራ የተናገረውን በፈጸመ ጊዜ በእግዚአብሔር ጣት የተጻፈባቸውን ከድንጋይ የሆኑ ሁለቱን የምስክር ጽላቶች ሰጠው። አሁንም ይህንኑ ህግ ይሆን የፃፈው?
ሴቲቱንም አንቺ ሴት፥ እነዚያ ከሳሾችሽ ወዴት አሉ? የፈረደብሽ የለምን?” አላት። እርስዋም፦ “ጌታ ሆይ፥ አንድ ስንኳ” አለች። ምን አይነት ርህሩህ ጌታ! አዳናት:: ይህ ማለት ግን ኃጥያት በፊቱ ምንም አይደለም ማለት ነው?! በፍጹም ኃጥያት በፊቱ ኃጥያት ነው::ስለዚህም ነው “እኔም አልፈርድብሽም፤ ሂጂ ከአሁንም ጀምሮ ደግመሽ ኃጢአት አትሥሪ፡” ያላት። ደግመሽ ኃጥያት አትስሪ!! ኃጥያተኛን እንጂ ኃጥያቱን አይወድም:: የኃጥያተኞት ወዳጅ መድኃኒት እየሱስ ስሙ ይባረክ:: እኛም በዙሪያችን ያሉትን ከመውቀስ በቀና ልብ እውነትን በፍቅር ይዘን ሰዎችን ወደ ጌታ እናምጣ እንጂ በማንም እንዳንፈርድ:: ፍርድ አልተሰጠንም ጌታም እንኳን እኔ በዓለም ልፈርድ አልመጣሁም ብሎ የለ:: ይህ ዘመን ኃጥያተኞችን ከየመንገዱ እየሰበሰብን ቤቱን የምንሞላበትጊዜ ነው:: መኽሩ ነጥቷል!
አባት ሆይ ከፈራጅነት ወጥቼ በርህራሄ ይህንን የደረሰውን አዝመራ ስትሰበስብ ገንዘብህ አድርገኝ:: በእየሱስም አሜን!
ዮሐንስ 8:12፤ ደግሞም ኢየሱስ፦ “እኔ የዓለም ብርሃን ነኝ፤ የሚከተለኝ የሕይወት ብርሃን ይሆንለታል እንጂ በጨለማ አይመላለስም፡” ብሎ ተናገራቸው።
እየሱስ የዓለም ብርሃን ነው!! ጨለማ በፊቱ አይቆምም የእኛንም ጨለማ አጠፋው!! ስንከተለውም የሕይወት ብርሃን ሆነልን እንጂ በጨለማ አንመላለስም::
ምን አይነት ህይወት ተሰጠን በጨለማ ከመደናበር አውጥቶ ወደ ፍቅሩ ልጅ መፍለስ:: ይህ ጨለማ ግን ብቻውን አይደለም ሰይጣን የሚሰለጥንበትና እንደወደደ የሚያደርግበት ነው:: ነፃ የወጣነው ከጨለማውም ገዢ ነው:: እርሱ በእኛ ላይ አንዳች የለውም:: ብርሃናችን እየሱስ በርቶልናል!!
ዮሐንስ 8: 13-20
14፤ ኢየሱስ መለሰ አላቸውም፦ “እኔ ስለ ራሴ ምንም እንኳ ብመሰክር ከወዴት እንደመጣሁ ወዴትም እንድሄድ አውቃለሁና ምስክርነቴ እውነት ነው፤ እናንተ ግን ከወዴት እንደ መጣሁ ወዴትም እንድሄድ አታውቁም።
15፤ እናንተ ሥጋዊ ፍርድን ትፈርዳላችሁ፤ እኔ በአንድ ሰው ስንኳ አልፈርድም።
16፤ የላከኝ አብ ከእኔ ጋር ነው እንጂ ብቻዬን አይደለሁምና እኔ ብፈርድ ፍርዴ እውነት ነው።
17፤ የሁለት ሰዎችም ምስክርነት እውነት እንደ ሆነ በሕጋችሁ ተጽፎአል።
እየሱስ ከወዴት እንደመጣ ወዴትም እንዲሄድ ያውቃል ምስክርነቱ እውነት ነው፤ በዙሪያው ያሉት ግን ከወዴት እንደ መጣ ወዴትም እንዲሄድ አያውቁም። ምክንያቱም ስጋዊ ናቸውና የዮሴፍና የማርያም ልጅ እያሉ ነው የሚያውቁት ምንም እንኳን መሲህ ይመጣል ብለው በጉጉት እየጠበቁ ቢሆንም:: የማንንም ምስክርነት የማይፈልገው እየሱስ የአባቱን ምስክርነት አግኝቷል በእርሱ ደስ የሚለኝ የምወደው ልጄ እርሱ ነው ብሏልና:: የሰውም ምስክርነት በደንብ አግኝቷል በተለይ ከመጥምቁ ዮሃንስ ግን አልሰሙም::
እነርሱ ላይ እንፈርዳለን እንጂ እኛም ይህንን ጌታ ጌታችንና ንጉሳችን አዳኛችን መመክያችን ብለን ስናበቃ የምንመላለሰው እንዴት ነው? አሁን ጌታ ተናግሮን በቃሉ አጽናንቶን እረድቶን ተመልሰን እዛው ውስጥ እንገኝ የለም? እግዚአብሔር ይገስጸውና ይህ ጠላት የምድሩን እያሳየ ወደ ምድር ሊስበን ይፈልጋል:: ዛሬ ካለንበት እንውጣ በላይ ያለውን እንሻ ወዴት እንደምንሄድ የምናውቅ ነንና ብል በማይበላበት ነገራችንን እናከማች:: የከበበንን ሁሉ አልሰማህም በጌታዬ እታመናለሁ! እንቢ እንበለው!! በእየሱስ ስም ከበባ ሁሉ ይበተን! አምላካችን የቅርብ አምላክ ነው ከምስጋና ጋር ልመናችንን እናሳውቅ እንጂ በአንዳች አንጨነቅ! እንድንጨነቅ አልተጠራንም እንድንከተለውና እንድናብለጨልጨው እንጂ:: ስለ እኔ የሚያስብ በሰማይ አለ! አሜን!!
ዮሐንስ 8: 21-30
23፤ እንዲህም አላቸው፦ “እናንተ ከታች ናችሁ፥ እኔ ከላይ ነኝ፤ እናንተ ከዚህ ዓለም ናችሁ፥ እኔ ከዚህ ዓለም አይደለሁም።
24፤ እንግዲህ፦ ‘በኃጢአታችሁ ትሞታላችሁ፡’ አልኋችሁ፤ እኔ እንደሆንሁ ባታምኑ በኃጢአታችሁ ትሞታላችሁና።”
25፤ እንግዲህ፦ አንተ ማን ነህ? አሉት። ኢየሱስም አላቸው፦ “ከመጀመሪያ ለእናንተ የተናገርሁት ነኝ።
28፤ ስለዚህም ኢየሱስ እንዲህ አላቸው፦ “የሰውን ልጅ ከፍ ከፍ ባደረጋችሁት ጊዜ፡ እኔ እሆን ዘንድ አባቴም እንዳስተማረኝ፡ እነዚህን እናገር ዘንድ እንጂ ከራሴ አንዳች እንዳላደርግ፡ በዚያን ጊዜ ታውቃላችሁ።
29፤ የላከኝም ከእኔ ጋር ነው፤ እኔ ደስ የሚያሰኘውን ዘወትር አደርጋለሁና አብ ብቻዬን አይተወኝም።”
30፤ ይህን ሲናገር ብዙዎች በእርሱ አመኑ።
እኔ ከዚህ ዓለም አይደለሁም እያለ ቢነግራቸው ወይም በኃጢአታችሁ ትሞታላችሁ፡’ አልኋችሁ፤ እኔ እንደሆንሁ ባታምኑ በኃጢአታችሁ ትሞታላችሁና ቢላቸውም ሊገባቸው አልቻለም:: ምክንያቱም እነሱ ከዚህ ዓለም ናችሁ፥ እርሱ ግን ከላይ ነው፤ እንዴት ይግባቡ:: እኛም የገባን ጌታ ገልጦልን እንጂ በዝች አእምሮ ይህንን ጌታ መረዳት አይታሰብም::
በክርስቶስ ያሉት ኩነኔ የለባቸውም የተባለበት ምክንያት እኔ እንደሆንሁ ባታምኑ በኃጢአታችሁ ትሞታላችሁና የሚለውን አምነን ከኃጥያታችን በታች ከመሆን ስላመለጥን ነው::
የሰውን ልጅ ከፍ ከፍ ባደረጋችሁት ጊዜ፡ ብሎ ሲል ስለመስቀሉ እንጂ ስለ መሾም ወይም ስለመንገስ እንዳልሆነ ማን ያስተውላል:: እየሱስ በመስቀል ላይ ከፍ ከፍ ሲል እኛንም ወደእርሱ ሳበንና ዳንን:: እርሱ የኖረው አባቱን በመታዘዝና ደስ በማሰኘት ነው:: የላከኝም ከእኔ ጋር ነው፤ እኔ ደስ የሚያሰኘውን ዘወትር አደርጋለሁና አብ ብቻዬን አይተወኝም።” እኛም እርሱን እንታዘዝና ደስ እናሰኘው:: ትእዛዚቱም እርሱን እንድንወድ ሌሎችንም እንደራሳችን እንድንወድ ነውና:: ፍቃዱን ማድረግ ይሁንልን::
በዚህ ሁሉ ክርክር ውስጥ በእርሱ የሚያምኑ ተገኙ:: ለሰዎች ስንመሰክር ቃሉ ምን አይነት ልብ ላይ እንደሚያርፍ አናውቅምና መመስከራችንን ከእግዚአብሔር ጋር ታረቁ ማለታችንን አንተው እንዲያውም አብዝተን እናድርግ አለበለዚይያ ግን በኃጥያታቸው ይሞታሉ እርሱን ካላወቁት:: ጌታ ይርዳን እንደ ሊድያም የተከፈቱ ልብ ያላቸውን ይስጠን! አሜን!
አባት ሆይበእኔ ስራ እየሱስ ይታይ!
አሜን
ዮሐንስ 8: 31-39
31፤ ኢየሱስም ያመኑትን አይሁድ እንዲህ አላቸው፦ “እናንተ በቃሌ ብትኖሩ በእውነት ደቀ መዛሙርቴ ናችሁ፤
32፤ እውነትንም ታውቃላችሁ እውነትም አርነት ያወጣችኋል።”
ደቀ መዝሙር የሚያደርገን በቃሉ ስንኖር ነው ቃሉም የሚነግረን እርሱን እንድንወድ የሰውንም ልጅ ሁሉ እንደራሳችን እንድንወድ ነው:: በዚህም ምልክት (በፍቅር ) ደቀ መዛሙርት መሆናችን ይታወቃል:: ቃሉም እውነት ነውና የሚያሸንፈው የለምና ስናውቀው አርነት ያወጣናል::
ይህንን ሲላቸው የዳኑትም ማፈግፈግ ያዙ የምን አርነት ነው የምትለን እኛ ባርያ አይደለንም አሉት በእነሱ አባባል መንፈሳዊዉን አይደለም የምድሩን ነው ነገር ግን በሮም አገዛዝ ስር ባርያ ነበሩ:: በግብጽም በሌሎችም ነገስታት ባርያ ሆነዋል:: የቱን ነው የሚያወሩት ግን?
ኢየሱስ መለሰ፥ እንዲህ ሲል፦ “እውነት እውነት እላችኋለሁ፥ ኃጢአት የሚያደርግ ሁሉ የኃጢአት ባርያ ነው። እየሱስ ስለኃጥያት ባርነት ያወራል እነሱ ስለዘር! ባርያም ለዘላለም በቤት አይኖርም፤ ልጁ ለዘላለም ይኖራል። እንግዲህ ልጁ አርነት ቢያወጣችሁ በእውነት አርነት ትወጣላችሁ። ይህ እውነት የሆነ ቃል እየሱስ ማንም ማንፃት ከማይችለው ኃጥያት ከተባለ በሽታ ነፃ ያወጣል አለበለዚያ ግን በኃጥያት መሞት ነው የሚጠብቃቸው::
መልሰውም፦ “አባታችንስ አብርሃም ነው፡” አሉት። ኢየሱስም፦ “የአብርሃም ልጆች ብትሆኑ የአብርሃምን ሥራ ባደረጋችሁ ነበር። አብርሃም ጌታን አምኖ ጽድቅ ሆኖ የተቆጠረለት እንዲሁም ደግሞ ወደ እርሱ ሲመጣ ምግብን አዘጋጅቶ ያቀርብ ነበር እንጂ ሊገድለው አልተነሳም ነበር:: ይህ ነበረ የአብርሃም ምሳሌ ማመንና ጌታን መቀበ::
እየሱስ አርነት ያወጣኸኝ እውነቴ ጌታዬና መድኃኒቴ እውነትም ህይወትም መንገድም አንተ ነህና እንዳውቅህ ስለረዳኸኝ ተመስገን! እገዛልሃለሁኝ! እንዳዳንከኝም ምስክር እሆናለሁ! ጸጋህ በሙላት በእኔና በህዝብህ ላይ ይገለጥ:: አሜን!!
ዮሐንስ 8: 40-47
42፤ ኢየሱስም አላቸው፦ “እግዚአብሔርስ አባታችሁ ከሆነ በወደዳችሁኝ ነበር፤ እኔ ከእግዚአብሔር ወጥቼ መጥቻለሁና፤ እርሱ ላከኝ እንጂ ከራሴ አልመጣሁምና።
43፤ ንግግሬን የማታስተውሉ ስለ ምንድር ነው? ቃሌን ልትሰሙ ስለማትችሉ ነው።
45፤ እኔ ግን እውነትን የምናገር ስለ ሆንሁ አታምኑኝም።
46፤ ከእናንተ ስለ ኃጢአት የሚወቅሰኝ ማን ነው? እውነት የምናገር ከሆንሁ እናንተ ስለ ምን አታምኑኝም?
47፤ ከእግዚአብሔር የሆነ የእግዚአብሔርን ቃል ይሰማል፤ እናንተ ከእግዚአብሔር አይደላችሁምና ስለዚህ አትሰሙም።”
እግዚአብሔርስ አባታችን ነውና እኛስ ጌታን እንወደዋለን!! ምክንያቱም ጌታ እየሱስ ከእግዚአብሔር ወጥቶ መቷልና፤ እርሱ ተልኮ እራሱን አዋርዶ መጣ እንጂ በራሱ አልመጣም። ለእነርሱ ግን ንግግሬን የማታስተውሉ ስለ ምንድር ነው? ቃሌን ልትሰሙ ስለማትችሉ ነው:: ብሎ ጥያቄ ጠይቆ እራሱ መለሰው ቃሉን ማመንና ማስተዋል አልሆነላቸውም:: እኔ ግን እውነትን የምናገር ስለ ሆንሁ አታምኑኝም አላቸው። ለምን ንግግሩን እንደማያስተውሉ ይገርማል ወደ እርሱ የሚመጡትም አንዳች እንማራለን ወይም እርሱ መሲህ ይሆንን በሚል ሳይሆን እግረ መንገዳቸውን ወይም ጉዳያቸውን እያደረጉ ለመስማት ያህል እንጂ ህይወትን ፈልገው አይመስልም:: እየሱስ ግን እውነትን ይናገራል:: እርሱ እውነት ነውና ይዋሽ ዘንድ የሰው ልጅ አይደለም! የሚሰማ ዛሬም ይስማ ይህ ቃል እውነት ነው! የሚሰራ ነው! መንፈስም ነው!
ይህ አባባሉ ልቤን ይነካዋል ከእናንተ ስለ ኃጢአት የሚወቅሰኝ ማን ነው? እውነት የምናገር ከሆንሁ እናንተ ስለ ምን አታምኑኝም? እውነቱን ነው እኮ:: በእውነትና በጽድቅ እየተመላለሰ መሲሁ ሲመጣ የሚያደርጋቸውን ምልክቶች እያደረገ ሊሰሙት አልቻሉም:: እንግዲህ ምን ያድርግ እውነትም ግራ ያጋባል ምን እንደሚፈልጉ! ዛሬስ እኛ ቃሉን እንደ እግዚአብሔር ቃል አክብረን እንወስዳለን ወይስ ለመስማት ያህል ነው? ይህ ጌታ የከበረ ቃሉም እውነት ነው እንመስረትበት እንደቃሉ እንጂ በሎጂክ አንመላለስ!
እናንተ ከአባታችሁ ከዲያብሎስ ናችሁ የአባታችሁንም ምኞት ልታደርጉ ትወዳላችሁ። እርሱ ከመጀመሪያ ነፍሰ ገዳይ ነበረ፤ እውነትም በእርሱ ስለ ሌለ በእውነት አልቆመም። ሐሰትን ሲናገር ከራሱ ይናገራል፥ ሐሰተኛ የሐሰትም አባት ነውና። ከእግዚአብሔር የሆነ የእግዚአብሔርን ቃል ይሰማል፤ እናንተ ከእግዚአብሔር አይደላችሁምና ስለዚህ አትሰሙም። አለቀ!! ከእግዚአብሔር የሆንን እኛ ግን እንሰማለን ቃሉም ከእኛ ጋር ይዋሃዳል:: እግዚአብሔር በእውነት በጸጋው ይርዳን ይደግፈን!!
አባት ሆይ ቃልህን መስማትና ማስተዋል ይብዛልን! አሜን!
ዮሐንስ 8: 48-59
56፤ አባታችሁ አብርሃም ቀኔን ያይ ዘንድ ሐሤት አደረገ፥ አየም ደስም አለው።”
58፤ ኢየሱስም፦ “እውነት እውነት እላችኋለሁ፥ አብርሃም ሳይወለድ እኔ አለሁ፡” አላቸው።
59፤ ስለዚህ ሊወግሩት ድንጋይ አነሡ፤ ኢየሱስ ግን ተሰወራቸው ከመቅደስም ወጥቶ በመካከላቸው አልፎ ሄደ።
ከእግዚአብሔር የሆነ የእግዚአብሔርን ቃል ይሰማል፤ እናንተ ከእግዚአብሔር አይደላችሁምና ስለዚህ አትሰሙም።” ሲላቸው ጋኔን አለብህ ብለው ለማለት ትንሽም አላፈሩ ነገር ግን ደፈሩ! ኢየሱስም መለሰ፥“እኔስ ጋኔን የለብኝም፡ ነገር ግን አባቴን አከብራለሁ፡ እናንተም ታዋርዱኛላችሁ።
እኔ ግን የራሴን ክብር አልፈልግም፤ የሚፈልግ የሚፈርድም አለ። እኔ ራሴን ባከብር ክብሬ ከንቱ ነው፤ የሚያከብረኝ እናንተ አምላካችን የምትሉት አባቴ ነው:: ክብር የሚገባው አለ እርሱም አብ አባት ነው አላቸው! ዛሬ በህይወቴ አከብርሃለሁ! ጌታ እየሱስ ክብር አልፈልግም አለና እራሱን በመስቀል ሰጠ ያኔ ከሁሉ በላይ ከበረ ከስምም ሁሉ በላይ ስምን አገኘ! አሜን እየሱስ ክርስቶስ ጌታ ነው ለዚህ ስም ሁሉ ይንበረከካል!! በአብ ቀኝ በክብር ከፍ ብሎ ስልጣን ሁሉ በሰማይና በምድር ተሰቶት አለ! እርሱ አልፋና ኦሜጋ ነው! አሜን
እየሱስም እንደዚህ አላቸውአብን አውቀዋለሁ። አላውቀውም ብል እንደ እናንተ ሐሰተኛ በሆንሁ፤ ዳሩ ግን አውቀዋለሁ ቃሉንም እጠብቃለሁ:: እውነት እውነት እላችኋለሁ፥ ቃሌን የሚጠብቅ ቢኖር ለዘላለም ሞትን አያይም።” በነገር ሁሉ እንድንመስለው የሚፈልግ ጌታ እኔ ቃሉን ጠብቄአለሁና እናንተም ቃሌን ጠብቁ ብሎ ህይወትን ሰጠን:: ይህንን ህይወት ማንም ከእኛ አይወስደውም ምክንያቱም ወደእኔ የመጡትን ወደ ውጪ አላወጣም ብሏልና::
አብርሃም ቀኔን ያይ ዘንድ ሐሤት አደረገ፥ አየም ደስም አለው።” ሲላቸው ግራ ገብቷቸው አንተ ሃምሳ አመት አልሞላህ አሉት እርሱ ግን ገና በሰላሳዎቹ መጀመርያ ነበረ:: ይህ ማለት ባየነውም ጊዜ ደም ግባት የለውም እንደተባለው በኢሳያስ መልክት ጌታ ከእድሜው በላይ ይመስል ይሆንን ብዬ አስባለሁ:: ኢየሱስም፦ “እውነት እውነት እላችኋለሁ፥ አብርሃም ሳይወለድ እኔ አለሁ፡” አላቸው። አሜን እርሱ የሁሉ ፈጣሪ የሁሉ መገኛ የዘላለም አምላክ ነው:: አሜን!
ስለዚህ ሊወግሩት ድንጋይ አነሡ፤ ኢየሱስ ግን ተሰወራቸው ከመቅደስም ወጥቶ በመካከላቸው አልፎ ሄደ። ፍጥረት ፍጥረትነቱን ሲረሳ እንደዚህ ይሆናል:: በእርሱ ላይ ያለጊዜው አንዳች ማድረግ አልቻሉም:: በጊዜው ግን እራሱን ሰጠ ነፍሱን በፈቃዱ አኖራት ስለ እኛ:: እሰይ መጣህልን ልትታደገን ማለት ሲገባው የሰው ልጅ ጭራሽ ከእሱ ጋር ክርክር ገባ ጌታም ታህሶ የመጣበትን ፈጽሞ ሄደ ምን አይነት ጌታ ነው? ምን አይነትስ ፍቅር ነው? ዛሬ የትኛው ክብራችን ነው አሳዝኖን ከመመስከር ወደኃላ እንድንል የሚያደርገን?! ለጌታ እኛነታችን ይገባዋል እርሱ ክብሩን ትቶ ስለእኛ መቷልና እኛም ለእርሱ እንኑር::
አባት ሆይ እራሴን በፊትህ ቅዱስና ህያው መስዋአት አድርጌ አቀርባለሁ ተጠቀምብኝ!!
ዮሐንስ 9: 1-5
3፤ ኢየሱስም እንዲህ ብሎ መለሰ፦ “የእግዚአብሔር ሥራ በእርሱ እንዲገለጥ ነው እንጂ እርሱ ወይም ወላጆቹ ኃጢአት አልሠሩም።
4፤ ቀን ሳለ የላከኝን ሥራ ላደርግ ይገባኛል፤ ማንም ሊሠራ የማይችልባት ሌሊት ትመጣለች።
5፤ በዓለም ሳለሁ የዓለም ብርሃን ነኝ።”
የቀደመውን ምዕራፍ የዘጋው ሊገድሉት ሲፈልጉ በመካከላቸው አልፎ እንደሄደ ነግሮን ነው:: ሲያልፍም ይህንን ሰው አየው:: ግን ከነበረበት ሁኔታ ማድረግ የነበረበት ያንን አካባቢ ጥሎ መሄድ ነበር እርሱ ግን አሳቡ ሁሉ የመጣበትን ዓላማ መፈጸ ም ላይ ነበረ::
በሰውየው በኩል ምንም አይነት አስበኝ የሚልም ነገር የለውም የዕለት ተዕለት ተግባሩን እያከናወነ ነው:: ደቀ መዛሙርቱ ግን ምክንያቱን ማወቅ ፈለጉ ለምን እውር ሆኖ ተወለደ? የማን ኃጥያት ነው? ኢየሱስም እንዲህ ብሎ መለሰ፦ “የእግዚአብሔር ሥራ በእርሱ እንዲገለጥ ነው እንጂ እርሱ ወይም ወላጆቹ ኃጢአት አልሠሩም። መፈላሰፍ አያስፈልግም የእግዚአብሔር ክብር መገለጥ ነው የሚያስፈልገው:: አንዳንዴ መውጫ የሌለው ቅርቃር ውስጥ እንገባለን በእንደነዚህ ባሉ ጥያቄዎች ተተብትበን:: ከመፍረድ ወተን አሁን መደረግ ያለበት ላይ ነው ትኩረታችንን ማድረግ ያለብን::
ጌታ እየሱስ የመጣበትን ዓላማ አስታወሳቸው:- ቀን ሳለ የላከኝን ሥራ ላደርግ ይገባኛል፤ ማንም ሊሠራ የማይችልባት ሌሊት ትመጣለች። በዓለም ሳለሁ የዓለም ብርሃን ነኝ አላቸው :: ዛሬ ለእኛ ቀን ነው የተላክን ነንና የላከንን እናገልግል:: ክብሩን ለመግለጥ በእኛ ውስጥ እየሱስ አለ ይሰራል:: አባቴ ይሰራል እኔም እሰራለሁ እንዳለው የሚሰራ ጌታ ይዘን ቁጭ አንበል:: የዓለም ብርሃን አድርጎናል በዚህ ጨለማ በዋጠው ዓለም እያበራን በችግር ውስጥ ባሉትም ላይ ሳንፈርድ የዋልንበትም ቀን ሳይረብሸን (እየሱስ የሞት ሙከራ ነበር የተደረገበት ከደቂቃዎች በፊት) በፍቅርና በመራራት እናብራና እናብለጭልጨው::
አባትሆይ ፈቃድህን ፈጽሜ ልታዘዝህ የጊዜው ነገር ልቤን አይያዘው ልቤን በመንገዴ ላይ ላድርግ እርዳኝ::
ዮሐንስ 9: 6-7
6፤ ይህን ብሎ ወደ መሬት እንትፍ አለ በምራቁም ጭቃ አድርጎ በጭቃው የዕውሩን ዓይኖች ቀባና፦
7፤ “ሂድና በሰሊሆም መጠመቂያ ታጠብ፡” አለው፤ ትርጓሜው፡ “የተላከ፡” ነው። ስለዚህ ሄዶ ታጠበ፡ እያየም መጣ።
ቀን ሳለ የላከኝን ሥራ ላደርግ ይገባኛል፤ ማንም ሊሠራ የማይችልባት ሌሊት ትመጣለች ብሎ ይህንን ሰው አሰበው:: አዳምን ከአፈር ያበጀው ጌታ ይህ ሰው ዓይኑ እንዳልተፈጠረ አውቆ ልምድ ስላለው እንትፍ ብሎ አፈሩን ዓይን አደረገው! ሃሌሉያ!! ሳይንስ ምን ቢመራመር ከአፈር አንዳች ነገር አይሰራም እንዲያውም አያስበውም:: ለሰርጀሪ እንኳን እንዴት እንደሚያጸዱ እናውቃለን::
ይህ ሰው ያልጠበቀው ነው የሆነለት ዛሬ የፈውሴ ቀን ነው ብሎ አላሰበም ድንገት ግን ስለእርሱ ውይይት ተነሳ:: እየሱስ ፈጣሪው አጠገቡ መቆሙንም አላወቀም:: ማን እንደሆነም አላወቀውም የታለ ሲባልም እኔ እንጃ ነበረ መልሱ:: እምነትም ልመናም አልነበረውምና ጭቃውን ከቀባው በኃላ አንድ ነገር አዘዘው ሂድና በሰሊሆም መጠመቂያ ታጠብ፡” አለው፤ ትርጓሜው፡ “የተላከ፡” ነው። ስለዚህ ሄዶ ታጠበ፡ እያየም መጣ። እምነቱ በመሄዱ ላይ ነበረ:: ያለ እምነት እግዚአብሔር ደስ ማሰኘትና ከእርሱም መቀበል አይቻልም:: ዛሬም ድንገት ወደ ነገራችንይህጌታ ይምጣ ጥያቄያችን ይመለስ::
አምላኩ አሰበውና ከወደቀበት ጨለማ ገላገለው:: እየሱስ አንድ አይነት ብቻ የፈውስ መንገድ አይከተልም ይሄኛው ደግሞ ከሁሉም በጣም የተለየየ ነው:: ይህ መሲህ ሲመጣ ከሚሆኑት ምልክቶች አንዱ ይህ ነው እውሮች ይበራሉ:: ጌታ እየሱስ እንዲታጠብ የላከው ቦታ “የተላከ” ነው የተላከ መሆኑን እየጠቆመ ቢሆንም እንኳን ህግን እናውቃለን የሚሉትና የሚያዮት ታውረዋልና መሲሁን ጌታ አላወቁትም::
አባት ሆይ አንተን ማወቅ ሆኖልኛልና ተመስገን!! ጨለማዬን አብርተሀልና ተመስገን የህይወት ብርሃኔ እየሱስ ክበር! ዛሬም በስራ ላይነህና በጨለማ የሄደ ህዝብ ብርሃን ያይ ዘንድ የሰዎችን ልብ አብራ የሚድኑ ነፍሳትንም እንደሊድያ ልባቸውን እየከፈትህ ስጠን :: አሜን!
ዮሐንስ 9: 8-34
17፤ ከዚህም የተነሣ ዕውሩን፦ “አንተ ዓይኖችህን ስለ ከፈተ ስለ እርሱ ምን ትላለህ?” ደግሞ፥ አሉት። እርሱም፦ “ነቢይ ነው፡” አለ።
25፤ እርሱም መልሶ፦ “ኃጢአተኛ መሆኑን አላውቅም፤ ዕውር እንደ ነበርሁ፡ አሁንም እንዳይ፡ ይህን አንድ ነገር አውቃለሁ፡” አለ።
27፤ እርሱም መልሶ፦ “አስቀድሜ ነገርኋችሁ አልሰማችሁምም፤ ስለ ምን ዳግመኛ ልትሰሙ ትወዳላችሁ? እናንተ ደግሞ ደቀ መዛሙርቱ ልትሆኑ ትወዳላችሁን?” አላቸው።
ዓይኖቹ በተከፈቱለት ሰው ምክንያት ብዙ ውዝግብ ነበረ አንዳንዶች እሱ ነው ሲሉ ሌሎች እሱ አይደለም በሚል ሲሆን ሌላው ይህ ሰው ሰንበትን አያከብርምና ከእግዚአብሔር አይደለም፡” ሌሎች ግን፦ “ኃጢአትኛ ሰው እንደነዚህ ያሉ ምልክቶች ሊያደርግ እንዴት ይችላል?” አሉ። በመካከላቸውም መለያየት ሆነ።
አሁንም አሁንም ሲጠይቁት ሰውዬው መለሰ፥ እንዲህም አላቸው፦ “ከወዴት እንደ ሆነ እናንተ አለማወቃችሁ ይህ ድንቅ ነገር ነው፥ ዳሩ ግን ዓይኖቼን ከፈተ። አስተማሪና መሪ ነን የሚሉት እየሱስን አለማወቃቸው ገርሞታን እንደዚህ ያለ ነብይ መኖሩ እንዴት ጠፋቸው ብሎ ነው እየሱስ ለሱ ገና ነብይ ነው በዚህ ሰዓት:: እግዚአብሔርን የሚፈራ ፈቃዱንም የሚያደርግ ቢኖር ያንን እግዚአብሔር ይሰማዋል እንጂ ኃጢአተኞችን እንዳይሰማ እናውቃለን። ዕውር ሆኖ የተወለደውን ዓይኖች ማንም እንደ ከፈተ ዓለም ከተፈጠረ ጀምሮ አልተሰማም፤ ይህ ሰው ከእግዚአብሔር ባይሆን ምንም ሊያደርግ ባልቻለም ነበር አላቸው:: እንደዚህ ያለ ስብከት በፈሪሳውያን ፊት የሚገርምና ያለውን ውጥረት ያገናዘበ አይመስልም ሰውየው::እውነቱን ነው ማንም እንደዚህ አይነት ምልክት አድርጎ አያውቅም ነበረ::
እነርሱም “አንተ ሁለንተናህ በኃጢአት ተወለድህ፥ አንተም እኛን ታስተምረናለህን?” አሉት። ወደ ውጭም አወጡት። ስለ እየሱስ ስለመሰከረ አውጥተው ጣሉት በባዶ ቅናት:: አንዳንዶቻችን እንደዚህ ነበርን በባዶ ቅናት የምንመላለስ ዛሬ ግን ብርሃን በርቶልን እየሱስ ጌታ ነው እንላለን የምንመላለሰውና የምናመልከው በመንፈስ ሆነልን! ስሙ ይባረክ! በተራ ክርክር ውስጥ ላሉት ታግሰን በፍቅር ወደ እየሱስ ማምጣት ይሁንልን::
አባት ሆይ ዓይኖቻችንን አብርተህ ወደ ፍቅርህ ልጅ ስላፈለስከን ተመስገን::
ዮሐንስ 9: 35-41
35፤ ኢየሱስም ወደ ውጭ እንዳወጡት ሰማ፡ ሲያገኘውም፦ “አንተ በእግዚአብሔር ልጅ ታምናለህን?” አለው።
36፤ እርሱም መልሶ፦ “ጌታ ሆይ፥ በእርሱ አምን ዘንድ ማን ነው?” አለ።
37፤ ኢየሱስም፦ “አይተኸዋልም፡ ከአንተ ጋርም የሚናገረው እርሱ ነው፡” አለው።
ይህ ሰው እየሱስን በተለያየ ማንነቱ አወቀው:: መጀመርያ በዮሐንስ 9:11፤ “ኢየሱስ የሚባለው ሰው‘ በማለት ሰው ብሎ ነው ያወቀው:: ሲቀጥልም እርሱ ነብይ ነው አለ በቁ 17:: እንደዚሁም በቁ 27፤ እናንተ ደግሞ ደቀ መዛሙርቱ ልትሆኑ ትወዳላችሁን?” አላቸው። አስተማሪና መሪ መሆኑን አውቆ እራሱንም ከተከታዮቹ ወይም ከደቀ መዝሙር አንዱ አድርጎ የቆጠረ ይመስላል:: በዚህ አላበቃም እርሱ ከእግዚአብሔር ነው አለ ቁ 33:: ከዛም ቀጥሎ ከቁ 35-38 ባለው ክፍል የእግዚአብሔር ልጅ እንደሆነ ከራሱ ከእየሱስ ሰምቶ አወቀ:: አምነው ዘንድ ማነው ብሎ ጠይቆ ጌታውን አውቆ አምናለሁ ብሎ ሰገደ:: እየሱስም ስግደት አይገባኝም አላለም ተቀበለው:: የትኛውም ነብይ ወይም ሐዋርያ ወይም መልአክ ከሰው አምልኮ ሲቀበሉ አናውቅም:: አምልኮ የሚገባው ጌታ ግን ተቀበለ::
ኢየሱስም ወደ ውጭ እንዳወጡት ሰማ፡ ሲያገኘውም፦ “አንተ በእግዚአብሔር ልጅ ታምናለህን?” አለው። እራሱ እየሱስ ፈልጎት መጣ እናትና አባቱ እንኳን አብረውት አልቆሙም:: እንደቃሉ ጌታዬ በስሙ በተገፋው ዘንድ ተገኘ በውሃ ውስጥ ባለፍክ ጊዜ እኔ ከአንተጋር እሆናለሁ እንዳለ እንዲሁም እኔ ከእናንተ ጋር ነኝ የሚለን ቃሉ እውነት እንደሆነ አሳየን:: ሁሉ የተውትን ፈልጎ መጣ! እራሱንም በበለጠ ገለጠለት:: አቤት የጌታ አሰራር ከሰው ይለያል!
ሌሎች እያዩ እውሮች ተባሉ ኃጥያታቸውም ይኖራል ምክንያቱም አዳኝ አልፈለጉምና በጌታ ባለማመናቸው አሁኑኑ ተፈርዶባቸዋል:: ማን በራሱ ንጹ ሊሆን ይችላል በዚህ ቅዱስ በሆን አምላክ ፊት? ከክርስቶስ በቀር ከእግዚአብሔር ቁጣ ማምለጫ መንገድ የታለና::
አባት ሆይ አንተ አብልጠህ የምትጠጋጋ ወዳጅ ነህና አመሰግንሃለሁ:: ማንም ከጎናችን የሚቆም ሳይኖር የምትደርስ ጌታ ተባረክ! አሁንም በአንተ እንታመናለን ጌታችን ሆይ የምታስመካ ጌታ አንተ ነህ!
አሜን!
ዮሐንስ 10: 1-5
1፤ እውነት እውነት እላችኋለሁ፥ ወደ በጎች በረት በበሩ የማይገባ በሌላ መንገድ ግን የሚወጣ እርሱ ሌባ ወንበዴም ነው፤
2፤ በበሩ የሚገባ ግን የበጎች እረኛ ነው።
3፤ ለእርሱ በረኛው ይከፍትለታል፤ በጎቹም ድምፁን ይሰሙታል፥ የራሱንም በጎች በየስማቸው ጠርቶ ይወስዳቸዋል።
4፤ የራሱንም ሁሉ ካወጣቸው በኋላ በፊታቸው ይሄዳል፥ በጎቹም ድምፁን ያውቃሉና ይከተሉታል፤
5፤ ከሌላው ግን ይሸሻሉ እንጂ አይከተሉትም፥ የሌሎችን ድምፅ አያውቁምና።
ሰዎች ሲናገሩ በእስራኤል በጎች ስም ይወጣላቸዋል ልክ እኛ ለውሻ እንደምናወጣው:: የእረኛቸውንም ድምጽ ለይተው ያውቃሉ:: የእረኛውን ልብስ እንኳን ለብሰው ለማሞኘት ሲሞክሩ በጎቹ አይሰሙም አይታዘዙምም ልብሱን ሳይሆን የሚያውቁት ድምጹን ነውና:: በጎቹ የሚያድሩት ብዙ በጎች በሚያድሩበት በረት ውስጥ ነው:: ጠዋት እረኛው መቶ በረኛውም አሳልፎት ወደ በሩ ይመጣና ይጠራቸዋል ከያሉበት ከጥጋ ጥግ ተነስተው ሁሉም ይከተሉታል:: እረኛው ከፊት ይሄዳል እነርሱም ይከተሉታል:: የሌላ የሆኑት ግን ድምጹን ስለማያውቁ አይሰሙም እዛው ቀርተው እረኛቸውን ይጠብቃሉ እንጂ ምን እንዳለም አይሰሙም::
ይህንኑ ምሳሌ ነው ጌታ የሚነግረን እረኛችን እየሱስ በስማችን የሚጠራን በዚህ ምድር የምንኖር እንኳን ብንሆን በያለንበት ድምጹን ሰምተን የምንከተል ነን:: ምንም አይነት አዲስ ነገር ለመስማት ሊገጠምልን አያስፈልግም እርሱን ለመስማት ብቃት ተሰጥቶናል! ሃሌሉያ! እናውጅ ጠላት አያጭበርብረን ድምጹን እንስማና እንከተል! ከሌላው ግን እንሸሻለን እንጂ አንከተለውም፥ የሌሎችን ድምፅ አናውቅም። እውቅናም አንሰጥም::
በረኛው መንፈስ ቅዱስ እየሱስን ወደእኛ እንዲመጣና እንዲመራን ይሰጠዋል:: በ1 ጴጥሮስ 1:3-5፤ ኢየሱስ ክርስቶስ ከሙታን በመነሣቱ ለሕያው ተስፋና ለማይጠፋ፥ እድፈትም ለሌለበት፥ ለማያልፍም ርስት እንደ ምሕረቱ ብዛት ሁለተኛ የወለደን የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ አምላክና አባት ይባረክ፤ ይህም ርስት በመጨረሻው ዘመን ይገለጥ ዘንድ ለተዘጋጀ መዳን በእምነት በእግዚአብሔር ኃይል ለተጠበቃችሁ ለእናንተ በሰማይ ቀርቶላችኋል። እኛ በእግዚአብሔር ኃይል የምንጠበቅ ነን!!!!
እረኛዬ እየሱስ ተባረክ አምኜ እከተልሃለሁ! ድምጽህን ለመስማት ብቃት ስለሰጠኸኝ ማንም ስለማይወስድብኝ አከብርሃለሁ! አመሰግንሃለሁ! ተባረክ!
ዮሐንስ 10: 7-13
9፤ በሩ እኔ ነኝ፤ በእኔ የሚገባ ቢኖር ይድናል፥ ይገባልም ይወጣልም መሰማሪያም ያገኛል።
10፤ ሌባው ሊሰርቅና ሊያርድ ሊያጠፋም እንጂ ስለ ሌላ አይመጣም፤ እኔ ሕይወት እንዲሆንላቸው እንዲበዛላቸውም መጣሁ።
11፤ መልካም እረኛ እኔ ነኝ። መልካም እረኛ ነፍሱን ስለ በጎቹ ያኖራል።
እውነተኛ እረኛ እየሱስ ነው:: ነፍሱን ስለእኛ የሰጠና ያዳነን:: በሩ እኔ ነኝ ሲል በዘመኑ የነበሩት ሰዎች በደንብ ይገባቸዋል ምክንያቱም በባህላቸው የበጎች ማረፊያ አንድ በር ነው ያለው እበሩም ላይ እረኛው ይተኛል ተኩላ ከመጣም በመጀመሪያ የሚያገኘው እረኛውን ነው:: እየሱስ በር ሆኖ ተኩላውን እያባረረ አኑሮናል:: እውነተኛ እረኛችን ይባረክ!
በእኔ የሚገባ ቢኖር
1. ይድናል፥ መሰማሪያም ያገኛል አለን እየሱስ:: መዳን ከክፉ ከዓለም ከኃጥያት:
2. ይገባልም – ወደቤቱ መግባት
3. ይወጣልም – ወደ ውጪው ዓለም ወደ ጨለማው ወተን እናበራለን እንናጠቃለን::
4. መሰማሪያም ያገኛል – የሚያሰማራን የሚመራን እርሱ ነው:: የሚያይልን! እንዲሁም እየሱስ የሚለን እኔ ሕይወት እንዲሆንላችሁ እንዲበዛላችሁም መጣሁ። አሜን!
በተቃናኒው ሌባው
1. ሊሰርቅና ሊያርድ
2 . ሊያጠፋም እንጂ ስለ ሌላ አይመጣም፤
ሌላም አላማ የለውም ሰርቆ መግደል ካልሆነለት ያገኘውን ሁሉ ያጠፋል:- ጤና ቢሆን ህብረትን ቢሆን : መልካም አስተሳሰብን ቢሆን: ንብረታቭችንን ቢሆን ጌታ የሚከብርበትን ሁሉ ያጠቃል ምን ከምን ሳይመርጥ ያሳድዳል:: ጌታ ግን አሸንፎታል እበሩ ላይ ነውና አያስገባውም ስለዚህ ሰርቆማረድ አይሆንለትም የት ያገኘናል:: እኛም እናውቀዋለን እርሱም ያውቀናል::
ኦ! መልካም እረኛ እኔ ነኝ እንዳልከን እየሱስ አንተም መልካሙ እረኛ ነፍሱህን ስለ እኛ አኖርክ ። ክብር ይሁንልህ!! እረኛዬ አንተው አውጣናአግባኝ በወደድክበትም አሰማራኝ! አሜን!
ዮሐንስ 10: 14-21
14-15፤ መልካም እረኛ እኔ ነኝ፥ አብም እንደሚያውቀኝ እኔም አብን እንደማውቀው የራሴን በጎች አውቃለሁ የራሴም በጎች ያውቁኛል፤ ነፍሴንም ስለ በጎች አኖራለሁ።
16፤ ከዚህም በረት ያልሆኑ ሌሎች በጎች አሉኝ፤ እነርሱን ደግሞ ላመጣ ይገባኛል ድምፄንም ይሰማሉ፥ አንድም መንጋ ይሆናሉ እረኛውም አንድ።
መልካም እረኛ እኔ ነኝ፥ ብሎ ሲደመድም ሌላ ስለሌለ ነው:: አብን በሚያውቅበት እውቀቱ ነው የራሱን በጎች የሚያውቀው በጎቹም ያውቁታል:: ምን አይነት መዋሃድ ነው በእረኛችንና በእኛ መካከል ያለው:: ሰው እድሜው ሲገፋ የራሱን ልጅ ሳይቀር ይረሳል ጌታ ግን አልረሳሽም በስምሽ አውቅሻለሁ አውቅሃለሁ ነው የሚለን:: ነፍሴን ደግሞ አነሣት ዘንድ አኖራለሁና ስለዚህ አብ ይወደኛል አለ:: እራሱ ነው ነፍሱን የሰጠው እንጂ ማንም ነፍሱን ከእርሱ ለመውሰድ ስልጣን የለውም! አብን ታዘዘ አብም የምወደው ልጄ ይህ ነው ብሎ መሰከረለት:: እኛም ዛሬ እንታዘዘዋለን::
ስለምወዳቸው ነፍሴንም ስለ በጎች አኖራለሁ ብሎ ለራሱ ሳይሳሳ ህይወቱን ሰጥቶን ከራሱ ጋር አስታረቀንና በመንፈሱ ሞልቶ የራሱ አደረገን:: ሃሌሉያ! የራሱ የማድረጉ እቅድ ለእስራኤል ብቻ አልነበረም ነገር ግን ከዚህ በረት ያልሆኑ ሌሎች በጎች አሉኝ ብሎ እኛንም አስቦን ነበረና እነርሱን ደግሞ ላመጣ ይገባኛል ድምፄንም ይሰማሉ፥ አንድም መንጋ ይሆናሉ እረኛውም አንድ ይሆናል:: እረኛችን ባለመለያየት ለሁለቱም እኩል ነገር ነው ያደረገው:: እርሱ አይለያይም እኛም እመንጋው ውስጥ ገባን ድምጹንም የምንሰማ ሆንን:: ደስ የሚለው ይህ ለዘላለም ነው የማያልቅ ህብረት! እየሱስም ነፍሴን ደግሞ አነሣት ዘንድ አኖራለሁና ስለዚህ አብ ይወደኛል አለ:: እራሱን ሳይሰስት ህይወቱን ሰጠን!
ይህንን ሲሰሙ ከእነርሱም ብዙዎች፦ “ጋኔን አለበት፡ አብዶአልም፤ ስለ ምንስ ትሰሙታላችሁ?” አሉ።ሌሎችም፦ “ይህ ጋኔን ያለበት ሰው ቃል አይደለም፤ ጋኔን የዕውሮችን ዓይኖች ሊከፍት ይችላልን?” አሉ። ይህ ሁሉ ማንነቱ የተገለጠው ከታምራቱ በኃላ ነው ዛሬም ጸጋ ይሰራል እራሱን በተአምራት ይግለጥ::
እረኛችን ሆይ እናመሰግንሃለን! ከፍ በል! እኛም እንታዘዝሃለን::
ዮሐንስ 10: 22-27
24፤ አይሁድም እርሱን ከበው፦ “እስከ መቼ ድረስ በጥርጣሪ ታቆየናለህ? አንተ ክርስቶስ እንደ ሆንህ ገልጠህ ንገረን፡” አሉት።
የዚህን ጥያቄ መልስ ለማወቅ ጏጏሁ:: ጥሩ አጋጣሚ ነው የመጣለት እየሱስ ክርስቶስ ነህን የሚል ጥያቄ መቼም ለማወቅ ፈልገው መሆን አለበት ያሰኛል::
እርሱ ግን ልባቸውን ያውቃልና የመለሰላቸው እንዲህ ሲል፦ “ነገርኋችሁ፡ አታምኑምም፡ እኔ በአባቴ ስም የማደርገው ሥራ ይህ ስለ እኔ ይመሰክራል:: የሚመሰክረው ስራው ነው:: የሚታይ ስራ እያደረገ ነው አስቀድሞ በኢሳይያስ 61:1፤ የጌታ የእግዚአብሔር መንፈስ በእኔ ላይ ነው፥ ለድሆች የምሥራችን እሰብክ ዘንድ እግዚአብሔር ቀብቶኛልና፤ ልባቸው የተሰበረውን እጠግን ዘንድ፥ ለተማረኩትም ነጻነትን ለታሰሩትም መፈታትን እናገር ዘንድ ልኮኛል።የሚያለቅሱትንም ሁሉ አጽናና ዘንድ፤ 3፤ እግዚአብሔር ለክብሩ የተከላቸው የጽድቅ ዛፎች እንዲባሉ ለጽዮን አልቃሾች አደርግላቸው ዘንድ፥ በአመድ ፋንታ አክሊልን፥ በልቅሶም ፋንታ የደስታን ዘይት፥ በኀዘንም መንፈስ ፋንታ የምስጋናን መጐናጸፊያ እሰጣቸው ዘንድ ልኮኛል። የሚለው እየተፈጸመ ነው በፊታቸው ግን አላስተዋሉም::
ቀጥሎም ቁርጣቸውን ነገራቸው እናንተ ግን እንደ ነገርኋችሁ ከበጎቼ ስላልሆናችሁ አታምኑም አላቸው:: እየጠበቁት ያለው ጌታ በመካከላቸው ቆሞ አላወቁትም:: በእኔ ተገለጥ ብለን ጌታን እንጋብዘው በኃይልም በብርታትም አይደለም በመንፈሱ እንጂ የመንግስቱ ስራ የሚሰራው::
አባት ሆይ አንተን ማወቅ ስለሆነልኝ ተመስገን:: በስራህ ጌትነትህንና አዳኝነትህ ይታያልና አሁንም በመካከላችን በስራህ ተገለጥ: በጨለማ የሄደ ህዝብ ብርሃን ይይ:: አሜን!
ዮሐንስ 10: 28-42
28፤ እኔም የዘላለም ሕይወትን እሰጣቸዋለሁ፥ ለዘላለምም አይጠፉም፥ ከእጄም ማንም አይነጥቃቸውም።
29፤ የሰጠኝ አባቴ ከሁሉ ይበልጣል፥ ከአባቴም እጅ ሊነጥቃቸው ማንም አይችልም።
30፤ እኔና አብ አንድ ነን።”
እረኛችን የሚያደርግልን ነገር:-
እኔም የዘላለም ሕይወትን እሰጣቸዋለሁ፥ ለዘላለምም አይጠፉም፥
ከእጄም ማንም አይነጥቃቸውም!
የሰጠኝ አባቴ ከሁሉ ይበልጣል ስለዚህ:-
ከአባቴም እጅ ሊነጥቃቸው ማንም አይችልም። የገባንበት ህይወት አስተማማኝ ነው ማንም ከማያወጣን ከልዑል ጉያ ገብተናል! ሃሌሉያ! ሰው ቢሆን ሰይጣን ቢሆን ከፍታ ቢሆን ዝቅታ ምንም ቢመጣ እኛ ግን በአባታችን ፍቅር ተሞልተን እንለመልማለን! አሜን!
ጌታ እየሱስ እኔና አብ አንድ ነን አለን:: አሜን አንድ አምላክ እናመልካለን! ብዙዎች ይህ ሚስጢር አይገባቸውም ጌታ ግን በግልጥ ተናግሯል::
ይህ አሳብ እንደገና ሊወግሩት አስነሳቸው ህይወትን መስጠት ብቻ ሳይሆን ያ አምላካችሁ እኔ ነኝ ሲላቸው አልተዋጠላቸውም:: ኢየሱስ፦ “ከአባቴ ብዙ መልካም ሥራ አሳየኋችሁ፤ ከእነርሱ ስለ ማናቸው ሥራ ትወግሩኛላችሁ?” ብሎ መለሰላቸው። አብ ቀድሶ የላከውን አልተቀበሉትም እንዲያውም ትሳደባለህ አሉት:: እርሱ እንዲያዩለት የፈለገውበማደርገው እንኳን እመኑ እኔ የአባቴን ሥራ እያደረኩኝ ነውና:: እኔን ስንኳ ባታምኑ አብ በእኔ እንደ ሆነ እኔም በአብ እንደ ሆንሁ ታውቁና ታስተውሉ ዘንድ ሥራውን እመኑ።” አላቸው:: ያደረገ ሁሉ መልካም ነበረ በአንድም ሰው አልፈረደም!
ጌታዬ ሆይ አምናለሁ! መልካሙ እረኛ ዛሬም ድንቅን ትሰራለህና በስራህ ተገለጥ:: ሰዎች አምላክ እንዳለ ይረዱና ያውቁ ዘንድ በምድር እንደተመላለስከው ዛሬም በዋጀኸው ህዝብህ ውስጥ ተመላለስና ሰዎችን ወደ መንግስትህ አፍልስ:: አሜን!
ዮሐንስ 11: 1-16
3፤ ስለዚህ እኅቶቹ፦ “ጌታ ሆይ፥ እነሆ የምትወደው ታሞአል፤” ብለው ወደ እርሱ ላኩ።
4፤ ኢየሱስም ሰምቶ፦ “ይህ ህመም የእግዚአብሔር ልጅ በእርሱ ይከብር ዘንድ ስለ እግዚአብሔር ክብር ነው እንጂ ለሞት አይደለም፡” አለ።
ይህንን ቤተሰብ ጌታ ይወድ ነበረና ምንም እንኳን ሊገድሉት የሚፈልጉት አይሁድ ቢኖሩም ወደ ይሁዳ ለመሄድ ተነሳ:: ይህንንም አሳብ ደቀ መዛሙርቱ ተቃወሙ እንዲያውም ሄደን እንሙት እስኪሉ ነበረ የገለጡት ያለውን ውጥረት:: እየሱስ ግን ብርሃን ሆኖ ወደ ዓለም መቶ እያበራ እያለ በለሊት እንመላለስ የሚሉትን አይሁድ ሊረዳቸው አይችልም እጃቸውንም ከቀኑ በፊት እንዲጭኑበት አልፈቀደም:: እርሱ የአባቱን ፈቃድ ማድረግ ነውና የሚፈልገው ክብሩ ወደ ሚገለጥበት ዋጋ የሚያስከፍልም ቢሆን ለመሄድ ተነሳ::
ይህ ህመም የእግዚአብሔር ልጅ በእርሱ ይከብር ዘንድ ስለ እግዚአብሔር ክብር ነው እንጂ ለሞት አይደለም፡” አለ። የመሞቱ ዜና ለደቀ መዛሙርቱ አልገባቸውም ተኝቷል ሲላቸው ይነሳላ አሉት:: እንደዚህ እየተላለፍን ይሆን?! ከዚህም በኋላ፦ እንግዲህ ያን ጊዜ ኢየሱስ በግልጥ አላቸው፦ “አልዓዛር ሞተ:: ለመሄድም የሚያስነሳው ይኸው የእርሱ መክበርና በሞትም ላይ ስልጣን እንዳለው የሚያሳይበት ነው:: ከአምላካችን በቀር ማነው በሞት ላይ ስልጣን ያለው?! እየሱስ አምላኬ ሆይ ክበር! አንተ ሞትን ድል አድርገኸዋል::
ቶማስ ግን ሄደን እንሙት በማለት ፋንታ ሄደን ክብርህን እንይ ማለት ነበረበት:: የእግዚአብሔርን አሳብ ከማወቅ የዘገየን እንዳንሆን ጌታ ይርዳን::
አባት ሆይ:- የልብህን አሳብ ስትገልጥልኝ ከአንተ ጋር መስማማት ይሁንልኝ:: ድምጽህን የመስማት ብቃት ሰተኸኛልና ሳልዘገይ ሰምቼህ እንድመላለስ እርዳኝ:: ከአንተ ጋር መተላለፍ አልፈልግም:: ክብርህን በምትገልጥበት መገኘት ይሁንልኝ:: በጨለማ ላሉትም ብርሃን ልሁን:: አሜን!
ዮሐንስ 11: 17-37
17፤ ኢየሱስም በመጣ ጊዜ በመቃብር እስከ አሁን አራት ቀን ሆኖት አገኘው።
23፤ ኢየሱስም፦ “ወንድምሽ ይነሣል፡” አላት።
እየሱስ ወደ ቢታንያ ሲመጣ አልአዛር አራት ቀን ሆኖት ነበረ ከተቀበረ:: በባህላቸው ነፍስ ለሶስት ቀን እዛው አካባቢ ታንዣብባለች ብለው በአፈ ታሪክ ያምኑነበረና ነው እየሱስ አራት ቀን የቆየው የሚሉም አሉ:: እንደመጣ ያገኘው ማርታን ነበረ ስታገኘው ያለችው ቃል በቃል ማርያምም መታ የምትለውን ነው:: ጸሎታቸው “ጌታ ሆይ፥ አንተ በዚህ ኖረህ ብትሆን ወንድሜ ባልሞተም ነበር” ነው ያሉት:: ሁለቱም በቁጭት ውስጥ ናቸው የሚፈውስ እያለ አንተን የመሰለ ወዳጅ እያለን አለፈ ወንድማችን:: ለእየሱስ የረፈደበትና አሁን ምንም ማድረግ እንደማይችል አድርገው ነው የጸለዮት ወይምእያወሩት ያለው:: ቁጭት!!
ኢየሱስም አላት፦ “ትንሣኤና ሕይወት እኔ ነኝ፤ የሚያምንብኝ ቢሞት እንኳ ሕያው ይሆናል፤ ሕያው የሆነም የሚያምንብኝም ሁሉ ለዘላለም አይሞትም፤ ይህን ታምኚያለሽን?” አሜን! እርሱ ትንሣኤና ሕይወት ነው!!! ሃሌሉያ! “ወንድምሽ ይነሣል፡” ሲላት አሜን ማለት ትታ በትንሳኤ ብላ ወደፊት ቀጠረች ግን አንተ መሲህ እንደሆንክ አምናለሁ አለች:: እየስስን በደንብ ገና አላወቀችውም ማርታ:: እምነት ማለት አሁን ነው::
ማርያምም ሊያጽናናቸው የተሰበሰበውን ሰው ሁሉ አስከትላ መጣችና ያንኑ ጸሎት እግሩ ስር ወድቃ እያለቀሰች ነገረችው እርሱም አለቀሰ:: በዙሪያው ያሉት አይሁድ ይህ የእውሩን አይን ያበራ ይህንን እንዳይሞት ማድረግ አይችልም ነበረ ተባባሉ አሁንም ቁጭት:: እየሱስ ወደ ማዶ የተሻገረው ይህ ፈውስ እስኪረሳሳና ነገሩ እስኪረጋጋ ነበረ እነርሱ ግን አልረሱለትም:: የሚያውቁትም የታመመውን እንደሚያድን ብቻ ነው:: የተደገሰላቸውን ተአምር አላወቁም ገና የሚያውቁት መፈወስ መቻሉን ነው::
እየሱስም “ወዴት አኖራችሁት?” አለም። እነርሱም፦ “ጌታ ሆይ፥ መጥተህ እይ፡” አሉት። ኢየሱስም እንባውን አፈሰሰ። እመቃብሩጋ ሄዶ የሚያለቅስ ነበረ የመሰላቸው:: ስለዚህ አይሁድ፦ “እንዴት ይወደው እንደ ነበረ እዩ፡” አሉ።
ጌታዬ ሆይ አንተ ትንሳኤና ህይወት ነህና በአንተ መታመን ይሁንልኝ! እምነትም አሁን ነውና አምናለሁ! ያለቀለት ነገር የተውኩት የተቀበረ ሁሉ አሁን ይነሳ:: አሜን!
ዮሐንስ 11: 38-44
39፤ ኢየሱስ፦ “ድንጋዩን አንሡ፡” አለ። የሞተውም እኅት ማርታ፦ “ጌታ ሆይ፥ ከሞተ አራት ቀን ሆኖታልና አሁን ይሸታል፡” አለችው።
ወደ ቢታንያም ይሁን ወደ መቃብሩ ከመምጣቱ በፊት ያመጣው ነገር ክብሩን ለመግለጥና አባቱን ለማስከበር ነው::“ድንጋዩን አንሡ፡” ባለ ጊዜ ተቃውሞ የተነሳበት እኔ ትንሳኤና ህይወት ነኝ ሲላት ከቆየችው ከማርታ ነበረ:: እውነት ወንድምዋ እንዳይነሳ ፈልጋ ነው? አይደለም ግን እንቅፋት ልትሆን የተነሳችው ቃሉ ከእርስዋ ጋር ስላልተዋሃደ ነው:: ቢዋሃድ ኖሮ እንደማርያም ዝም ብላ ትጠብቅ ነበረ:: በራሳችን ነገር ላይ እንቅፋት አንሁን ቃሉ በሙላት ይኑርብን ይህ ቃል ህይወት ነው መንፈስም ነው:: ይሰራል!!! በእኛ ዙሪያ ባለው ሁኔታ እግዚአብሔርን ልናስረው አንሞክር እርሱ ትልቅ አምላክ ነውና:: ክብር ይሁንለት አሜን!!
ለማርታ የመለሰላት “ብታምኚስ የእግዚአብሔርን ክብር እንድታዪ አልነገርሁሽምን?” አላት። እዛው ክፍል ነው የከለሳት ከደቂቃዎች በፊት ወደተናገራት ህይወትነቱና ትንሳኤውን ማለቱ ነው:: ጊዜያችንን እያባከንን አንድ ክላስ ስንከልስ እንዳንገኝ ጌታ ይርዳን:: ዛሬም ብናምን ክብሩን እናያለን!! አሜን!
ሰዎቹ ያለ ምንም ተጨማሪ ጥያቄ ድንጋዩን ለማንሳት ታዘዙ:: እማስበው ግን በዚያ ዙሪያ የነበሩት ሰዎች ምን እያሰቡ ይሆን? ምን ሊያደርግ ነው ብለው እርጭ ብለው እየጠበቁ ነው መቼም:: ድንጋዩንም አነሡት። ኢየሱስም ዓይኖቹን ወደ ላይ አንሥቶ እንዲህ አለ።፦ “አባት ሆይ፥ ስለ ሰማኸኝ አመሰግንሃለሁ። ሁልጊዜም እንድትሰማኝ አወቅሁ፤ ነገር ግን አንተ እንደ ላክኸኝ ያምኑ ዘንድ በዚህ ዙሪያ ስለ ቆሙት ሕዝብ ተናገርሁ።” ብሎ አጭር ጸሎት ጸለየ የጸለየበትም ምክንያት በዙሪያው ያሉት ይሰሙና ጸሎቱም ሲመለስ አይተው እንዲያምኑ ነው:: ዛሬም ይህ ጌታ አልተለወጠም እንወራረድበት አንዳች እንደፈቃዱ ስንለምን ይሰማናል:: ፈቃዱንም የሚያስታውቀን በህያው ቃሉ ነው:: እየሱስ ጌታና አዳኝ መሆኑን አብ ዛሬም ይመሰክርለታል ብቻችንን አይደለንም ስንመሰክር ሰማይ ሁሉ አብሮ ይሰራል::
ይህንም ብሎ፡ በታላቅ ድምፅ፦ “አልዓዛር ሆይ፥ ወደ ውጭ ና፡” ብሎ ጮኸ። የሞተውም እጆቹና እግሮቹ በመግነዝ እንደ ተገነዙ ወጣ፤ ፊቱም በጨርቅ እንደ ተጠመጠመ ነበር። ኢየሱስም፦ “ፍቱትና ይሂድ ተዉት፡” አላቸው። ሃሌሉያ! ሰውን ፈቶ የሚለቅ ጌታ! ነገራችን አሁን ቢሞት ወይም ትላትና ወይም ደግሞ ቆይቶም ቢሆን ትንሳኤ አለ:: ሃሌሉያ! ዛሬም ይሰራል!
አባት ሆይ፥ ስለ ሰማኸኝ አመሰግንሃለሁ። ሁልጊዜም እንድትሰማኝ አወቅሁ፤ ብለህ እንዳልክ እኔም በምስጋና ወደፊትህ እንደምትሰማኝ አውቄ መጣሁ:: አንተ አልተለወጥክም ተራራ የሆነ ነገር ሁሉ አሁን ሜዳ ይሁን የሞተው ነገሬህይወትን ያግኝና የክብርህ መገለጫ ይሁን:: ትንሳኤና ህይወት እምነትም አሁን ነውና አሁን አድን:: እየሱስ ህያው ነው ብዬ የሰበኳቸው ሁሉ ይዳኑና ክብርህን ይዩ ህይወትም ይሁንላቸው:: በድፍረት ልወራረድብህ! ጸሎቴን እንደምትሰማኝ አምናለሁ:: ተመስገን!!
ዮሐንስ 11: 45-57
51፤ ይህንም የተናገረ ከራሱ አይደለም፥ ነገር ግን በዚያች ዓመት ሊቀ ካህናት ነበረና ኢየሱስ ስለ ሕዝቡ ሊሞት እንዳለው ትንቢት ተናገረ፤
የአላዛርን መነሳት ከማርያም ጋር የመጡት፥ ኢየሱስ ያደረገውን አይተው ብዙዎች በእርሱ አመኑ ይላል:: ከእነርሱ አንዳንዶቹ ግን ወደ ፈሪሳውያን ሄደው ኢየሱስ ያደረገውን ነገሩአቸው። ለምን ይሆን መሲህ ተገኝቷል ይሆን ወይስ ሌላ ምክንያት? ይህ መረጃ ግን እየሱስን ለመግደል እንዲያሴሩ አደረጋቸው::
እንግዲህ የካህናት አለቆችና ፈሪሳውያን ሸንጎ ሰብስበው፦ “ምን እናድርግ? ይህ ሰው ብዙ ምልክቶች ያደርጋልና። እንዲሁ ብንተወው ሁሉ በእርሱ ያምናሉ፤ የሮሜም ሰዎች መጥተው አገራችንን ወገናችንንም ይወስዳሉ፡” አሉ። ህዝቡ በእርሱ ማመናቸውና የሮማውያን መጥቶ መውረርን ምን አገናኘው ያሰኛል ምናልባትም እስራኤሎች ብቻ ነበሩ አምላካቸውን እንዲያመልኩ በሮም ህግ የተደነገገላቸውና የተፈቀደላቸው ምክንያቱም ይሞታሉ እንጂ ለቄሳር አይሰግዱም አሁን እየሱስ የሚታይ ንጉስ ማምለክ ቢጀምሩ አመፃችሁ ይባላሉ ይመስላል ፍራቻቸው ያም ሆነ ይህ እየሱስ ተላልፎ መሰጠት ነበረበት:: የፈሩትም ከጥቂት ዓመታት በኃላ ተፈጸመ እየሩሳሌም ጠፋች እየሱስ ግን ቀድሞ አልቅሶላታል::
ለምክራቸው መቋጫ ያመጣው በዚያ ጊዜ ሊቀ ካህናቱ ትንቢትን በመናገር ነበረ: ሕዝቡም ሁሉ ከሚጠፋ አንድ ሰው ስለ ሕዝቡ ይሞት ዘንድ እንዲሻለን አታስቡም፡” አላቸው። እንግዲህ ከዚያ ቀን ጀምረው ሊገድሉት ተማከሩ።ከዚያ ወዲያም ኢየሱስ በአይሁድ መካከል ተገልጦ አልተመላለሰም፤ ነገር ግን ከዚያ በምድረ በዳ አጠገብ ወዳለች ምድር፥ ኤፍሬም ወደምትባል ከተማ ሄደ፤ በዚያም ከደቀ መዛሙርቱ ጋር ተቀመጠ።
እየሱስ በዚህ ሁሉ ውድጥ አልፈህ ስለ ሁላችን እራስህን አሳልፈህ ስለሰጠህ ተመስገን! ከጨለማ ወደ ብርሃን አመጣኸን ተባረክ! አሜን
ዮሐንስ 12: 1-11
3፤ ማርያምም ዋጋው እጅግ የከበረ የጥሩ ናርዶስ ሽቱ ንጥር ወስዳ የኢየሱስን እግር ቀባች፤ በጠጕርዋም እግሩን አበሰች፤ ቤቱም ከናርዶስ ሽቱ ሞላ።
በዚህ የእራት ግብዣ እየሱስ ታድሟል:: ዋው እየሱስን ለእራት መጋበዝ አምላክ የሆነ ጌታ በቤታቸው ተገኘ:: ዛሬም ጌታ ወደ እኛ ይመጣል በዮሐንስ 14:23፤ ኢየሱስም መለሰ፡ አለውም፦ “የሚወደኝ ቢኖር ቃሌን ይጠብቃል፤ አባቴም ይወደዋል፡ ወደ እርሱም እንመጣለን፡ በእርሱም ዘንድ መኖሪያ እናደርጋለን። አሜን! ለዘላለም በእኛ ዘንድ ይኖራል:: አማኑኤል!
ሌላው በእራቱ ላይ የነበረው ከሞት የተነሳው አልአዛር ነው:: በዚህ ደስታ ውስጥ ነው ይህ ቤተሰብ ያለው ለቅሶ ቀርቶ ደስታ ሆነላቸው:: በዚህ መሃል ለየት ያለ አምልኮ ነው ማርያም ያደረገችው ምናልባትም ከባህሉም ወጣ ያለ:: ሽቶ አፍስሶ በጸጉር ማበስ ሽቶውም ቤቱን ሞላው:: በመነዳት ነው ታደርገው የነበረው እርስዋ ግን ፍቅርዋን ለመግለጽ ነበረ:: ክብርዋን ጥላ ገንዘብዋንም አውጥታ ደስታዋንና አምልኮዋን እየገለጠች ነው:: እያደረገች ያለውንም በቅጡ የተረዳች አትመስልም ነገር ግን ጌታ ገብቶታል:: ይህንን ያደረገችው ለመቃብሬ ነው አለ ምክንያቱም ፋሲካ እየደረሰ ነው:: ተላልፎ ለመሰጠትም የቀረው ጥቂት ቀናት ነው:: ዛሬም በመንፈስ መነዳት ይሁንልንና እርሱን መታዘዝ ፈቃዱንም ማድረግ ይብዛልን::
ማርያም ይህንን አምልኮ ስታደርግ የተቃወመ ነበረ ምክንያቱ ደሃን በማሰብ በሚል የሚኮንን አስተያየት ነገር ግን ጏዳው ሲፈተሽ ሌብነት ስለነበረበት ነው ይላል ቃሉ:: ተቃውሞ ቢነሳ ጌታን ታዘን አይድነቀን ብቻ እርሱን ደስ እናሰኝ:: ህብረት ውስጥ ብዙ አይነት ሰው አለ ፍረዱ ሳይሆን የተባልነው በፍቅር አቅኑ ነውና ጌታ ይርዳን::
የሚገርመው አይሁድ እየሱስን ብቻ ሳይሆን አላዛርንም ለማጥፋት ተማከሩ:: እርሱ ህያው ምስክር ሆኖ አስቸግሯልና ነው:: ዛሬም እኔ ከዘላለም ሞት ከጥፋት አምልጬ ወደ መንግስቱ የገባሁ በመንፈስ ቅዱስ የታተምኩኝ ነኝና ጠላት አዋጅን አውጥቷል ሊሰርቅ ሊያጠፋና ሊገድል:: እኔ ግን ብርሃኔን እየሱስን እያብለጨለጭኩኝ እኖራለሁ:: እኔ ምስክር ነኝ ከሞትም ወደ ህይወት የተሻገርኩኝ ነኝና::
አባት ሆይ ተመስገን እኔም ዛሬ ከፍ አደርግሃለሁ በዝማሬና በአምልኮ በመገዛትና በመታዘዝ እራሴን ወደ አንተ ህያውና ቅዱስ መስዋእት አድርጌ አቀርባለሁ:: አሜን
ዮሐንስ 12: 13-19
13፤ የዘንባባ ዛፍ ዝንጣፊ ይዘው ሊቀበሉት ወጡና፦ “ሆሣዕና፤ በጌታ ስም የሚመጣ የእስራኤል ንጉሥ የተባረከ ነው፡” እያሉ ጮኹ።
ዮሐንስ 12:14-15፤ “አንቺ የጽዮን ልጅ አትፍሪ፤ እነሆ፥ ንጉሥሽ በአህያ ውርንጫ ላይ ተቀምጦ ይመጣል፤” ተብሎ እንደ ተጻፈ፥ ኢየሱስ የአህያ ውርንጫ አግኝቶ በእርሱ ተቀመጠ።
መጽሃፍት ሁሉ ስለ እኔ ይናገራሉ እንዳለ ጌታ በመዝሙር 118:25፤ አቤቱ፥ እባክህ፥ አሁን አድን፤ አቤቱ፥ እባክህ፥ አሁን አቅና። እንደሚል እርሱን ለመቀበል ህዝቡ ሆሣዕና እያሉ የዘንባባ ዛፍ ዝንጣፊ ይዘው ሊቀበሉት ወጡ:: እርሱም በትንቢት እንዲህ እንደተነገረው “አንቺ የጽዮን ልጅ አትፍሪ፤ እነሆ፥ ንጉሥሽ በአህያ ውርንጫ ላይ ተቀምጦ ይመጣል፤” ተብሎ እንደ ተጻፈ፥ ኢየሱስ በአህያ ውርንጫ ተቀመጠ። ቃሉን የሚያከብር ጌታ ይባረክ!
አሁንም አልተለወጠም ቃሉን ይፈጽማልና እምነታችንን እናበርታ አይናችንንም በእርሱ ላይ እናድርግ:: ተላልፎ ወደ መሰጠት ከመሄዱ በፊት ያደረገው ይህ ተአምር ብዙዎችን እንዲያምኑበት በጠላትነት የተነሱበትንም አይሁዶች የሚይዙትን ያሳጣበት ክስተት ነው:: የነገሮችን መክረር እናያለን በእርሱ በኩል ስናየው ሁሉ በእቅድ ወደ ፍፃሜው እየሄደ ነበረ:: ከጌታ ጋር ከተራመድን ነገር ሁሉ እንደፈቃዱ ሲሆን ያስደንቀናል እንመነው ብቻ ይህንን ጌታ:: እርሱ ትህትናውን ለመግለጥ በአህያ እንደመጣ ትህትናንም ከእኔ ተማሩ ስላለን በትህትና ዝቅ ብለን እርሱን እያሳየን መመላለስ ይሁንልን::
አባት ሆይ ማስተዋልን ስጠን! ጸጋህም ይብዛልን! አሜን
ዮሐንስ 12: 20-26
23፤ ኢየሱስም መለሰላቸው፥ እንዲህ ሲል፦ “የሰው ልጅ ይከብር ዘንድ ሰዓቱ ደርሶአል።
24፤ እውነት እውነት እላችኋለሁ፥ የስንዴ ቅንጣት በምድር ወድቃ ካልሞተች ብቻዋን ትቀራለች፤ ብትሞት ግን ብዙ ፍሬ ታፈራለች።
25፤ ነፍሱን የሚወድ ያጠፋታል፥ ነፍሱንም በዚህ ዓለም የሚጠላ ለዘላለም ሕይወት ይጠብቃታል።
26፤ የሚያገለግለኝ ቢኖር ይከተለኝ፥ እኔም ባለሁበት አገልጋዬ ደግሞ በዚያ ይሆናል፤ የሚያገለግለኝም ቢኖር አብ ያከብረዋል።”
ከግሪክ ለበዕሉ ሊሰግዱ የመጡ ሰዎች እየሱስን ማየት ፈለጉና ጠየቁ:: ደቀመዝሙቱም መተው ሲነግሩት እርሱ የሚመልሰውና የሚጠይቁት የሚገናኝ አይመስልም:: ነገር ግን እነዚህ ሰዎች እየሱስን ልናይ እንወዳለን ነበረ ጥያቄያቸው እንጂ እንደከዚህ ቀደሙ ወደእርሱ ለፈውስ እንደመጡት አህዛብ አልነበረም ጥያቄያቸው:: የሚፈልጉት መሲሁን ነው! እየሱስም ያለው፦ “የሰው ልጅ ይከብር ዘንድ ሰዓቱ ደርሶአል:: ምክንያቱም አህዛብም አዳኝ እየፈለጉ ነውና:: አጥብቆ ሲናገር የነበረውና ሁለት ሁለትም አድርጎ ለአገልግሎት ሲልካቸው አገልግሎቱ ለእስራኤል ልጆች እንደሆነ ግልጽ አድርጎ ነበረ:: በተባራሪ መተው ፈውስ ከተቀበሉት በቀር ያተኮረው በእስራኤል ላይ ብቻ ነበር::
ሰዓቱ ደርሶአል ብሎ ሲል “የሰው ልጅ ይከብር ዘንድ” መልካም ነገር አይመስልም? እንደው ወድያው ንጉስ የሚያደርጉት አይመስልም? መክበር ሲል ግን ምሳሌ እንደሰጠው እንደስንዴዋ ቅንጣት ነው:: ካልሞተች ብዙውን ፍሬ እንደማትሰጥ እየሱስም ካልከበረ የሰውን ልጅ ማዳንና የጥሉን ግድግዳ ማፍረስ አይችልም ነበረ:: ከዚህ የሚበልጥ ፍቅር ለማንም የለውም::
እየሱስ እንዳለን ነፍሱን በዚህ ዓለም የሚጠላ ለዘላለም ሕይወት ይጠብቃታል። እርሱ ይህንን አድርጎ ፈለጋውን ትቶልን አለፈ:: ስለዚህ የሚያገለግለኝ ቢኖር ይከተለኝ፥ እኔም ባለሁበት አገልጋዬ ደግሞ በዚያ ይሆናል፤ የሚያገለግለኝም ቢኖር አብ ያከብረዋል።” ብሎ አለን:: ዓለምን ንቀን ለእርሱ በጸጋው እየተገዛን ስንመላለስ እርሱ ከእኛ ጋር ይሆናል::
አባት ሆይ ስራዬን ሁሉ ሰርተህ አንተ ባለህበት ህይወቴን ሸሽገኸዋልና አመሰግንሃለሁ:: ፈለጋህን እንድከተልና ፍሬ እንዳፈራ አሁንም እራሴን ለአንተ እሰጣለሁ:: የሰዎች መጥፋት ግድ ይበለኝ! አንተን እንደሚያሳስብህ ያስስበኝ!
ዮሐንስ 12: 27-36
27፤ “አሁን ነፍሴ ታውካለች ምንስ እላለሁ? አባት ሆይ፥ ከዚህ ሰዓት አድነኝ። ነገር ግን ስለዚህ ወደዚህ ሰዓት መጣሁ።
28፤ አባት ሆይ፥ ስምህን አክብረው።” ስለዚህም፦ “አከበርሁት ደግሞም አከብረዋለሁ፡” የሚል ድምፅ ከሰማይ መጣ።
ሰዕቱ ደረሰ ብሎ አውጆ እየተዘጋጀ ነው:: በዚህ ዝግጅት መካከል ያደረገው ጸሎት ነው ምክንያቱም አሁን ነፍሴ ታውካለች ምንስ እላለሁ? አባት ሆይ፥ ከዚህ ሰዓት አድነኝ። ነገር ግን ስለዚህ ወደዚህ ሰዓት መጣሁ እያለ:: ጸሎቱን ሲጨርስ መልስ ከሰማይ መጣ መልሱ ግን ለእርሱ እንዳልሆነ ነገራቸው ምክንያቱም እየሱስ ማረጋገጫ አያስፈልገውም:: በዙሪያው ያለእ ህዝብ ግን አብ ከእየሱስ ጋር እንዳለና ስሙንም እንደሚያከብር መሰከረ:: ለሰው ልጅ ሲል እየሱስ ነፍሱ ታወከች አድነኝ ብሎም ለመነ መልሶ ደግሞ እራሱን ያጽናናል ወደዚህ የመጣሁት ለዚህ ሰዓት ነው እያለ:: አንዳንዴ ግራ ግብት የሚል ነገር ውስጥ ስንገባ እናስታውስ እየሱስም ገጥሞት እንደነበረና ሊረዳን አብሮን እንደሆነ::
ከሰማይ የመጣውን ድምጽ መልአክ ተናገረው ሲሉ ሌሎች ደግሞ ነገድጏድ ነው አሉ የእግዚአብሔር ነገር ለስጋውያን ሞኝነት ነውና አልተረዱትም ምንም አይነት ሪአክሽን አልነበራቸውም እንግዲህ ምን ይምጣ ድምጹን ከሰማይ ከመላክ በላይ? ቀጠለ ሊያስረዳ አሁን የዚህ ዓለም ፍርድ ደርሶአል፤ አሁን የዚህ ዓለም ገዥ ወደ ውጭ ይጣላል፤ እኔም ከምድር ከፍ ከፍ ያልሁ እንደ ሆነ ሁሉን ወደ እኔ እስባለሁ።” አላቸው በምን አይነት ሞት እንደሚሞት የሮም ስርዓት ነው ሰውን በመስቀል ላይ መስቀል:: አልገባቸውም! ክርስቶስ ለዘላለም ይኖራሉ ብለው መለሱለት:: የእግዚአብሔር በግ ሆኖ እንደመጣም አላወቁምና::
አሁንም ተስፋ ሳይቆርጥ ኢየሱስም፦ “ገና ጥቂት ጊዜ ብርሃን ከእናንተ ጋር ነው። ጨለማ እንዳይደርስባችሁ ብርሃን ሳለላችሁ ተመላለሱ፤ በጨለማም የሚመላለስ ወዴት እንዲሄድ አያውቅም።
የብርሃን ልጆች እንድትሆኑ ብርሃን ሳለላችሁ በብርሃኑ እመኑ፡” አላቸው። ኢየሱስም ይህን ተናግሮ ሄደና ተሰወረባቸው። ብርሃኑን እየሱስን አምነው እንዲያመልጡ ነገራቸው እነሱ ግን አልገባቸውም:: ይህ የህይወት ብርሃን በርቶልናልና ሳንሰለች ስለዚህ ስለተንገላታ ጌታ መመስከርን እናብዛ!
ዮሐንስ 12: 37-46
44፤ ኢየሱስም ጮኸ፥ እንዲህም አለ፦ “በእኔ የሚያምን በላከኝ ማመኑ ነው እንጂ በእኔ አይደለም፤
45፤ እኔንም የሚያይ የላከኝን ያያል።
46፤ በእኔ የሚያምን ሁሉ በጨለማ እንዳይኖር እኔ ብርሃን ሆኜ ወደ ዓለም መጥቻለሁ።
ነገር ግን ይህን ያህል ምልክት በፊታቸው ምንም ቢያደርግ፤ ነቢዩ ኢሳይያስ፦ “ጌታ ሆይ፥ ማን ምስክርነታችንን አመነ? የእግዚአብሔርስ ክንድ ለማን ተገለጠ?” ብሎ የተናገረው ቃል ይፈጸም ዘንድ በእርሱ አላመኑም። ያመኑትም በአደባባይ መመስከርን ፈሩ:: ስለዚህም ኢየሱስ ጮኸ፥ እንዲህም አለ፦ “በእኔ የሚያምን በላከኝ ማመኑ ነው እንጂ በእኔ አይደለም፤ እኔንም የሚያይ የላከኝን ያያል አላቸው መፍራታቸውን ሲያይ:: ዛሬስ የሚያስፈራን ምንድነው? ስለእየሱስ ጌትነት በሙላት እንመስክር::
ጌታም እንዳለ በእኔ የሚያምን ሁሉ በጨለማ እንዳይኖር እኔ ብርሃን ሆኜ ወደ ዓለም መጥቻለሁ ብሏል:: ብርሃናችን እየሱስ ለእኛም የህይወት ብርሃን ሆነልን:: ጨለማችን በራ!! በጨለማ ላሉት የዔለም ብርሃን አደረገን:: ምንም ውስጥ ብንገባ ብርሃናችን ከሩቁ ይታያልና ደምቀን በሙላት እየታየን እንመላለስ እንጂ አንደበቅ!
አባት ሆይ የሰዎች ልብ ተከፍቶ አንተን ያውቁ ዘንድ እርዳን:: እኛም በድፍረት ጌትነትህን እንድንመሰክር በመንፈስ ቅዱስ እርዳን:: አሜን
ዮሐንስ 13:1፤ ኢየሱስም ከፋሲካ በዓል በፊት፥ ከዚህ ዓለም ወደ አብ የሚሄድበት ሰዓት እንደ ደረሰ አውቆ፥ በዚህ ዓለም ያሉትን ወገኖቹን የወደዳቸውን እስከ መጨረሻ ወደዳቸው።
እየሱስ ወደ መስቀል ከዛም ወደመጣበት ክብሩ የሚሄድበት ጊዜ እንደ ደረሰ አውቆ መውደዱን የሚያሳይበት ወቅት ላይ ነው:: በዚህ ዓለም ያሉትን ወገኖቹን የወደዳቸውን እስከ መጨረሻ ወደዳቸው። አቤት ምን አይነት መወደድ ነው? እራሱን እስኪሰጥ ድረስ እኛን መውደዱ?! ይወዳቸው ነበረ ግን እስከመጨረሻ ሄዶ መውደዱን ያሳየበት መስቀሉ ነው:: ሰው ምን ያህል እንደተወደደ ከገባው ዘመኑን ሁሉ በእርካታና በእረፍት ይኖራል እንጂ በትልቅ በትንሹ የሚሸበር አይሆንም:: በጌታው ተማምኖ የሚመላለስ ይሆናል:: ይህንን ፍቅር ለማወቅ ጣሩ ይላል ቃሉ::
እግዚአብሔር ሰውን መውደዱ የተገለጠው አንድያ ልጁን ወደ ዓለም ነፍሱን እንዲሰጥ ሲልከው ነው:: የእግዚአብሔር በግ ተብሎ ተሰየመ:: እየሱስ ስለ እኔ በሸላቾቹ ፊት ዝም አለ:: ሃሌሉያ! እኔን ለማዳን ይህች ጽዋ ከኔ ትለፍ እያለ ግን ቀጠለበት:: እራሱን በፈቃዱ አሳልፎ ሰጠኝ!
አባት ሆይ ምን አይነት ፍቅር ነው?! አመሰግንሃለሁ! ስምህንም እባርካለሁ! የተወደድኩበት ፍቅር ጥልቅ ነውና ዓለት ዕለት ለማወቅ ልዘርጋ እርዳኝ::
ዮሐንስ 13: 2-5
3፤ ኢየሱስ አብ ሁሉን በእጁ እንደ ሰጠው ከእግዚአብሔርም እንደ ወጣ ወደ እግዚአብሔርም እንዲሄድ አውቆ፥
4፤ ከእራት ተነሣ ልብሱንም አኖረ፥ ማበሻም ጨርቅ ወስዶ ታጠቀ፤
5፤ በኋላም በመታጠቢያው ውኃ ጨመረ፥ የደቀ መዛሙርቱንም እግር ሊያጥብና በታጠቀበትም ማበሻ ጨርቅ ሊያብስ ጀመረ።
እየሱስ ፍጹም ፍቅሩን የሚገልጥበት ጊዜ ደርሷል:: ፍቅሩም የሚገለጠው እራሱን በመስጠት ነው::
በጣም የገረመኝ ነገር እራትም ሲበሉ ዲያብሎስ በስምዖን ልጅ በአስቆሮቱ በይሁዳ ልብ አሳልፎ እንዲሰጠው አሳብ ካገባ በኋላ ነው እየሱስ ጊዜው አሁን ነው ብሎ የተነሳው:: ጠላት አሳልፎ ሊሰጠው ሲዶልት አብ አባት ደግሞ ቃሉ እንደሚለን አብ ሁሉን በእጁ እንደ ሰጠው አውቆ:: የእንግሊዘኛው power እንደሰጠው ነው የሚነግረን:: ሁሉ ስልጣን የተሰጠው ታድያ ትሁት ሆኖ በሸላቾቹ ፊት ዝም ይላል እንዴ?! እስኪ እናስበው ስልጣን የተሰጠው ሰው ወድያውበስሩ ባሉት ላይ ለመሰልጠን ነው የሚነሳው :: እየሱስ ግን ከእራት ተነሣ ልብሱንም አኖረ፥ ማበሻም ጨርቅ ወስዶ ታጠቀ ይላል!!
እየሱስ ትህትናን ከእኔ ተማሩ ሲለን ሳይኖረው አይደለም ይኸው ኖሮት ነው:: ትህትና የመንፈስ ፍሬ አይደለም የምናፈራው ነው እንጂ! ይህ ሁሉ በእጁ የተሰጠው ጌታ ማድረግ የነበረበት ይሁዳን መግለጥና መቆጣ መውቀስ ነበረ ሌላም ሌላም ማለት ይቻላል የአይሁድን መሪዎች እንደፈለገ ማድረግ ይችላል ወይም የሮምን አገዛዝ . . . ግን አላደረገውም:: ለጊዜውለሆኑና ለሚያልፉ ነገሮች ህይወታችንን አንበጥብጥ አልፈን ፍቅርን እናሳይና በትህትና እናሳልፍ!
ይህ ታላቅጌታ በመታጠቢያው ውኃ ጨመረ፥ የደቀ መዛሙርቱንም እግር ሊያጥብና በታጠቀበትም ማበሻ ጨርቅ ሊያብስ ጀመረ:: እንማር! ዝቅ ማለት አቅቶን ይሆን? ጌታን ብቻ በፊታችን እንይ! እርሱን ምሰሉ ነውና የተባልነው:: ከእግዚአብሔር እጅ በታች እራስን ማዋረድ በፈቃድ የሚደረግ ነው::
አባት ሆይ ትህትናን ከአንተ ልማር አንተንም ወደ መምሰል ልምጣ እርዳኝ! ዛሬ በጎደልኩበት ሁሉ ጸጋህ ሙላት ይሁነኝ:: ቀኔን በፊትህ እቀድሳለሁ እራሴንም በፊትህ ዝቅ አደርጋለሁኝ አንተ ክበር:: ጠላት ለሚያመጣው ሽንገላ እንዳልታለል ማስተዋልን ስጠኝ::
ተባረክ አባ!
ዮሐንስ 13: 6-10
8፤ ጴጥሮስም፦ “የእኔን እግር ለዘላለም አታጥብም፡” አለው። ኢየሱስም፦ “ካላጠብሁህ፥ ከእኔ ጋር ዕድል የለህም፡” ብሎ መለሰለት።
ጴጥሮስ እግሩን ለመታጠብ ፈቃደኛ አልሆነም:: አስራ አንዱ ይሁዳንም ጨምሮ ሲታጠቡ እርሱ ግን አሻፈረኝ አለ:: ችኩል ይሁን እንጂ ብዙ ነገር እንድንማርረድቶናል በብዙ አጋጣሚ:: ኢየሱስም መልሶ፦ “እኔ የማደርገውን አንተ አሁን አታውቅም፥ በኋላ ግን ታስተውለዋለህ፡” አለው። ይህ ስንቅ ነበረ ለሐዋርያት ወደፊት እንዴት ማገልገል እንዳለባቸው የሚያስተምር:: ማንንም ሳይለዮ ዝቅ ብሎ ይሁዳንም ማጠብ ማለት ነው::
ስንቅም ብቻ ሳይሆን እየተወላቸው ያለው በሌላው እቅጣጫ የየዕለት ኑሮን እንዴት እንደሚኖር ያሳያል:: አታጥበኝም ለሚለው ለጼጥሮስ አተያየት ሁለተኛው ምላሹ ከባድ ነበረ:- “ካላጠብሁህ፥ ከእኔ ጋር ዕድል የለህም፡” ለምን ይህንን አለ? በየዕለቱ የሚገጥመንን አውቀን ነውና እይሱስን መከተል ያለብን:: ይኸውም እግር መታጠብ:- ለምን አስፈለገ ለምን ሌላውን አካል አይጨምርም:: በዛ ዘመን ባህሉንም ብናይ በሌላም ቃል ስናይ ለምሳሌ መሃልዬ ላይ ያለችው ሴት እግሬን ታጥቤ በአልጋ ነኝ አለች ነጽታ የቅኑን ቁሻሻ ሁሉ አራግፋ ተኛች ከሙሴም ጋር ጫማህን አውልቅ ነበረ::
በክርስቶስ የሆንን በደሙ ነጽተናል በዝች ቁሻሻ ዓለም ስንመላለስ የምንረጋግጠው ነገር አለና እራስን በንስሃ ካላየን ከእርሱ ጋር እድል ፋንታ የለንም:: የዓለም ነገር በልጦብን ጥለን የምንሄድ እንሆን ይሆናልና ነው:: አገልግዬ የተጣልኩኝ እንዳልሆን እራሴን እየጎሸምኩ አስገዛለሁ እንደሚለው ነው:: ስለዚህም ጌታ፦ “የታጠበ እግሩን ከመታጠብ በቀር ሌላ አያስፈልገውም፥ ሁለንተናው ግን ንጹሕ ነው፤ እናንተም ንጹሐን ናችሁ አለው። አሜን ዛሬ በደሙ ታጥበን ንጹ ሆነናል::
አባት ሆይ እራሴን መመርመር ይሁንልኝ ጎዳናዬን ስጠበጥብ ከአንተ ጋር እድል ፋንታ ያለው በንስሃ የታጀበ ህይወትን እንድኖር እርዳኝ::
ዮሐንስ 13: 11-20
12፤ እግራቸውንም አጥቦ ልብሱንም አንሥቶ ዳግመኛ ተቀመጠ፥ እንዲህም አላቸው፦ “ያደረግሁላችሁን ታስተውላላችሁን?
13፤ እናንተ መምህርና ጌታ ትሉኛላችሁ፤ እንዲሁ ነኝና መልካም ትላላችሁ።
15፤ እኔ ለእናንተ እንዳደረግሁ እናንተ ደግሞ ታደርጉ ዘንድ ምሳሌ ሰጥቻችኋለሁና።
የገረመኝ ክፍል:- “ያደረግሁላችሁን ታስተውላላችሁን? የሚለው ጥያቄ ነው:: ያደረኩትን ሳይሆን ያደረኩላችሁን ነው ያለው:: ያደረገውን እንድናደርግ እርስ በእርሳችን እንድንተጣጠብ ነው እንጂ ቁጭ ብለን እንድናደንቅ አይደለም የተደረገውም በሰው ላይ ውጤት የሚያመጣ ነው:: የሰውን በደል ይቅር ማለትና ማጠብ ማስወገድ ማንፃት በቃሉም ማጽናናት ይጠበቅብናል:: ጌታ እንዳደረገ እኛም ለሰዎች ልናደርግላቸው ይገባናል:: ምሳሌ ነው የተወልን!! ይህንንም ማድረጋችን ብጹእ ያስብለናል:: እናንተ መምህርና ጌታ ትሉኛላችሁ፤ እንዲሁ ነኝና መልካም ትላላችሁ አላቸው አሁንም ማስተዋላችሁ ያደረኩት ላይ ይሁን ምንም ከፍታ ቢኖራችሁ ዝቅ ማለት አይክበዳችሁ።
እርሱ ትልቅ ሆኖ ሳለ እግርን ካጠበ እኔማ እንዴት አልማር ከዚህ?! ይሁዳንም ሳይለይ ካጠበ ታድያ እኔ ማነኝ ሰውን የምለይ?! እየሱስ ልፈርድ አልመጣሁም ለማዳን እንጂ እንዳለ ላስተውልና ከፍርድ ወንበር ወርጄ ሰውን ሳለይ ላገልግል ይገባል:: መለየትና መፍረድ በስተመጨረሻ የጌታ ነውና::
“እውነት እውነት እላችኋለሁ፥ ማናቸውን የምልከውን የሚቀበል እኔን ይቀበላል፥ እኔንም የሚቀበል የላከኝን ይቀበላል።” ጌታ ወደ ህይወታችን የላከውን ሰዎች እንቀበል:: በዙሪያችን ስላሉ ቅዱሳን ጌታን እናመስግን እሱ ልኳቸዋልና::
አባት ሆይ ስለ ቃልህ ተመስገን! አከብርሃለሁ ! በህይወቴ ስለሰጠኸኝ ሰዎች ተመስገን ዝቅ ብዬ ባለመለየት ሁሉንም በትህትናና በፍቅር እንዳገለግል ጸጋህን ስጠኝ! አሜን!
ዮሐንስ 13: 21-30
21፤ ኢየሱስ ይህን ብሎ በመንፈሱ ታወከ መስክሮም፦ “እውነት እውነት እላችኋለሁ፥ ከእናንተ አንዱ አሳልፎ ይሰጠኛል፡” አለ።
27፤ ቍራሽም ከተቀበለ በኋላ ያን ጊዜ ሰይጣን ገባበት። እንግዲህ ኢየሱስ፦ “የምታደርገውን ቶሎ ብለህ አድርግ፡” አለው።
ኢየሱስ ይህን ብሎ በመንፈሱ ታወከ የሚለው ክፍል እንዴት ይነካል?! ለዚህ ሰዓት ቢመጣም ቅሉ የሚጠብቀው ያውቅ ነበረና ነው:: የሰይጣን ድፍረት ቀን ከለሊት ከእየሱስ ጋር የሚመላለሰውን ደቀ መዝሙር መጥለፍ ቻለ:: ከእየሱስ ስር አባብሎ ወረሰው:: አንድ መዋግያው ሃሳብን ማስገባት ነው:: ለዚህ ነው አእምሯችን ባዶ መሆን የሌለበት ቃሉን በቀንም በለሊትም አሰላስሉት የተባልነው:: የፈጠረን ጌታ ስለሚያውቀን ነው ይህንን ያለን ስለዚህ ቃሉን የምናሰላስል እንሁን::
ያዕቆብ 1:13፤ ማንም ሲፈተን፦ “በእግዚአብሔር እፈተናለሁ፡” አይበል፤ እግዚአብሔር በክፉ አይፈተንምና፤ እርሱ ራሱስ ማንንም አይፈትንም። 14፤ ነገር ግን እያንዳንዱ በራሱ ምኞት ሲሳብና ሲታለል ይፈተናል። 15፤ ከዚህ በኋላ ምኞት ፀንሳ ኃጢአትን ትወልዳለች፤ ኃጢአትም ካደገች በኋላ ሞትን ትወልዳለች።
እግዚአብሔር አይፈትንም ነገር ግን ምኞታችንን ወይም ሃሳባችንን ጠላት እንዳይጠቀምበት ሃሳባችንን በሃሳቡ እንግዛውና ለጠላት እድል ፋንታ አንስጠው::
ይሁዳ አሳልፎ ሳይሰጠው በፊት እየሱስ ያውቅ ነበረ ደቀ መዝሙሩም እንደማይሆን እያወቀ እግሩን አጠበው አለየውም:: ይህንን የሚያደርግበት ከጌታ የደረሰበት ነገር የለም::
አባት ሆይ ሃሳቤ ሁሉ ቃልህን በማሰላሰል ይሞላ:: ቃልህ ህይወት ነው መንፈስ ነውና ህይወቴን ይሙላው:: አሜን!
ዮሐንስ 13: 31-35
34፤ እርስ በርሳችሁ ትዋደዱ ዘንድ፥ እንደ ወደድኋችሁ እናንተ ደግሞ እርስ በርሳችሁ ትዋደዱ ዘንድ አዲስ ትእዛዝ እሰጣችኋለሁ።
35፤ እርስ በርሳችሁ ፍቅር ቢኖራችሁ፥ ደቀ መዛሙርቴ እንደ ሆናችሁ ሰዎች ሁሉ በዚህ ያውቃሉ።”
ይሁዳ የመጨረሻውን ቁራሽ ይዞ ከወጣ በኃላ ጌታ መክበሩን ነገራቸው:: ታሪኩን ወደፊት የሚሆነውን ስናይ ግን ከመክበር በፊት የመስቀል መከራ ይጠብቀው ነበረ:: ሌላው ያደረገው ነገር የጠለቀውን ትምህርት ደቀ መዝሙር ለመሆን የሚያስፈልጋቸውን ያስተምራቸው ጀመረ::
በብሉይ ኪዳን በዘሌዋውያን 19:18፤ . . . ነገር ግን ባልንጀራህን እንደ ራስህ ውደድ፤በሚለው ስርዓት ነው እየኖሩ የነበረው ሌላውን መውደድ አዲስ አይደለም ያውቁታል ከአስሩ ትዕዛዛት አንዱ ነውና:: ይህንን ትዕዛዝ ግን አዲስ የሚያደርገው ነገር ጌታ ዙሩን አከረረውና በስጋ የማይቻል አደረገው:: ትዕዛዙም:- እንደ ወደድኋችሁ እናንተ ደግሞ እርስ በርሳችሁ ተዋደዱ የሚል ነው::
ለምን አዲስ ሆነ?
ምክንያቱም በበፊቱ ትዕዛዝ ላይ ሌሎችን መውደድ ያለብኝ እራሴን እንደምወደው ልክ ነበረ ነገር ግን የአሁኑ አዲሱ ትዕዛዝ ክርስቶስ ሰውን በወደደበት ልክ መውደድ አለብኝ:: የክርስቶስ ፍቅር ምን አይነት ነው? እስከሞት ድረስ ፤ ያለ ስስት ፤ የራሱን ሳይፈልግ ዝቅ ብሎ የባርያን መልክ አስይዞ የሚያስመጣ ፤ በትእግስት የተሞላ ፍቅር፤ ለዘላለም የሆነ ፍቅር:: ታድያ እንደዚህ ሰውን እወዳለሁ? ከባድ ትዕዛዝ ነው ለካ:: ቃሉ የሚለን ግን በራሴ ይህንን ስለማልችል በመንፈስ ቅዱስ ፍቅሩ በእኛ ውስጥ ፈሷል ይህንን ፍቅር እለማመደዋለሁ:: እየሱስ በእኔ ውስጥ ይወዳል!! አሜን!
በዚህ ፍቅር ስንዋደድ ደቀ መዛሙርቱ እንደ ሆንን ሰዎች ሁሉ በዚህ ያውቃሉ። አሜን!
ዮሐንስ 13:34፤ እርስ በርሳችሁ ትዋደዱ ዘንድ፥ እንደ ወደድኋችሁ እናንተ ደግሞ እርስ በርሳችሁ ትዋደዱ ዘንድ አዲስ ትእዛዝ እሰጣችኋለሁ።
ዙሩ ከሯል እርስ በእርሳችን ብቻ ሳይሆን ጠላታችንንም መውደድ ይጨምራል:: ይህ ለመውደድ ጥረት ማድረግ አይደለም እግዚአብሔር ፍቅር ነውና ከእርሱ ተቀብለን ፍቅርን በመንፈስ ቅዱስ እንወዳለን:: የወደዱኝን መውደድማ ቀላል ነው ይህንን ግን ሽሮት በፍጹም ፍቅር እንድንመላለስ ፈልጏል:: ጌታ ይርዳን!
አባት ሆይ ከመታወቅ ስለሚያልፈው ፍቅርህ ተመስገን:: እኔም በዚህፍቅር መጥለቅለቅ ይሁንልኝ:: ከውስጤ ይህ ምንጭ ይፍለቅ:: ሁሉን ለአንተ ሰጠሁህ መንፈስ ቅዱስ:: አሜን!
ዮሐንስ 13: 36-38
38፤ ኢየሱስም እንዲህ ብሎ መለሰለት፦ “ነፍስህን ስለ እኔ ትሰጣለህን? እውነት እውነት እልሃለሁ፥ ሦስት ጊዜ እስክትክደኝ ድረስ ዶሮ አይጮኽም።”
እየሱስ በዝግ ሐዋርያቱን እያስተማረ ነው:: በዚህ መሃል ልሄድ ነው ማለቱን ሲሰማ ስምዖን ጴጥሮስም፦ “ጌታ ሆይ፥ ወዴት ትሄዳለህ?” አለው። ኢየሱስም፦ “ወደምሄድበት አሁን ልትከተለኝ አትችልም፥ ነገር ግን በኋላ ትከተለኛለህ፡” ብሎ መለሰለት። ያለእኛ ወዴት ይሄዳል ብሎ ነው:: እነርሱ የሚያውቁት ጌታ አብሯቸው ይኖራል ደግሞም ይልካቸዋል ተአምራት ያደርጋሉ:: ሁሉ አልጋ ባልጋ ነው እየሱስ እያለ:: ታድያ የምን እሄዳለሁ ነው የሚለው ይመስላል::
ልትከተለኝ አትችልም ቢባልም ሊዋጥለትያልቻለው ጴጥሮስ ምን ሲሆን ብሎ ፎከረ:: ጴጥሮስም፦ “ጌታ ሆይ፥ አሁን ልከተልህ አለመቻሌ ስለ ምንድር ነው? ነፍሴን ስንኳ ስለ አንተ እሰጣለሁ፡” አለው። በኃይልም በብርታትም አይደለም በመንፈሴ ነው:: በስጋ የእግዚአብሔር ስራ አይሰራም:: እየሱስ ለዝች ሰዓት መጣ ማንም ሳያግዘውና ሳይረዳው የእግዚአብሔር በግ ሆኖ ህይወትን ሊሰጠን ብቻውን መሰጠት ነበረበትና ጌታ እንደተናገረው ሦስት ጊዜ እስክትክደኝ ድረስ ዶሮ አይጮኽምአደረገው::
እርሱ ብቻእን ድንቅ የሚሰራ ነውና በሚለን ልክ እንመላለስ:: በመንፈሱም በውስጥ ሰውነታችን እንበርታ:: አሜን!
አባት ሆይ የኔ ጽድቅ ቤትህን አይሰራም በመንፈስህ ግን አበርታኝ በራስ የሆነ ትምክህትንም ከእኔ አስወግድ:: አሜን
ዮሐንስ 14:1፤ ልባችሁ አይታወክ፤ በእግዚአብሔር እመኑ፥ በእኔም ደግሞ እመኑ።
እየሱስ ይህንን ሲላቸው ደቀ መዛሙርቱ በብዙ ልብ የሚያርድ ነገር ውስጥ እያለፉ ነበረ:: አንደኛው ነገር ከመካከላችሁ አንዱ ይክደኛል አለ ከዛም ቀጠለና እንደሚለያቸው ነገራቸው ሞት እንደሆነም ገብቷቸዋል ጴጥሮስም እስከሞት እከተልሃለሁ እያለው ነበረና ሌላው ደግሞ ክህደት ዶሮ ሳይጮህ ሶስትጊዜ መካድ:: በዚህ ሁሉ ውስጥ አቅም አተው ተጨንቀዋል ጌታግን ልባችሁ አይታወክ አላቸው:: የህይወት መውጫ ነውና ልብ እንዲታወክ ጌታ አይፈልግም:: የከበባቸው ነገር ግን መፍትሄ የሌለው ነው የሚወዱትን እየሱስን ማስጣል እንደማይችሉ ሲገባቸው ያናውጣል:: አትታወኩ ብሎ ቢያቆም ከባድ ነበረ ግን መታወክ የሌለባቸውንም ምክንያት እንዲሁም ምን ማድረግ እንዳለባቸው ነገራቸው::
ልባችን አይታወክም አልተባለም ስንታወክ ግን ምን እናድርግ? መልሱም በእግዚአብሔር እመኑ፥ በእኔም ደግሞ እመኑ ነው:: እርሱ መታመኛ ነው ማምለጫና መሸሸጊያ!! ለታወከው ልባችን መፍትሄው ልባችንን ከታወከበት ነገር ላይ አንስተን በእግዚአብሔር ላይ በመታመን መመላለስ ነው:: ቀላል ይመስላል ስንነጋገረው ዋናው በመከራው ውስጥ ስናልፍ ነውና ማስተዋል ይሁንልን:: ዳዊትነፍሱን አታውኪኝ እንዳለ እንዲሁ ልንል ይገባል::
አባት ሆይ በአንተ ላይ መደገፍ አንተን ማመን ይሁንልኝ:: አይኖቼ አንተ ላይ እንጂ በዙሪያዬ በሚሆነው ነገር ላይ እንዳይሆን እርዳኝ! አሜን!
ዮሐንስ 14: 2-4
2፤ በአባቴ ቤት ብዙ መኖሪያ አለ፤ እንዲህስ ባይሆን ባልኋችሁ ነበር፤ ስፍራ አዘጋጅላችሁ ዘንድ እሄዳለሁና፤ 3፤ ሄጄም ስፍራ ባዘጋጅላችሁ፥ እኔ ባለሁበት እናንተ ደግሞ እንድትሆኑ ሁለተኛ እመጣለሁ ወደ እኔም እወስዳችኋለሁ።
አትፍሩ እያለ እያበረታቸው ባለበት ጊዜ ጌታ ሃሴት የሚያደርግ ይመስለኛል ይህንን ሲናገር ምክንይቱም ከነገድ ከቋንቋ ሁሉ በቤቱ ስለሚሰበሰቡት አእላፋት እየተመለከተ ነውና:: ምንም እንኳን ሐዋርያት በዛ ሰዓት የሚይዙት የሚጨብጡት የጠፋባቸው ነገሮች ከሚጠበቅ ፍጥነት በላይ እየቸኮሉባቸው ባለበት ሰዓት መረጋጋትና የሚናገረውን ማገናዘብ አልቻሉም:: ስለዚህም ጠለቅ ብሎ ይነግራቸው ጀመረ::
በአባቴ ቤት ብዙ መኖሪያ አለ ማለትም ይህ ዓለም የእናንተ አይደለም መፃተኞች ናችሁ እያላቸው እኛንም እያለን ነው:: ልክ ልጅ ሊወለድ ሲል ወደዚህ ዓለም መምጫው ደርሷልና ቤተሰብ እየተዘጋጀ ይጠብቃል:: እንደዚሁ እየሱስ ስፍራ አዘጋጅላችሁ ዘንድ እሄዳለሁና አለን:: ስፍራ ተዘጋጅቷል ልጆቹን ለመቀበል አባት ጏጉቷል:: እንዴት ያለ ፍቅር ነው የተወደድንበት?!
ወዳዘጋጀልን ስፍራ ሊወስደንና ለዘላለም አብረነው እንድንኖር ይመጣል እየሱስ:: በዚህ ደስ ይበለን ሃሴትም እናድርግ:: የእርሱን መምጣት ስንጠባበቅ እራሱ በመንፈሱ በእኛ ውስጥ ሆኖ እየኖረ ነው እርቆ ሄዶ እንደምንም ብላችሁ ጠብቁኝ አላለንምና ስሙ ይባረክ!
አባት ሆይ ስለተዘጋጀልን ስፍራ እናመሰግንሃለን! ለዘላለም አብረንህ እንድንኖር ነው ዓላማህ ተመስገን! አሁንም እኛነታችንን ለአንተ አሳልፈን እንሰጣለን! አሜን
ዮሐንስ 14: 5-6
6፤ ኢየሱስም አለው፦ “እኔ መንገድና እውነት ሕይወትም ነኝ፤ በእኔ በቀር ወደ አብ የሚመጣ የለም።
መንገዱንም ታውቃላችሁ ባላቸው ጊዜ ቶማስ፦ “ጌታ ሆይ፥ ወደምትሄድበት አናውቅም፤ እንዴትስ መንገዱን እናውቃለን?” አለው። እርሱ የሚያስበው ከቦታ ወደቦታ የሚወስደውን መንገድ እንጂ እየሱስን እራሱን መንገዴ ነው ብሎ አላወቀውም:: እንኳንም ይህንን ጥያቄ ጠየቀ የእየሱስን ወደ አብ መሄጃ መንገድ እንደሆነና እንዲሁም እውነታችን እየሱስ: ህይወታችን እየሱስ እንደሆነ አሳወቀን:: ያለእየሱስ ወደ አብ መሄድ አይቻልም በፀሎትም ቢሆን በክርስቶስ ነው ወደፊቱ የምንቀርበው::
አባት ሆይ አመሰግንሃለሁ ህይወትን ሰተኸኝ ለዘላለም እውነት ሆነህ ውሸት የሌለብህ ጌታ ተቀብለህ ወደ አብ መድረሻ መንገድ ሆንከኝ:: ተባረክ!
ዮሐንስ 14: 7-14
9፤ ኢየሱስም አለው፦ “አንተ ፊልጶስ፥ ይህን ያህል ዘመን ከእናንተ ጋር ስኖር አታውቀኝምን? እኔን ያየ አብን አይቶአል፤ እንዴትስ አንተ፦ ‘አብን አሳየን፡’ ትላለህ?
ጌታ እየሱስ እኔንስ ብታውቁኝ አባቴን ደግሞ ባወቃችሁ ነበር። ከአሁንም ጀምራችሁ ታውቁታላችሁ አይታችሁትማል ሲላቸው ግራ የገባው ፊልጶስ፦ “ጌታ ሆይ፥ አብን አሳየንና ይበቃናል፡” አለው። ጌታ ያለው ከአሁን ጀምራችሁ ታውቁታላችሁ ነው እነሱ ግን ልክ እየሱስን እንደሚያዩት አብንም አሳየን ምናልባትም መገለጥ ይሆን የሚጠብቁት እነሙሴን አይተዋል አንዳንዶች ግን በምን መልኩ ነው አብን ማየት የፈለጉት? አብን አሳየንና ይበቃናል የሚለው ጥያቄ መልስ ሲሰጥ
– ይህን ያህል ዘመን ከእናንተ ጋር ስኖር አታውቀኝምን? እውነት ነው ለአእምሮ አይመችም የስላሴ ሚስጥር ግን እኔን ያየ አብን አየ: እኔና አብ አንድ ነን ካለን በቂ ነው::
– እኔ በአብ እንዳለሁ አብም በእኔ እንዳለ አታምንምን? እኔ የምነግራችሁን ቃል ከራሴ አልናገረውም፤ ነገር ግን በእኔ የሚኖረው አብ እርሱ ሥራውን ይሠራል።
– ስለዚህ ከእኛ የሚጠበቀው ማመን ነው:- እኔ በአብ እንዳለሁ አብም በእኔ እንዳለ እመኑኝ፤ ባይሆንስ ስለ ራሱ ስለ ሥራው እመኑኝ።
በእየሱስ ማመናችን ቃል እንደገባልን፥ በእኔ የሚያምን እኔ የማደርገውን ሥራ እርሱ ደግሞ ያደርጋል፤ ከዚህም የሚበልጥ ያደርጋል፥ አለን:: እርሱ ያደረገው ምንድነው የአባቱን ፈቃድ በመታዘዝ ማገልገል ነው:: አባቱን አከበረ የምናገረው የእኔ አይደለም የማደርገውም አባቴ ሲያደርግ የማየውን ነው ብሎ በአባቱ ላይ ታምኖ ተመላለሰ:: እርሱ እንደተመላለሰ መመላለስ ይሁንልን::
ሌላው እያስተማረ ያለው በስሙ እንድለምን ነግሮን የምንለምነውንም ደግሞ ሁሉ እንደሚያደርገው ቃል ገብቶልናል በስሙም ስንለምን በዚያ አብ ይከብራል::
ዮሐንስ 14:14፤ ማናቸውንም ነገር በስሜ ብትለምኑ እኔ አደርገዋለሁ።” አሜን!
ዮሐንስ 14: 15-18
15-16፤ “ብትወዱኝ ትእዛዜን ጠብቁ። እኔም አብን እለምናለሁ ለዘላለምም ከእናንተ ጋር እንዲኖር ሌላ አጽናኝ* ይሰጣችኋል፤ (* አጽናኝ ማለት በግሪክ ቋንቋ ጰራቅሊጦስ ማለት ነው)
17፤ እርሱም ዓለም የማያየውና የማያውቀው ስለ ሆነ ሊቀበለው የማይቻለው የእውነት መንፈስ ነው፤ ነገር ግን ከእናንተ ዘንድ ስለሚኖር በውሥጣችሁም ስለሚሆን እናንተ ታውቃላችሁ።
ትእዛዜን ጠብቁ ብሎ ሲለን መስፈርቱ ከወደዳችሁኝ ነው ያለን:: ትእዛዝ ብለን ስንል ለምሳሌ በዚሁ ምዕራፍ ያዘዘን ልባችሁ አይታወክ የሚል ሲሆን በቀደመው ምዕራፍ ደግሞ እኔ እንደወድኳችሁ እርስ በእርሳችሁ ተዋወዱ ነው::
እኔም አብን እለምናለሁ አለ ምንድነው የሚለምነው? የሚለምነው ለዘላለምም ከእኛ ጋር የሚኖር ሌላ አጽናኝ እንዲሰጠ:: ልመናው ተሰማ? በትክክል ተሰምቶ ሐዋ 2 ላይ መንፈስ ቅዱስ ወረደ ቤተክርስትያንንም ተረከበ:: ሃሌሉያ!
ይህ መንፈስ ቅዱድ ሌላ አጽናኝ ተብሎ ነው የተጠራው:: መንፈስ ቅዱስ ስብእና ያለው: ስሜት ያለው: ማንነት ያለው እንጂ ስሜታችን አይደለም:: እርሱም ዓለም የማያየውና የማያውቀው ስለ ሆነ ሊቀበለው የማይቻለው የእውነት መንፈስ ነው፤ ነገር ግን ከእናንተ ዘንድ ስለሚኖር በውሥጣችሁም ስለሚሆን እናንተ ታውቃላችሁ። ዋዉ አምላካችን ሰው በሰራው ህንፃ አይኖርም እራሱ በሰራው ሰው ውስጥ እንጂ:: አሜን!
ጌታእየሱስ ቃል ገብቶልናል ወላጆች እንደ ሌላቸው ልጆች አልተዋችሁም፤ ወደ እናንተ እመጣለሁ ብሎናል:: የምድር ወላጅ በሞት ይለያል የሰማዮ አባት ግን ሁልጊዜ ከእኛ ጋር ነው:: ይህ ደህንነት እንዴት ያለ ነው? ወልድም መንፈስ ቅዱስም ከእኛ ጋር የሆነበት ህይወት:: ብቸኝነት የሌለበት በወላጃችን ጉያ ውስጥ ሆነን የምንኖረው ኑሮ ነው:: ቅዱሳን እንንቃ ጠላት ማስተዋላችንን አይውሰድ ጌታ ከቦናል እርሱ በውስጣችን ሞልቷል የምንፈራውና ደረሰብኝ የምንለው ምንድነው?
አባት ሆይ ተመስገን ያለስጋት በአንተ ተማምኜና ተደላድዬ እኖራለሁ:: አሜን
ዮሐንስ 14: 19-20
19፤ ገና ጥቂት ዘመን አለ ከዚህም በኋላ ዓለም አያየኝም፤ እናንተ ግን ታዩኛላችሁ፤ እኔ ሕያው ነኝና እናንተ ደግሞ ሕያዋን ትሆናላችሁ።
20፤ እኔ በአባቴ እንዳለሁ እናንተም በእኔ እንዳላችሁ እኔም በእናንተ እንዳለሁ በዚያን ቀን ታውቃላችሁ።
ዓለም አያየኝም እናንተ ግን ታዩኛላችሁ ብሎ ሲላቸው ግራ ይገባል ለስጋዊ ሰው ምክንያቱም እነዚህ ሰዎች በአዲስ ኪዳን በር ላይ ይሁኑ እንጂ ብሉይ ኪዳን ላይ ናቸው:: እንዳለውም ከትንሳኤው በኃላ አብሯቸው አሳልፏል ዓለም አያየውም ነበረ:: አሁንም እየሱስን በዓይን ባናየውም እኛ ውስጥ በመንፈስ ቅዱስ ይኖራል::
እኔ ሕያው ነኝና እናንተ ደግሞ ሕያዋን ትሆናላችሁ። እራሱን የህያዋን አምላክ ብሎ ነው የሚጠራው እርሱ ህያው ነውና ለእኛም የዘላለምን ህይወት ሰጠን! ስሙ ይባረክ!
ዛሬ ጌታ እየስስ እንደነገረን በአባቱ እንዳለ እኛም በእርሱ እንዳለን እንወቅ:: ይህ ብቻ አይደለም እየሱስ በእኛ እንዳለ በዚያን ቀን እንደምናውቅ ነግሮናል:: ወላጆች እንደሌላቸው ልጆች የማይተወን ጌታ በእኛ ውስጥ እየኖረ ነው::
አባት ሆይ ስምህን እባርካለሁ በእኔ ውስጥ ስላለህ እኔም በአንተ ውስጥ ነኝ:: አባቴ ሆይ የማትተወኝ ጌታ ነህና ተባረክ! ይህ ህይወት የአንተ ነውና ክበርበት::
ዮሐንስ 14: 21-24
21፤ ትእዛዜ በእርሱ ዘንድ ያለችው የሚጠብቃትም የሚወደኝ እርሱ ነው፤ የሚወደኝንም አባቴ ይወደዋል እኔም እወደዋለሁ ራሴንም እገልጥለታለሁ።”
23፤ ኢየሱስም መለሰ፡ አለውም፦ “የሚወደኝ ቢኖር ቃሌን ይጠብቃል፤ አባቴም ይወደዋል፡ ወደ እርሱም እንመጣለን፡ በእርሱም ዘንድ መኖሪያ እናደርጋለን።
24፤ የማይወደኝ ቃሌን አይጠብቅም፤ የምትሰሙትም ቃል የላከኝ የአብ ነው እንጂ የእኔ አይደለም።
ጌታን መውደዳችን የሚታወቀው ትእዛዙ በእኛ ዘንድ ሲሆንና ቃሉንም በመጠበቅ እንደሆነ ጌታ ይናገራል:: እርሱን ስንወድ እኛ ደግሞ በአብ እንወደዳለን ይህም ብቻ አይደለም እራሱንም ይገጥልናል:: ምን ያህል ይወደናል?! በዚህ ጊዜ “ጌታ ሆይ፥ ለዓለም ሳይሆን ራስህን ለእኛ ልትገልጥ ያለህ እንዴት ነው? የሚል ጥያቄ ቀረበለት::
አሁንም መልሱ የሚወደኝ ቢኖር ቃሌን ይጠብቃል፤ አባቴም ይወደዋል፡ ወደ እርሱም እንመጣለን፡ በእርሱም ዘንድ መኖሪያ እናደርጋለን። እራሱን የሚገልጥልን አንዱ በቃሉ ሌላው ደግሞ በመንፈሱ ወደእኛ በመምጣት ነው:: ቅደም ተከተሉ ከእኛ የሚጠበቅብን እርሱን መውደድና ቃሉን መጠበቅ ከእርሱ የምንቀበለው ፍቅሩንና አብሮነቱን:: በኤፌ 3: 16-19 ላይ ጳውሎስ እንደፀለየው እንፀልይ::
በተቃራኒው የማይወደኝ ቃሌን አይጠብቅም፤ የምትሰሙትም ቃል የላከኝ የአብ ነው እንጂ የእኔ አይደለም።
አባት ሆይ እወድሃለሁ በሰጠኸኝም ጸጋ ቃልህን እጠብቃለሁ:: እራስህን ስለምትገልጥልኝና በእኔም ዘንድ ልትኖር ስለምትመጣ ተመስገን::
ዮሐንስ 14: 25-26
25፤ ከእናንተ ዘንድ ስኖር ይህን ነግሬአችኋለሁ፤
26፤ አብ በስሜ የሚልከው ግን መንፈስ ቅዱስ የሆነው አጽናኝ እርሱ ሁሉን ያስተምራችኋል እኔም የነገርኋችሁን ሁሉ ያሳስባችኋል።
ጌታ ነግሬአችኋለሁ የሚለን በስሙ ስለሚላክልን ረዳት ነው:: አሁን በዓለም እየሰራ ያለው ያገልግሎቱን አደራ የተረከበው መንፈስ ቅዱስ ነው:: ያለ እርሱ አንዳች አናደርግም ብለን ስንል ለማለት ያህል አባባል ሳይሆን እውነት ነው::
ከላይም በቁ 16 ላይም እንደጠቀሰው ይህ አጽናኝ ዓለም የማያየው እየሱስ አብን ለምኖ የተላከልን ነው:: ይህ አጽናኝ በእየሱስ ስም ነው የተላከልን ስለዚህ ላክልን ማለት አያስፈልገንም መቀበል እንጂ:: ወደ ህይወታችን መጋበዝ ብቻ ነው:: ጳውሎስም በ ሐዋ. ሥራ 19:2፤ ባመናችሁ ጊዜ መንፈስ ቅዱስን ተቀበላችሁን? አላቸው። መቀበል ነው አንድ ጊዜ በእየሱስ ተለምኖ የተሰጠን ነው:: አሜን!
መንፈስ ቅዱስ የሚያደርገው ነገር:-
አጽናኝ ነው
ሁሉን የሚያስተምረን ነው
እየሱስ በቃሉ የነገረንን ሁሉ የሚያሳስበን
ነው::
አብ አባት ሆይ መንፈስ ቅዱስን ስለላክልን ተመስገን:: ያለ አንተ አንዳች ማድረግ እንደማልችል አውቄያለሁና እርዳኝ:: የምታጽናና የምታስተምር ቅዱሱ መንፈስ ሆይ አስተምረኝ ቃሉንም እኖርበት ዘንድ አሳስበኝ ምራኝ እየሱስንም በህይወቴ አክብረው አንተንም በማወቅ ሙላኝ:. አሜን!
ዮሐንስ 14: 27-31
27፤ ሰላምን እተውላችኋለሁ፥ ሰላሜን እሰጣችኋለሁ፤ እኔ የምሰጣችሁ ዓለም እንደሚሰጥ አይደለም። ልባችሁ አይታወክ አይፍራም።
ሳይሆን ገና የሚሆነውን ሁሉ እየነገረና እያጽናናቸው ነው ጌታ:: ምዕራፍ 14-17 በሰዓታት ውስጥ የተደረገ የመጨረሻው ወደ መስቀል ከመሄዱ በፊት እንደ ስንቅ የሰጣቸው ምክሩና ትምህርቱ ነው:: ብዙ ነገር የታጨቀበት ነው:: እኔ እሄዳለሁ ወደ እናንተም እመጣለሁ እንዳልኋችሁ ሰማችሁ። የምትወዱኝስ ብትሆኑ ከእኔ አብ ይበልጣልና ወደ አብ በመሄዴ ደስ ባላችሁ ነበር። በመሄዴ ደስ ሊላችሁ ነው የሚገባው አላቸው በእነሱ ቦታ ይህ ምንም ትርጉም አይሰጥም:: እየሱስ ግን የመጣው ተላልፎ ሊሰጥና እንደበግ ሊታረድልን ነው:: በዛ የኃጥያት ስርየት ተገኘ ወደ አብ ሲሄድና ሲከብር ደግሞ መንፈስ ቅዱስን ላከልን:: ለዚህም ነው በመሄዴ ደስ ይበላችሁ የሚላቸው:: ግን አልገባቸውም::
ሲጀምርም ምዕራፉ ልባችሁ አይታወክ አላቸው ሲጨርሰውም በዚሁ ነው እየጨረሰው ያለው:: እንዴት ግን አይታወኩም ያሉበት ሁኔታ ውጥር ያለ ነው?! መፍትሄንም ሰጥቶ ነው አትታወኩ የሚለው የሰጠንም ‘ሰላሙን’ ነው:: ሰላምን እተውላችኋለሁ፥ ሰላሜን እሰጣችኋለሁ፤ እኔ የምሰጣችሁ ዓለም እንደሚሰጥ አይደለም። ትቶልን ሄዷል ማንም ከእኛ አይወስድብንም:: ምክንያቱም እኛ ተግተን የምናገኘው ሳይሆን የመንፈስ ፍሬ ነው ይህንን ፍሬ በላያችን የሚያደርገው እራሱ መንፈስ ቅዱስ ነው:: ይህ አእምሮን የሚያልፍ ሰላም ዓለም እንደምትሰጠው አይደለም:: ልባችንን ይጠብቅ ዘንድ ከሰላሙ አለቃ ተሰቶናልና ልባችንን እንጠብቅ የህይወትም መውጫ ከዛ ነውና:: ጌታ ለልባችን መታወክ መፍትሄ ሰቶናል ሰላሙንና አብሮነቱን (በእግዚአብሔር እመኑ በእኔ እመኑ ብሎ):: ወላጅ እንደሌላቸው አይደለንም እርሱ ከእያንዳንዳችን ጋር ነው:: የክርስትያን ድሉ ሰላሙ ነው ጠላት ሊያውክ ነው የሚመጣው ተረጋግተን እንድንኖር ጌታ ሰጥቶናል:: ሁሉ የተሰጠው ነው እንጂ ለተወሰነ ሰው ብቻ አይደለም::
እየሱስ አባቱን ከመውደዱ የተነሳ አብን ታዘዘ :: ነገር ግን አብን እንድወድ ዓለም ሊያውቅ፥ አብም እንዳዘዘኝ፥ እንዲሁ አደርጋለሁ። ተነሡ፤ ከዚህ እንሂድ።” ብሎ እራሱን አሳልፎ ሊሰጥ ተነሳ:: ጌታ እየሱስ ምን አይነት ፍቅር ነው::
አባት ሆይ ተመስገን ሰላምህን ትተህልኝ ሄደሃል ይህ ሰላም በማልፍበት ሁሉ ይረዳኛልና ልቤ እንዳይታወክ የአንተን ሰላም በላዬ ላይ አውጃለሁ በእምነት እቀበላለሁም:: አሜን!
ዮሐንስ 14 – ክለሳ
የተሰጠን ትእዛዝ :-
ልባችሁ አይታወክ
ብትወዱኝ ትእዛዜን ጠብቁ።
የተሰጠን መፍትሄ ለትእዛዙ
በእግዚአብሔር እመኑ፥
በእኔም ደግሞ እመኑ።
ሰላሜን ትቼላችኃለሁ::
የተሰጠን ተስፋ:
ስፍራ አዘጋጅላችሁ ዘንድ እሄዳለሁና፤
ሁለተኛ እመጣለሁ ወደ እኔም
እወስዳችኋለሁ።
በእኔ የሚያምን እኔ የማደርገውን ሥራ
እርሱ ደግሞ ያደርጋል፤ ከዚህም
የሚበልጥ ያደርጋል፥
ጸሎት የሚመለሰው አብ እንዲከብር
ነው:- አብም ስለ ወልድ እንዲከበር
በስሜ የምትለምኑትን ሁሉ
አደርገዋለሁ።
ማናቸውንም ነገር በስሜ ብትለምኑ እኔ
አደርገዋለሁ።
ወላጆች እንደ ሌላቸው ልጆች
አልተዋችሁም፤ ወደ እናንተ እመጣለሁ።
እኔ ሕያው ነኝና እናንተ ደግሞ ሕያዋን
ትሆናላችሁ።
እኔ በአባቴ እንዳለሁ እናንተም በእኔ
እንዳላችሁ እኔም በእናንተ እንዳለሁ
በዚያን ቀን ታውቃላችሁ።
ትዛዙን/ቃሉን ለሚጠብቅ የተሰጠ ተስፋ
የሚወደኝ እርሱ ነው፤ የሚወደኝንም አባቴ ይወደዋል እኔም እወደዋለሁ ራሴንም እገልጥለታለሁ።
አባቴም ይወደዋል፡ ወደ እርሱም እንመጣለን፡ በእርሱም ዘንድ መኖሪያ እናደርጋለን።
የተቀበልነው ተስፋ:-
እኔም አብን እለምናለሁ ለዘላለምም ከእናንተ ጋር እንዲኖር ሌላ አጽናኝ* ይሰጣችኋል፤
አብ በስሜ የሚልከው ግን መንፈስ ቅዱስ የሆነው አጽናኝ እርሱ ሁሉን ያስተምራችኋል እኔም የነገርኋችሁን ሁሉ ያሳስባችኋል።
ሰላምን እተውላችኋለሁ፥ ሰላሜን እሰጣችኋለሁ፤ እኔ የምሰጣችሁ ዓለም እንደሚሰጥ አይደለም።
የተሰጠን ድል:-
የዚህ ዓለም ገዥ ይመጣልና፤ በእኔ ላይም አንዳች የለውም:: በእየሱስ ላይ አንዳች እንደሌለው ሁሉ በእኛላይም የለውም እኛ የእየሱስ ነን:: ይህችን ክፉ ዓለም ክደናል::
ከእየሱስ የምንማረው:-
አብም እንዳዘዘኝ፥ እንዲሁ አደርጋለሁ።
አባት ሆይ ይህ ሁሉ ተስፋ አለኝ! ምን እላለሁ ክበርተመስገን!
ተመስገን ስለሰጠኸን ተስፋ: መንፈስህንም እንዳንረታ ስለሰጠኸን ተወደስ:: ለዘላለም ከእኔ ጋር ስለሆንክ ህያው ስላደረከኝ ተመስገን::
ዮሐንስ 15: 1-2
1፤ “እውነተኛ የወይን ግንድ እኔ ነኝ፤ ገበሬውም አባቴ ነው።
ዮሐንስ 15:2፤ ፍሬ የማያፈራውን በእኔ ያለውን ቅርንጫፍ ሁሉ ያስወግደዋል፤ ፍሬ የሚያፈራውንም ሁሉ አብዝቶ እንዲያፈራ ያጠራዋል።
የወይን ግንድ እኔ ነኝ ብቻ አይደለም ያለው ነገር ግን እውነተኛ ብሎ ጨምሮበታል:: ውሸተኞች አሉ ማለት ነው ልክ እንደወይኑ ግንድ ሰው ተጣብቆባቸው መኖር የሚያስችሉ የሚመስሉ ለምሳሌ:- ሃብት: ዝና: ዘርና የመሳሰሉት:: እነዚህ ግን የተወሰነ መንገድ ድረስ ነው የሚሄዱት አያዋጡም ይሰበራሉ:: የእኛ ጌታ ግን ሁልጊዜ ከእኛ ጋር ነው::
ይህ እውነተኛ የወይን ግንድ መደገፍያ መኖርያም ነው:: ግንዱ የሚያስፈልገውን ሁሉ ካላቀረበ ቅርንጫፉ ይሞታል ቅርንጫፉ በራሱ የሚያደርገው ነገር የለም ተማምኖ መኖር ብቻ ነው:: ደርሶ ያደረግን ቢመስለን እንኳን ውሸት ነው ሁሉ የሆነው በጸጋው ነውና:: የሚገርመው ወይን ከግንዱ ብቻ ሳይሆን ከሌላውም ቅርንጫፍ ጋር ይጠላለፍና ይደጋገፋል አንዱ በአንዱ ይበረታል ቅርንጫፉ እንደዚህ ሲሰናሰን የመውደቁ አጋጣሚ እምንት እየሆነ ይመጣል:: በዚህ ውስጥ የምናየው አጠገባችን ያሉት ቅዱሳን ለመቆምና ለመበርታት እንደሚያስፈልጉን ነው:: ንፋሱም ምኑም ገፍቶ አደጋ ላይ እንዳይጥለን እርስ በእርስ እንጠባበቃለን:: ስለዚህ በወገኖች ውስጥ ያለ ጸጋ ያስፈልገኛል እኔም አስፈልጋቸዋለሁኝ ማለት ነው:: ለብቻዬ እኖራለሁ የሚባል ክርስትና የለም ጸጋ ሁሉ የተለያየ ነውና በአንዱ ላይ ሁሉ ጸጋ የለምና ይህንን አውቀን ህብረት ከቅዱሳን ጋር እናድርግ::
ሌላው ህብረታችን ከወይኑ ግንድ ከእየሱስ ጋር ገበሬውም እየተከታተለ የሚንከባከበን ከአብ እንዲሁም ከእኛ ጋር ከሚኖር መንፈስ ቅዱስ ጋር ነው:: በ1 ዮሐንስ 1:3፤ እናንተ ደግሞ ከእኛ ጋር ኅብረት እንዲኖራችሁ ያየነውንና የሰማነውን ለእናንተ ደግሞ እናወራላችኋለን። ኅብረታችንም ከአባት ጋር ከልጁም ከኢየሱስ ክርስቶስ ጋር ነው።
ይህ ገበሬ የሚያደርገው መጉዳት ሳይሆን አብዝተን እንድናፈራ ማድረግ ነው:: የትኛው አባት ሰብሮ ያስተምራል እርሱ የሚራራ አባት ነውና መጎዳታችንን አይፈልግም:: እንዴት ይገርዘናል ? በቃሉና በመንፈሱ ነው የሚያደርገው:: በአእምሯችን መታደስ ተለውጠን እንድንመላለስ ነው የሚፈልገው ስለዚህ ቃሉ ህይወት እንደሆነና መንፈስም እንደሆነ ተነግሮናል ይህ ቃል ይሰራናል ይለውጠናል መንፈሱም ይህንኑ ስራ ቃሉን በማስታወስና በማስተማር በማጽናናት የመንፈስ ፍሬ ሁሉ አፍርተን ለበጎ ስራ የበቃንና ፍሬ እንዲበዛልን ያደርጋል:: ስለዚህ በወይን ግንዱ ላይ እንጣበቅ ሾርት ከት የለም ማደግ ጊዜ ይወስዳልና ጊዜ እንስጠው በፊቱ እንገኝ::
አባት ሆይ ተመስገን እንደዚህ አድርገህ ስለተንከባከብከኝ ተመስገን:: አንተን እታመናለሁ በዙርያዬም ስለሰጠኸኝ ቅዱሳን ተባረክ:: አሜን!
ዮሐንስ 15: 3-4
4፤ በእኔ ኑሩ እኔም በእናንተ። ቅርንጫፍ በወይኑ ግንድ ባይኖር ከራሱ ፍሬ ሊያፈራ እንዳይቻለው፥ እንዲሁ እናንተ ደግሞ በእኔ ባትኖሩ አትችሉም።
እዚህ ስፍራ ላይ እናንተ ስለ ነገርኋችሁ ቃል አሁን ንጹሐን ናችሁ ብሎ ሲል ማንም በክርስቶስ ላይ የሚበቅልና የሚጣበቅ ከኃጥያቱ የታጠበ ወደ እረፍቱ የገባ ነው ይህ እውነት ህይወታችንን ሲገዛው ንጹሃን ነን በስብከት ሞኝነት አምነን ህይወታችንንም የሰጠነው በቃሉ አይደል?
በእኔ ኑሩ እኔም በእናንተ የሚለው በጣም ጥልቀት ያለው የክርስትና ህይወት ነው:: ይህ ማለት ጸሎት ማለት አይደለም ይህ ማለት መዘመር አይደለም ወይም የክርስትና ትእዛዛትንም መፈጸም አይደለም:: በእኔ ኑሩ ማለት ባለማቋረጥ በቀጣይነት ልክ እንደምንተነፍሰው አየር መለያየት እንደማንችለው አየሩ ለደቂቃ ከሌለ እንደማንኖር በእርሱ መኖር ይህ ነው ወይም የህይወት ዘይቤ ነው:: በዕብራ 4:11፤ እንግዲህ እንደዚያ እንደ አለመታዘዝ ምሳሌ ማንም እንዳይወድቅ ወደዚያ ዕረፍት ለመግባት እንትጋ። እንደሚል መትጋት ያለብን በዚህ እረፍት ላይ ለመሆን ነው::
ፍሬ በህይወታችን አይተን ልባችን እብጥ ብ ት ል ከግንዱ እንዳገኘነው እንወቅ ጌታን እናክብር እንጂ ቅርንጫፍ ከመቼ ወዲህ ነው በራሱ ፍሬ የሚያፈራው?! እርሱ በእኛ እኛም በእርሱ ስንኖር ፍሬ የማይቀር ሃቅ ነው እናፈራለን ወይም እርሱ በእኛ ውስጥ ያፈራል:: ፍሬውም ለእኛ ይቆጠር እንጂ የእሱ ነው:: ጠላትም ይህንን ስለሚያውቅ የሚያንቀን ብራቮ ይህንን የመሰለ ምሳሌ የሆነ ህይወት ብሎ ይሞላናል ሰልፉ ስውር ነው እውነትም ስንል ነው ጉዱ መልሳችን መሆን ያለበት እኔም ይገርመኛል በእኔ ሆኖ ክርስቶስ ያፈራው ፍሬ ብለን ብንመልስ ጭራውን ቆልፎ ይሮጣል:: እንንቃ!! ውጊያው እውነት ነው እየሱስንም ፈትኗል ሲያቅተውን ጭራሹን ትቶት ሄደ አይልም ለጊዜው ተለየ እንጂ:: እኛንም እንደዚሁ ነው የሚዋጋን ከእየሱስ ውስጥ አውጥቶ በራሳችን ሊያቆመንና ስንደርቅ ሊያይ:: ጎበዝ አይናችንን በመንገዳችን ላይ ህይወታችንን በግንዱ ላይ እናድርግ::
ቅርንጫፍ በወይኑ ግንድ ባይኖር ከራሱ ፍሬ ሊያፈራ እንዳይቻለው፥ እንዲሁ እናንተ ደግሞ በእኔ ባትኖሩ አትችሉም። አለቀ ምንም ማብራሪያ አያስፈልገውም! በእርሱ ካልሆንን አናፈራም!
አባት ሆይ እዳዬን ከፍለህ ማዳንህ ሳያንስ አንተን እመስል ዘንድ በአንተ ላይ አብቅለኸኝ በእኔ ውስጥ ፍሬን እያፈራህ አለህ:: ከኔ የሆነ ምናለ ጌታ ሁሉ ባንተ ነውና ምስጋናዬ መገዛቴ ይኸው:: በሰንበት እረፍት ውስጥ እርፍ እላለሁ የቀረ የምሰራው የለም! ተፈጸመ ላልከው ለበጉ ክብር ይሁን!!! አሜን!
ዮሐንስ 15: 5-8
7፤ በእኔ ብትኖሩ ቃሎቼም በእናንተ ቢኖሩ የምትወዱትን ሁሉ ለምኑ ይሆንላችሁማል።
8፤ ብዙ ፍሬ ብታፈሩና ደቀ መዛሙርቴ ብትሆኑ በዚህ አባቴ ይከበራል።
አሁንም ደግሞ እኔ የወይን ግንድ ነኝ እናንተም ቅርንጫፎች ናችሁ። ያለ እኔ ምንም ልታደርጉ አትችሉምና በእኔ የሚኖር እኔም በእርሱ፥ እርሱ ብዙ ፍሬ ያፈራል እያለ እየደገመ ነገራቸው:: ፍሬ የሚያፈራው እርሱ መሆኑን እንድናውቅ ነው መልክቱ የአድርግና አታድርግ ዘመን አልፎ ሞተናል እርሱ ህያው ሆኖ በእኛ ይኖራል:: ህይወት እንዲበዛልንና እንዲትረፈረፍልን ነው ጌታ የመጣው::
ሌላው ነገር ያስተማረው በእኔ የማይኖር ቢሆን እንደ ቅርንጫፍ ወደ ውጭ ይጣላል ይደርቅማል፤ እነርሱንም ሰብስበው ወደ እሳት ይጥሉአቸዋል፥ ያቃጥሉአቸውማል። ሰው በክርስቶስ ብቻ ነው በህይወት መኖርየሚችለው ምንም ፍሬ የለም በዓለም ምንም እንኳንየሚደንቅ ህይወት የሚኖሩ ቢኖሩም ጌታ ሲያየው ተስፋ ቢስ የደረቀ ቅርንጫፍ እንጂ ፍሬ አያገኝበትም:: የፈለገውን ነገር ያድርግ የፈለገውን ያህል ኃብትና ዝና ትምህርትና እውቅና ይኑረው ክርስቶስ ከሌለው ሙት ነው እኛ አናሻሽለውም:: እንዲያውም አትኩሮታችንን በመዳኑ ላይ እናድርግ:: ጌታ ይርዳን በምናየው ነገር ተታለን ያልዳነውን ድኗል ብለን የተሰጠንን አጋጣሚ እንዳናባክን::
የምንለምነው ሁሉ የሚሆንልን መቼ ነው? ጌታ እንዳለን:–
1. በእኔ ብትኖሩ
2. ቃሎቼም በእናንተ ቢኖሩ
ከዛስ ምን ይሆናል እነዚህ ሲሟሉ?
የምትወዱትን ሁሉ ለምኑ ይሆንላችሁማል ተባልን:: በእርሱ ስንኖር የምናስበውና የምንለምነው እንደፈቃዱ ይሆናል:: ቃሉ በውስጣችን ሲሞላ ቃሉን ነው የምንፀልየው:: ይህንን እንደባዶ ቼክ የፈለግነውን የምንፅፍበት አድርገው ሰዎች ይወስዳሉ ነገር ግን ከላይ ያለው ሲሟላ ነው የጠየቅነው ሁሉ የሚሰጠን አለዚያ ፀሎታችን በሉቃስ 9:54፤ ደቀ መዛሙርቱም ያዕቆብና ዮሐንስ አይተው፦ “ጌታ ሆይ፥ ኤልያስ ደግሞ እንዳደረገ እሳት ከሰማይ ወርዶ ያጥፋቸው እንል ዘንድ ትወዳለህን?” የሚል ይሆናል:: ይህንን ፀሎት አይሰማም እንደዚህ የምንፀልይ አንሆንም በእርሱ ስንኖርና ቃሉ ሲሞላን:: እኛ በፍቅር የምንመላለስ ነው የምንሆነው:: ፀሎታችንን መቃኘት ይሁንልን:: እንደቃሉ እንፀልይ::
ፍሬ እንድናፈራ ለምን ተፈለገ? ድነናል አይበቃም?
ልጅ ወልደን ባያድግና ያው የሚታቀፍ ህፃን ቢሆን በሰውነቱም በቁመቱም ባያድግ ምን አለበት እንደማለት ነው:: ደግሞም ከተፈጥሮ ውጪ ነው:: ስለዚህም ፍሬ እያፈራን እየሱስን እየመሰልን እንድንመጣ አንድ ጊዜ ተወስኗል ይህም ብቻ ሳይሆን ብዙ ፍሬ ብታፈሩና ደቀ መዛሙርቴ ብትሆኑ በዚህ አባቴ ይከበራል። አሜን! በፍሬያችን አብ ስለሚከብር ነው::
አባት ሆይ ተመስገን በፍሬዬ አንተትከብራለህና:: በአንተ ውስጥ ነኝና ተመስገን:: አሜን!
ዮሐንስ 15: 9፤ አብ እንደ ወደደኝ እኔ ደግሞ ወደድኋችሁ፤ በፍቅሬ ኑሩ።
አብ ለልጁ ያለውን ፍቅር በአደባባይ ተናገረ “በእርሱ ደስ የሚለኝ የምወደው ልጄ ይህ ነው፤ እርሱን ስሙት፡” በማለት:: እየሱስም ለእኛ ያለውን ፍቅር የገለጠው ከአባቱ ፍቅር ጋር በማወዳደር ነው:: እንዴት ያለ ህብረት ውስጥ ነው የገባነው? ይህ እንደምን ያለ ነገር ነው?! እግዚአብሔር ፍቅር ነው በእርሱ መኖር በፍቅሩ ውስጥ መኖር ነው:: ፍቅር ማለት ማንነቱ ነው:: ይህ ፍቅር መጠን የለውም በቃሉ እንደሚል ከቅዱሳን ሁሉ ጋር ስፋቱና ርዝመቱ ከፍታውም ጥልቅነቱም ምን ያህል መሆኑን ለማስተዋል፥ ከመታወቅም የሚያልፈውን የክርስቶስን ፍቅር ለማወቅ ትበረቱ ዘንድ፥ እስከ እግዚአብሔርም ፍጹም ሙላት ደርሳችሁ ትሞሉ ዘንድ።
ከዚህ ፍቅር ውስጥ ምን ያወጣናል? ምንም!!!! በሮሜ 8:35፤ ከክርስቶስ ፍቅር ማን ይለየናል? መከራ፥ ወይስ ጭንቀት፥ ወይስ ስደት፥ ወይስ ራብ፥ ወይስ ራቁትነት፥ ወይስ ፍርሃት፥ ወይስ ሰይፍ ነውን? . . . በክርስቶስ ኢየሱስ በጌታችን ካለ ከእግዚአብሔር ፍቅር ሊለየን እንዳይችል ተረድቼአለሁ። ፍቅሩ ይህንን ሁሉ እንድናልፍ ያደርገናል:: ጠላት ግን በስጋት እንድንኖር ይፈልጋል አረ አንሰጋም ጌታ አስተማማኝ ነው:: ስሙ ይባረክ!!!
ጌታ ብዙ ባህሪያት ቢኖረውም የጋበዘን ግን በፍቅሩ እንድንኖር ነው በኃይሌ ኑሩ ወይም በጥበቤ ወይም በቅድስናዬ ወይም በሌላ አላለንም – ያለን በፍቅሬ ኑሩ ስርና መሰረታችሁ በፍቅር የጸና ይሁን ነው::
አባት ሆይ ስለወደድከኝ አመሰግንሃለሁ!! በፍቅርህም እንድኖር ስለምትፈልግ ተመስገን:: ይህንን ፍቅር እንዳውቅ ዕለት ዕለት እርዳኝ:: ከአእምሮ በላይ በሆነ ፍቅር ስለወደድከኝ አመሰግንሃለሁ! ሃሌሉያ
ዮሐንስ 15: 10-13
10፤ እኔ የአባቴን ትእዛዝ እንደ ጠበቅሁ በፍቅሩም እንደምኖር፥ ትእዛዜን ብትጠብቁ በፍቅሬ ትኖራላችሁ።
11፤ ደስታዬም በእናንተ እንዲሆን ደስታችሁም እንዲፈጸም ይህን ነግሬአችኋለሁ።
ጌታ እየሱስ የአባቱን ፈቃድ ፈጽሞ ታዘዘ እናም ምሳሌን ተወልን:: በእርሱ ደስ የሚለኝ ብሎ መስክሮለታል:: በ1 ዮሐንስ 2:5፤ ቃሉን ግን የሚጠብቅ ሁሉ በእርሱ የእግዚአብሔር ፍቅር በእውነት ተፈጽሞአል። በእርሱ እንዳለን በዚህ እናውቃለን ይላል::
በመታዘዙ ውስጥ በፍቅር መኖር አለ እንዲሁም ስንታዘዝ አብረን መኖር እንችላለን:: ትእዛዙን ስንጠብቅ በፍቅሩ እንኖራለን:: ትእዛዙንም የምንጠብቀው በጸጋው ነው::
ደስታዬ በእናንተ እንዲሆን አለን:: ደስታው ምንድነው? ትእዛዙን እንድንፈጽም: በእርሱ እንድንኖር እንዲሁም እርሱ እንደወደደን እንድንዋደድ ነው::
እየሱስ ፍቅሩን የገለጠበት መንገድ እራሱን በሞት አሳልፎ በመስጠት ነው:: እርሱም እንዳለን ነፍሱን ስለ ወዳጆቹ ከመስጠት ይልቅ ከዚህ የሚበልጥ ፍቅር ለማንም የለውም። እውነት ነው!! ማንም ነፍሱን እስከሚሰጥ ወዶኝ አያውቅም ከእየሱስ በቀር!!
አባት ሆይ እራስህን እስክትሰጥ ስለወደድከኝ አመሰግንሃለሁ:: እኔም እራሴን እሰጥሃለሁ አንተ በእኔ ኑር በወይኑ ግንድ ላይ መጣበቅ ይሁንልኝ!
ዮሐንስ 15: 14-15
14፤ እኔ ያዘዝኋችሁን ሁሉ ብታደርጉ እናንተ ወዳጆቼ ናችሁ።
15፤ ከእንግዲህ ወዲህ ባሮች አልላችሁም፤ ባርያ ጌታው የሚያደርገውን አያውቅምና፤ ወዳጆች ግን ብያችኋለሁ፥ ከአባቴ የሰማሁትን ሁሉ ለእናንተ አስታውቄአችኋለሁና።
ወዳጅነት እንዲቀጥል ሰው መስማማትና በአንድ ጎዳና ላይ መሆንንም ይጠይቃል አለበለዚያ ወዳጅ ብዬ ለማለት አልችልም:: እንደዚሁም እየሱስ ወዳጆቼ ናችሁ ሲለን ቅድሚያ ሁኔታን አስቀምጦ ነው:: እርሱም እኔ ያዘዝኋችሁን ሁሉ ብታደርጉ ያኔ ወዳጅ ነን አብረን መጏዝ እንችላለን ነው ያለን:: ያዘዝኳችሁን ብታደርጉ ሲል መታዘዝን አስተምሮን ነው የሄደው እርሱ አባቱን እስከ መጨረሻ ድረስ ፈቃድህ ይሁን ብሎ እስከመስቀል ሞት ድረስ ታዘዘ:: እኛ ግን የተጠየቅነው ጸጋውንና አብሮነቱንም ሰቶን ነውና ለመታዘዝ እራሳችንን ወደ እርሱ እናቅርብና ወዳጅ መሆናችንን እናስመስክር::
ከእንግዲህ ወዲህ ባሮች አልላችሁም ያለን ምክንያቱ ከአባቱ የሰማውን ሁሉ ስላሳወቀን ነው። ወዳጅ ያስባለን ሚስጥር የሚሆነውን ሁሉ ስለነገረና ስላሳወቀን ነው:: እንደዚሁም ደግሞ የእግዚአብሔር ሚስጥር የሆነውን እየሱስንና መንግስቱን እንድናውቅ የሰማይ አባት ስለገለጠልን ወዳጅ ተባልን:: ወዳጅ ብሎ እንዴት ያለ ክብርን ሰጠን:: የሰው ልጅ እኮ እራሱን ለሰይጣን ባርያ አድርጎ የጣለ ነበረ:: ዛሬ በክርስቶስ ቤዛነት መዋጀት ብቻ ሳይሆን ጠጋ አድርጎ ወዳጅ አለን:: ይህ ምን አይነት ፍቅር ነው?! እጁን ዘርግቶ ተቀበለን:: እንግዲህ እንደወዳጅ እንመላለስ::
አባት ሆይ የፍቅርህ ጥልቀት በቃልህ ውስጥ ሳየው ይገርማል ተመስገን:: ወዳጅ ብለህ ስላቀረብከኝ አመሰግንሃለሁ:: ትእዛዝህንም የምጠብቅበትና የምታዘዝበት ብቃት ሁሉ በጸጋህ ውስጥ ስለተሰጠኝ ተመስገን:: ባርነት የለም ወዳጅ ነኝና! ክበር ተመስገን!!
አሜን
ዮሐንስ 15: 16-17
16፤ እኔ መረጥኋችሁ እንጂ እናንተ አልመረጣችሁኝም፤ አብም በስሜ የምትለምኑትን ሁሉ እንዲሰጣችሁ፥ ልትሄዱና ፍሬ ልታፈሩ ፍሬአችሁም ሊኖር ሾምኋችሁ።
17፤ እርስ በርሳችሁ እንድትዋደዱ ይህን አዛችኋለሁ።”
ወዳጅ ብያችኃለሁ እያላቸው ቆይቶ ይህንን ጨመረበት እኔ መረጥኋችሁ እንጂ እናንተ አልመረጣችሁኝም:: እኛም አልመረጥነውም ነገር ግን በእርሱ ታስበን ዛሬ በቤቱ እየለመለምን አለን:: ከእኛ የሆነ የምንመካበት አንዳችም የለም ክብር ለንጉሱ ይሁን:: የተመረጥነውም ደግሞ ፍሬ ልናፈራ ነው ፍሬያችንም እንዲኖር እንጂ ጊዜያዊ እንዲሆን አይደለም::
አብም በስሜ የምትለምኑትን ሁሉ እንዲሰጣችሁ፥ እየሱስ በዝች ለሊት ከነሱ ይለያልና ከዚህ በኃላ በስሙ እንዲለምኑ ነው የሚነግራቸው:: በጸሎት ነው የምትለምኑትን ከዚህ በኃላ የምትቀበሉት እንጂ በአካል አብሯቸው እንዳልሆነ እንዲያውቁ ነው::
ልትሄዱና ፍሬ ልታፈሩ ፍሬአችሁም ሊኖር ሾምኋችሁ:: ሾምኳችሁ ሲባል መቼም እንደምናውቀው ባለስልጣን መሆ ን ማለት ነው:: ስለዚህ ፍሬ በማፍራት ላይ ተሹሙናል ማን ይሽረናል ታድያ? ፍሬ ማፍራት ግድ ነው ምክንያቱም የተሾምንበት ነውና:: የመንፈስ ፍሬ ግን ፍቅር፥ ደስታ፥ ሰላም፥ ትዕግሥት፥ ቸርነት፥ በጎነት፥ እምነት፣ የውሃት፥ ራስን መግዛት እነዚህን እናፈራለን:; ማፍራታችንን ብቻ ሳይሆን የሚፈልገው ፍሬያችንም አብሮን እንዲኖር ነው የሚፈለገው::
በተጨማሪም ደግሞ የሚያዘን እርስ በርሳችን እንድትዋደድ ነው። መቼም ሐዋርያቱ የመዋደድን ትእዛዝ ስንት ግዜ በጥቂት ደቂቃዎች ውስጥ እየደጋገመ ነገራቸው? ሊሄድ ነውና እንደለመዱት እኔ እበልጥ እኔ እበልጥ የሚለውን ልጅነት ትተው የነሱንም የሌላውንም አይን በአንድነት ወደ እየሱስ እንዲያደርጉ ነው:: መዋደድ ትእዛዝ ነው ደቀ መዝሙርም መሆናችን የሚታወቀው በዚህ ነውና::
አባት ሆይ ተመስገን ፍሬ ላፈራ ተሹሜአለሁና:: ይህ ፍሬ በእኔ ውስጥ ይንዠረገጋልና ወደ ህይወቴ መተህ ቅጠል ብቻ ሆኜ አልገኝምና ክበር:: አሁንም እራሴን የጽድቅ የጦር እቃ አድርጌ አቀርባለሁኝ:: አሜን
ዮሐንስ 15: 18-27
18፤ “ዓለም ቢጠላችሁ ከእናንተ በፊት እኔን እንደ ጠላኝ እወቁ።
23፤ እኔን የሚጠላ አባቴን ደግሞ ይጠላል።
26፤ ዳሩ ግን እኔ ከአብ ዘንድ የምልክላችሁ አጽናኝ እርሱም ከአብ የሚወጣ የእውነት መንፈስ በመጣ ጊዜ፥ እርሱ ስለ እኔ ይመሰክራል፤
ዓለም ለምን እየሱስን ጠላ ብለን ብንል በጽድቅ እየተመላለሰ ስለኮነናቸው ነው:: ክእርሱ በኃላ እኛን የጠላን ምክንያትም ያው ጌታ በእኛ ውስጥ መጥቶ መኖር ስለጀመረ ነው:: እየሱስን የሚጠላ ሁሉ አብንም ይጠላል የሚጠሉን ሰዎች ግን ምክንያታቸው ለእግዚአብሔር ቀንተን ነው የሚሉት:: በ2 ጢሞቴዎስ 3:12፤ በእውነትም በክርስቶስ ኢየሱስ እግዚአብሔርን እየመሰሉ ሊኖሩ የሚወዱ ሁሉ ይሰደዳሉ። ቃሉ በብዙ አስረግጦ የሚነግረን መገፋት እንዳለ ነው እርሱን ከመሰልን:: ስለዚህ እንበርታ!
በዚህ መገፋት ውስጥ ግን የሚመሰክረው ማነው? እየሱስ እንዳለን:- ዳሩ ግን እኔ ከአብ ዘንድ የምልክላችሁ አጽናኝ እርሱም ከአብ የሚወጣ የእውነት መንፈስ በመጣ ጊዜ፥ እርሱ ስለ እኔ ይመሰክራል:: ብሎናል:: አሜን ይመስክርለት:: የምንገፋውና የምንጠላው ምንም ስላደረግን ሳይሆን ጌታን ወደ ህይወታችን ስለጋበዝን ነውና ምንም አይምሰለን:: በተጨማሪም ከመንፈስ ቅዱስ ጋር እናንተም ደግሞ ከመጀመሪያ ከእኔ ጋር ኖራችኋልና ትመሰክራላችሁ አላቸው:: እኛም ከመዳናችን ጀምሮ ከእኛ ጋር ለነበረው ጌታ ከመንፈስ ቅዱስ ጋር እየተባበርን እንመሰክርለታለን::
አባት ሆይ እርሱ ስለ እኔ ይመሰክራል ብለሃልና መንፈስ ቅዱስእነሆኝ ህይወቴ ስለእየሱስ መስክር እኔም ደስ እያለኝእተባበራለሁ! እንዳልክ እንደፈቃድህ ይሁን! አሜን!
ዮሐንስ 16:1-7
1፤ “እንዳትሰናከሉ ይህን ተናግሬአችኋለሁ።
7፤ እኔ ግን እውነት እነግራችኋለሁ፤ እኔ እንድሄድ ይሻላችኋል። እኔ ባልሄድ አጽናኙ ወደ እናንተ አይመጣምና፤ እኔ ብሄድ ግን እርሱን እልክላችኋለሁ።
ይህንን ሁሉ ቀድሞ የሚነግራቸው ሲሆን እንዳይደናገጡ ነው:: ነገር ግን ጊዜው ሲደርስ እኔ እንደ ነገርኋችሁ ታስቡ ዘንድ ይህን ተናግሬአችኋለሁ። ከእንናንተም ጋር ስለ ነበርሁ በመጀመሪያ ይህን አልነገርኋችሁም። ከእነርሱ ጋር እያለ የአይሁድ ክስና ማሳደድ ሁሉ በእርሱ ላይ ነበረ የሚሳደደውም እርሱ ነበረ አሁን ግን እርሱ ሲሄድ ያ ሁሉ ቁጣ ወደ እነርሱ እንደሚዞር ስለሚያውቅ ነው:: ዓለም ጌታችንን ትጠላለች ምክንያቱም መንግስቱ ከዚህ አይደለምና የዚህ ዓለም ገዢ ዲያቢሎስ ነው አንዳችም በእኔ ላይ የለውም አለን ጌታ:: እርሱ ነው ይህንን ሁሉ ማዕበል የሚያስነሳው የሚውጠውን ፈልጎ ይዞረን የለም እድል እስኪያገኝ?! ነገር ግን ጌታ የሰጠው መፍትሄ ምንድነው? ከምዕራፍ 14 ጀምሮ እያስተዋወቃቸው ያለው የምሽቱን ሸክም ሁሉ የሚወስድ አጽናኝ አለ እርሱም መንፈስ ቅዱስ ነው::
ሌላ ጥያቄ መጠየቅ እስከማይችሉ በኃዘን ውስጥ ናቸው:: እየሱስ የሚለው የመለየቱና የመሄዱ ነገር ገብቷቸዋል :: እነሱ ያዘኑት እንዳይለያቸው እሱ ደግሞ የሚላቸው እኔ እንድሄድ ይሻላችኋል ነው:: እርሱ የሚሻል ነው ብሎ ነው የሚለው:: ለነርሱ የተመቻቸው ከእየሱስ ጋር መኖር እርሱ ግን እኔ ባልሄድ አጽናኙ ወደ እናንተ አይመጣምና፤ እኔ ብሄድ ግን እርሱን እልክላችኋለሁ። ወደ እኛ የተላከው ይህ መንፈስ ቅዱስ የሚረዳን ነው በበአድ ምድር በእንግድነት ስንኖር እየሱስን እያከበረ እኛን እያጽናና ያራምደናል:: የዓለም ነገር እየከፋ ነው የሚሄደው አናሻሽለውም ፃድቁም ፅድቁን ኃጥያተኛውም ኃጥያትን ማድረጉን ይቀጥላል:: እኛ ግን መብራታችን በርቶ እንመላለስ የዓለምን ማሳደድ ፈርተን እየሱስን አንሸሽገው::
አባት ሆይ ለዘላለም ከእኔ ጋር እንዲኖር ወደ ህይወቴ የላከው መንፈስ ቅዱስ በሁሉ የሚረዳኝ ነውና ተመስገን::
ወደ እውነት የምትመራኝ
ስደክም የምታበረታኝ
ሳዝን የምታጽናናኝ
ስሳደን በደስታ የምትሞላኝ
ኃዘንን ከእኔ የምትገፍ
አእምሮን የሚያልፍ ሰላም የምትሞላኝ
እየሱስን በእኔ ውስጥ የምትገልጠው
ስንቱን ልጥቀስ አባ?!
ጌታ መንፈስ ቅዱስ ተባረክ!
አንተ እግዚአብሔር ነህ!
አሁንም እኔነቴ ያንተ ነውና ክበር::
አሜን!
ዮሐንስ 16: 8-11
8፤ እርሱም መጥቶ ስለ ኃጢአት ስለ ጽድቅም ስለ ፍርድም ዓለምን ይወቅሳል፤
9-10፤ ስለ ኃጢአት፥ በእኔ ስለማያምኑ ነው፤ ስለ ጽድቅም፥ ወደ አብ ስለምሄድ ከዚህም በኋላ ስለማታዩኝ ነው፤
11፤ ስለ ፍርድም፥ የዚህ ዓለም ገዥ ስለ ተፈረደበት ነው።
እየሱስ ፍንትው አድርጎ የመንፈስ ቅዱስን ስራ እየነገረን ነው:: መንፈስ ቅዱስ በብዙ መልክ ተገልጧል በመጽሃፍ ቅዱስ ነገር ግን እነዛን ምሳሌዎቹን ነው ማለት ግን አይደለም:: ንፋስ ወይም እርግብ ወይም ዘይት ወይም ደግሞ እሳት አይደለም:: በእርግጥ በነዚህ መልኩ ተገልጧል እርሱ ግን የፈጠረን እግዚአብሔር አምላካችን ነው:: ሃሌሉያ!!!
እርሱ መጥቶ ነው ስራውን የሚሰራው:: ግን የት ነው የሚመጣው? በእኛ በዳነው ውስጥ ይመጣና ይገለገላል:: ስራውም:-
1. ስለ ኃጢአት፥ በእኔ ስለማያምኑ ይወቅሳል:: ይህ የእርሱ ስራ እንጂ የእኛ አይደለም:: እኛ የተባልነው ምስክሮቼ ሁኑ ነው:: ስለኃጥያት መውቀስ የእርሱ ስራ ነውና ያለስራችን ያልተባልነውን እንዳናደርግ:: በፍቅር እውነትን መግለጥ እንጂ የሰውን ልብ እያሻከሩ ከጌታ ማራቅ አይደለም ስራችን:: የሚያደርገውም በእየሱስ ሰው እንዲያምን ሌላ መውጫ እንደሌለ ማሳየት ነው:: እርሱ ልብን ካልነካ ምን ብንጥር ለውጥ የለም:: መውቀስን ለእርሱ እንተው እኛ ግን እየሱስ አዳነኝ ብለን እንደዛች ሳምራዊት ሴት ወደ እርሱ እናምጣ::
2. ስለ ጽድቅም፥ ወደ አብ ስለምሄድ ከዚህም በኋላ ስለማታዩኝ ነው:: እየሱስ ክርስቶስ በምድር ተመላልሶ የአባቱን ፈቃድ አድርጎ በእርሱ ደስ የሚለኝ የምወደው ልጄ ተብሎ ተመስክሮለት ፥ በመስቀል ስለ እኛ እንጂ ስለራሱ ምንም መስወአት ማቅረብ ሳያስፈልገው ህይወቱን ሰጥቶ ፥ በሶተኛው ቀን በትንሳኤው ኃይል ተነስቶ ፥ በአብ ቀኝ የተቀመጠ ጻድቅ ጌታ ነው:: ጻድቅና እንከን የሌለው እጹብ ድንቅ መሆኑን አስመስክሯል:: ማንም በአንዳች አይከሰውም ኃጥያት አልተገኘበትም ጻድቅ ጌታ ነው:: አንድ ጊዝ ስለእኛ ደሙን እያንጠባጠበ ወደ አብ ገባ!!! ደግሞ መቶ ይህንን ማድረግ አላስፈለገውም! ስለዚህም ደግመን በምድር ሲመላለስ ስጋ ለብሶ አናየውም አንድ ጊዜ ተ ፈ ጸ መ!!!! ብሎ ጨረሰው!!! ለስሙ ክብር ይሁን!!!!
3. ስለ ፍርድም፥ የዚህ ዓለም ገዥ ስለ ተፈረደበት ነው:: የዚህ ዓለም ገዢ አንዳች የለውም በእኔ ላይአለን:: እየሱስ መጥቶ አዳም ያስረከበውን ሁሉ ከሰይጣን ላይ ተረከበ:: በሰማይና በምድር ሙሉ ስልጣን ተሰጠኝ አለ:: ለአለቅነትና ለሥልጣንም ሁሉ ራስ በሆነ በእርሱ ሆናችሁ ተሞልታችኋል። እርሱ የሁሉ ራስ ሆነ ይህንንም እያዞረ አሳየ:: የሞትንና የሲኦልን ቁልፍ ተቀበለ:: በዚህ ዓለም ብቻ ሳይሆን በሚመጣውም ራስ እየሱስ ነው::
ገዢና አለቃ
አልፋና ኦሜመጀመርያና መጨረሻ
እየሱስ ቻ ነው!!!!
አሜን ሃሌሉያ!
አባት ሆይ አንዳች ሳታስቀር ተፈጸመ ብለህ ሁሉን ጨረስከው! ድል በድል አደረከን ዛሬም በእኛ ውስጥ የምትሰራ አንተ ነህና ክበር የአንተን ስራ እንዳንጋፋ ነገርግን እራሳችንን ለአንተ እንሰጣለን:: ክበር እየሱስ!!!
ዮሐንስ 16: 12-15
12፤ የምነግራችሁ ገና ብዙ አለኝ፥ ነገር ግን አሁን ልትሸከሙት አትችሉም። 13፤ ግን እርሱ የእውነት መንፈስ በመጣ ጊዜ ወደ እውነት ሁሉ ይመራችኋል፤ የሚሰማውን ሁሉ ይናገራል እንጂ ከራሱ አይነግርምና፤ የሚመጣውንም ይነግራችኋል። 14፤ እርሱ ያከብረኛል፥ ለእኔ ካለኝ ወስዶ ይነግራችኋልና።
ሐዋርያት ሊሸከሙ ስላልቻሉ ሊነግራቸው የሚፈልገውን ያህል አልነገራቸውም:: በዚህ ምሽት ተናጋሪው እየሱስ ነው በኃጥያተኞች እጅ ተላልፎ ለመሰጠት ሰዓታት ብቻ ነው የነበረውና ያለውን ሁሉ እንደፈለገው ሊሰጣቸው አልቻለምና ከዚህ ከቆመበት የሚቀጥለውን እያስተዋወቃቸው ነው::
መንፈስ ቅዱስ ሐዋርያትን ተጠቅሞ የአዲስ ኪዳን ክፍሎችን ባይጽፍልን ኖሮ ብዙ ክፍተት ይኖር ነበረ:: አንዱን ምሳሌ ባነሳ:- አህዛብ አብረን እንደምንወርስ አላወቁም ነበር ለእስራኤል ብቻ ሳይሆን ለአዳም ዘር ሁሉ መምጣቱን አልተረዱም ነበረ:: መንፈስ ቅዱስ ባይረዳቸው ባልደረሱን ነበር::
ይህንን ሁሉ ትምህርት ሲያስተምር የነበሩት ማትዮስና ማርቆስ (የተቀሩት ወንጌላት) ይህንን ጥልቅ ትምህርት አልፃፉትም:: ዮሐንስም በመንፈስ እየተነዳ ባይጽፍልን ይህንን ሁሉ አናውቅም ነበረ:: ድንቅ ነው!
የእውነት መንፈስ በመጣ ጊዜ:-
1. ወደ እውነት ሁሉ ይመራችኋል፤ እውነት ማነው? እውነትና መንገድ ህይወትም እየሱስ ነውና ወደ እርሱ ነው የሚመራን::
2. የሚሰማውን ሁሉ ይናገራል እንጂ ከራሱ አይነግርምና፤ እየሱስ የአባቱ ፈቃድ መብሉ ነበረ አሁንም መንፈስ ቅዱስ ከወልድ የሰማውን ይነግረናል::
3. የሚመጣውንም ይነግራችኋል:- እርሱ እግዚአብሔር ነውና ከጅማሬ ፍፃሜን ያያል ሳያውቀው የሚሆን ነገር የለም:: ለእርሱ ሰርፕራይዝ የለም::
4. እርሱ ያከብረኛል፥ መንፈስ ቅዱስ ግቡ ሁሉ እየሱስን ማግነን ነው:: የእኛም ስራ ይኸው ነው ምክንያቱም መንፈስ ቅዱስ በእኛ ውስጥ እየሰራ ነው የሚያገነውና::
5. ለእኔ ካለኝ ወስዶ ይነግራችኋልና:- የምናመልከው አንድ አምላክ ነው መንፈስ ቅዱስ በኃላ ስለመጣ ስራው ያነሰ አይምሰለን ለእኛ የተገለጠው ስራውን ከእየሱስ ሲቀበል ስለሆነ ነው:: ለኔ ካለኝ ሲል ሌላ ማንነት አንፈልግ አምላካችን አንድ ነው::
ዮሐንስ 16:15፤ ለአብ ያለው ሁሉ የእኔ ነው፤ ስለዚህ፦ ‘ለእኔ ካለኝ ወስዶ ይነግራችኋል፡’ አልሁ።”
አባት ሆይ እየሱስን ልታገነው መተሃልና በእኔ ውስጥ አግንነው::
አክብረውም ፤ የሚመጣውንም አሳውቀኝ ፤ ወደ እውነትም ምራኝ ፤ የምትለኝንም መስማት ይሁንልኝ ልትሸከሚ አትችይም አልባል:: አሜን
ዮሐንስ 16: 16-24
19፤ ኢየሱስም ሊጠይቁት እንደ ወደዱ አውቆ፡ እንዲህ አላቸው፦ “ጥቂት ጊዜ አለ፥ አታዩኝምም፤ ደግሞም ጥቂት ጊዜ አለ፥ ታዩኛላችሁ፡ ስላልሁ፥ ስለዚህ እርስ በርሳችሁ ትመራመራላችሁን?
ከላይ ሲነግራቸው የመጣው ስለመንፈስ ቅዱስ ነበረ:: ያለ ምሳሌ በቀጥታ እየነገራቸውና እያስተማራቸው ቢሆንም አብዛኛው ሃሳብ አልገባቸውም:: ለመታሰርና ወደ መስቀል ለመሄድ ሰዓታት ነው የቀረው እነሱ ግን አልገባቸውም::
ጥቂት ጊዜ አለ፥ አታዩኝምም፤ ደግሞም ጥቂት ጊዜ አለ፥ ታዩኛላችሁ ሲላቸው ምሳሌያዊ ንግግር መሰላቸውና እንደልማዳቸው እንዲያብራራላቸው ፈልገው እርስ በእርሳቸው ሲጠያየቁ ገብቶት ሊያብራራላቸው ጀመረ:: ነገር ግን እየመጣ ያለው ነገር ምንም ማብራርያ አያስፈልገውም:: አልገባቸውምና ከሴት ምጥ ጋር አመሳስሎ ነገራቸው ዓለም ደስ ይለዋል እነሱ ግን ያዝናሉ:: ምክንያቱም ይህ ሊፈጸም ያለ ነገር እንጂ ምሳሌ አልነበረምና ከዚህ በላይ መብራራት አይችልም:: በሃዘን ውስጥ እንደሚሆኑ ከዛም ደግሞ ሲያዩት በደስታ እንደሚሆኑ ታላቁን ሚስጥር ትንሳኤን ነገራቸው:: ገብቷቸዋል? በፍጹም ለዚህም ነው ከያሉበት የሰበሰባቸው ከትንሳኤው በኃላ:: ይነሳል ብለው አልጠበቁም ሁሉን ትተው ሄዱ:: እነርሱማ የሚጠብቁት በተለያየ የእስራኤል መንግስት ስልጣን ላይ መቀመጥ ነበረ እንጂ ሞቱን አይደለም::
በዚያን ቀንም ከእኔ አንዳች አትለምኑም። እውነት እውነት እላችኋለሁ፥ አብ በስሜ የምትለምኑትን ሁሉ ይሰጣችኋል። ይህ በብሉይ ኪዳን ውስጥ ለሚኖር ሰው ከባድ ነው:: ካህን ጋር ሳይሄዱ መስዋአትን ሳያቀርቡ ያለ መካከለኛ ወደ ቅዱሱ እግዚአብሔር መቅረብ የማይመስል ነገር ነው:: በእየሱስ የመስቀል ስራ የእግዚአብሔር በግ ታርዶ ይህ ተቻለ:: ዛሬ በስሙ አብን እንለምናለን እርሱም ይመልሳል:: ሃሌሉያ!
እስከ አሁን በስሜ ምንም አልለመናችሁም፤ ደስታችሁ ፍጹም እንዲሆን ለምኑ ትቀበሉማላችሁ። እየሱስ እብሯቸው ስለነበረ ጥያቄያቸውን በሌላ አባባል ጸሎታቸውን ወደ እርሱ ነበረ የሚያመጡት እርሱም ጸልዮ የጠየቁትን ይሰጣቸዋል ይህንን ሊቀይረው ነው:: አሁን በስሙ ለምነን እንቀበላለን:: ይህ ስም አብ ያከበረውና ሁሉ የሚገዙለት ነው:: ደስታችሁ ፍጹም እንዲሆን ለምኑ ትቀበሉማላችሁ! ደስታችን ፍጹም እንዲሆን የሚወድ ጌታ ስሙይባረክ!
አባት ሆይ ተመስገን ይህንን የከበረ ስም ስለሰጠኸኝ:: ስምህን እባርካለሁ! ስምህ ይቀደስ! ደስታዬን በስምህ ለምኜ በመቀበል አገኛለሁ:: እኔ ወላጅ የሌለኝ አይደለሁኝም አባት አለኸልኝ በሰማይ የምትኖር እኔም ውስጥ ለመኖር የመጣህ ጌታ ተባረክ!! ላትተውኝ የወደድከኝ የወለድከኝ ጌታ ተወደስልኝ!!! አሜን
ዮሐንስ 16:25-28
26፤ በዚያን ቀን በስሜ ትለምናላችሁ፤ እኔም ስለ እናንተ አብን እንድለምን የምላችሁ አይደለሁም፤ 27፤ እናንተ ስለ ወደዳችሁኝ ከእግዚአብሔርም ዘንድ እኔ እንደ ወጣሁ ስላመናችሁ አብ እርሱ ራሱ ይወዳችኋልና። 28፤ ከአብ ወጥቼ ወደ ዓለም መጥቻለሁ፤ ደግሞ ዓለምን እተወዋለሁ ወደ አብም እሄዳለሁ።
በምሳሌ ሳይሆን በግልጥ እየነገራቸው ነው ግን ጥቂት ጊዜ አለኝ ወይም በዚያን ቀን ያለውን በውል አልተረዱም:: ጥቂት ያለው ሰዓታትን ነበረና ያቺ ቀን መጥታ በራሳቸው የሚለምኑበት ቀን አለና የሚያስፈልጋቸውን ሁሉ እውቀት እየሰጣቸው ነው:: ከልባችሁ አይታወክ ጀምሮ ብቻቸውን እንደማይሆኑና መንፈስ ቅዱስ እንደሚመጣላቸው እንዲሁም ስለተሰጣቸው ስም ይህም ስም አብ መልስ የሚሰጥበት እንደሆነና ብዙ ነገሮችን እያስተማረ ነው::
በዚያን ቀን በስሜ ትለምናላችሁ፤ እኔም ስለ እናንተ አብን እንድለምን የምላችሁ አይደለሁም:: ሐዋርያቱ የለመዱት ነገር ጉዳዮችን ሁሉ ወደ እርሱ ያመጣሉ እርሱም አባቱን ይለምናል ይፈጸማል:: እያላቸው ያለው ይህ ግን አሁን ሊቀየር ነው በስሜ አብን ለምናችሁ ትቀበላላችሁ:: እኔ አለምንላችሁም አሁን ወደ አብ ለመግባት ድፍረት አላችሁ ከኃጥያት ነጽታችኃልና በስሜ ለምናችሁ ተቀበሉ እያለ ነው:: ስሜን ተጠቀሙ ሲላቸው ከነሙሉ ማዕረጉ ነው የሰጣቸው ልክ እየሱስ እንደሚለምን ነው አብ የሚያየው በስሙ ስንቀርብ:: ሃሌሉያ!!
አብ ገና ኃጥያተኞች ሳለን ወደደን:: ወላጁን የሚወድ ልጁን ደግሞ ይወዳል::
ከአብ ወጥቼ ወደ ዓለም መጥቻለሁ፤ ደግሞ ዓለምን እተወዋለሁ ወደ አብም እሄዳለሁ አለን። አሜን! በአብ ቀኝ በክብር የተቀመጠው ጌታ የተባረከ ይሁን!
አባት ሆይ ወደፊትህ ቀርቤ በእየሱስ ክርስቶስ ስም ለምኜ እቀበል ዘንድ ፈቃድህ ስለሆነ ተመስገን!! ስለዚህ ስለከበረው ስምህ አመሰግናለሁ! አሜን!!
ዮሐንስ 16: 29-33
31፤ ኢየሱስም እንዲህ ብሎ መለሰላቸው፦ “አሁን ታምናላችሁን? 32፤ እነሆ፥ እያንዳንዳችሁ ወደ ቤት የምትበታተኑበት እኔንም ለብቻዬ የምትተዉበት ሰዓት ይመጣል፥ አሁንም ደርሶአል፤ ነገር ግን አብ ከእኔ ጋር ስለ ሆነ ብቻዬን አይደለሁም። 33፤ በእኔ ሳላችሁ ሰላም እንዲሆንላችሁ ይህን ተናግሬአችኋለሁ። በዓለም ሳላችሁ መከራ አለባችሁ፤ ነገር ግን አይዞአችሁ፤ እኔ ዓለምን አሸንፌዋለሁ።”
የሐዋርያቱ ዓይን እየተከፈተ ነበረና ሁሉን እንድታውቅ ማንምም ሊጠይቅህ እንዳትፈልግ አሁን እናውቃለን፤ ስለዚህ ከእግዚአብሔር እንደ ወጣህ እናምናለን፡አሉት። መልሱ ግን አሁን ታምናላችሁን? ነበረ ምክንያቱም ከጥቂት ሰዓት በኃላ የሚሆነውን ያውቅ ነበረና በመከራ ውስጥ ጥለውት እንደሚበታተኑ ነገራቸው:: በሰላም ተቀምጠው እያሉ ይህንን ማለቱ ያስከፋል ግን እርሱ በደንብ ያውቃቸዋል ስለዚህም ተፈጽሞ አየነው::
ጥለውት እንደሚሄዱ አውቆ እራሳቸውን እንዳይወቅሱ ካልሆነ በቀር ለምን አብ ከእኔ ጋር ስለ ሆነ ብቻዬን አይደለሁም አላቸው:: ትተውኛላችሁ ይበቃ ነበረ:: በዙሪያችን ሰዎች እስከተወሰነ ደረጃ ነው አብረውን መጏዝ የሚችሉትና ሰውን አንታዘብ እንዘንም ጌታ እራሱ ለብቻ መተው ምን ማለት እንደሆነ ስለሚያውቅ ስለተፈተነበት አብሮን ይሆናል:: እኔና እርሱ ብቻ የምንሆንባቸው ጊዜያትአሉ:: ሁሉ ቢሄድ እርሱ ግን አይሄድም:: እየሱስ የአባቱን ፈቃድ ብቻውን አከናወነ እናንግስህ ያሉት ትተውት አይሁንብህ ያሉትም ያመናቸው ጥቂት ሐዋርያትም ትተውት ብቻውን ሆኖም ወደ ዓላማው ሄደ እንጂ ምክንያት አድርጎ ከመጣበት ዓላማ አልተዛነፈም:: ህይወቱን ለእኛ ሰጠ!
ዓለም ሁሉ ፊቱን እንደሚያዞርበትና ብቻውን እንደሚሆን እያወቀ በእኔ ሳላችሁ ሰላም እንዲሆንላችሁ ይህን ተናግሬአችኋለሁ ይላቸዋል:: በዚህ ውስጥ ሆኖም ሰላምን ይሰጣል:: ይህም ብቻ አይደለም በዓለም ሳላችሁ መከራ አለባችሁ፤ ነገር ግን አይዞአችሁ፤ በሰውኛ ግን ተላልፎ መሰጠት መታሰር መደብደብ መሰቀልና መሞት ድል አይመስልም መሸነፍ እንጂ:: እየሱስ ግን የሚመጣውን እያየ አይዟችሁ አላቸው:: ምን አይነት ፍቅር ነው!! በቁጣ መሞላትና እነርሱን ልክ ልካቸውን መንገር ነበረ ለእኛ የሚቀናን እርሱ ግን በስጋ መጋፈጥ እንደማይችሉ መንፈሱ ግን ከላይ ሲወርድባቸው አንበሳ እንደሚያደርጋቸው አውቆ ታገሰ አይዟችሁ አላቸው:: በድካም ላሉት እንፀልይ እንጂ አንፍረድ እርሱ አንስቶ እንደገና ሊጠቀምባቸው ይችላልና::
እኔ ዓለምን አሸንፌዋለሁ ሲላቸው ገና ምንም አልተፈጠረም ነበር:: በህይወቱ ጠላትን ድል ነሳ እርሱ አንዳች ኃጥያት አልተገኘበትም ንፁ የእግዚአብሔር በግ:: በሞቱም ድልነሳ በትንሳኤውም ድል ነሳ! ድል ለነሳው በግ ክብር ይሁን!
አባት ሆይ ይህንን ድል እንዳጣጥም ስለረዳኸኝ ተመስገን በዓለም መከራ ቢኖርም ሁሉን ድል አድርገህልኛልና ድል እየነሳሁ በሰላም ተሞልቼ እመላለሳለሁ:: ሃሉሉያ!
አሜን!
ዮሐንስ 17:1-2
ኢየሱስም ይህን ተናግሮ ወደ ሰማይ ዓይኖቹን አነሣና እንዲህ አለ፦ “አባት ሆይ፥ ሰዓቱ ደርሶአል፤ ልጅህ ያከብርህ ዘንድ፥ በሥጋም ሁሉ ላይ ሥልጣን እንደ ሰጠኸው፥ ለሰጠኸው ሁሉ የዘላለምን ሕይወት ይሰጣቸው ዘንድ ልጅህን አክብረው።
እየሱስ ለራሱ ከቁ 1-5 ድረስ ፀለየ:: ፀሎቱንም አባት ሆይ እያለ እየተጣራ ይፀልይ ነበረ:: በፀሎቱም ልጅህ እያለ እራሱን ይጠራል:: በደህንነታችን ስራ ውስጥ አብንና ወልድን ያሳየናል:: አብ ፀሎቱን በዚህ ስፍራ ባይሰማው ኖሮ ደህንነት በሌለ:: እራሱን በአብ ፊት እየቀደሰና የሌላውን ኃጥያት እየተሸከመ ያለበት ሰዓት ነው:: ልክ በብሉይ ኪዳን ካህናት የሰውየውን ኃጥያት ወደ በሚታረደው እንሰሳ አናት ላይ ጭነው እንደሚያደርጉት አይነት ማለት ነው:: መስዋትነቱ የጀመረው እዚህ ጋር ነው::
በፀሎቱም ልጅህ ሊያከብርህ ሰዓቱ ደርሷል አለ:: መቼም ይህንን ፀሎት ለሚሰማ ወደ ሞት በመሄድ ነው አባቱን የሚያከብረው ብሎ መገመት አይቻልም:: ግን እውነቱ እርሱ ነው በሞቱ ሊያከብረው ነው:: ነገር ግን ልጅህ ያከብርህ ዘንድ አክብረው ነው እያለ ያለው:: ይህም ማለት እርዳኝ በዚህ ሞት አከብርህ ዘንድ ምክንያቱም ከዚህ ሞት በኃላ የዘላለምን ሕይወት የሚሰጠን! የተገዛነው በከበረው በእየሱስ ህይወት መስዋትነት ነው!
በዚህ ሞት ውስጥ አብ እየሱስን ሲያከብረው እየሱስ በሥጋም ሁሉ ላይ ስልጣንን ይቀበላል በዚህም ስልጣን አብ ለሰጠኸው ሁሉ የዘላለምን ሕይወት ይሰጣቸዋል:: አብ ከሳበው በቀር ወደ እኔ የሚመጣ የለም ብሎናል::
አባት ሆይ የዘላለምን ህይወት እንድናገኝ እየሱስን ስላከበርከውና መስዋእቱን ስለተቀበልክ ተመስገን:: በከበረው በልጅህ መስዋትነት የራስህ ስላደረከኝ አባ አባት ብዬ እንድጠራህ መንፈስህን ስለሰኸኝ አመሰግንሃለሁ:: ማንም በራሱ አይበረታምና እኔም ዛሬ ፈቃድህን እንድታዘዝና እንዳከብርህ ፀጋህን አብዛልኝ እርዳኝም! አሜን!
እየሱስ ሰዓቱ ደርሷልና ልጅህን አክብር እያለ ወደ አባቱ ቀና ብሎ ሲፀልይ ይህ ሰዓት ምን የሚሆንበት ነው ማለት ያስፈልጋል::
ሁለቱ መንግስቶች የሚለይላቸው ጊዜ ነው ውድድር የሚገቡ ናቸው ለማለት ሳይሆን ሰይጣን በድለላው ሄዋንንና አስቶ አዳምን ከነዘሩ በስሩ አድርጎ ነበረና ነው::
የእባቡ ራስ የሚቀጠቀጥበት ጊዜ ነው::
ሙሴ እንደሰቀለው የናስ እባብ ያዮት ሁሉ ከተነደፉበት መርዝ ነፃ እንደሆኑ እንዲሁም ሰይጣን የነደፈው ሁሉ የሰው ልጅ ነፃ የሚወጣበት ሰዓት ነው::
እየሱስ ከፍ ከፍ ሊልና ምርኮን ሊካፈል ጊዜው ነው::
አለቆች ስልጣናት ጌትነት ሁሉ መበርከክያቸው ሰዓት ነው::
ትንሳሳኤም ሊሆን ነው!!!
የሲኦልና የሞት ቁልፍም ሊነጥቅ ጊዜው ነው::
ሞት ሆይ መውጊያህ የታል ሊባል ጊዜው ነው::
በሰማይና በምድር ስልጣን ተሰጠኝ ሊል ጊዜው ነው!
እርሱ ሲከብር የእግዚአብሔር መንፈስ በህዝቡ ሊመጣና ሊያትም እንዲሁም ድልን ሊሰጥ ጊዜው ነው::
ይህንን ሁሉ ጦርነት ለመጀመር እየሱስ ሰዓቱ ደርሷል አለ ከዛ በፊት ግን አንዳች ሊያደርጉበት ወይንም ሊይዙት እንዳልቻሉ ቃሉ ይነግረናል አሁን ግን ሰዓቱ ነውና ለኃጥያተኞች ተላልፎ ለመሰጠት ወደ ቀጠሮው ቦታ እየሄደ ነው:: ልጅህን አክብር ብሎ ለሰይጣን ፈተናና ሽንገላ ያልተረታውን ማንነቱን እያቀረበ:: ሰይጣን ይህንን ማንነቱን በአዳም እንደለመደው ለመደለልና ለመውሰ ድ ሞክሯል የእግዚአብሔር ልጅ ከሆንክ ይህንንና ያንን አድርግ ደግሞም ወድቀህ ብትሰግድልኝ እያለ ፈትኖት አልተሳካለትም አልተጠመደም ስለዚህ ይህ የመጨረሻ ጦርነት ሊጀመር ነው::
እራሱን ለመስዋትነት ሲያቀርብ እንደ ካህንም እንደ እግዚአብሔር በግም ነው እየሆነ ያለው:: አብረሃም ከልጁ ጋር ወደ ተራራው ያደረጉትን ጉዞ ያስታውሰኛል ይስሃቅ የሚሰዋው የታለ ብሎ ሲጠይቅ እግዚአብሔር ያዘጋጃል የተባለው በግ እየተዘጋጀ ነው:: በብሉይ ኪዳን እንከን የሌለው እንደሆነ የሚቀርበው መስዋእት ካህኑ ያረጋግጣል እየሱስም እንከን የሌለው በብዙ ተፈትኖ ያለፈ ነውና አክብረኝ እያለ እንከን የለሽ ምመስዋት ሆኖ ለመቅረብ ፀለየ::
ዋዉ!!! አባት ሆይ ይህ ሁሉ ለሰው ልጅ?! ምን እንላለን ተመስገን!!! ፍቅርህ እንዴት ብዙ ነው!!
ዛሬም የቀደስከውንና በመንፈስህ ያተምከውን እኔነቴን በፊትህ የጽድቅ የጦር እቃ አድርጌ አቀርባለሁ:: ይህ ማንነቴ የአንተ ነው በዋጋ የተገዛ እነሆኝ አባት ሆይ ተጠቀምብኝ ብዙዎችን ከጠላት መንጋጋና ከጨለማው ስልጣን ለማውጣት የዳነውንም ህዝብህን ለማበርታት ተጠቀምብኝ!!!! ባከበርከው በልጅህ በእየሱስ ክርስቶስ ስም! አሜን
ዮሐንስ 17:3፤ እውነተኛ አምላክ ብቻ የሆንህ አንተን የላክኸውንም ኢየሱስ ክርስቶስን ያውቁ ዘንድ ይህች የዘላለም ሕይወት ናት።
የዘላለም ህይወት ለሁሉም የተሰጠ ነው ሰው ለዘላለም የሚኖር ፍጥረት ነው የሚለየው ዘላለሙን የት ያሳልፋል የሚለው ላይ ነው::
እየሱስ የሚለን:- የዘላለም ህይወት ማለት ሁለት ነገር ማወቅ ነው:-
1. እውነተኛ አምላክ ብቻ የሆንህ አንተን
2. የላክኸውንም ኢየሱስ ክርስቶስን
እግዚአብሔር ልጁን እንዲልክ እየሱስም ህይወቱን እንዲሰጥ ያደረገው ፍቅር ነው:: በምድር ሲመላለስ አላወቁትም ይህንን ጌታ:: እኛ ግን በስብከት ሞኝነት አምነን በመንፈስ ቅዱስ እራሱን ገልጦን አወቅነው:: ወደ እርሱ ሮጠን ተሸሸግን!
ዮሐንስ 3:16፤ በእርሱ የሚያምን ሁሉ የዘላለም ሕይወት እንዲኖረው እንጂ እንዳይጠፋ እግዚአብሔር አንድያ ልጁን እስኪሰጥ ድረስ ዓለሙን እንዲሁ ወዶአልና።
አባት ሆይ ስለወደድከን እንዳንጠፋ አድነህ እራስህን አሳወከን:: አንተን ማወቅ ስለሰጠኸኝ ተመስገን:: ሃሌሉያ!
ዮሐንስ 17: 4-5
4፤ እኔ ላደርገው የሰጠኸኝን ሥራ ፈጽሜ በምድር አከበርሁህ፤
5፤ አሁንም፥ አባት ሆይ፥ ዓለም ሳይፈጠር በአንተ ዘንድ በነበረኝ ክብር አንተ በራስህ ዘንድ አክብረኝ።
ይህንን ፀሎት መስማት እንዴት የሚገርም አጋጣሚ ነው:: ሙሴ እንደተባለው ጫማ ማውለቅ የሚያስጠይቅ መሆን ነበረበት:: ወልድ ለአብ የሚናገረውን እያደመጡ ነው ያሉት በሌላ አባባል እኛም እየሰማን ነው ይህንን ፀሎት:: እየሱስ ሲፀልይ የመጀመርያው አይደለም ለሊቱን ሁሉ ሲፀልይ ያድር ነበረ ይሄኛው ግን ሊቀ ካህንነቱን በግልጽ እያሳየ ስለራሱም ስለሐዋርያቱም እንዲሁም በሩቅ ስላለነው ስለእኛ ፀለየ:: ዋዉ!!
የመስቀሉን ስራ ገና አልጨርረሰም ግን እኔ ላደርገው የሰጠኸኝን ሥራ ፈጽሜ በምድር አከበርኩህ አለ:: እራሱን አሳልፎ በፈቃዱ ለመስጠት ወደ ቀጠሮ ስፍራው እንደሚሄድ ስለሚያውቅና እንዲሁም ከዚህ በኃላ ስለሚያዋክቡት ተረጋግቶ የሚፀልይበት ጊዜ እንደሌለውም አውቆ:: መስቀል ላይ ገና ሳይወጣ እራሱን ለመስዋእት አቀረበ:: ልክ ካህናት በብሉይ ኪዳን እንደሚያደርጉት የሚቀርበውን መስዋእት እንከን የሌለው መሆኑን አገላብጠው አይተው እንደሚያረጋግጡት እንዲሁምእየሱስ ህይወቱን በአብ ፊት አቅርቦ እንከን የሌለው በግ መሆኑን አሳየ:: ፈጽሜ አከበርኩህ እያለ ፀለየ እርሱ እፁብ ድንቅ ነው:: ንፁ በግ! በዕብራውያን 4:14-15፤ እንግዲህ በሰማያት ያለፈ ትልቅ ሊቀ ካህናት የእግዚአብሔር ልጅ ኢየሱስ ስላለን፥ ጸንተን ሃይማኖታችንን እንጠብቅ:: ከኃጢአት በቀር በነገር ሁሉ እንደ እኛ የተፈተነ ነው እንጂ፥ በድካማችን ሊራራልን የማይችል ሊቀ ካህናት የለንም።
ለሐዋርያቱም እምነት እንዲሆናቸው እፊታቸው ስለማንነቱ ፀለየ:: እንዲህም አለ:- አባት ሆይ፥ ዓለም ሳይፈጠር በአንተ ዘንድ በነበረኝ ክብር አንተ በራስህ ዘንድ አክብረኝ። ይህንን ክብር ጥሎ ሲመጣ ፍቅር ነው ያመጣው ሁሉን ቁጭ አድርጎ ሊታደገን መጣ:: አሁንም ወደዛው ክብሩ ሊመለስ ነው:: እግዚአብሔር ከሆነ ለምን ይህንን ፀሎት ፀለየ የሚሉ ሰውኢች የፀለየውን የሰሙ አይመስሉም:: አንድ አምላክ እንዳለ እርሱንም እንደሚተካከልና አንድ እንደሆነ እያወጀ ያለበት ፀሎት ነው:: አንተው አክብረኝ ብሎ እራሱን ሰጠ! ስለእኔና ስለሰው ልጅ ሁሉ!!
አባት ሆይ ተመስገን የተቀደሰውን እራስህን ስለሰው ልጅ መስዋእት ስለሰጠህ እናመሰግናለን:: በከበረው ዙፋንህ ላይ ነህና ክበር:: እኔም የቀደስከውን ማንነቴን እሰጥሃለሁ ክበርበት:: አሜን!
ዮሐንስ 17: 6-13
6፤ ከዓለም ለሰጠኸኝ ሰዎች ስምህን ገለጥሁላቸው። የአንተ ነበሩ ለእኔም ሰጠሃቸው፤
ጌታ እየሱስ ወደ አባቱ የፀለየው ፀሎቱ
ቃሉን ሐዋርያቱ እንደተቀበሉት ነው:: ሲቀበሉትም :- ቃሉን እንደጠበቁ: ሁሉን ከአባቱ መቀበሉን እንዳወቁ: ቃሉንም እንደሰጣቸውና ከአብ ወጥቶ መምጣቱን እንዳመኑ ይመሰክርላቸዋል::
በመቀጠልም የካህንነቱን ስራ ሲሰራ እናያለን እኔ ስለ እነዚህ እለምናለሁ፤ ስለ ዓለም አልለምንም ስለ ሰጠኸኝ እንጂ፤ የአንተ ናቸውና፤ የእኔም የሆነ ሁሉ የአንተ ነው የአንተውም የእኔ ነው፤ እኔም ስለ እነርሱ ከብሬአለሁ። እየማለደ ያለው ስለቅዱሳን እንጂ በዓለም ስላሉት አይደለም:: አብ ወደ ክርስቶስ ከሳበው በቀር ማንም እንደማይመጣ ቃሉ ይነግረናል ጌታም ስለሰጠኸኝ ሰዎች ብሎ ነው የፀለየው:: የአንተ የሆነው ሁሉ የእኔ ነው የእኔም የሆነው የአንተ ነው:: ስለዚህ ልመጣ ነውና በዚህ ዓለም አብሬአቸው አልኖርምና በስምህ እንዳይጠፉ ጠበኳቸው ከጥፋት ልጅ በቀር አሁንም አንተ አባት ሆይ እነዚህን እንደኛ አንድ እንዲሆኑ በስምህ ጠብቃቸው! ብሎ ፀለየ:: ዋዉ ዛሬ በስሙ ከእርሱ ጋር አንድ እንድንሆን ከዚህ ፀሎት የተነሳ አብ አባት እየጠበቀን ነው:: ለካስ ብርታቴ ትጋቴ እርሱን መፈለጌ አይደለም በቤቱ የተከለኝ ከፀጋም በላይ እየተደረገልኝ ያለው ጥበቃ ነው::
አብ አባት ሆይ ተመስገን ከዚህ ፀሎት የተነሳ ህብረቴ ከአንተጋር እንዲሆንና እንዲፀና በአንተ ስምና ኃይል እየተጠበኩ ስለሆነ አመሰግንሃለሁ! ሃሌሉያ! እልልልልልል!!! አሜን
ዮሐንስ 17: 14-18
18፤ ወደ ዓለም እንደ ላክኸኝ እንዲሁ እኔ ወደ ዓለም ላክኋቸው፤
ጌታ እየሱስ ሰጥቻቸዋለሁ የሚለው ቃሉን ነው:: ከዛም ይህ ቃል የሚያደርገውን እንይ:- በእውነትህ ቀድሳቸው፤ ቃልህ እውነት ነው። ቃሉ ይቀድሳል:: እንደዚሁም እየሱስ እራሱን ሰጥቶ ቀደሰን:- እነርሱም ደግሞ በእውነት የተቀደሱ እንዲሆኑ እኔ ራሴን ስለ እነርሱ እቀድሳለሁ። ብሎ ፀለየና የራሱን ቅድስና ለእኛ ሰጠን::
ሌላው የፀለየው:- እኔም ከዓለም እንዳይደለሁ ከዓለም አይደሉምና ዓለም ጠላቸው። ደግሞም እንደገና እኔ ከዓለም እንዳይደለሁ ከዓለም አይደሉም አለ::
ከዓለም አይደለንም መንገደኞችና መፃተኞች ነን:: ከዚህ ዓለም ጋር ለመዋሃድ አንሞክር አይሰራም!! ስለዚህም ጌታ ከክፉ እንድትጠብቃቸው እንጂ ከዓለም እንድታወጣቸው አልለምንም ብሎ ነው የፀለየው:: እዚህ ዓለም ላይ ስንኖር ከክፉ እንድንጠበቅ ጌታ ፀልዮልናልና ክፉ ይመኛል እንጂ አያገኘኝም!!! ሃሌሉያ!
እሺ ቀደሰን በቃሉና እራሱን በመስጠት እንዲሁም ከክፉ ተጠበቅን ከዛስ?
ከዛማ ወደ ዓለም እንደ ላክኸኝ እንዲሁ እኔ ወደ ዓለም ላክኋቸው ብሎ ላከን:: ከዓለም አይደለንም በዓለም ከሚሰራው መንግስት ተፋተን የእግዚአብሔር ወገን ተብለን ተቆጥረን:: ክፉ በሚቆጣጠረው ዓለም ላይ የመንግስታችንን ስራ ለመስራት አምባሳደር ተደርገን ተሹመናል!! ስራችንን ስንጨርስ ወደ አገራችን እንሄዳለን ዛሬ ግን ተልከናል ወደዝች ክፉ ወደ ሰለጠነባት ዓለም:: በክፋት ሁሉ ላይ ስልጣን ተሰቶናል ሊጎዳን አይችልምና እናባርረዋለን እናስለቅቀዋለን እንቀማዋለንን እናስተፋዋለን:: ድል ለእግዚአብሔር ህዝብ ነው!!! አሜን
አባት ሆይ ተመስገን በዚህ ቃልህ ስለቀደስከኝ:: ይህ የእየሱስ ፀሎት ዛሬም በፊትህ ነውና ክፉ ስለማይነካኝ አመሰግንሃለሁ:: በአጠገቤ ሺህ በቀኜም አስር ሺህ ይወድቃል እንጂ ወደ እኔ አይቀርብም!! ሃሌሉያ! ከበርልኝ!! ወደዚች ዓለም ተልኬያለሁና ስራህና ፈቃድህ በእኔ ይፈፀም:: መንግስትህ ትምጣ ትግዛ! አሜን!
ዮሐንስ 17:20-21፤ “ሁሉም አንድ ይሆኑ ዘንድ፥ ከቃላቸው የተነሣ በእኔ ስለሚያምኑ ደግሞ እንጂ ስለ እነዚህ ብቻ አልለምንም፤ አንተ እንደ ላክኸኝ ዓለም ያምን ዘንድ፥ አንተ፥ አባት ሆይ፥ በእኔ እንዳለህ እኔም በአንተ፥ እነርሱ ደግሞ በእኛ አንድ ይሆኑ ዘንድ እለምናለሁ።
ጌታ እየሱስ ስለእኛ የፀለየውን እንይ:-
ሁሉም አንድ ይሆኑ ዘንድ ብሎ ነው ያለው:: ለምን አንድ መሆናችን ተፈለገ?! ወረድ ብሎ እንደሚለው *አንተ እንደ ላክኸኝ ዓለም ያምን ዘንድ* ይሄ ነው ምክንያቱ:: እየሱስ ወደ ዓለም ተልኮ መምጣቱን ሁሉ እንዲያውቅ ነው:: ወንጌልም ከአንድነታችን የተነሳ እንዲሮጥነው::
ይሄ ፀሎት ተመልሷል:: እኔ የገጠመኝን ልመስክር:- አንድ የገበያ ስፍራ ላይ ከምትሸጥ እህትጋር መነጋገር ጀመርንና ከየት አገር ነው የመጣሽው ብዬ ስጠይቃት ከኢራን አለችኝ:: እኔም አገርሽ ሰላም ነው እንዴት ናቸው? ብዬ ስጠይቃት አይይ አባረሩን አለችኝና ከአንገትዋ ላይ መስቀልዋን አውጥታ ስታሳየኝ የአገር ጥያቄዬ ምኔ ሁሉ ጠፍቶ የጠፋችብኝን እህቴን ያገኘሁኝ ያህል ደስታ ወረረኝ:: ለካስ ክርስትያን ስትሆን ሊገድልዋትስለሚፈልጉ ነው ከአገርዋ የተሰደደችው:: ቀጥላም እየሱስ መሃላችን ተገለጠ አለችኝ ከዛማ እልል ወደ ማለትና ፀሎት ወሰደኝ:: አላውቃት አታውቀኝ ይህ የፀሎቱ መልስ ነው:: በእርሱ አንድ ነን::
ይህንን ሁልጊዜ ጠላት ይዋጋዋል ሊለያይና ሊበትን ነው የሚፈልገውና አንድነትን መጠበቅ ከእኛ ይጠበቃል:: አንድ አካል አለ የዚህም አካል ራስ እ የ ሱ ስ ነው! አሜን! ሁላችን በዚህአካል ውስጥ እየተጋጠምን እናድጋለን:: በኤፌሶን 4:11፤ እርሱም አንዳንዶቹ ሐዋርያት፥ ሌሎቹም ነቢያት፥ ሌሎቹም ወንጌልን ሰባኪዎች፥ ሌሎቹም እረኞችና አስተማሪዎች እንዲሆኑ ሰጠ፤ እርሱ ነው የሰጠው ለአካሉ:: በ1 ቆሮንቶስ 12:12፤ አካልም አንድ እንደ ሆነ ብዙም ብልቶች እንዳሉበት ነገር ግን የአካል ብልቶች ሁሉ ብዙዎች ሳሉ አንድ አካል እንደ ሆኑ፥ ክርስቶስ ደግሞ እንዲሁ ነው፤
አሜን!
ስለዚህ እየሱስ ሲፀልይ በእኔ እንዳለህ እኔም በአንተ፥ እነርሱ ደግሞ በእኛ አንድ ይሆኑ ዘንድ እለምናለሁ። ከእርሱ ጋር አንድ እንድንሆን ወዶ ፈቅዶ ፀልዮልናል:: ህብረታችን ከአብ ጋር ከልጁም ከእየሱስ ጋር ነው:: አሜን
አባት ሆይ በአንተ ውስጥ መኖርና ከአንተ ጋር አንድ መሆን ከቅዱሳንም ጋር አንድ መሆን ስለተሰጠን ተመስገን:: በዚህ ውስጥ ለዘላለም እንኖራለን! በየትኛውም አገር ውስጥ ስላሉ እህትና ወንድሞቼ እፀልያለሁ አባት ሆይ ባሉበት ይጠበቁ ዘንድና የሚድኑ ነፍሳት በእነርሱ ላይ እንዲጨመሩ እፀልያለሁኝ::
አሜን!
ዮሐንስ 17:22-23፤ እኛም አንድ እንደ ሆንን አንድ ይሆኑ ዘንድ፤ እኔም በእነርሱ አንተም በእኔ ስትሆን፥ በአንድ ፍጹማን እንዲሆኑ፥ የሰጠኸኝን ክብር እኔ ሰጥቻቸዋለሁ፤ እንዲሁም ዓለም አንተ እንደ ላክኸኝ በወደድኸኝም መጠን እነርሱን እንደ ወደድሃቸው ያውቃል።
ጌታ ደግሞ ይህንኑ ጸሎት ጸለየ ስለአንድነትና ስላለን ህብረት:: መደጋገሙ የሚያሳየን እንዴት አስፈላጊ መሆኑን ነው::
እኛም አንድ እንደ ሆንን አንድ ይሆኑ ዘንድ፤ – የአብና የወልድ አንድነት ምን አይነት ነው? የእኔ ሳይሆን የአንተ ፈቃድ ይሁን የሚያሰኝ አንድነት ነው::
እኔም በእነርሱ አንተም በእኔ ስትሆን፥ በአንድ ፍጹማን እንዲሆኑ፥ የሰጠኸኝን ክብር እኔ ሰጥቻቸዋለሁ፤ – እየሱስ በእኛ ውስጥ እንዳለ እራሱ እያወጀ ነው:: እኔና አብ እንመጣለን በእርሱም ዘንድ መኖርያ እናደርጋለን:: ይህ የሚሆነው በአንድ ፍፁማን እንድንሆንና የሰጠኸኝን ክብር እኔ ሰጥቻቸዋለሁ እንዳለ ክብሩን እንድንቀበል ነው::
የሰጠን ክብር ምንድነው? በሰማይና በምድር ሙሉ ስልጣን ተሰጠኝ እንግዲህ ሂዱና ብሎ ሙሉ የአምባሳደርነትን ማዕረግ ተቀበልን እንዲሁም ከስም ሁሉ በላይ የሆነውን ስም ተቀብሎ ለእኛ እንድንድንበት ሰጠን:: በፊልጵስዩስ 2:10፤ ይህም በሰማይና በምድር ከምድርም በታች ያሉት ሁሉ በኢየሱስ ስም ይንበረከኩ ዘንድ፥ 11፤ መላስም ሁሉ ለእግዚአብሔር አብ ክብር ኢየሱስ ክርስቶስ ጌታ እንደ ሆነ ይመሰክር ዘንድ ነው። አሜን:: እንደዚሁም ከእርሱ ጋር አንድ የሚያደርገንን በመንፈስ ቅዱስን ሰጠን!
እንዲሁም ዓለም አንተ እንደ ላክኸኝ በወደድኸኝም መጠን እነርሱን እንደ ወደድሃቸው ያውቃል። ለዓለም የሚቀረው ምስክርነት መወደዳችንን ማወቁ ነው:: የተወደድነውም ልክ እየሱስ በተወደደበት መጠን ነው:: አብም ይህንን ብሏል:- በማርቆስ 1:11፤ “የምወድህ ልጄ አንተ ነህ፥ በአንተ ደስ ይለኛል፡” የሚል ድምፅ ከሰማያት መጣ። እንግዲህ በዚህ ፍቅር ተወደናል::
አባት ሆይ ክብርህን ስለሰጠኸን ስለወደድከን እናመሰግናለን:: እንደተወደዱ ልጆች መመላለስ ይሁንልን! አሜን! ይህ ፍቅር ላልገባውና አንተን ለማያውቁ እኛ ነንና መናገሪያ መንገዶችህ እርዳን ለጠፉት ግድ ብሎን እንድንመሰክር!
ዮሐንስ 17:24፤ አባት ሆይ፥ ዓለም ሳይፈጠር ስለ ወደድኸኝ የሰጠኸኝን ክብሬን እንዲያዩ እኔ ባለሁበት የሰጠኸኝ እነርሱ ደግሞ ከእኔ ጋር ይሆኑ ዘንድ እወዳለሁ።
አባት ሆይ ብሎ አብን እንድንጠራ ያስተማረን ጌታ እርሱም እንደዛው እየፀለየ ነው:: ዓለም ሳይፈጠር ስለ ወደድኸኝ አለ ጌታ ይህ ማለት በሌላ ክፍል ላይም እንደሚለው እግዚአብሔር ፍቅር ነው:: ይህ ፍቅር ድሮም ያለ ማንነቱ እንጂ አሁን የተፈጠረ አይደለም::
ሌላው በአባት ፊት የሰጠኸኝን ብሎ ነው እኛን የሚጠራን ቃሉ እንደሚለን አብ ካልሳበው በቀር ወደ እየሱስ የሚመጣ የለም ይህ ማለት እያንዳንዳችንን አብ እራሱ ለእየሱስ የሰጠን ልጆቹ ነን:: አሜን!
ስለፍቅሩ አነሳ እኛንም ከእጁ ስለመቀበሉ አነሳና በዮሐንስ 14:2፤ በአባቴ ቤት ብዙ መኖሪያ አለ፤ እንዲህስ ባይሆን ባልኋችሁ ነበር፤ ስፍራ አዘጋጅላችሁ ዘንድ እሄዳለሁና፤ ይህንን ቃል ኪዳኑን ይፀልየዋል::
ይኸውም በተዘጋጀልን ስፍራ ከእርሱ ጋር እንድንኖርና የሚፈልገውም ክብሩን እንድናይ ፀለየልን:: እርሱ ባለበትም እንድንኖር ለዘላለም እኔ ባለሁበት የሰጠኸኝ እነርሱ ደግሞ ከእኔ ጋር ይሆኑ ዘንድ እወዳለሁ። አሜን ይህ ፀሎት ተመልሷል እኛ በዚህ ምድር ብንመላለስም ወደ ፍቅሩ ልጅ መንግስት ተሸጋግረናል:: እንዲሁም በአብ ቀኝ በእየሱስ ውስጥ ተሰውረናል:; በትክክል ይህ ፀሎት ተመልሷል! አሜን
አባት ሆይ እላለሁ እኔም ስምህ ይባረክ አንተ ባለህበት ስለተገኘሁ በዚህ ሰዓት ስምህ ይባረክ! በዘላለም ፍቅርህም ስለወደድከኝ ተባረክ! አሜን!
ዮሐንስ 17: 25-26
25፤ ጻድቅ አባት ሆይ፥ ዓለም አላወቀህም፥ እኔ ግን አወቅሁህ እነዚህም አንተ እንደ ላክኸኝ አወቁ፤
26፤ እኔንም የወደድህባት ፍቅር በእነርሱ እንድትሆን እኔም በእነርሱ፥ ስምህን አስታወቅኋቸው አስታውቃቸውማለሁ።”
በጸሎቱ መዝጊያ የሚያነሳቸው ኃሳቦች/የጸሎት ርዕስ:-
እየሱስ አብን የሚጠራበትን ስናይ:- ጻድቅ አባት ሆይ ይለዋል:: ወደ መስቀልና መከራ እየሄደ ጻድቅ አባት ሆይ ይላል:: ዓለም ዛሬም አላወቀውም አልተረዳውም ለምን እየሱስ እዳ እንደከፈለ ነገር ግን ይሞግታል የተሻለ መንገድ አልነበረም ወይ? ለምን አዳምን ፈተነው? እዛው ጋር ለምን ህይወት አላበቃምና ሌላም ሌላም አወቅን የእውቀትን ጥግ አየን በሚሉ በየዘመኑ የተነሱ ሁሉ ብዙ ብለዋል:: ነገር ግን ገና አዳም ሲወድቅ ቃል እንደገባው ቃሉን ጠብቆ ተወለደ:: እየሱስ:- እኔ ግን አወቅሁህ ይላል:: ስለ ሐዋርያትም:-እነዚህም አንተ እንደ ላክኸኝ አወቁ ብሎ ይመሰክርላቸዋል:: የእግዚአብሔርን ዓላማ ማወቅ እንደምን መታደል ነው:: ዛሬም እኛ አወቅነው እራሱ ስለገለጠልን:: መስቀል ኃይላችን እንደሆነ ተገነዘብን::
እኔንም የወደድህባት ፍቅር በእነርሱ እንድትሆን ብሎ ከላይም ጸልዮታል:: እየሱስ በተወደደበት በዚህ ፍቅር ነው የተወደድነው::
እኔም በእነርሱ:- ቃሉን ተቀብለው አምነዋልና በእነርሱ ዘንድ መኖርን ጸለየ:: እኔና አብ በእርሱ ዘንድ መኖርያን እናደርጋለን እንዲሁም እራሴንም እገልጥለታለሁ እንደሚለው ቃል ማለት ነው::
ስምህን አስታወቅኋቸው አስታውቃቸውማለሁ። ይህንን ስም ዛሬም ያስታውቀናል ቀጣይነት ያለው ነው:: ይህ ስም የምንጠበቅበት ነው ከስም ሁሉ በላይ ነው:: ከላይም እንደጸለየው የሰጠኸኝን በስምህ ጠበኳቸው አለ:: አሁንም በስሙ እንጠበቃለን:: ከስም ሁሉ በላይ የሆነ ስም አለልን! ይህ ስም ከነሙሉ ማዕረጉ እንድንጠቀምበት ተሰጥቶናል:: አሜን!
ጻድቅ አባት ሆይ ስምህ ይቀደስ! ስምህ ይባረክ! ይህንን ስም ስለሰጠኸኝ እባርክሃለሁ:: ስምህን አስታውቀኝ አሁንም:: ከስም ሁሉ በላይ የሆነው ስምህ በጠላቶቼ ላይ ይገለጥ!
አንተንም ማወቅ ስለተሰጠኝ አመሰግንሃለሁ:: መውደድህ ለዘላለም ነውና ክበርልኝ!
ዮሐንስ 18: 1-11
8፤ ኢየሱስ መልሶ፦ “እኔ ነኝ፡ አልኋችሁ፤ እንግዲህ እኔን ትፈልጉ እንደ ሆናችሁ እነዚህ ይሂዱ ተዉአቸው፡” አለ፤
9፤ ይህም፦ “ከእነዚህ ከሰጠኸኝ አንዱን ስንኳ አላጠፋሁም፡” ያለው ቃል ይፈጸም ዘንድ ነው።
እየሱስ ሊሸከሙት የሚችሉትን ሁሉ አስተምሮና ጸልዮ ሲያበቃ ተላልፎ ወደሚሰጥበት ስፍራ መጣ:: ይሁዳም አሳልፎ ሊሰጠው ሰራዊት ይዞ መጣ:: ጌታ እየሱስ ማንን ትፈልጋላችሁ ? ብሎ ጠየቃቸው እነርሱም “የናዝሬቱን ኢየሱስን፡” ብለው መለሱለት። ኢየሱስ፦ “እኔ ነኝ፡” አላቸው። እንግዲህ፦ “እኔ ነኝ፡” ባላቸው ጊዜ ወደ ኋላ አፈግፍገው በምድር ወደቁ። ሃሌሉያ! እኔ እኔ ነኝ ማለት የሚችለው የእኛ ጌታ ብቻ ነው:: እኔ ነኝ በሚለው ማንነቱ ፊት ማን መቆም ይችላል?! እንግዲህ ምን ነካቸውና ወደፊት ሳይሆን እንደተገፉ ያህል ሁሉም ወደኃላ ወደቁ:: የሚያስተውል ቢኖር ይቅርብኝ ብሎ የሚያስተው ነበረ ግን አላስተዋሉም:: አልፋና ኦሜጋ የሆነውን ጌታ በቆመጥና በዱላ ሊይዙ መጡ:: አቤት ትህትና!!! ምን አይነት ጌታ ነው እንዴት ቢወደን ነው እንደዚህ የተዋረደው?!
ይህ ክብር ዛሬም ይሰራል እነ ዳንኤል እራሱም ዮሃንስ በራዕይ ላይ ወድቀዋል በክብሩ ፊት:: እነዚህ ግን ሳይጋበዙ ወደ ክብሩ የቀረቡ ናቸው:: ሊቋቋሙት የሚለው ባይመጥንም ግን በነሱ ቤት ሞክረዋል:: ጴጥሮስን፦ “ሰይፍህን ወደ ሰገባው ክተተው፤ አብ የሰጠኝን ጽዋ አልጠጣትምን?” አለው።
የጌታ”እኔ ነኝ” የሚለው ክብሩ ያልገባው ጴጥሮስ ግን እራሱን መከላከል የሚችለውን እየሱስን ለማስጣል ባለችው ሰይፍ ሊዋጋ ተነሳ:: ጌታ ስንት ሰይፍ አለን ብሎ ጠይቋቸው ሁለት ብለውት ነበረ:: አንዱ አገልግሎት ላይ ባይውልም ቅሉ አንዱን ግን ጴጥሮስ ተጠቀመበት:: ጴጥሮስ የገባውና ሲዘጋጅ የቆየው ለዚህ ነበረ እንጂ ጸልይ ሲባል ቢጸልይ የተሻለ ነገር ይሆን ነበረ:: የጌታ ስራ የሚሰራው በመንፈሱ ነው እንጂ በብርታታችን አይደለም:: እፊቱ ክብሩ እየተገለጠ ጴጥሮስ አላስተዋለም:: የጎዳውን ሰው ጆሮ ፈውሶ ጴጥሮስንም ገስጾ እራሱን ለኃጥያተኞች አሳልፎ ሰጠ ጊዜው ስለሆነ::
ጌታ የተያዘው አድፍጠው ስለጠበቁት ወይንም ብዙ ሆነው ስላልመጡ ሳይሆን በቃሉእንደሚለው የሚመጣውን ሁሉ አውቆ ማንን ትፈልጋላችሁ አላቸውና በፈቃዱ እራሱን ሰጠ:: ለአባቱም ቃል እንደገባው ከአንዱ በቀር ሁሉን ጠበኩ በስምህ እንዳለው እነዚህንተዋቸው ይሁዱ አለ:: እነርሱም ተበታተኑ:: በዚህ ውስጥ ሆኖ ስለእነርሱ ደህንነት ያሰበ ጌታ ዛሬም ስለእኔ ያስባል! የራሴን ጸጉር በቁጥር ያውቃል! ይጠብቀኛል! ይጋርደኛል! ደግሞም ይዋጋልኛል!!! አሜን!
አባት ሆይ እራስህን ስለእኔ አዋርደህ ስለሰጠህ ተመስገን:: ዛሬ ኃይልህና ጸጋህ በእኔ ይገለጥ:: በራሴ እንዳልደገፍ እርዳኝ! አንተ በስራ ላይ ነህ!
ዮሐንስ 18: 12-18
14፤ ቀያፋም፦ “አንድ ሰው ስለ ሕዝብ ይሞት ዘንድ ይሻላል፡” ብሎ ለአይሁድ የመከራቸው ነበረ።
በባለ ስልጣናቱ በኩል ስናየው የእየሱስ መያዝ:- እየሱስን መጀመርያ የወሰዱት ወደ ሐና ነበረ ምክንያቱም የሊቀ ካህናቱ አማት ስለነበረ:: ምን ስልጣን ኖሮት ነው ታድያ ወደ እርሱ የሚያመጡት? እግዚአብሔር እንደደነገገላቸው እየኖሩ ይሆን?! ምናልባትም በአላዛር ከሞት መነሳት የተነሳ ብዙ አይሁድ በእርሱ ስላመኑ በዛም ምክንያት አለቆች እሱን ብቻ ሳይሆን አላዛርንም ለመግደል ተማከሩ ይላል:: ከተማከሩት አለቆች መካከል አንዱ ሳይሆን አይቀርም ፍሬህን እየው ለማለት::
በሐዋርያቱ በኩል ስናየው:- ሁለት ደቀ መዛሙርት ተከትለውታል ዮሃንስና ጴጥሮስ የተቀሩት ተበትነዋል:: ዮሃንስ ስለራሱ ሲጽፍ ሌላኛው እያለ ግን በደንብ የሆነውን ልክ እዛው እንደሆነ ነው የሚናገረው:: በሊቀ ካህናቱ ዘንድ ዮሃንስ ስለሚታወቅ ያለ ችግር ወደ ጊቢው ገባ ጴጥሮስ ግን በውጪ ስለነበረ ተመልሶ ወቶ ጥበቃ ላይ ለነበረችው ነግሮ አስገባው:: እርሷም የእርሱ ደቀ መዝሙር ነህ ስትለው እዛው በዛው ጴጥሮስ ካደ:: እርስዋው አስገብታው እያወቀች ካደ! አይ ጴጥሮስ!
በጌታ በኩል ስናየው:- ከአንዱ ወደ አንዱ ተቀባበሉት ዓላማችንን አሳካን እያሉ::ሊቀ ካህናቱ “አንድ ሰው ስለ ሕዝብ ይሞት ዘንድ ይሻላል፡” ብሎ ትንቢትን መናገሩንም ያወቀ አይመስልም:: በእጃቸው በፈቃዱ የገባው ማን እንደሆነ ባወቁ:: አይ ሊቀ ካህናት ስለህዝቡ በማን ፊት የሚቆም መሰለው?! ለእርሱም ነበረ የጌታ መምጣት! በፊቱ መጥቶ የሚቆመው የነገስታት ንጉስና የጌቶች ጌታ ዋና ሊቀ ካህን እየሱስ መሆኑን ባወቀ!!! ማን ነው በማን ፊት እየቆመ ያለው?! ሊቀ ካህንነቱ ሊሻር በተሻለ ኪዳን ሊተካና ይህ ካህን ቅዱስ በሆነ ለራሱ መስዋአት ማቅረብ በማያስፈልገው ሊተካ ጊዜው መሆኑን ባወቀ:: ወይ ሰው አለማስተዋሉ?!!! አቤት የእግዚአብሔር ፍቅር: ትግስትና ትህትና:: ጌታ አልዛተም አዳሜ በፊቴ ትቆሚያታለሽ አሳይሻለሁ አላለም አፉንም አልከፈተም በሸላቾቹ ፊት ዝም እንደሚል በግ ዝም አለ:: ወይ የኔ ጌታ!!
በሰማያት ያለኸው ሊቀ ካህኔ እየሱስ እኔ ዛሬ አገንሃለሁ!! ምስጋናዬንም በፊትህ አኖራለሁ ይህንን ሁሉ ያደረከው ለሰው ልጅ መዳንና ለእኔም ነው:: ተመስገን ስለፍቅርህ ስለትግስትህ ስለትህትናህ! ክበር!
ዮሐንስ 18: 19-24
20፤ ኢየሱስም መልሶ አለው፦ “እኔ በግልጥ ለዓለም ተናገርሁ፤ አይሁድ ሁሉ በሚሰበሰቡበት በምኵራብና በመቅደስ እኔ ሁልጊዜ አስተማርሁ፥ በስውርም ምንም አልተናገርሁም።
21፤ ስለምን ትጠይቀኛለህ? ለእነርሱ የተናገርሁትን የሰሙትን ጠይቅ፤ እነሆ፥ እነዚህ እኔ የነገርሁትን ያውቃሉ” አለው::
ሊቀ ካህናቱ ሐና ኢየሱስን ስለ ደቀ መዛሙርቱና ስለ ትምህርቱ ጠየቀው። መልሱም በግልጥ ሁሉም ባለበት አስተምሬአለሁ ወይም በግልጥ አስተምሬአለሁ ምንም በስውር አልተናገርኩም ስለምን ትጠይቀኛለህ? ለእነርሱ የተናገርሁትን የሰሙትን ጠይቅ፤ እነሆ፥ እነዚህ እኔ የነገርሁትን ያውቃሉ” አለው:: ምስክር ጥራ እንደ ህጉ እንጂ እንደዚሁ መፍረድ አትችልም እያለው ነው:: ደግሞም እኔ ያስተማርኩትን ከሌሎች ስማ አለው ህዝቡ ግን ስለሚፈርቸው ይህንና ያንን አስተምሯል እውነተኛ ነው ብሎ የሚል የለም:: ብዙዎች አመኑበት ቢልም ቅሉ ማንም ወደ ፊት መጥቶ አልተከራከረለትም:: ሐዋርያቱንም ጨምሮ:: ሰው ፊቱን ከእርሱ ማዞር ጀምሯል::
ከሎሌዎች አንዱ፦ “ለሊቀ ካህናቱ እንዲህ ትመልሳለህን?” ብሎ ኢየሱስን በጥፊ መታው። ማነው ሊቀ ካህኑ እየሱስ ወይንም የሚሻረው ለጊዜው ያለው ሐና? ይህ ታላቅ ጌታ ግን መልሶ፦ “ክፉ ተናግሬ እንደ ሆንሁ ስለ ክፉ መስክር፤ መልካም ተናግሬ እንደ ሆንሁ ግን ሰለ ምን ትመታኛለህ?” አለው። ወደ ፊት በግርማው ፊት ሲቆም ምን ይል ይሆን?! እጁን ሲዘረጋ ወድቆ አለመሞቱ የሚያሳየው የጌታን ፍቅር: ትግስትና ርህሩህነት ነው::
አባት ሆይ ተመስገን ልጅህን እየሱስን ስለላክልን:: እየሱስ አንተ ሊቀ ካህን ነህ ለዘላለም! ይህንን ሁሉ መዋረድ ታግሰህ አለፍህ ይህ ሁሉ ስለ እኔ ነውና አመሰግንሃለሁ:: በሄድኩበት ሁሉ ታላቅነትህ ይታይ! ግነን! አሜን
ዮሐንስ 18:25-32
27፤ ጴጥሮስም እንደ ገና ካደ፥ ወዲያውም ዶሮ ጮኸ።
28፤ ኢየሱስንም ከቀያፋ ወደ ገዡ ግቢ ወሰዱት፤ ማለዳም ነበረ፤ እነርሱም የፋሲካ በግ ይበሉ ዘንድ እንጂ እንዳይረክሱ ወደ ገዡ ግቢ አልገቡም።
ጴጥሮስ ርቆ አይርቅ እየሱስን ይዘው በመጡት ሰዎች መካከል እየተገኘ ከእርሱ ጋር ነበርክ ሲሉት ይክዳቸዋል:: ጌታም አስቀድሞ ነግሮት ነበርና ክህደቱን ቀጠለ ማንም በራሱ አይበረታምና::
በእየሱስ አንፃር ደግሞ ስናይ ከአንዱ ጊቢ ወደ ሌላው እየትወሰደ ነው:: በመጀመርያ ወደ ሐና ከዛም ወደ ቀያፋ አሁን ደግሞ ወደ ገዢው ወደ ጲላጦስ:, በስተመጨረሻ ግን ወደ አባቱና ወደ አባታችን ደሙን እያንጠባጠበ ይገባና ስለእኛ ይታያል!
አንድ የገረመኝ ነገር በዚህ ክፍል ውስጥ:- እነርሱም የፋሲካ በግ ይበሉ ዘንድ እንጂ እንዳይረክሱ ወደ ገዡ ግቢ አልገቡም ይላል:: የፋሲካውን በግማ ይኸው ለኃጥያተኞች አሳልፈው ሰጡት እነርሱ የሚያስቡት ምሳሌውን ለመዘከርና ለመብላት ነው ዋናው ግን በእጃቸው ነበረ:: ብዙ ትንቢት በብሉይ ኪዳን መጽሐፍት ሁሉ የተናገረለት እውነተኛው የእግዚአብሔር በግ በፊታቸው ነበረ ግን አላስተዋሉም?! እርሱን እንደቀላል ነገር አሳልፈው ሰጡት::
ደግሞም ክሳቸው ሲገርም:- ይህስ ክፉ አድራጊ ባይሆን ወደ አንተ አሳልፈን ባልሰጠነውም ነበር፡” አሉት ለጲላጦስ::
ጲላጦስም፦ “እናንተ ወስዳችሁ እንደ ሕጋችሁ ፍረዱበት፡” አላቸው። አይሁድም፦ “ለእኛስ ማንንም ልንገድል አልተፈቀደልንም፡” አሉት፤ ምን?! እንዴ ታድያ እስጢፋኖስን ማን ገደለው?! ሲፈልጉ ይገላሉ ሲፈልጉ ደግሞ አይገድሉም:: ነገሩ ግን እየሱስ በድንጋይ ተወግሮ መሞት ስለሌለበት ነው ይህ የሆነው:: በቃሉም እንደሚል ኢየሱስ በምን ዓይነት ሞት ሊሞት እንዳለው ሲያመለክት የተናገረው ቃል ይፈጸም ዘንድ ነው ይላል እሱም በመስቀል ላይ መሞት:: ስለእያንዳንዳችን እየሱስ ተላልፎ ተሰጠ::
አባት ሆይ ማንም አብሮት የሚቆም ሳይኖር እየሱስ ስለእኛ ተላልፎ ተሰጠ ምን እንላለን ተመስገን!! ተመስገን! ክብር ምስጋና አምልኮ ለታረደው በግ ይሁን!
ዮሐንስ 18: 32-40
36፤ ኢየሱስም መልሶ፦ “መንግሥቴ ከዚህ ዓለም አይደለችም፤ መንግሥቴስ ከዚህ ዓለም ብትሆን፥ ወደ አይሁድ እንዳልሰጥ ሎሌዎቼ ይዋጉልኝ ነበር፤ አሁን ግን መንግሥቴ ከዚህ አይደለችም፡” አለው።
ጲላጦስ ግራ ገብቶታል እናም “የአይሁድ ንጉሥ አንተ ነህን?” ብሎ ጠየቀው ምክንያቱም የሚወጣው ክስ አይደለምና ይሄ ክስ:: ሌላ ንጉስ የሮም መንግስት በሚያስተዳድረው ስር መንገስ አይችልምና አይሁድንም ያስፈራቸው ይኸው ነው:: በእርግጥ ቅናትም ይኖራል ሁሉ እርሱን ተከተሉት እያሉ ነበረና ህዝቡም ሊያነግሱት ፈልገው ነበረ:: ስለዚህ ስለህዝቡ አንድ ሰው ቢጠፋ ይሻላል ብለው አሳልፈው ሰጡት:: ለጥያቄውም ኢየሱስ “አንተ ይህን የምትለው ከራስህ ነውን ወይስ ሌሎች ስለ እኔ ነገሩህን?” አለው። እኔ አይሁድ አይደለሁ ነበረ መልሱ:: አሳልፈው ሰጡህ ብሎ ስልጣኑን ሊያሳየው ፈለገ::
ጲላጦስ በፊቱ የቆመውን አላወቀውም ለማወቅም የተስፋውን ቃል አያውቅም እሩቅ የሆነ አህዛብ ነው:: ከዚህ በፊት የነበረው ገዢ ግን ንጉስ እንደሚወለድ ከሰባ ሰገል አውቆ ህፃናትን አስፈጅቶ ነበረ ያንን ዘመን ቢያሰላና ታሪክ ቢያገላብጥ ይደርስበት ይሆናል:: መልሱ ግን እኔ አይሁድ አይደለሁ ነበረ:: የሆነ ሆኖ ኢየሱስም መልሶ፦ “መንግሥቴ ከዚህ ዓለም አይደለችም፤ መንግሥቴስ ከዚህ ዓለም ብትሆን፥ ወደ አይሁድ እንዳልሰጥ ሎሌዎቼ ይዋጉልኝ ነበር፤ አሁን ግን መንግሥቴ ከዚህ አይደለችም፡” አለው። ጴጥሮስ ሞክሮ ነበረ ግን ሎሌዎቼ የሚለው መልአክቱን ነበረ:: ለውጊያ የሚመጣበት ጊዜ አለ ዛሬ ግን በግ የመሆን ጊዜ ነው አንበሳ ሆኖ ሲመጣ ማን ይቆማል በፊቱ? ይህች መንግስት ምን ልታደርግ እንደምትችል አለማወቁ እንጂ ፍርድን በእጅ በግድግዳ ጽፎ በትል ተመቶ መሞትም አለ:: ሌላውንም በአምላኮቹ ፊት ሞተ ሰራዊቱም አለቀ:: ፈርኦንም ከነሰራዊቱ በባህር ሰጠመ:: ይህ ጌታ የሚለው መንግስት ከሁሉ በላይ ነው:: አሜን! ለዚህ መንግስት አምባሳደር አደረገኝ!
መቼ ንግስና ፈለገ እየሱስ? ሰይጣንም ስገድልኝና ይህንን ልስጥህ ብሎት ነበረ ነገር ግን እየሱስ ማንነቱንና የመጣበትን አላማ ያውቃል:: ከሙታን ሲያስነሳው በዚህ ዓለም ብቻ ሳይሆን በሚመጣውም ሁሉ ላይ ገዢና ጌታ ነው!! አሜን!
ጲላጦስ ማንን ልፍታ በዚህ ፋሲካ ቢላቸው በርባንን ብለው የመጀመርያው ወንበዴ ከሞት አመለጠ እኔም እርሱን የምመስል ወንበዴና ኃጥያተኛ ከሞት ወደ ህይወት መጣሁና እራሱን አልብሶኝ ጻድቅ ተብዬ ልጁም አድርጎኝ እመላለሳለሁ! ለታረደው በግ ንግስናና ክብር ይሁን! አሜን
አባት ሆይ ምን እላለሁ ስለወደድከኝ አመሰግንሃለሁ!
ዮሐንስ 19:1፤ በዚያን ጊዜም ጲላጦስ ኢየሱስን ይዞ ገረፈው።
እየሱስን ይዞ?!?!?!
ማንም ሊቀርበው በማይችል ብርሃን ውስጥ የሚኖረውን ሰውን ከአፈር ያበጀውን ጌታ ይዞ! የተያዘለት ግን ስለእኔ ነው!! ስሜቴ ድብልቅልቅ ብሏል አንድ ልቤ ምናለ ቢያመልጥ ይላል በሌላው በኩል ደግሞ እኔ መያዝና ይህንን ሁሉ ቅጣት ስለኃጥያቴ መቀበል ሲገባኝ እርሱ ለወጠኝ የሚለው ሃሳብ ይመጣብኛል:: መያዝ ብቻ አይደለም ገረፈው?! ወይ ጉድ ምንም አላገኘሁበትም እያለ እንደገና በዚህ ክፉ በሆነ መግረፊያቸው ገረፉት ምናልባትም ጲላጦስ በህይወት ሊለቀው ያሰበ ይመስላል:: እየሱስ ግን ለዚህ መጣ!
ይህ ገረፈው የሚለው ሃሳብ ቀላል ይመስላል ነገር ግን በዚህ ግርፋት ጀርባው ተተልትሏል እያንዳንዱ ግርፋት ሲያርፍበት ጀርባውን እየገሸለጠውና እያረሰው ነው የሚሄደው:: በመስቀል ላይ ወንበዴዎች ብዙ ጣር እንዳይዛቸው ያደርጋል እንዲሁም የሰሩትን ወንጀል ይናዘዛሉ እየሱስ ግን ምን አድርጏልና ይናዘዝ? በሰውም በእግዚአብሔርም ፊት አንዳች አልተገኘበትም:: በግርፊያው እዚሁ አዳክመው ነው ወደ መስቀል የሚወስዷቸው:: ነገር ግን እየሱስ ስለስጋዬ ፈውስ እንደዚህ ዋጋ ከፈለ:: ከዚህ ቃል እውነት ጋር እስማማለሁ!! በመገረፉ ቁስል ተፈውሻለሁ! እየሱስ እውነቴ እውነትም አርነት እንደሚያወጣ በዚህ እውነት አርነት ለስጋዬ ፈውስን አውጃለሁ! አሜን!
አባት ሆይ ነፍሴን ብቻ ሳይሆን ይህንንም ስጋዬን ማደርያህን ከበሽታ ስለፈወስከው አመሰግንሃለሁ!!
ዮሐንስ 19:2-5
5፤ ኢየሱስም የእሾህ አክሊል ደፍቶ ቀይ ልብስም ለብሶ ወደ ውጭ ወጣ።
ጲላጦስ እጅ ከገባ ጀምሮ ያደረጉበት:-
1. ወታደሮችም ከእሾህ አክሊል ጐንጕነው በራሱ ላይ አኖሩ:- የእሾክ አክሊል ደፍተው ቢያሾፉም እርሱ የምስጋናን ዘውድ ደፍቷል: በከፍታም ከብሯል! በራእይ 5:12፤ በታላቅም ድምፅ አሉ፦ “የታረደው በግ ኃይልና ባለ ጠግነት ጥበብም ብርታትም ክብርም ምስጋናም በረከትም ሊቀበል ይገባዋል። አሜን ይገባዋል!
2. ቀይ ልብስም አለበሱት፤ ይህ የዘመኑ የነገስታት አለባበስ ነው:: ለነገስታትም ንጉስ ነው ይህ ጌታ::
3. አላገጡበት:- የአይሁድ ንጉሥ ሆይ፥ ሰላም ለአንተ ይሁን፡” እያሉ:- በእርግጥም እርሱ የነገስታት ንጉስና የይሁዳ አንበሳ ሁሉን ድል የነሳ ነው:: አልፋና ኦሜጋ!
በጥፊም ይመቱት ነበር:- የመቱትምና የወጉት ያዩታል ያኔ ዋይ ከማለት ውጪ ምን ይሉ ይሆን?! በራእይ 6:16፤ ተራራዎችንና ዓለቶችንም፦ “በላያችን ውደቁ፡ በዙፋንም ከተቀመጠው ፊት ከበጉም ቍጣ ሰውሩን:: ይህንን ነው የሚሉት::
ይህንን ሁሉ የሆነው በምን እዳው ነው? የሰው ልጅ ይህንን ሁሉ ለራሱ መክፈል ሲገባው እርሱ ጣልቃ ገባ:: ፍቅር ጎትቶ ከዙፋኑ አመጣው!! ይህ ሁሉ ስለእኔ ነው!
ከዚህ ሁሉ በኃላ ጲላጦስም ደግሞ ወደ ውጭ ወጥቶ፦ “እነሆ፥ አንዲት በደል ስንኳ እንዳላገኘሁበት ታውቁ ዘንድ እርሱን ወደ ውጭ አወጣላችኋለሁ፡” አላቸው። ድሮስ ምን ያገኝበት ኖሯል?! ንጹህ በግ እራሱን በአባቱ ፊት መርምሮ ያቀረበ ሊቀ ካህን ነው:: ሊለቀው ስለፈለገና ህዝቡ እንዲራሩለት ፈልጎ ነበረ:: ለሮምም ሆነ ለመንግስቴ የሚያሰጋ አይደለም ነው ነጥቡ:: አላወክ ጉድህን ዝም ስላለ ናከው? የሚያደርገውን የሚያውቅ ጌታ ነው:: ገና በፊቱ ትቆማለህ!
አባት ሆይ ይህንን ሁሉ መንገላታትና መናቅ ስለ እኔ ተቀበልክ:: ምድርን በቃልህ ደግፈህ የያዝክ ጌታ አሾፉብህ ተዘባበቱብህ ገረፉህ በእሾህ ራስህን አጠሩት:: አንተ ግን እኛን ነፃ ለማውጣት መጥህ:: ተመስገን ጌታ ሆይ! እገዛልሃለሁ!
ዮሐንስ 19: 6-11
11፤ ኢየሱስም መልሶ፦ “ከላይ ካልተሰጠህ በቀር በእኔ ላይ ምንም ሥልጣን ባልነበረህም፤ ስለዚህ ለአንተ አሳልፎ የሰጠኝ ኃጢአቱ የባሰ ነው፡” አለው።
ጲላጦስ ገርፎ ሲያበቃ እየሱስን ወደ ውጪ አውጥቶ እነሆ ሰውየው አላቸው:: ይራሩለት እንደሆነ ብሎ አስቦ ይመስላል ነገር ግን መልሳቸው ስቀለው ነበረ:: ጲላጦስም፦ “እኔስ አንዲት በደል ስንኳ አላገኘሁበትምና እናንተ ወስዳችሁ ስቀሉት፡” አላቸው። አንዳች በደል በምድርም ህግ ፊት በአባቱም ፊት ያልተገኘበት ንጹ በግ! አይሁድም መልሰው፦ “እኛ ሕግ አለን፥ እንደ ሕጋችንም ሊሞት ይገባዋል፥ ራሱን የእግዚአብሔር ልጅ አድርጎአልና፡” አሉት።
አሁን ዋናው ክስ ታወቀ ስለዚህ ጲላጦስ ይህን ነገር በሰማ ጊዜ እጅግ ፈራ፤ የከሰሱት ንጉስ ልሁን ስላለ ሳይሆን ራሱን የእግዚአብሔር ልጅ አድርጎአልና ነው:: ይሄ ታድያ ከሮም ስርአት ጋር ምን አገናኘው?! የህጋቸውና የኃይማኖታቸው ጉዳይ ነበረ:: ዮሃንስ እዛው ስለነበረ እያንዳንዱን ነገር ዘገበው:: ግራ የተጋባው የሚስቱንም ህልም ያስታወሰው ጲላጦስም “አንተ ከወዴት ነህ?” አለው። ኢየሱስ ግን አንድ እንኳ አልመለሰለትም። ከዚህ በፊት መንግስቴ ከዚህ ምድር አይደለችም እንጂ ሎሌዎቼ ይዋጉልኝ ነበር ብሎ ነግሮት የለም እንዴ ለምን ደግሞ ይጠይቀዋል?!
ስለዚህ ጲላጦስ፦ “አትነግረኝምን? ልሰቅልህ ሥልጣን እንዳለኝ ወይም ልፈታህ ሥልጣን እንዳለኝ አታውቅምን?” አለው። ስልጣን? የምን ስልጣን? እየሱስ ነው እራሱን አሳልፎ በፈቃዱ የሰጠው እና የምን ስልጣን ነው ጲላጦስ የሚያወራው:: እየሱስ እንደሌሎቹ እስረኞች ለነፍሱ አለመነም ስልጣኑንም ፈርቶ አላጎበደደም ያደረገውም ዝምታን መረጠ:: ስልጣንማ ካለህ ፍታዋ ያለ ጥፋቱ እየተፈረደበት ያለውን እያየ ነገር ግን አልቻለም:: ታድያ ምን የሚሉት ስልጣን ነው ይሄ?! ጌታዬም ስልጣኑን ለማንም የማይሰጥ ጌታ ፦ “ከላይ ካልተሰጠህ በቀር በእኔ ላይ ምንም ሥልጣን ባልነበረህም፤ ስለዚህ ለአንተ አሳልፎ የሰጠኝ ኃጢአቱ የባሰ ነው፡” አለው።
ማንም በእርሱ ላይ ስልጣን የለውም ስልጣን ሁሉ የጌታዬ ነው:: ዛሬም ስልጣን በሚሆነው ሁሉ የጌታ ነው::
አባት ሆይ ተመስገን ስልጣን ሁሉ የአንተ ነው:: ስለተገደድህ መውጫ ስለሌለህ ሳይሆን ወደህ እራስህን አሳልፈህ ሰጠህ ምህረት ይደረግልኝ ንፁ ነኝም አላልክም:: በሸላቾችህ ፊት ዝም አልክ ስለእኔ! ምን እላለሁ ተባረክ!
ዮሐንስ 19: 12-15
15፤ እነርሱ ግን፦ “አስወግደው፥ አስወግደው፥ ስቀለው፡” እያሉ ጮኹ። ጲላጦስም፦ “ንጉሣችሁን ልስቀለውን?” አላቸው። የካህናት አለቆችም፦ “ከቄሣር በቀር ሌላ ንጉሥ የለንም፡” ብለው መለሱለት።
ከዚህ በኋላ ጲላጦስ ሊፈታው ፈለገ፤ ነገር ግን አይሁድ፦ “ይህንስ ብትፈታው የቄሣር ወዳጅ አይደለህም፤ ራሱን ንጉሥ የሚያደርግ ሁሉ የቄሣር ተቃዋሚ ነው፡” አስወግደው፥ አስወግደው፥ ስቀለው፡” እያሉ ጮኹ። አቤት አለማወቅ!
ጲላጦስም በፍርድ ወንበር ተቀመጠ:: ፈራጅ ሆነ በፈጠረው ላይ:: ምንም እንኳን ሊፈታው ቢፈልግም የካህናት አለቆችም፦ “ከቄሣር በቀር ሌላ ንጉሥ የለንም፡” ስቀለው አሉት::
ከዚህ በፊት ንጉስን አንግስልን ብለው ሲጠይቁ እግዚአብሔር እኔን ነው የናቁት አንግስላቸው ብሎ ነበረ:: አሁን ደግሞ የሮም ንጉስ ንጉሳችን ነው ማለታቸው የመጎብኛ ጊዜአቸውን አላወቁምና ከዓመታት በኃላ እየሩሳሌም ፈራረሰች:: የፈሩትም ደረሰ አንድ ሰው ስለህዝቡ ቢሞት ይሻላል ከምንበተን ነበረ ምክሩ ግን አልቀረላቸውም እስከ ዛሬ በየአገሩ ተበትነዋል:: እውነት ያንን ቀን ከትውልዱ መካከል ማን አስተዋለ?! አጋጣሚ ወይም እንደማንኛውም ቀን ነው የሚመስለው:: ይህ ጌታ ለእነርሱ መጥቶ ሳለ አለማወቅና አሳልፈው መስጠት?!
በመንፈሳዊው ዓለም ዛሬስ ምን እየተካሄደ ነው? አንተ የምትተኛ ንቃ ነው የሚለውን ቃሉ:: በትራንፕ ዙሪያ የተሰበሰቡት የቴክኖሎጂ ሰዎች ምን ይሆን ግባቸው እግዚአብሔር የሰጠንን መብት ሁሉ መቀማትና ለሃሰተኛው ክርስቶስ ማዘጋጀት? ምን እየተሰራ ይሆን አፍንጫችን ስር? እኛ ግን የተሰቀለውን ክርስቶስን እንሰብካለን አገራችንም በሰማይ ነው:: አያረጅብንም ንጉሳችን ነው ይመጣልናል:: ማራናታ!
አባት ሆይ ቶሎ ና! አሜን!
ዮሐንስ 19:16፤ ስለዚህ በዚያን ጊዜ እንዲሰቀል አሳልፎ ሰጣቸው።
በምዕራፉ መጀመርያ በመግረፍ የጀመረውን እንዲሰቅሉት አሳልፎ በመስጠት ፍርዱን አጠናቀቀ:: ጲላጦስ ያላወቀው ነገር ግን ይህ እፁብ ድንቅ ቅዱስና መልካም ጌታ እራሱን ባለመከልከል መስጠቱን ነው:: እንዲህ ባይሆንማ ማን ወንድ ይይዘው ነበረ? ሊይዙት ሲመጡ እኔ ነኝ ሲላቸው ሁሉም ወደኃላቸው ወደቁ:: መንግስቴ ከዚህ አይደለችም እንጂ ሎሌዎቼ ይዋጉልኝ ነበረ እንዳለው ነው:: አንድ መልአክ ለስንቱ ይበቃ ነበረ ነገር ግን ይህንን ሁሉ ማድረግና ማቆም እየቻለ አላደረገውም ስለዚህም እራሱን በፈቃዱ አሳልፎ ሰጠ!
የሮም ሰራዊት ወይም ጲላጦስ ወይንም ደግሞ ቄሳር ይህ እንዲሆን ስልጣን የላቸውም:: ጌታ ኢየሱስም እንዳለው፦ “ከላይ ካልተሰጠህ በቀር በእኔ ላይ ምንም ሥልጣን ባልነበረህም” ነው ያለው። በፈቃዱ እራሱን ሰጠ በፈቃዱ ነፍሱንም ሰጠ! ማንም አላስገደደውም ፈልጎና አውቆ ስለእኛ ይህንን አደረገ:: እዳችንን በሙሉ ከፈለ በእኛ ላይየቀረ የሚወራረድ እዳ የለም:: በክርስቶስ ላሉት አሁን ኩነኔ የለባቸውም:. አሜን!!!
አባት ሆይ እራስህን ስለሰጠኸን እናመሰግንሃለን!! ተባረክ በመስቀል ምጥ ልጅህ ስላደረከኝ ተመስገን:: ተባረክ! አሜን
ዮሐንስ 19: 17-27
18፤ በዚያም ሰቀሉት፥ ከእርሱም ጋር ሌሎች ሁለት፥ አንዱን በዚህ አንዱን በዚያ ኢየሱስንም በመካከላቸው ሰቀሉ።
እራሱን በመስቀል ላይ አሳልፎ ሰጠን!
ይህንን ዝማሬ ያስታውሰኛል:-
ጐልጐታ ፡ ትመስክር ፡ ቀራንዮ ፡ ትናገር
የጌታ ፡ ጣሩን ፡ የአኳሃኑን ፡ ነገር
ከዚህስ ፡ የሚበልጥ ፡ ፍቅር ፡ የለም
ከኢየሱስ ፡ የሚበልጥ ፡ ፍቅር ፡ የለም
ከአምላኬ ፡ የሚበልጥ ፡ ፍቅር ፡ የለም
ከጌታ ፡ የሚበልጥ ፡ ፍቅር ፡ የለም
ነፍሱን ፡ ስለእኔ ፡ የሚያሰጥ ፡ መውደድ
መስቀል ፡ አሸክሞ ፡ አስጐንብሶ ፡ የሚያስኬድ
የጌታዬን ፡ ፍቅር ፡ ምን ፡ ይመጥነዋል
ከምንም ፡ ከምንም ፡ ከምንም ፡ ይበልጣል::
አሜን!
በዚህ ክፍል ላይ የተፈጸሙ ትንቢቶች:-
በኢሳይያስ 53:12፤ . . . ከዓመፀኞችም ጋር ተቈጥሮአልና – ፃድቁ ጌታ እንደዚህ ተቆጠረ ስለእኔ! ወይ ፍቅር!
በ መዝሙር 22:18፤ ልብሶቼን ለራሳቸው ተከፋፈሉ፥ በቀሚሴም ላይ ዕጣ ተጣጣሉ።
እየሱስ ለዮሐንስ እናቱን አደራ ሰጠ:: እስከመጨረሻ ከእርሱ ጋር መዝለቅ የቻለ አንድ ደቀ መዝሙር እርሱ ብቻ ነው:: በዛ ስፍራ የተገኙት ሌሎቹ እናቱና ሴቶች ነበሩ:: ምን አይነት ታማኝነት ነው ያለው ዮሃንስ ሁሉ ጥለው ሲሸሹ እርሱ ግን አብሮት ዘለቀ:: ከዚህ በኋላ ደቀ መዝሙሩን፦ “እናትህ እነኋት፡” አለው። ከዚህም ሰዓት ጀምሮ ደቀ መዝሙሩ ወደ ቤቱ ወሰዳት። ታማኝ መሆን! ጌታ ፀጋውን ያብዛልን በመንፈስ እንጂ በብርታት ታማኝ መሆን አይቻልምና::
ጲላጦስም ደግሞ ጽሕፈት ጽፎ በመስቀሉ ላይ አኖረው፤ ጽሕፈቱም፦ “የአይሁድ ንጉሥ የናዝሬቱ ኢየሱስ፡” የሚል ነበረ። አይሁድም ይህንን ሲቃወሙ ጲላጦስም፦ “የጻፍሁትን ጽፌአለሁ፡” ብሎ መለሰ። እርሱ የአይሁድ ንጉስ ብቻ ሳይሆን የጲላጦስም የአይሁድ አለቆችም ሊሰቅሉት የተሰበሰቡትም ሁሉ እንዲሁም የዓለም ሁሉ ንጉስ ነው::
ጻድቅ አባት ሆይ ተመስገን በምን አይነት ፍቅር ወደድከን? እራስህን ስለኃጥያታችን ስለሰጠህና ለመስቀል ሞት ስለታዘዝክ እናመሰግናለን:: እኛም እንደዮሃንስ ታማኝ እንድንሆን ጸጋህን ስጠን በመንፈስ ቅዱስም አበርታን! አሜን
ዮሐንስ 19: 28-30
28፤ ከዚህ በኋላ ኢየሱስ አሁን ሁሉ እንደተፈጸመ አውቆ፡ የመጽሐፉ ቃል ይፈጸም ዘንድ፦ “ተጠማሁ፡” አለ።
30፤ ኢየሱስም ሆምጣጤውን ከተቀበለ በኋላ፦ “ተፈጸመ፡” አለ፥ ራሱንም አዘንብሎ ነፍሱን አሳልፎ ሰጠ።
የጌታ የእየሱስ የመጨረሻው ሰዓታት ስቃይ የበዛበት ዮሃንስ ባይዘግበውም አባት ሆይ ለምን ተውከኝ እያለ የለመነበት ነበር:: ከዚህም በኃላ ተጠማሁ አለ አንዳንዶች ተወው ኤልያስ መቶ ይርዳው እያሉ አፌዙበት አንድ ሰው ግን ቆምጣጤን ሰጠው:: ኢየሱስም ሆምጣጤውን ከተቀበለ በኋላ፦ “ተፈጸመ፡” አለ፥ ራሱንም አዘንብሎ ነፍሱን አሳልፎ ሰጠ::
ተፈጸመ ሲል ህመምን በኃጥያት መከሰስን ከእግዚአብሔር ጋር የነበረው ጠብ መነሳቱን የብሉይ ኪዳን የህግ ዘመን ማለፉንና አዲስ ኪዳን የፀጋ ዘመን መሆኑን ሁሉ ያወጀ ነው:: በትንቢት የተፃፈውን ሁሉፈጸመው:: በምድርም አባቱን አከበረና ታዘዘ ለእኛም ማምለጫ መንገድ ሆነልን! አቤትእንዴት ያለ ፍቅር ነው ይሄ!!! እራሱን በፈቃዱ ሰጠ! ሌሎች እንደዘገቡት ፀሃይ ብርሃንዋን ከለከለች የቤተክርስቲያን መጋረጃም ከላይ ወደታች ተቀደደ ቅድስተ ቅዱሳን በምድር የለም በሰማይ እንጂ ወደ እዛም እየሱስ አንድ ጊዜ ደሙን እያንጠባጠበ ገባ:: በእየሱስ ማለትም በስጋው በኩል እኛም ገብተናል ወደ አብ! ሃሌሉያ!!
አባት ሆይ በክርስቶስ ያለነው ኩነኔ የለብንም እየሱስ ስለእኛ እራሱን ሰቷልና! ተመስገን አባት ሆይ ወደ አንተ መቅረብ ችለናልና በፊትህም ካህንነት ለማጠን ተሰቶናልና ተባረክ! ምስጋንና አምልኮን ወደፊትህ አመጣለሁ!
ዮሐንስ 19: 31-42
33፤ ወደ ኢየሱስ በመጡ ጊዜ ግን እርሱ ፈጽሞ እንደ ሞተ አይተው ጭኑን አልሰበሩም፤
ዮሐንስ 19:34፤ ነገር ግን ከጭፍሮች አንዱ ጎኑን በጦር ወጋው፤ ወዲያውም ደምና ውኃ ወጣ።
አይሁድም የማዘጋጀት ቀን ስለ ሆነ ያ ሰንበት ትልቅ ነበረና ሥጋቸው በሰንበት በመስቀል ላይ እንዳይኖር፥ ጭናቸውን ሰብረው እንዲያወርዱአቸው ጲላጦስን ለመኑት። ለምን ይሆን ይህ ሰንበት ትልቅ የሆነው? ከግብጽ የጥፋት ልጅ እንዳያገኛቸው ያመለጡበት ስለነበረም አይደል? የበጉን ደም በበራቸው ስላደረጉ የግብፅ በኩር ሁሉ ሲሞት በእስራኤሎች ዘንድ ግን ሞት ተከለከለ:: ይህ በብሉይ ጥላ የነበረው አሁን በፊታቸው ፋሲካቸው እየሱስ እየፈፀመው መሆኑን አላስተዋሉም:: ሞታቸውን የሚሞተው የእግዚአብሔር በግ አላወቁትም! ከጌታ ጋር የተሰቀሉትን ጭን ሲሰብሩ በትንቢት እንደተነገረው የእርሱን ግን አልሰበሩም ምክንያቱም እርሱ በፈቃዱ ነፍሱን ሰቶ ስለነበረ ሞቶ ነው ያገኙት:: እነሱ ቢገድሉትማ በፈቃዱ አልሰጠም ነበረ ነገር ግን ያለ ማንም ተጽዕኖ እርሱ ነፍሱን ሰጠ!
የወጉት ሁሉ ያዩታል የሚለው ወደፊት የሚፈፅም ሲሆን እስከአሁን ከቃሉ አንዳች ስላልጎደለ በእርግጥ ይህ ከጭፍሮች አንዱ ጎኑን በጦር የወጋው ጌታን ያያል:: ሲወጋው የወጣው ደምና ውኃ ነበረ ከተለመደው ደንብ እግርን ከመስበር መሞቱን ለማረጋገጥ አድርጎትም ይሆናል::
ሌላው በስተመጨረሻ የተገኙትና ስጋውን ያሳረፉት በድብቅ ደቀመዝሙር የነበረው የአርማትያሱ ዮሴፍና በለሊት የመጣው ኒቆዲሞስ ነበሩ:: ዮሴፍ የእየሱስን ስጋ አስፈቀደ ኒቆዲሞስ ደግሞ ከርቤና የእሬት ቅልቅል ይዞ መጣና በወጋቸው ገነዙትና ማንም ባልተቀበረበት አዲስ መቃብር ውስጥ አኖሩት:: መቃብሩ ከባለፀጎች ጋር መቃብሩ ሆነ እንደሚለው ትንቢት መሰረት ሆነ::
አባት ሆይ አመሰግንሃለሁ! ይህንን እውነት እንድገነዘብና በእየሱስ ሞት መዳኔን እንዳውቅ ስለረዳኸኝ ተመስገን! የእግዚአብሔር በግ እየሱስ ስለእኔና ስለሰውልጅ ሁሉ እንደዚህ ዋጋ ከፍለሃልና ተመስገን! ሃሌሉያ!
ዮሐንስ 20:1፤ ከሳምንቱም በፊተኛው ቀን መግደላዊት ማርያም ገና ጨለማ ሳለ ማለዳ ወደ መቃብር መጣች ድንጋዩም ከመቃብሩ ተፈንቅሎ አየች።
ገና ጨለማ ሳለ በማለዳ መቅደላዊት ማርያም ፍለጋ መጣች ቢለንም ዮሃንስ በሌሎቹ ወንጌሎች ግን ሌሎች እህቶችም ነበሩ:: ምናልባት እዛ እንገናኝ በማለዳ ተባብለው እርስዋ ቀድማ መጥታ ይሆን? የእነዚህ ሴቶች ትጋትና ፍቅር ምን አይነት ነው? ከተያዘ ጀምሮ በኃዘን ነበረ የከረሙት በእውነትም የሚፈልጉት ያለ ህግ በግፍ መገደሉን የሚያውቁ እህቶች:: ፍቅራቸውን ሊገልጹ መጡ የከበረ ነገር ለማብሰር ፊተኞች ሆኑ:: ዮሴፍና ኒቆዲሞስ ካቆሙበት አገልግሎታቸውን ቀጠሉ:: እርሱም ማብሰር!
በደረሰችበት ሰዓት ብዙ ነገር ተፈጽሟል ያ ሁሉ ጣርና ጭንቅ የከሳሾቹም ማሽሟጠጥና ማሰቃየት አልፎ እየሱስ መቃብሩን ፈነቃቅሎ ተነስቷል!!! እነርሱም መተው ድንጋዮን እንዲያንከባልሉለት አልጠበቀምም አላስፈለገውምም!!! ድንጋዮን ፈነቃቅሎ ተነሳ ሞት እንደለመደው ሁሉን ገቢ አድርጎ እንደሚይዘው ሊይዘው አልቻለም:: የእግዚአብሔርም የብርታቱ ጉልበት የታየበት ትንሳኤ ሆነ! ሞትና ሲኦል መውጊያቸውን ተነጠቁ:: እርሱ ሲነሳ እኛም አብረን ተነሳን:: ሃሌሉያ!
አባት ሆይ ተመስገን ስለ ትንሳኤው ኃይል የሞትን ጣር አጥፍተህ ኢየሱስን አስነሳኸው! ይህ የትንሳኤው ኃይል በእኔ ላይ ይምጣና እየሱስን ያሳይ! አሜን! በእኔም ውስጥ ትጋትን ጨምርልኝ! አሜን
ዮሐንስ 20:2፤ እየሮጠችም ወደ ስምዖን ጴጥሮስና ኢየሱስ ይወደው ወደ ነበረው ወደ ሌላው ደቀ መዝሙር መጥታ፦ “ጌታን ከመቃብር ወስደውታል ወዴትም እንዳኖሩት አናውቅም፡” አለቻቸው።
ኢየሱስ ሞትን አሸንፎ ትንሳኤ ሆንዋል ተከታዮቹ ግን አላወቁም የተናገራቸውንም ቃል አላስተዋሉም:: ስንት ጊዜ ነበር እንደሚነሳ የነገራቸው? ማርያም ከእግሩ ስር የማትነሳ የተሻለውን መረጠች የተባለች ሆና ሳለ ስለትንሳኤው ረሰታ ፦ “ጌታን ከመቃብር ወስደውታል ወዴትም እንዳኖሩት አናውቅም፡” ብላ ለጴጥሮስና ዮሃንስ ነገረቻቸው:: እነሱም እዛው ጋር አለቀንዋትም:- እነሳለሁ ብሏል አታስታውሺም ማለት ነበረባቸው:: እነሱም ለዜናው እንግዳ ሆነው ወደ መቃብር ስፍራ ሮጡ:: ህያውን ከሙታን መካከል ሊፈልጉ::
የማርያም ነገር አይግረመን ብዙዎቻችን በዚህ ውስጥ እየዳከርን እንገኛለን:: ዛሬም ማስተዋል ይሁንልን ጌታ የሚናገረውን እናስተውል እንጂ ሰምተን የምንረሳ አንሁን:: ምን ተስፋ ሰቶናል? ከተናገረ ይፈጽማል እርሱ በጊዜ አይወሰንም ዘገየ ብለንም መስጋት የለብንም መታመን ብቻ ነው ያለብን:: እርሱን ለሚወዱት እንደ አሳቡም ለተጠሩት ነገርሁሉ ለበጎ ይደረጋልና::
ጻድቅ አባት ሆይ ክብር ለአንተ ይሁን ዛሬም በስራ ላይ ነህ:: በመንፈስ ቅዱስ ማስተዋልን ስጠኝ:: አንተ ስትናገር የሚሰማና የሚያደምጥ ጆሮ የሚያስተውል ልብን ስጠኝ! ቃልህ ከእኔ ጋር በእምነት ይዋሃድና ይጥቀመኝ:: አሜን!
ዮሐንስ 20: 3-10
3፤ ስለዚህ ጴጥሮስና ሌላው ደቀ መዝሙር ወጥተው ወደ መቃብሩ ሄዱ።
9፤ ከሙታን ይነሣ ዘንድ እንዲገባው የሚለውን የመጽሐፉን ቃል ገና አላወቁም ነበርና።
ጴጥሮስና ዮሃንስ “ጌታን ከመቃብር ወስደውታል ወዴትም እንዳኖሩት አናውቅም፡” የሚለውን ዜና ከማርያም ሲሰሙ ወደ መቃብሩ ሮጡ:: በዓይናችን ሳናይ ያልሽውን አናምንም የሚሉ ይመስላል:: ደርሰውም በመቃብር አለመኖሩን አረጋገጡ :: የተከፈነበትም ጨርቅና በጭንቅላቱም ተጠምጥሞ የነበረው ጨርቅ ተቀምጠው አገኙ:: ግን ሰው ቢወስደው መገነዙን ለምን ይፈታል ብለው እንኳን አላሰቡም:: የማርያምን ዜና ካረጋገጡና ካመኑ በኃላ ግን ወደ ቤታቸው ነው የሄዱት:: እየፈረድኩኝ አይደለም እራሴን በነሱ ውስጥ እያየሁኝ ነው:: የመንፈስ ነገር በመንፈስ ነው የሚገባው::
ከሙታን ይነሣ ዘንድ እንዲገባው የሚለውን የመጽሐፉን ቃል ገና አላወቁም ነበርና ይላል ቃሉ:: እነርሱ ከሙታን መካከል እየፈለጉት ነው እርሱ ግን የኤማኦስን መንገደኞች እየመለሰ ሁሉንም እያገደ ያለ ከሞት የተነሳ እረኛ ነበረ:: ሁሉንም ወደ ቀጠሮ ቦታ እየጠራ ያለ ታጋሽ ጌታ:: ይህንን ሁሉ ጊዜ አስተምሬያቸው የታሉ? በአንድ ቦታ ተሰብስበው እንኳን መጠበቅ አቃታቸው እኔ ይህንን ሁሉ አድርጌ?! አላለም:: መጽሐፍትን ገለጠላቸው እንጂ! ታግሶ ሰበሰባቸው! ዋዉ! ሲያገኛቸውም ሰላም ለእናንተ! ነበረ ያላቸው እንጂ ወደ መወቃቀስም አልሄደም::
እራሱ እየሱስ እየተገለጠ መነሳቱን ያበስራቸው ጀመረ:: መንፈስ ቅዱስ ስላልወረደ የጠለቀውን የእግዚአብሔርን መንግስት መረዳት አልቻሉም ምንም እንኳን ሶስት ዓመት ተኩል ከእርሱ ጋር ሲመላለሱ የቆዮና የተማሩ ቢሆንም አላስተዋሉም ይላል:: ዛሬም መንፈስ ቅዱስ ወደ እውነት ሁሉ ይመራናል ቃሉንም ይተረትርና ማስተዋልን ይሰጠናል::
አባት ሆይ ተመስገን! ስምህ ይባረክ! አንተ ታጋሽና ርሁሩህ ጌታ ነህ:: የምትለውን የምንረዳበትን ጸጋ ስጠን:: መንፈስ ቅዱስ የምትናገረውን ማስተዋል ይሁንልን በራሳችን እንዳንመካና የአንተን ነገር ችላ እንዳንል እርዳን!
ዮሐንስ 20: 11-16
11፤ ማርያም ግን እያለቀሰች ከመቃብሩ በስተ ውጭ ቆማ ነበር። ስታለቅስም ወደ መቃብር ዝቅ ብላ ተመለከተች፤
ደቀ መዛሙርቱ ወደ ቤታቸው ሲሄዱ ማርያም ግን እዛው እያለቀሰች ቆየች:: ያስተማራቸውን ቃሉን ባይዘነጉ እዚህ ሁሉ ውስጥ ባልገቡ ነገር ግን የእውነት መንፈስ ሲመጣ ሁሉን ማስተዋል ቻሉ:: ሐዋርያቱን የጠራቻቸው መጀመርያውንም እንዲረድዋት ነበር እነርሱ ግን ወደቤታቸው ሲሄዱ መልስ ሳላገኝ አልሄድም ብላ እዛው ቆይታ መልስን አገኘች:: ምን አይነት ፍቅር ነው?! በዚህም መሃል ወደ መቃብር ዝቅ ብላ ተመለከተች፤ ሁለት መላእክትም ነጭ ልብስ ለብሰው የኢየሱስ ሥጋ ተኝቶበት በነበረው አንዱ በራስጌ ሌላውም በእግርጌ ተቀምጠው አየች። እነዚህ መልአክት መቼም መቃብሩን እየጠበቁ አይደለም ባዶ ነው ምኑን ይጠብቁታል? ለእርስዋ መልክት ይዘው ነበረና “አንቺ ሴት፥ ስለ ምን ታለቅሻለሽ?” አሉአት። እርስዋም፦ “ጌታዬን ወስደውታል ወዴትም እንዳኖሩት አላውቅም፡” አለቻቸው። መልአክት መሆናቸውን እንኳን አልደነቃትም ወይም አላስተዋለችም የምትፈልገው ጌታዋን ብቻ ነው:: እርስዋ በኃዘንዋ ውስጥ ናት በራስዋ ነገር ተይዛለች:: በተለያየ ነገር ተይዘን ጌታን ሳንሰማው እንዳንቀር ጌታ ይርዳን::
ነገር ግን ይህንም ብላ ወደ ኋላ ዘወር ስትል ኢየሱስን ቆሞ አየችው፤ ኢየሱስም እንደ ሆነ አላወቀችም። እስዋ ብቻ ሳትሆን የኤማኦስም መንገደኞች አብሯቸው ተጉዞም አላወቁትም:: የኃዘንዋን ጥልቀት ያየው ጌታ መልአክቱ የጠየቁትን መልሶ ጠየቃት “አንቺ ሴት፥ ስለ ምን ታለቅሻለሽ? ማንንስ ትፈልጊያለሽ?” አላት። እርስዋም የአትክልት ጠባቂ መስሎአት፦ “ጌታ ሆይ፥ አንተ ወስደኸው እንደ ሆንህ ወዴት እንዳኖርኸው ንገረኝ እኔም እወስደዋለሁ፡” አለችው። አቤት?!የምትገርም ሴት ናት ስጋውን ስጡኝ ለኔ የከበረ ነው የት ወሰዳችሁት? እያለች የፍቅርዋን ትወተውታለች የጥያቄዋ መልስ ስጋውን የምትጠይቀው እራሱ እየሱስ በፊትዋ ቆሟል:: መልሳችን በፊታችን እንዳይሆን ብቻ የእኛ ሃሳብ በብዙ ተይዞ እንዳንሸዋወድ::
ወድያውም ኢየሱስ፦ “ማርያም፡” አላት። እርስዋ ዘወር ብላ በዕብራይስጥ፦ “ረቡኒ፡” አለችው፤ ትርጓሜውም፦ “መምህር ሆይ፡” ማለት ነው። ያን ጊዜ አወቀችው! ጌታ ማስተዋል ይስጠን:: የእግዚአብሔር ነገር በመንፈስ ነው:: ይህ መልካም ጌታ ካለችበት ሊያወጣት እርስዋን ጠበቀ:: ይገርማል! በስማችን የሚያውቀን እረኛ አይፈርድብንም ባለንበት ይገናኘናል::
አባት ሆይ አንተ መልካም ነህ መንፈሳዊዉን ነገር በስጋ ለመረዳት እንዳንሞክር እርዳን:: ማስተዋልንም ስጠን:: መንፈስ ቅዱስ በአንተ ላይ መደገፍ ይብዛልን:: አሜን
ዮሐንስ 20: 17-18
17፤ ኢየሱስም፦ “ገና ወደ አባቴ አላረግሁምና አትንኪኝ፤ ነገር ግን ወደ ወንድሞቼ ሄደሽ፦ እኔ ወደ አባቴና ወደ አባታችሁ ወደ አምላኬና ወደ አምላካችሁ ዓርጋለሁ፡ ብለሽ ንገሪአቸው፡” አላት።
ሐዋርያቱ ቢሄዱም ማርያም እዛው ቆይታ መልስዋን አገኘች:: በዮሐንስ 11:25፤ ኢየሱስም አላት፦ “ትንሣኤና ሕይወት እኔ ነኝ፤ የሚያምንብኝ ቢሞት እንኳ ሕያው ይሆናል ብሏት አምና የሞተው ወንድሟ ተነስቷል:: ይሄንና እነሳለሁ ያለውን ቃል ብታስተውል ኖሮ እንደዚህ በኃዘን ውስጥ አትሆንም ደግሞም እርሱ በሌለበት ስፍራ ከሙታን መካከል ትንሳኤና ህይወት የሆነውን አትፈልግም ነበር:: የሚለንን ዛሬም በመንፈስ ቅዱስ ኃይል ማስተዋል ይሁንልን ቃሉም በእምነት ከእኛ ጋር ተዋህዶ ይጥቀመን::
የአትክልት ጠባቂ የመሰላት እየሱስ ግን ስምዋን ሲጠራ ነቃችና ረቡኒ አለችው:: እርሱም ገና ወደ አባቴ አላረግሁምና አትንኪኝ አላት:: ምናልባትም ገና እንደተነሳ ነው የደረሰችው ስለዚህም አትንኪኝ አላት:: በአብ ፊት ደሙን እያንጠባጠበ የታረደው በግ ሊገባና ስለ እኛ ሊታይ ይገባዋል:: ወድያውም ተመልሶ ሐዋርያቱን መሰብሰብ ይጀምራል ገና አብሯቸው አርባ ቀን ይቆይ የለ::
ለማርያምም:- “ወደ ወንድሞቼ ሄደሽ” ተብላ የትንሳኤው አብሳሪ ሆነች:: በዘመኑ ፍርድ ስርአት ውስጥ ሴት ለምስክርነት አትበቃም ጌታ ግን ላካት ወንድ የለም ሴት የለም ደሃ የለም ሃብታም የለም ሁሉ በክርስቶስ አንድ ነው:: ምናልባትም እርስዋ ልትናገር ስትሄድ ሌሎቹ እህቶች መተዋል ምክንያቱም በማቴዎስ 28:9፤ እነሆም፥ ኢየሱስ አገኛቸውና፦ “ደስ ይበላችሁ፡” አላቸው። እነርሱም ቀርበው እግሩን ይዘው ሰገዱለት። እርስዋን ከልክሎ ለሌሎች መፍቀዱ አይመስልም ተመልሶ መቶ ይሆናል ብዬ እላለሁ::
የላከው መልእክት:- ” እኔ ወደ አባቴና ወደ አባታችሁ ወደ አምላኬና ወደ አምላካችሁ ዓርጋለሁ፡ ብለሽ ንገሪአቸው፡” አላት።” ከዚህ መልክት የምንረዳው አብ የእየሱስ አባት ብቻ ሳይሆን የእኛም መሆኑንና ልጅ መሆናችንን ይገልፃል:: በግልፅ ጌታ አወጀ ወደ አባታችሁ ብሎ:: እንዲሁም ወደ አምላካችሁ! አሜን! እርሱ አባትና አምላካችን ነው:: መግደላዊት ማርያም መጥታ ጌታን እንዳየች ይህንም እንዳላት ለደቀ መዛሙርቱ ነገረች። እየሱስ ተነስቷል! የሞትንና የሲኦልን ቁልፍ ይዟል የሚጎዳንም የለም::
አባቴና አምላኬ ሆይ ተመስገን! ጌታዬ እየሱስ ሆይ በአብ ፊት ስለታየህልኝ አመሰግናለሁ:: መንፈስ ቅዱስ የምትለኝን ሁሉ እንድሰማና ቃሉም ከእኔ ጋር እንዲዋሃድ እንድታዘዝም እርዳኝ! አሜን!
ዮሐንስ 20: 19-20
19፤ ያም ቀን እርሱም ከሳምንቱ ፊተኛው በመሸ ጊዜ፥ ደቀ መዛሙርቱ ተሰብስበው በነበሩበት፥ አይሁድን ስለ ፈሩ ደጆቹ ተዘግተው ሳሉ፥ ኢየሱስ መጣ፤ በመካከላቸውም ቆሞ፦ “ሰላም ለእናንተ ይሁን፡” አላቸው።
ያም ቀን እርሱም ከሳምንቱ ፊተኛው እየሱስ ከሙታን የተነሳበት ቀን ምን አይነት ቀን ነው? የሰው ልጆች ታሪክ የተለወጠበት!
ደቀ መዛሙርቱ ተሰብስበው በነበሩበት፥ አይሁድን ስለ ፈሩ ደጆቹ ተዘግተው ሳሉ፥ ኢየሱስ መጣ! አቤት ሲያዩት ደስታ በህይወት ስላለ እፍረት ጥለውት ስለጠፉ:: ድብልቅልቅ ያለ ስሜት ያለበት ክፍል ነው:: በሮቹ ተዘግተው ተቆልፈው ሳሉ በር ማንኳኳት የማይጠበቅበት ጌታ በመካከላቸው ቆመ:: ቀኑን ከማርያም ከሌሎችም እህቶችና ከኤማኦስ መንገደኞችጋር አሳልፎ ማምሻውን ደግሞ እዚህ በመካከላቸው መጣ:: ጌታ በስራ ላይ ነው ጊዜ አያባክንም:: ጌታ በመካከላቸው ሲቆም አስሩንም እያስነሳ የሚወቅሳቸው መስሏቸው ነበረ እርሱ ግን አልወቀሳቸውም ምንም እንዳልተፈጠረ በዛው በፍቅሩ ቀረባቸው:: ስለእነሱ ማልዶም ነበረ ይህም እንደሚሆን ያውቅ ነበረ ምንም አዲስ ነገር አልተፈጠረም::
በመካከላቸውም ቆሞ፦ “ሰላም ለእናንተ ይሁን፡” አላቸው እንጂ ሌላ አላለም እንዴት ልብን ይፈውሳል? የጠበቁት ሌላ የሆነው ሌላ:: ጌታቸውን በህይወት አግኝተው ሰላማቸውም ተመልሰ:: እነዚህ በር ዘግተው ፈርተው የተቀመጡ ወገኖች አንበሳ ሲሆኑ እናያለን ከመንፈስ ቅዱስ የተነሳ::
ይህንም ብሎ እጆቹንም ጎኑንም አሳያቸው። ደቀ መዛሙርቱም ጌታን ባዩ ጊዜ ደስ አላቸው። እንዴት ደስ አይላቸው ይህንን ጌታ በመካከላቸው ሲያገኙ?! ስለ እኔ ነው የተወጋኸው ተመሰገን ከዚህም የተነሳ ታሪክ ተለወጠ ሞትና ሲኦል ተሻሩ ፤ የኃጥያት ባርያ መሆን ተሻረ ፤ የዘለላ ም ህይወት ተሰጠን! ሀሌሉያ!
ጌታ ሆይ ተመስገን የኃጥያቴን እዳ ስለከፈልክልኝ:: ስለወደድከኝ ተመስገን ሰላምህን ስለ ሰጠኸኝ ተባረክ! አሜን!
ዮሐንስ 20: 21-23
ኢየሱስም ዳግመኛ፦ “ሰላም ለእናንተ ይሁን፤ አብ እንደ ላከኝ እኔ ደግሞ እልካችኋለሁ፡” አላቸው። ሰላሙን አስታጥቆ እርሱ እንደተላከው ልኮናል:: እኛ የሰማይ መንግስት አምባሳደሮች ነን:: ተልእኮውንም የተቀበልነው ከራሱ ከጌታ ነው:: እርዳን አባት ሆይ የላከንን ፈጽመን እንድናከብርህ በሰውም ፊት እንዳናፍር ነገር ግን እንድንገልጥህ እርዳን::
ስንላክም “መንፈስ ቅዱስን ተቀበሉ እንዳለው በመንፈስ ቅዱስ ተሞልተን መውጣት አለብን ምክንያቱም በኃይልም በብርታትም አይደለም በመንፈሴ ብሎናልና:: መንፈሱንም ሳይሰስት በልግስና ይሰጠናል:: ዕለት ዕለትም በመንፈስ ተሞሉ ተብለናልና መፈለግና መጠማት ካለ እርሱ ይሞላናል::
ኃጢአታቸውን ይቅር ያላችኋቸው ሁሉ ይቀርላቸዋል፤ የያዛችሁባቸው ተይዞባቸዋል፡” አላቸው። ይህንን በሁለት አቅጣጫ እረዳለሁ አንዱም የበደሉንን ይቅር ማለትና የሰዎችን ኃጥያት አለመያዝ ሲሆን ሌላው ወንጌልን እየሰበክን የእግዚአብሔር መንግስት ቀርባለችና ንስሃ ግቡ እያልን ሰዎች ከነኃጥያታቸው እንዳይኖሩ መርዳት:: ከላይም ሂዱ ብሎ ሲልከን ከእግዚአብሔር ጋር ታረቁ የምንል አምባሳደሮች ነን:: ይቅር የሚልና ከመንግስቱ የሚወልዳቸው እራሱ ጌታ ነው::
አባት ሆይ ተመስገን መንፈስህን ስላስታጠከን:: እየሱስ በምድር የሰጠኽኝን ፈጽሜ አከበርኩህ እንዳለና ምሳሌውን እንደተወልን እኛም በምድር እናክብርህ ሂዱ እንደተባልን የምንሄድና ምስራቹን የምናበስር አድርገን:: አባት ሆይ ዛሬ ም ብፊትህ ነንና በመንፈስህ ሙላን::
ዮሐንስ 20: 24-31
27፤ ከዚያም በኋላ ቶማስን፦ “ጣትህን ወደዚህ አምጣና እጆቼን እይ፤ እጅህንም አምጣና በጎኔ አግባው፤ ያመንህ እንጂ ያላመንህ አትሁን፡” አለው።
29፤ ኢየሱስም፦ “ስለ አየኸኝ አምነሃል፤ ሳያዩ የሚያምኑ ብፁዓን ናቸው፡” አለው።
ከሐዋይያት አንዱ ቶማስ ጌታ ለሌሎቹ ሲገለጥና እፍ ብሎ “መንፈስ ቅዱስን ተቀበሉ” ብሎ ሲባርካቸው አልነበረምና ተነስቷል ብሎ ለማመን ቸገረው:: እንዲያውም ከማመን ይልቅ “የችንካሩን ምልክት በእጆቹ ካላየሁ ጣቴንም በችንካሩ ምልክት ካላገባሁ እጄንም በጎኑ ካላገባሁ አላምንም፡” አላቸው። የተቀሩት ተነስቷል አልተነሳም ላይ አይደሉም:: ቶማስ ግን አልተቀበለም:: በስጋ ነው እያሰበ ያለው አእምሮአችን ካልታደሰና በመንፈስ ቅዱስ ካልታገዝን የእግዚአብሔርን ነገር ማወቅ አይቻልም:: ማየት ማመን ቢሆንም ከማየታቸው ባሻገር ትእዛዝን ተቀበሉ ወንጌል ለመስበክ እርሱ ግን ይህንን ጉብኝት አላገኘም ገና:: ያለ እምነት እግዚአብሔርን ደስ ማሰኘት አይቻልም:: እምነትም ከእግዚአብሔር አይጨመርም የሚመጣው ህያው ቃሉን ከመስማት ነው::
እንደተለመደው ደጆች ተዘግተው ሳሉ ኢየሱስ መጣ፤ በመካከላቸውም ቆሞ፦ “ሰላም ለእናንተ ይሁን፡” አላቸው። ምንም እንኳን አየሩ ደፍርሶ ቢመጣም አላምን ብሎ ያስቸገረ ቢኖርም እርሱ አሁንም ሰላም ለእናንተ ብሎ በመካከላቸው ቆመ:: ምን አይነት እረኛ ነው?! የሚረዳን የማይፈርድብን ታጋሽና ርህሩህ! ከዚያም በኋላ ቶማስን፦ “ጣትህን ወደዚህ አምጣና እጆቼን እይ፤ እጅህንም አምጣና በጎኔ አግባው፤ ያመንህ እንጂ ያላመንህ አትሁን፡” አለው። አምነን እንድንከተለው ነው ጌታ የሚፈልገው:: አለ ማመንም ማመን ነው:: እንደቃሉ ማሰብ ይሁንልን:: በዕብራውያን 11:1፤ እምነትም ተስፋ ስለምናደርገው ነገር የሚያስረግጥ፥ የማናየውንም ነገር የሚያስረዳ ነው። እንመን!
ቶማስም፦ “ጌታዬ አምላኬም፡” ብሎ መለሰለት። ኢየሱስም፦ “ስለ አየኸኝ አምነሃል፤ ሳያዩ የሚያምኑ ብፁዓን ናቸው፡” አለው። ቶማስን ግድ የለም ባታምን አላለውም ማመንና መከተል አስፈላጊ ነው:: በሚያምኑ ሰዎች እየሱስ እንዴት እንደተደነቀ እናስብ ሌላው የሰው ልጅ ሲመጣ እምነትን ያገኝ ይሆንን የሚለውንም አንርሳ:: እኛ ግን ባናየውም አምነነዋል!
ኢየሱስም በዚህ መጽሐፍ ያልተጻፈ ሌላ ብዙ ምልክት በደቀ መዛሙርቱ ፊት አደረገ፤ ነገር ግን ኢየሱስ እርሱ ክርስቶስ የእግዚአብሔር ልጅ እንደ ሆነ ታምኑ ዘንድ፥ አምናችሁም በስሙ ሕይወት ይሆንላችሁ ዘንድ ይህ ተጽፎአል። በቂ ቃል ተሰቶናል አላማውም አንድና አንድ ነው በእየሱስ አምነን እንድንድን!!
አባት ሆይ ክበር ተመስገን:: ሰላም ለእናንተ የምትል ጌታ ተባረክ! ስለተሰጠን ቃል ተባረክ! አሁንም ድንቅና ተአምራት ታደርጋለህ አላረጀህም አልተቀየርክም! አሜን!
ዮሐንስ 21: 1-14
5፤ ኢየሱስም፦ “ልጆች ሆይ፥ አንዳች የሚበላ አላችሁን?” አላቸው። “የለንም፤” ብለው መለሱለት።
ጌታ እየሱስ አብሯቸው በነበረበት ጊዜ በገንዘብ የሚደግፉ ሰዎች ነበሩ አሁን ግን ደጋፊ የሌላቸው ሐዋርያት ለመስራት ወጡ:: እየሱስ ነው ገሊላ እንገናኝ ብሎ የላካቸው ስለዚህ እየጠበቁ እያለ ለኑሮአቸውም መስራትን ጀመሩ:: ወደ ሰባት ደቀ መዛሙርት በተገኙበት እዛው እየሰሩ ባለበት ስፍራ ጌታ ለሶስተኛ ጊዜ ተገለጠ:: እነርሱ ለሊቱን ሙሉ ለፍተው ምንም አሳ አልያዙምና እንደቀደመው “መረቡን በታንኳይቱ በስተ ቀኝ ጣሉት ታገኙማላችሁ፡” አላቸው።
በጣሉትም ጊዜ እጅግ ብዙ አሳ ያዙ መረቡም አልተቀደደም ይላል:: ይህ ሁሉ ሲሆን አላወቁትም ምክንያቱም በደንብ አልነጋ ይሆናል ደግሞም ባህሩ ላይ ነበሩ እርሱ ግን ዳሩ ላይ ነበረና እርቀቱምተጽእኖ ይኖረዋል:: ወደ ምድርም በወጡ ጊዜ ፍምና ዓሣ በላዩ ተቀምጦ እንጀራም አዩ። የመረቡ አለመቀደድ እንዲሁ አልተጠቀሰም ለማለት የተፈለገው መያዝ ከሚገባው በላይ ይዟል ይህ ተአምር ነው:: ሙሉ ለሊት የተፈለገው አሳ መረብ እስኪቀደድ መገኘቱ ጌታ የሰራው ድንቅ ነው:: ዛሬም ለከበበን ለፍተን ምንም ባላገኘንበት ላይ ይህ እጁ ይገለጥና ተአምራት በህይወታችን ይሁን::
ይህ ተአምራት የጀመረው ልጆች ሆይ፥ አንዳች የሚበላ አላችሁን?” ከሚለው ጥያቄ ነው እነርሱም “የለንም፤” ብለው መለሱለት። የለም ብለው ባሉት ላይ ጌታ አለ ብሎ መሸከም ከሚቻለው በላይ አንበሸበሻቸው:: ሌላው ጌታ ሐዋርያቱን በምንም አልወቀሳቸውምና ከአገልግሎት እየኮበለሉ ነው ለማለት ይከብዳል:: ለእለት ኑሮ ለመስራት ነበረ የወጡት:: ጌታም እራሱ ምግብ አዘጋጅቶ ጠበቃቸው! ኢየሱስም፦ “ኑ፥ ምሳ ብሉ፡” አላቸው። ከደቀ መዛሙርቱ አንድ ስንኳ፦ “አንተ ማን ነህ?” ብሎ ሊመረምረው የደፈረ አልነበረም፤ ጌታ መሆኑን አውቀው ነበርና። ዮሃንስም ለጴጥሮስ ጌታ እኮ ነው እያለው ነበር:: ኢየሱስም መጣና እንጀራ አንሥቶ ሰጣቸው፥ እንዲሁም ዓሣውን።
አባት ሆይ ክብር ለአንተ ይሁን ዛሬም ድንቅና ተአምራትን ታደርጋለህ ሁሉን በፊትህ አናኖራለን:: ሩጫችንን ባርክ እንደቃልህ መውጣትና መውረስ ይሁንልን:: ድካም የበዛበት ሩጫ ከማድረግ ጠብቀን:: አሜን!
ዮሐንስ 21: 15-19
15፤ ምሳ ከበሉ በኋላም ኢየሱስ ስምዖን ጴጥሮስን፦ “የዮና ልጅ ስምዖን ሆይ፥ ከእነዚህ ይልቅ ትወደኛለህን?” አለው። “አዎን ጌታ ሆይ፥ እንድወድህ አንተ ታውቃለህ” አለው። “ግልገሎቼን አሰማራ፡” አለው።
የስጋቸውን ፍላጎት ምሳ አዘጋጅቶና አብልቶ ከጨረሰ በኃላ ወደ ጥያቄ ገባ:: “የዮና ልጅ ስምዖን ሆይ፥ ከእነዚህ ይልቅ ትወደኛለህን?” ብሎ ሶስት ጊዜ ጠየቀው:: ጥያቄው ትወደኛለህን ብቻ አይደለም ከእነዚህ ይልቅ ትወደኛለህን? የሚል ነው:: ጌታ ፉክክር አይወድም ለምን ይህን አለ? ከዚህ ቀደም ጌታ መሄጃው መድረሱን በነገራቸው ጊዜ ጴጥሮስ እነዚህ ሁሉ ቢከዱህ እኔ ከአንተ ጋር ነኝ እስከሞት ብሎ ሲያበቃ አላውቀውም ብሎ ሶስት ጊዜ ካደው:: ስለዚህም ነው እዚህ ጋርየካደውን ሁሉ እወድሃለሁ እያለ እራሱን ከመኮነንና በወንድሞቹም ፊት ከማፈር ሊያወጣው ነው:: እኛም እራሳችንን ከሌሎች ሳናስተያይ ምሳሌያችን እየሱስ ብቻ ይሁንልን::
ይህንን ጥያቄ ሲጠይቅ ጌታ ሃሳቡንም እንዳልቀየረ ለሌሎቹም ለማሳየት ነው:: ጴጥሮስ መሪ ነው ምንም እንኳን በቃሉ ተፈትኖ ወድቆ ቢገኝም:: ይህንን በሁሉ ፊት ሊያሳይና አገልግሎቱንም ሊያፀናለት ነው:: ኢየሱስም አለው፦ “ግልገሎቼንና በጎቼን አሰማራ፡” : “ጠቦቶቼን ጠብቅ፡” አለው:: ጌታ እየሱስ የተጠቀመው ቃል ግልገሎቼን በጎቼን ጠቦቶቼን- የእኔ ናቸው እያለ ነው:: ግልገሎች አይደለም ያለው የእኔን ግልገሎች ወይም ግልገሎቼን:: መንጋው የእየሱስ ነው እንጂ የማንም አይደለም:: የእግዚአብሔር ህዝብ የሞተለት እውነተኛ እረኛ አለው:: አሜን
አገልግሎት በፍቅር ነው የሚሰራው ይህም ማለት ከወደድነው የተሰጠንን ስራ እንሰራለን በቤቱ:: እዚህም ጋር የምናየው ከወደድከኝ በጎቼንና ግልገሎቹን አሰማራ ጠቦቶቹን ግን ጠብቅ:: ጠቦት ጎረምሳ ነው ትግስትን የራስን መተውንና ክትትልን ይፈልጋል መጠበቅ ሁልጊዜ አብሮ መሆንን ይጠይቃል ገና ቀንዱ በቀል በቀል ያለ ስለሆነ ከዚህም ከዛም ይጋጫል የራሱን ይፈልጋል ታድያ ያለፍቅር ይሄ እንዴት ይጠበቃል?! ጌታ የሰጠንን ፀጋ በፍቅር እንጠቀምበት :: ደቀ መዛሙርቱ መሆናችንንም በፍቅር እናሳይ:: እንደጌታ ይቅር የምንል እንሁን:: ክህደት ሊኖር ይችላል ይቅርታ ግን ሁሉንም ይፈውሳል!
አባት ሆይ በሰጠኸኝ ስፍራና ስራ ላይ እንደልብህ አሳብ በፍቅርና በመንፈስ ቅዱስ ኃይል እንዳገለግልህ እርዳኝ:: የይቅርታንም ልብ ስጠኝ ከፍቅር በቀር አንዳች እዳ አይኑርብኝ:: አሜን!
ዮሐንስ 21: 20-25
22፤ ኢየሱስም አለው፦ “እስክመጣ ድረስ ይኖር ዘንድ ብወድስ፥ ምን አግዶህ? አንተ ተከተለኝ።”
ጌታ እየሱስ ጴጥሮስን ትወደኛለህ ወይ ብሎ ሶስት ጊዜ ጠይቆ መልስን ካገኘ በኃላ ተከተለኝ አለው:: ለዚህ ትዕዛዝ መልስ ሳይሰጥ ዞር ብሎ ሲያይ ዮሃንስን አይቶ ኢየሱስን፦ “ጌታ ሆይ፥ ይህስ እንዴት ይሆናል?” አለው። እርሱ የተጠየቀው ተከተለኝ ነው ምናለ ለእርሱ ብቻ መልስ ቢሰጥ:: ደርሶ ኮሚቴ ማን አደረገው ጌታ የወደደውን ያደርጋል አንዱን ጠርቶ ይህንን ፀጋ ይሰጣል ለሌላው ደግሞ ሌላ:: እያንዳንዱ የራሱን መንገድ ይጠብጥብ!
ጌታም ለጴጥሮስ ሲመልስ “እስክመጣ ድረስ ይኖር ዘንድ ብወድስ፥ ምን አግዶህ? አንተ ተከተለኝ።” የራስህን እወቅ ስለሌላው ተው እያለውነው:: እያንዳንዳችን በእኔ ስራ ብለን ከእርሱ ጋር እንስማማ እንጂ ስለሌሎች ልጆቹ ጌታን ልንሞግት አንነሳ:: አንድ አገልጋይ የመሰከረው ትዝ ይለኛል ለአገልግሎት የሄደበት ቤተክርስቲያን አንዲት ሴት ያለችውን ሲመሰክር እኔና ባለቤቴ ከቸርች ቀርተን አናውቅም: ሰንበት ትምህርት ቤት እናስተምራለን: አስራት እንከፍላለን እርስዋ ግን ጌታ ድንቅ ያደረገላትን እያነሳች ቸርች እንኳን አንዳንዴ ነው የምትመጣውና እንዴት ለእኛ ቀርቶ ለእርስዋ ይደረጋል ብላ ጠየቀችው:: የእህትዋ መጎብኘት አስቀናት! ከዚህ መንፍስ ይጠብቀን በቤት ውስጥ እንዳንጠፋ አንድ ፊቱን ሸፍቶ የሄደው ልጅ ይሻል ነበር ተምሮ ወደ አባቱ በትህትና ተመለሰ:: በቤት ያለው ግን በመጣው ወንድሙ ተናደደና ቀና የአባቱ የሆነው ሁሉ የእርሱ መሆኑን ዘነጋና ጎሽ ጎሽ መባልን ፈለገ:: አደራውን ብቻ ከእርሱ ባገኘነው ፀጋ አገልግለን ጎሽታን እንዳንፈልግ:: የማንጠቅም አገልጋዮች ነን ማለትን ጌታ ይስጠን በቅዱሳንም መጎብኘት ደስ ይበለን::
ስለዚህ፦ “ያ ደቀ መዝሙር አይሞትም” የሚለው ይህ ነገር ወደ ወንድሞች ወጣ፤ ነገር ግን ኢየሱስ፦ “እስክመጣ ድረስ ይኖር ዘንድ ብወድስ ምን አግዶህ?” አለው እንጂ አይሞትም አላለውም። ስለ እነዚህም የመሰከረ ይህንንም ጽፎ ያለ ይህ ደቀ መዝሙር ነው፥ ምስክሩም እውነት እንደ ሆነ እናውቃለን። ዮሃንስ ነው ይህንን ሁሉ የጎደለውን ከብዙ መካከል በመንፈስ ተነድቶ የፃፈልን :: ደግሞም እውነት ለመናገር ጌታ ተላልፎ ከተጠበት ከመጀርያው ጀምሮ እስቀመስቀሉ ግርጌ ተገኝቶ የእናቱንም ኃላፊነት የተሰጠው ይኸው ሐዋርያ ነበረ:: ኢየሱስም ያደረገው ብዙ ሌላ ነገር ደግሞ አለ፤ ሁሉ በእያንዳንዱ ቢጻፍ ለተጻፉት መጻሕፍት ዓለም ራሱ ባልበቃቸውም ይመስለኛል ብሎ ወንጌሉን አጠናቀቀ!
በዚህ የዮሐንን ጥናት አጠናቀናል የረዳንን ጌታን አመሰግናለሁ!
ቅዱስ አባት ሆይ ክበር ተመስገን አንተ ወድደህና ፈቅደህ በምታደርገው የቤትህ ስራ ተባባሪ እንድሆን እርዳኝ! በቅዱሳን ውስጥ እንድትገለጥ ዛሬ በፊትህ እማልዳለሁ! በፀጋ ላይ ፀጋን ስጠኝ! አሜን