የሉቃስ ወንጌል

መግቢያ

ይህ ወንጌል የተፃፈው ለአህዛብ ሲሆን በተለይም ለቴዎፍሎስ ነበረ::  ፀሃፊውም እራሱ እስራኤላዊ አይደለም:: በዚህ ወንጌል ውስጥ ብቻ የሚገኙ ታሪኮች አሉ::  ለምሳሌ የመልአክት ዝማሬ እረኞች  ባሉበት ስፍራ መገለጡ ጌታ እየሱስ ሲወለድ: ርኅሩኁ ሳምራዊ ምሳሌ: የጠፋው ልጅ ታሪክ እናም የእየሱስ በልጅነቱ ወደ ቤተመቅደስ መሄዱ::

ይህ ወንጌል  የተፃፈው በዓይን ያዩትና የቃሉ አገልጋዮች የሆኑት እንዳስተላለፉልን ነው::  በማለት እርሱ የዓይን እማኝ እንዳልሆነ ይገልጣል::  የተፃፈውም በጥንቃቄ ሁሉን ከመጀመሪያው ተከትዬ በየተራው ነው የፃፍኩት ብሎ ይላል::

ሉቃስ 1:1-4፤ የከበርህ ቴዎፍሎስ ሆይ፥ ከመጀመሪያው በዓይን ያዩትና የቃሉ አገልጋዮች የሆኑት እንዳስተላለፉልን፥ በኛ ዘንድ ስለ ተፈጸመው ነገር ብዙዎች ታሪክን በየተራው ለማዘጋጀት ስለ ሞከሩ፥ እኔ ደግሞ ስለ ተማርኸው ቃል እርግጡን እንድታውቅ በጥንቃቄ ሁሉን ከመጀመሪያው ተከትዬ በየተራው ልጽፍልህ መልካም ሆኖ ታየኝ።

ጌታ ሆይ ተመስገን ይህንን ቃልህን እንደዚህ በጥንቃቄ የተፃፈውን እንድንማረውና ገንዘባችን እንድናደርገው እርዳን::

ሉቃስ 1:5፤ በይሁዳ ንጉሥ በሄሮድስ ዘመን ከአብያ ክፍል የሆነ ዘካርያስ የሚባል አንድ ካህን ነበረ፤ ሚስቱም ከአሮን ልጆች ነበረች፥ ስምዋም ኤልሳቤጥ ነበረ። 6፤ ሁለቱም በጌታ ትእዛዝና ሕግጋት ሁሉ ያለ ነቀፋ እየሄዱ በእግዚአብሔር ፊት ጻድቃን ነበሩ።7፤ ኤልሳቤጥም መካን ነበረችና ልጅ አልነበራቸውም፤ ሁለቱም በዕድሜያቸው አርጅተው ነበር።

እንግዲህ ሉቃስ ቃል እንደገባው ከመጀመርያ ጀምሮ ነው ስለተማረው ቃል እርግጡን እንዲያውቅ ለቴዎፍሎስ እየፃፈ ያለው እግዚአብሔር እኛን እያየ ነበረና ይኸው ዛሬ እኛጋር ደርሷል::

የጀመረውም ከዘካርያስና ከኤልሳቤጥ ነበረ በዚህ ውስጥም ስለ ሄሮድስም አንስቷል ይህ ገዢ ነው ህፃናትን የጨፈጨፈው እየሱስን ለመግደል አስቦ::  እርሱ የመሰለው ስልጣኑን የሚቀማው እየሱስ ግን በዚህኛው ዓለም ብቻ ሳይሆን በሚመጣውም ዓለም ገዢ ነው:: እርሱ የነገስታት ንጉስና የጌቶችም ጌታ ነው::

እነዚህ ባልና ሚስት ሁለቱም ከካህናት ዘር እንደሆኑ ይገልፃል ደግሞም በጌታ ትእዛዝና ሕግጋት ሁሉ ያለ ነቀፋ እየሄዱ በእግዚአብሔር ፊት ጻድቃን ነበሩ ይላል::  ልጅ የሌላቸውና እድሜያቸውም መግፋቱን ልጅ ማግኛው ዘመን ማለፉን ያመላክታል:: ፃድቅ ነበሩ የሚለው አሳብ እንዴት ይገርማል ::  ነገር ግን እንደነ አብረሃም በእምነት እንጂ በአዲስ ኪዳን እንዳለው ፃድቅነት አይደለም ምክንያቱም ሁሉም ኃጥያትን አድርገዋል የእግዚአብሔር ክብር ጎሏቸዋል ይላልና ቃሉ::   በብሉይ ኪዳን የኃጥያት ስርየት በእንስሳት ደም ማግኘት ይቻል ነበር ነገር ግን ዘላቂ አልነበረምና የእግዚአብሔር በግ እየሱስ መጣልንና አፀደቀን ልጅም አደረገን::  አሜን!

አባት ሆይ ተመስገን በደምህ ዋጅተህ ልጅ ስላደረከን::  ጌታ ሆይ አንተን የሚይዝህ ነገር የለም ከዚህ አለመቻል ውስጥ ዮሃንስ ተወልዷልና ዛሬም በህይወታችን ትሰራለህ የሚያቆምህ ምንም ነገር የለም ተመስገን! እታመንሃለሁ ጌታዬ!

ሉቃስ 1:8፤ እርሱም በክፍሉ ተራ በእግዚአብሔር ፊት ሲያገለግል፥ . . . ሉቃስ 1:11፤ የጌታም መልአክ በዕጣኑ መሠዊያ ቀኝ ቆሞ ታየው። . . . ሉቃስ 1:13፤ መልአኩም እንዲህ አለው፦ “ዘካርያስ ሆይ፥ ጸሎትህ ተሰምቶልሃልና አትፍራ፡ ሚስትህ ኤልሳቤጥም ወንድ ልጅ ትወልድልሃለች፥ ስሙንም ዮሐንስ ትለዋለህ።

በብሉይ ኪዳን ጥቂት ሰዎች ናቸው ጻድቅ ተብለው የተጠሩ ከነዛ መካከል  ዘካርያስ አንዱ ሆነ::  ይህ ሰው ካህን ነውና በተራው ገብቶ እግዚአብሔርን ያገለግላል ምንም እንኳን መሃንነት በህብረተሰቡ ዘንድ ጥያቄ ውስጥ የሚያስገባ ቢሆንም::  

የእግዚአብሔር የጉብኝት ሰዕት ሲደርስ ግን መልአኩን ልኮ የምስራች ነገረው::  ጸሎትህ ተሰምቶልሃልና አትፍራ!  በዚች አንድ ቀን ጉብኝት ወደ ዘካርያስ ቤት እየመጣ ያለውን ብናይ:- 

   – ደስታና ተድላም ይሆንልሃል፥ 

   – በመወለዱም ብዙዎች ደስ ይላቸዋል 

   – በጌታ ፊት ታላቅ ይሆናልና፥ የሚለው አሳብ ይገርማል ጌታ እየሱስ ስለእርሱ ሲመሰክር  “እላችኋለሁ፥ ከሴቶች ከተወለዱት መካከል ከመጥምቁ ዮሐንስ የሚበልጥ ማንም የለም፤ ብሎ ነበረ:: 

   – ገናም በእናቱ ማኅፀን ሳለ መንፈስ ቅዱስ ይሞላበታል የሚለው ይገርማል::  ህፃን ነው ገና በሆድ ግን መንፈሱ አገኘውና አላማውን እንዲተገብር ረዳው:: የጌታ አሰራር! 

ዘካርያስ ግን እስከአሁን ልጅ ስጠኝ ብሎ እየለመነ አይመስልም ጸሎቱን ከሁኔታዎች የተነሳ የተወው ይመስላል::   ጌታ ግን ለመመለስ መጣ ምንም እንኳን ዘካርያስ ዝግጁ ባይሆንምና ይህን በምን አውቃለሁ ብሎ ምልክትን ቢጠይቅም::  ምልክት ትፈልጋለህ እንግዲያውስ ዲዳ ሆነህ ቆይ እስኪፈፀም:: ለካስ እራሱ ነው ምልክት የጠየቀው?! 

አባት ሆይ በፀሎት በፊትህ የቀረብኩትን ሁሉ ሰምተኸኛል ዛሬ ያልተመለሱ ቢኖሩም ይመለሳሉ አንተ ታላቅ ነህና ተመስገን!  ተስፋ ባለመቁረጥ በቤትህ እንዳገለግልህ ጸጋህን ለእኔና ለወገኖቼም አብዛልን::  ዛሬ የቆየ ጥያቄ የሚመለስበት ቀን ይሁን::  አሜን!

ሉቃስ 1:14፤ ደስታና ተድላም ይሆንልሃል፥ በመወለዱም ብዙዎች ደስ ይላቸዋል።

በመልአኩ ለዮሃንስ የተሰጠው ተስፋና የሚመጣበት ዓላማ ወይም አገልግሎቱ በደንብ ለዘካርያስ ተነግሮታል::

ለቤተሰቡ:- ደስታና ተድላም ይሆንልሃል እንዲሁም ብዙዎች ደስ ይላቸዋል::

የእስራኤል ህዝብ ለመሲሁ መምጣት የተዘጋጀ አይደለምና ለማዘጋጀት የተላከ ከአወላለዱ ጀምሮ ማን ይሆን በሚያስብል ተአምራት የመጣ ልጅ ነው::

በጌታ ፊት ታላቅ ይሆናልና፥  – ተስፋ ነው::  ጌታ እየሱስም መስክሮለታል::

የወይን ጠጅና የሚያሰክር መጠጥ አይጠጣም፤ – ትእዛዝ

ገናም በእናቱ ማኅፀን ሳለ መንፈስ ቅዱስ ይሞላበታል፤ – የሚፈጸም ተስፋ ነው

ከእስራኤልም ልጆች ብዙዎችን ወደ ጌታ ወደ አምላካቸው ይመልሳል – አገልግሎቱ

እርሱም የተዘጋጁትን ሕዝብ ለጌታ እንዲያሰናዳ – መንገድን የመጥረግ አገልግሎት::  ህዝቡን እያጠመቀ እኔ እርሱ አይደለሁም እያለ እየመሰከረ ለሚመጣው ጌታ አዘጋጀ::   ደቀ መዛሙርቱንም የጌታ ሆኑ በስተመጨረሻ::

የአባቶችን ልብ ወደ ልጆች – አገልግሎት  ሲሆን ከአሮጌው ኪዳን ወደ አዲስ እንዲመጡና  እንደልጅ ሆነው እንዲቀርቡ እንዲያደርግ:: ባጭሩ ለውጥን እንዲቀበሉ

የማይታዘዙትንም ወደ ጻድቃን ጥበብ ይመልስ ዘንድ  – የማንቃት አገልግሎቱ

በኤልያስ መንፈስና ኃይል በፊቱ ይሄዳል – ይህ አገልግሎት መንገድን ለእየሱስ ለሚጠርገው የተሰጠ ነው:: በትንቢትም ኤልያስ ከመሲሁ ፊት ይመጣል ብለው ይጠብቁ ነበር ግን ሲስቱ እናያለን:: ይህ ህፃን ገና በእናቱ ሆድ እያለ በመንፈስ ቅዱስ ይሞላል በኤልያስም መንፈስና ኃይል ያገለግላል:: ታላላቆች ግን አላወቁም::

የእኔ አገልግሎት ምንድነው? ብለን ቆም ብልእን ልንጠይቅና ለተጠራንለት ዓላማ ልንቆም ያስፈልጋል:: በክርስቶስ አስቦ ወለደን እንደሚል ምን ይሆን ለእያንዳንዳችን ያሰበው?

አባት ሆይ ለእኔም እንዲሁ የሰጠኸኝ አገልግሎት አለና ከመንፈስ ቅዱስ ጋር ተስማምቼ እንዳገለግልህና መክሊቴንም እንዳተርፍበት እርዳኝ::  አሜን!

ሉቃስ 1:18 25

ዘካርያስም መልአኩን፦ “እኔ ሽማግሌ ነኝ ምስቴም በዕድሜዋ አርጅታለችና ይህን በምን አውቃለሁ?” አለው።

በእጣ ክፍሉ በታማኝነት በሚያገለግልበት ቦታና ሰዓት የምስራች ለዘካርያስ መጣለት::  ምንም እንኳን በእድሜው ያረጀ ቢሆንም እግዚአብሔር ሲናገር ማመን አልቻለምና ምልክትን ጠየቀ::  መልአኩም በጊዜው የሚፈጸመውን ቃሌን ስላላመንህ፥ ይህ ነገር እስከሚሆን ቀን ድረስ ዲዳ ትሆናለህ መናገርም አትችልም፡” አለው። አገልግሎም ሲወጣ ህዝቡ ራዕይ እንዳየ አስተዋሉ::

የእግዚአብሔር ቃል የሚፈፀም ነውና የተናገረንን አምነን እንጠባበቅ:: ለእርሱ የሚሳነው የለምና በሙሉ ልባችን እንመነው::

ከዚህም ወራት በኋላ ሚስቱ ኤልሳቤጥ ፀነሰችና፦ “ነቀፌታዬን ከሰው መካከል ያስወግድልኝ ዘንድ ጌታ በተመለከተበት ወራት እንዲህ አድርጎልኛል፡” ስትል ራስዋን አምስት ወር ሰወረች።  እርጉዝ ነኝ ብላ ማውራት አላስፈለጋትም ጊዜው ሲደርስ ሆድዋ እራሱ ይናገር ነበረና እራስዋን ሸሸገች!

አባት ሆይ ተመስገን የሰጠኸንን ቃል የምትፈጽም ጌታ ነህና የተናገርከንንም ሁሉ  እንወርሳለን::  አሜን!

እንደተናገረው ለሚያደርግ አምላክ ክብር ይሁን!  አሜን!

ሉቃስ 1: 26-33

27፤ ከዳዊት ወገን ለሆነው ዮሴፍ ለሚባል ሰው ወደ ታጨች ወደ አንዲት ድንግል ከእግዚአብሔር ዘንድ ተላከ፥ የድንግሊቱም ስም ማርያም ነበረ።

መልአኩ ገብርኤል  ያመጣላት መልእክት

እነሆም፥ ትፀንሻለሽ ወንድ ልጅም ትወልጃለሽ፥ 

ስሙንም ኢየሱስ ትዪዋለሽ – ይህ ስም የተቀባ ስም ዛሬም እንድንበት ዘንድ የተሰጠን ስም::  በላይ በሰማይ በምድር ከምድርም በታች ሁሉ ይንበረከክለታል::

እርሱ ታላቅ ይሆናል – አሜን ታላቅ ነው

የልዑል ልጅም ይባላል – የምወደው ልጄ ይህ እርሱን ስሙት ብሎ አብ መስክሮለታል::

ጌታ አምላክም የአባቱን የዳዊትን ዙፋን ይሰጠዋል – ቃል እንደገባው 2 ሳሙኤል 7:16፤ ቤትህና መንግሥትህም በፊቴ ለዘላለም ይጠነክራል፥ ዙፋንህም ለዘላለም ይጸናል።

በያዕቆብ ቤትም ላይ ለዘላለም ይነግሣል፥ 

ለመንግሥቱም መጨረሻ የለውም።

አሜን የጌታ መንግስት ለዘላለም የጸና ነው::  ለዚህ ቃሉን ተናግሮ ለሚፈጽም ጌታ ክብር ይሁን::  ዛሬም በስራ ላይ ነው:: ሁሉም ነገር እንዳለው ይሆናልና በዙሪያችን ባለውነገር አንሸበር የመጨረሻው ውሳኔ የጌታ ነው::  ሃሌሉያ!

ሉቃስ 1: 34-38

34፤ ማርያምም መልአኩን፦ “ወንድ ስለማላውቅ ይህ እንዴት ይሆናል?” አለችው።

የተፈጥሮን ነገር ሁሉ ያላሟላ ስለሆነ መልእክቱ ግራ ገብቷት መጠየቅዋ ትክክል ነበረ::  ምንም እንኳን  በእግዚአብሔር ፊት ጸጋ አግኝተሻልና አትፍሪ የተባለች ብትሆንም እርስዋም አዳኝ ያስፈልጋታልና እንዴት ከስዋ የመጣ ያድናል የሚለውን ጥያቄ ይመልሳል::  መልአኩም መልሶ እንዲህ አላት፦ “መንፈስ ቅዱስ በአንቺ ላይ ይመጣል፥ የልዑልም ኃይል ይጸልልሻል ስለዚህ ደግሞ ከአንቺ የሚወለደው ቅዱስ የእግዚአብሔር ልጅ ይባላል። አሜን! እርሱ በድንግልና የተወለደ  የእግዚአብሔር ልጅ ነው:: ቃል ስጋ ሆነ ጸጋንና እውነትን ተሞልቶ በእኛ አደረ!

በዚሁ ሌላ መልካም ዜና ነገራት:- ዘመድሽ ኤልሳቤጥ፥ እርስዋ ደግሞ በእርጅናዋ ወንድ ልጅ ፀንሳለች፥ ለእርስዋም መካን ትባል ለነበረችው ይህ ስድስተኛ ወር ነው አላት የሁለቱ ልጆች ግንኙነትና ተልእኮ ባይገባትም እንኳን በጉብኝቱ ደስ ብሏታል::  

ወንድ የማታውቀው አርግዛ እንድትወልድ እንዲሁም ያረጀችው ልጅ እንድታቅፍ የሚያደርግ ጌታ ስሙ ይባረክ::  ሳይንሱን ሁሉ የገለባበጠው ጌታ ይባረክ::  ለእግዚአብሔር የሚሳነው ነገር የለምና። አሜን!

በዚህ ውስጥ ማርያምም፦ “እነሆኝ የጌታ ባሪያ እንደ ቃልህ ይሁንልኝ፡” አለች። መልአኩም ከእርስዋ ሄደ። ከጌታ ጋር ተስማማች ምንም እንኳን በባህሉ ከትዳር ውጪ አርግዞ መገኘት ዋጋ ቢያስከፍልም እርሱ ብሏል ብላ ቆመች::  እርሱም የሚሳነው የለምና ቃሉን ይፈጽማል:: 

ለተናገረን ነገር እኛ በእምነት እንቁም ሌላውን ሁሉ ኤልሻዳዮ ጌታ ይወጣዋል::

አባት ሆይ ተመስገን ቃልህ ከእኛ ጋር ይዋሃድና ይጥቀመን::  እንደተናገርከንም መታዘዝ ይሁንልን ምሕረትህ ዛሬ በእኛ ላይ ትገለጥ::  አሜን!

ሉቃስ 1: 39-45

41፤ ኤልሳቤጥም የማርያምን ሰላምታ በሰማች ጊዜ ፅንሱ በማኅፀንዋ ውስጥ ዘለለ፤ በኤልሳቤጥም መንፈስ ቅዱስ ሞላባት፥ 

ማርያም ኤልሳቤጥን ልትጠይቅ  መጣች:: እግዚአብሔር ለዘካርያስ በነገረው መሰረት  ይኸው ህፃኑ በመንፈስ ቅዱስ ተሞልቶ በማኅፀንዋ ውስጥ ዘለለ:: ቃል ስጋ ሆንዋል በማህፀንም እያለ ይሰራል:: 

እነሆ፥ የሰላምታሽ ድምጽ በጆሮዬ በመጣ ጊዜ ፅንሱ በማኅፀኔ በደስታ ዘሎአልና።

ከጌታ፤ የተነገረላት ቃል ይፈጸማልና ያመነች ብፅዕት ናት። እግዚአብሔር እንደተናገረው እንደቃሉ ነውና የተስፋ ቃላችንን ሁሉ እንወርሳለን ምክንያቱም የተናገረው የታመነ ነው:: አሜን! 

ሉቃስ 1: 46-56

46፤ ማርያምም እንዲህ አለች፦ “ነፍሴ ጌታን ታከብረዋለች፥ 47፤ መንፈሴም በአምላኬ በመድኃኒቴ ሐሴት ታደርጋለች፤

ማርያም እንደቃልህ ይሁንልኝ ብላ ለእግዚአብሔር ቃል ታዘዘችና ቃል የሆነው እየሱስ በእርስዋ ውስጥ ተፀነሰ::  ኤልሳቤጥም በመንፈስ ተሞልታ ትንቢትን እንደተናገረች ሁሉ ማርያምም ቃል እየጠቀሰች በመንፈስዋ ሃሴት እያደረገች ጌታን ማክበርና መባረክ ይዛለች::  የእየሱስ እናት መሆን እንዴት የሚገርም መመረጥ ነው? ነገር ግን እርስዋም የእግዚአብሔር ክብር ይጎድላታልና አዳኝ አስፈልጏታል:: 

እርስዋም:- ብርቱ የሆነ እርሱ በእኔ ታላቅ ሥራ አድርጎአልና፤ ስሙም ቅዱስ ነው። ብላለች አሜን እርሱ ቅዱስነው::  እናውቃለን ብለው የታበዮትን አዋረዳቸው ለትሁታን ግን ፀጋን ሰጠ!

አምላካችንን እናመስግን እናድንቅ እናወዳድሰው ስለሚገባው ይህ ንጉስ እኛን ፍለጋ ሲመጣ ይህንን ሁሉ ነገር ሰርቶ ነውና ይክበርልን:: አሜን! እኛም እንደማርያም ነፍሴ ጌታን ታከብረዋለች እንበል::

ሉቃስ 1: 57-66

57፤ የኤልሳቤጥም የመውለጃዋ ጊዜ ደረሰ፥ ወንድ ልጅም ወለደች። 58፤ ጎረቤቶችዋም ዘመዶችዋም ጌታ ምሕረቱን እንዳገነነላት ሰምተው ከእርስዋ ጋር ደስ አላቸው።

የጌታን መልእክት እንዴት ይሆናል ብሎ እንዳላለ ዘካርያስ እንደተባለው አባት ሆነ::  ይህንንም በዓይኑ አይቶ ሙሉ ለሙሉ እስኪታዘዝ ድረስ ዲዳ ነበረ::  እነሆም፥ በጊዜው የሚፈጸመውን ቃሌን ስላላመንህ፥ ይህ ነገር እስከሚሆን ቀን ድረስ ዲዳ ትሆናለህ መናገርም አትችልም፡” አለው። የእግዚአብሔር ቃል የሚፈጸም ነው::  አሜን!

ጌታ ምሕረቱን እንዳገነነላት ሰምተው ከእርስዋ ጋር ጎረቤቶችዋና ዘመዶችዋ ደስ አላቸው። ምሕረቱን በእያንዳንዳችን ቤት ላይ ያግንነው::

ስም ሊያወጡለት የፈለጉት የአባቱን ስም ነበረ ነገር ግን እናትምአባትም ተቃወሙና ስሙ ዮሐንስ ነው ሲሉ እነርሱም፦ “ከወገንሽ ማንም በዚህ ስም የተጠራ የለም፡” አሉአት። የእግዚአብሔር ነገር ሰው ባሰመረለትና በተለመደው መንገድ አይሰራምና መቀበል ግድ ነበረ::  አይሆንም ባይሉ ግን ስሙን ይቀይሩት ነበረ ማለት ነው:: 

አባት ሆይ ያልከው እንደሚፈፀም አውቀን በሰጠን የተስፋ ቃል እንድንታመንና እንድንጠብቅ እርዳን:: አሜን!

ሉቃስ 1: 65-71

67፤ አባቱ ዘካርያስም መንፈስ ቅዱስ ሞላበትና ትንቢት ተናገረ እንዲህም አለ፦

68፤ “የእስራኤል ጌታ አምላክ ይባረክ፥ ጐብኝቶ ለሕዝቡ ቤዛ አድርጎአልና፤

እዚህ ምዕራፍ ላይ ኤልሳቤጥ በመንፈስ ቅዱስ ተሞልታ ትንቢትን ስትናገር አይተናል እንዲሁም ማርያም አሁን ደግሞ ዘካርያስ:: እርሱም የጀመረው እግዚአብሔርን በመባረክ ነው::   አሁን ያሉት ዮሃንስ ሊገረዝ ባለበት ስርዓት ላይ ቢሆንም እንኳን  አባትየው በመንፈስ ተነድቶ  ስለመሲሁ እየተናገረ ነው:: ጐብኝቶ ለሕዝቡ ቤዛ አድርጎአልና እያለ::  አሜን የሰውን ልጅ ያሰበው ጌታ ይባረክ::

ሲቀጥልም ከጥንት ጀምሮ በነበሩት በቅዱሳን ነቢያት አፍ እንደ ተናገረ፥ 

በብላቴናው በዳዊት ቤት የመዳን ቀንድን አስነስቶልናል::  ይህ የመዳን ቀንድ የሆነው መሲሁ እየሱስ ‘ማዳኑም ከወደረኞቻችንና ከሚጠሉን ሁሉ እጅ ነው ብሎ መንፈስ ቅዱስ መሰከረለት::  አሜን  ከሚጠሉን ከሰይጣንና ከአጋንንቶች እጅና መንጋጋ ነው::  ጨለማችንን አብርቶ ፤  በደላችንንም ይቅር ብሎ ፤   በጽድቁ አጽድቆ ፤  በቤቱ ተክሎን ፤   ከዓለም ውጡና የተለያችሁ ሁኑ ብሎ አባት ሆኖን፤  በእጁም መዳፍ ቀርጾ ማንም ከእጄ አያወጣችሁም ብሎን ፤   አይዞአችሁ ዓለምን አሸንፌአለሁ ብሎን ፤  በእኛ ውስጥ ለመኖር መጣ:: ምን አይነት ህይወት ነው?!

አባት ሆይ ተመስገን ክብርህን ጥለህ የባርያን መልክ ይዘህ ተዋርደህ ለእኛ የመጣህ ጌታ እናመሰግንሃለን:: እኛነታችን ሁሉ የአንተ ነውና ክበርበት! አሜን

ሉቃስ 1: 72-75

72-73፤ እንደዚህ ለአባቶቻችን ምሕረት አደረገ፤ ለአባታችን ለአብርሃምም የማለውን መሐላውን ቅዱሱን ኪዳን አሰበ፤ 74-75፤ “በእርሱም ከጠላቶቻችን እጅ ድነን በዘመናችን ሁሉ ያለ ፍርሃት በቅድስናና በጽድቅ በፊቱ እንድናገለግለው ሰጠን።

ዘካርያስ ትንቢቱን ሲቀጥል ለአባታችን ለአብርሃምም የማለውን መሐላውን ቅዱሱን ኪዳን አሰበ አለ እንዲህ ያለውን:-

ዘፍጥረት 22:16 – 18፤ እንዲህም አለው፦ “እግዚአብሔር፦ ‘በራሴ ማልሁ፡’ ይላል፤ ይህን ነገር አድርገሃልና፥ አንድ ልጅህንም አልከለከልህምና፣ በእውነት በረከትን እባርክሃለሁ፥ ዘርህንም እንደ ሰማይ ከዋክብትና በባሕር ዳር እንዳለ አሸዋ አበዛዋለሁ፤ ዘርህም የጠላቶችን ደጅ ይወርሳል፤ የምድር አሕዛብ ሁሉም በዘርህ ይባረካሉ፥ ቃሌን ሰምተሃልና።”

አብርሃም ቃሉን ሰምቶ አንድ ልጁን መስዋእት ለማድረግ ስላልሳሳ  በራሱ ምሎ እራሱ መጣና ተቤዥን::  በአብርሃም የምድር አሕዛብ ሁሉም በዘርህ ይባረካሉ  እንደሚል ይኸው እኛ ከአህዛብ ወገን የሆንን ለዚህ ቃል መፈጸም የቆምን ምልክቶች ነን:: አሜን!

በእርሱም ከጠላቶቻችን እጅ ድነን በዘመናችን ሁሉ ያለ ፍርሃት በቅድስናና በጽድቅ በፊቱ እንድናገለግለው ሰጠን። ሃሌሉያ! ! ዓለም ሳይፈጠር፥ በፊቱ ቅዱሳንና ነውር የሌለን በፍቅር እንሆን ዘንድ በክርስቶስ መረጠን::  አሜን!

ሉቃስ 1: 76-80

78፤ ይህም ከላይ የመጣ ብርሃን በጐበኘበት በአምላካችን ምሕረትና ርኅራኄ ምክንያት ነው፤ 79፤ ብርሃኑም በጨለማና በሞት ጥላ ተቀምጠው ላሉት ያበራል እግሮቻችንንም በሰላም መንገድ ያቀናል።”

ስለዮሃንስ ደግሞም አንተ ሕፃን ሆይ፥ የልዑል ነቢይ ትባላለህ፥ መንገዱን ልትጠርግ በጌታ ፊት ትሄዳለህና፤ “እንደዚህም የኃጢአታቸው ስርየት የሆነውን የመዳን እውቀት ለሕዝቡ ትሰጣለህ ነው የመጣበት አገልግሎት::  እራሱም መስክሯል እኔ እርሱአይደለሁም በማለት:: መንገድን መጥረግና የመዳንን እውቀት ለሕዝቡ መግለጥ ነበረ ::  ጌታ የሰጠን ስራ ምን ይሆን?  የተሰጠንማ ስራ አለን::  ይህንኑ ጌታ ይግለጥልን::

ይህም ከላይ የመጣ ብርሃን በጐበኘበት በአምላካችን ምሕረትና ርኅራኄ ምክንያት ነው::  አሜን!  የአምላካችን ምሕረትና ርኅራኄ ጉብኝት አገኘን::  ይህ ብርሃን በራልን ጨለማችንም በራ! 

ብርሃኑም በጨለማና በሞት ጥላ ተቀምጠው ላሉት ያበራል እግሮቻችንንም በሰላም መንገድ ያቀናል። አሜን!  በሞት ጥላ ተቀምጠን ነበረ ያለ መፍትሄ ምንም መውጫ የሌለበት::  በኢየሱስ ግን አመለጥን ውደ ህይወት ተሻገርን!  ጨለማችንንም አበራው!  እግሮቻችንንም በሰላም መንገድ ያቀናው ምሕረቱንና ርህራሄውን ያበዛልን ጌታ ይባረክ!

አባት ሆይ ተመስገን መፍትሄ የሌለውን ፍፃሜያችንን ለውጠህ አባ አባት የምንልበትን መንፈስ ሰጥተህ በቤትህ አለመለምከን::  በአብ ቀኝ ተቀመጥን!

ሉቃስ 2: 1-7

7፤ የበኵር ልጅዋንም ወለደች፥ በመጠቅለያም ጠቀለለችው፤ በእንግዶችም ማደሪያ ስፍራ ስላልነበራቸው በግርግም አስተኛችው።

በዚያም ወራት ዓለሙ ሁሉ እንዲጻፍ ትእዛዝ ወጣ ይህ ትእዛዝ ከነገስታት የወጣ ይምሰል እንጂ ወራቱን ጠብቆ ትእዛዝ ያወጣው አምላካችን ነው::  ትእዛዙም የወጣው ትንቢቱ እንዲፈፀም እየሱስ በቤተልሔም ይወለድ ዘንድ ነውና ዮሴፍም ለመቆጠር እጮኛውን ይዞ ወደ ቤተልሐም መጣ:: ትንቢቱም  በሚክያስ 5:2፤ አንቺም ቤተ ልሔም ኤፍራታ ሆይ፥ አንቺ በይሁዳ አእላፋት መካከል ትሆኚ ዘንድ ታናሽ ነሽ፤ ከአንቺ ግን አወጣጡ ከቀድሞ ጀምሮ ከዘላለም የሆነ፥ በእስራኤልም ላይ ገዥ የሚሆን ይወጣልኛል። የሚለው ነው:: በዝችው ከተማ ነበረ ዳዊትም የተቀባው::

የትንቢቱ ትእዛዝ ሲፈፀም እንደመቃብሩ ሁሉ የከበሬታን ቦታ ማዘጋጀት ይችል ነበረ ነገር ግን  የነገስታት ንጉስና የጌቶቹ ጌታ ስፍራ ጠፍቶ በከብቶች በረት  በግርግም ተወለደ::  እውነትም እንዴት ነው እራሱን አዋርዶ የመጣልን?! እየሱስ ተወለደ ዓለም ሁሉ አላወቀም::  ዓለሙን ሁሉ በቃል የፈጠረው ጌታ መወለዱን ከጥቂቶች በቀር አብዛኛው አላወቀም::  እርሱም እውቅና ስጡኝ አላለም::   ትሁት ጌታ! ተመስገን!  የእኛም ህይወት ከዚህ ግርግም የማይለይ ቁሻሻ ነበረ እርሱ ሲገባ ግን በደሙ አነፃንና ፃድቅ ቅዱሳን ተባል! ሃሌሉያ!

አባት ሆይ የዝቅታን ዝቅታ ስለእኛ አየህ::  ተመስገን ስለተወለድክና ስለመጣህልን እናመሰግንሃለን!  ልጆችህ ስላደረከን ከፍ በል! ይህንን የመጣህበትን የማዳን ወንጌል ይዘን እንድንወጣና እንድንመሰክር እርዳን በጸጋህንም ሙላን::  አሜን

ሉቃስ 2: 8-20

10፤ መልአኩም እንዲህ አላቸው፦ “እነሆ፥ ለሕዝቡ ሁሉ የሚሆን ታላቅ ደስታ የምሥራች እነግራችኋለሁና አትፍሩ፤

11፤ ዛሬ በዳዊት ከተማ መድኃኒት እርሱም ክርስቶስ ጌታ የሆነ ተወልዶላችኋልና።

12፤ ይህም ምልክት ይሆንላችኋል፤ ሕፃን ተጠቅልሎ በግርግምም ተኝቶ ታገኛላችሁ።”

እየሱስ ለህዝብ ሁሉ የሚሆን ታላቅ ደስታ የምሥራች እረኞች ተነገራቸው::  ይህም የምስራች መድኃኒት እርሱም ክርስቶስ ጌታ የሆነ ተወልዶላችኋል የሚል ነበረ::  ይህ ለሊት ምን አይነት የተለየ ለሊት ነው? አምላክ ሰው ሆኖ የተወለደበት ለሊት::  ዓለሙ ሁሉ በእንቅልፍ ላይ ነው እነዚህ እረኞች በማንም አጀንዳ ላይ የማያሰፍራቸው ይህንን ክብር ያዮ ዘንድ ተመረጡ:: የመልአኩን መልአክት ሰሙ አብረውም ያሉትን መልአክትን ዝማሬ አደመጡ:- 

“ክብር ለእግዚአብሔር በአርያም ይሁን ሰላምም በምድር ለሰውም በጎ ፈቃድ።”

እነዚህ እረኞች ሰምተው ብቻ ዝም አላሉም መላእክቱ ከእነርሱ ተለይተው ወደ ሰማይ በወጡ ጊዜ፥ እረኞቹ እርስ በርሳቸው፦ “እንግዲህ እስከ ቤተ ልሔም ድረስ እንሂድ እግዚአብሔርም የገለጠልንን ይህን የሆነውን ነገር እንይ፡” ተባባሉና ታዘዙ::  ዛሬም ወድያው መታዘዝ ይሁንልን ጌታ በሚያሳየንና በሚያዘን ነገር ላይ::  ጸጋህን ስጠን!

በፍጥነትም መጡ ህፃኑንም በግርግም ተኝቶ አገኙት::  ከቤተሰቡ በተጨማሪ እነዚህ እረኞች ናቸው ያወቁት ስለመሲሁ:: ማርያም ግን ይህን ነገር ሁሉ በልብዋ እያሰበች ትጠብቀው ነበር። የተቀበልነውን ነገር እምነታችንን እንዳይጎዳ በልባችን እንጠብቅ:: 

እረኞችም እንደ ተባለላቸው ስለ ሰሙትና ስላዩት ሁሉ እግዚአብሔርን እያመሰገኑና እያከበሩ ተመለሱ። እኛም ዛሬ ይህንን መሲህ እኛን ያሰበውን እናመስግን::

ሉቃስ 2: 21 – 28

21፤ ሊገርዙት ስምንት ቀን በሞላ ጊዜ፥ በማኅፀን ሳይረገዝ በመልአኩ እንደ ተባለ፥ ስሙ ኢየሱስ ተብሎ ተጠራ።

ገና ሳይፀነስ መልአኩ እንደተባለው ስሙን ኢየሱስ  ብለው ጠሩት:: ማርያም እንደቃልህ ብላ ተስማምታ ነበረና የዘካርያስ እጣ አልደረሰባትም::  ታዘዘች ይኸው  እግዚአብሔርም እንደተናገረ ወንድ ልጅን እርሱም የዓለምን መድኃኒት አቀፈች::

እነሆም፥ በኢየሩሳሌም ስምዖን የሚባል ሰው ነበረ፥ ይህም ሰው የእስራኤልን መጽናናት ይጠባበቅ ነበር፤ ጻድቅና ትጉህም ነበረ፥ መንፈስ ቅዱስም በእርሱ ላይ ነበረ። በጌታም የተቀባውን ሳያይ ሞትን እንዳያይ በመንፈስ ቅዱስ ተረድቶ ነበርና ሲያመጡት ተቀብሎ አቀፈው::  ይህ ሰውን ከምድር አፈር ያበጀ ጌታ  ሰውእጅ ገባ::  ምን አይነት ዝቅታ ነው በሰው እጅ መታቀፍ በሰው እጅ መብላት መጠጣት መታቀፍ እንደማንኛውም ልጅ ቋንቋ መማር  መዳህ መውደቅ መነሳት ሁሉን አድርጏል::  ስናስበው ግን ማንም  ሊቀርበው በማይችል ብርሃን ውስጥ የሚኖር  ጌታ: በሲና ተራራ ሲገለጥ የቀረበ ሰው ወይም እንሰሳ ሁሉ ይሞት ነበረ: ዮሃንስ እንኳን በደንብ የሚያውቀው መቆም አልቻለም በፊቱ::  እንግዲህ ይህንን ጌታ ነው ተቀብሎ ያቀፈው::  ክብሩን ሁሉ ጥሎ እራሱን አዋርዶ መጣ::  ኃጥያት ባይኖርበትም እንደህጉ ለእርሱም መስዋእት ቀረበ::

ስምኦን ጌታውን ጠበቀ በመንፈስ እንደተረዳውም ተቀብሎም አቀፈው::  የተሰጠን የተስፋ ቃል የሚወረስ ነው::  አምላካችን የተናገረውን የሚፈጽም ነው:: አሜን! 

አባት ሆይ ክብርህን ትተህ እኔን ፍለጋ ተዋርደህ ስለመጣህልኝ አመሰግናለሁኝ:: እገዛልሃለሁኝ: አመልክሃለሁኝ! አሜን!

ሉቃስ 2:29-35

30-31፤ ዓይኖቼ በሰዎች ሁሉ ፊት ያዘጋጀኸውን ማዳንህን አይተዋልና፤ 32፤ ይህም ለአሕዛብ ሁሉን የሚገልጥ ብርሃን ለሕዝብህም ለእስራኤል ክብር ነው።”

ስምእኦን የምጠብቀውን አይቻለሁና አሰናብተኝ እያለ ነው::  የሚገርመው ይህ ሰው የተቀባውን ሳያይ ሞትን እንዳያይ በመንፈስ ቅዱስ ተረድቶ ነበርና ጌታን ባመጡትበት ቀን በመንፈስ ተመርቶ ወደ መቅደስ መጣ:: መጥቶም የሚጠባበቀውን ጌታ አቀፈ::ብዙዎች እናውቃለን ያሉ በመካከላቸው የተገኘውን ጌታ አላወቁትም::

እንደስምኦን ከመንፈስ ቅዱስ ጋር የበረታ ህብረት ሊኖረን ይገባል እርሱ መቼም አያደላ በፊቱ እንሁን እንጂ ይመራል ይናገራል::  ጌታ እየሱስ እንዳለን ከእኔ ወስዶ ለእናንተ ይነግራል ስለወደፊቱም ያሳውቃችኃል ብሏል::  እንጠማው መንፈስ ቅዱስን ያለ እርሱ አንዳች ማድረግ አይቻልም::

ስምኦን ስለጌታ ያለውን እናስተውል ያዘጋጀኸውን ማዳንህን እንዲሁም ለአሕዛብ ሁሉ የሚገልጥ ብርሃን ለሕዝብህም ለእስራኤል ክብር ነው። ይሄ ቃል ኪዳን የተገባው ለአብርሃም ነበረ በአንተ የምድር  ነገዶች ሁሉ ይባረካሉ ተብሎ ነበረ:: ይህ የሚባርክ ጌታ ለአህዛብ ሁሉ መጣ ወይም ለሰው ልጆች!  በደህንነት ስራው ውስጥ አህዛብን ሁሉ ያሰበ ጌታ ይባረክ!  ዛሬ በፊቱ ይህ ብርሃን በርቶልን ቆመናልና ክብር ምስጋና ይብዛለት!

አባት ሆይ ከአንተ ጋር ህብረት ማድረግ በመንፈስ መመላለስ የጊዜውንና የውደፊቱን እቅድህን ከአንተ በመስማት የነቃን አድርገን በምትሰራበትም ጊዜ ገንዘቦችህ አድርገን::  አሜን!

ሉቃስ 2: 36-40

38፤ በዚያችም ሰዓት ቀርባ እግዚአብሔርን አመሰገነች፤ የኢየሩሳሌምንም ቤዛ ለሚጠባበቁ ሁሉ ስለ እርሱ ትናገር ነበር።

40፤ ሕፃኑም አደገ፥ ጥበብም ሞልቶበት በመንፈስ ጠነከረ፤ የእግዚአብሔርም ጸጋ በእርሱ ላይ ነበረ።

ነብይት ሃና በጣም አርጅታ ነበር፤ በጾምና በጸሎትም ሌሊትና ቀን እያገለገለች ከመቅደስ አትለይም ነበር። አርጅታም እንኳን ከአገልግሎት አልታጣችም በዚህም ላይ ጨምራ በጾምና በጸሎት ሌሊትና ቀን ትተጋ ነበረ::  ይገርማል!!  ጌታ ግን አይቷት ነበረና ወደ ቤተመቅደሱ ባመጡት በዚያው ሰዓት የምትጠባበቀውን ጌታ አገኘችው::  ይገርማል በዚያች ሰዓት ተገኘች!  እርስዋም የኢየሩሳሌምንም ቤዛ ለሚጠባበቁ ሁሉ ስለ እርሱ ትናገር ነበር።

እኛም ዛሬ ጌታ ሊመጣ በደጅ ባለበት ሰዓት ላይ ነንና በትጋት እንጠባበቅ ስምኦንም ሃናም ያደረጉት ይህንኑ ነው ደግሞም አላፈሩም አገኙት::  ሌላው ስለእርሱ ትናገር ነበረ ይላል::  ወንጌልን ልንናገር የተጠራን ነንና ስለጌታችንና አምላካችን ማዳን በነፃ ስለሆነው ወንጌል እንናገር::

ሕፃኑም አደገ፥ ጥበብም ሞልቶበት በመንፈስ ጠነከረ፤ የእግዚአብሔርም ጸጋ በእርሱ ላይ ነበረ። አሜን!  ይህ የእግዚአብሔር ጸጋ በእኛም ላይ ይሁን ጥበብን ይሙላብን ያበርታን ያጠንክረንለተጠራንለትጥሪ ያስታጥቀን::

አባት ሆይ ልትመጣ በደጅ ነህና  ተዘጋጅተን በመክሊታችንም አትርፈን ዘይታችንም ሞልቶ እንድንገኝ እርዳን:: አሜን!

ሉቃስ 2: 41-52

49፤ እርሱም፦ “ስለ ምን ፈለጋችሁኝ? በአባቴ ቤት እሆን ዘንድ እንዲገባኝ አላወቃችሁምን?” አላቸው።

50፤ እነርሱም የተናገራቸውን ነገር አላስተዋሉም።

የአንድ ቀን መንገድ ከሄዱ በኃላ ነበረ ዮሴፍና ማርያም ብላቴናው ኢየሱስ ከፋሲካው በዓል አብሯቸው እንዳልተመለሰ ያስተዋሉትና ፍለጋ የተመለሱት:: ባዩትም ጊዜ ተገረሙ፥ እናቱም፦ “ልጄ ሆይ፥ ለምን እንዲህ አደረግህብን? እነሆ፥ አባትህና እኔ እየተጨነቅን ስንፈልግህ ነበርን፡” አለችው። እርሱ ግን  “ስለ ምን ፈለጋችሁኝ? በአባቴ ቤት እሆን ዘንድ እንዲገባኝ አላወቃችሁምን?” ሲላቸው እነርሱ ግን አላስተዋሉም:: በዓመት አንድ ጊዜ ወንድ ሁሉ በእግዚአብሔር ፊት መታየት ስላለበት ይህንኑ ለመፈጸም መገኘታቸውን ብቻ ነው ያሰቡት::  ሊፈልጉት የሄዱት ጌታ በመካከላቸው እየተመላለሰ እንዳለ ባወቁ!

እየመለሰላቸው ያለው አባቴ እግዚአብሔር ነው የምገኘውም በቤቱ ነው እያላቸው ነው:: በ12 ዓመቱ የአባቱን ቤት ስራ እየሰራ ነበረ::  ከቤተሰቡ ስር እንኳን ወደኃላ ቢቀርም ብዙም አልተሰማውም::  እኛም ጉዳያችን ሁሉ ስለቤቱ ስራ መሆን አለበት:: ልጆቻችንንም ወደቤቱ እንዲመጡና እንዲተከሉ እናድርግ ደግሞም እንጸልይ::

አባት ሆይግድ የሚለን የአንተ ቤት ስራ ይሁን የምትናገረንንም እንድናስተውል እርዳን::  ልጆቻችንም በቤትህ ይለምልሙ እራስህንም ግለጥላቸው:: በኢየሱስ ስም አሜን!

ሉቃስ 3: 1-20

2፤ ሐናና ቀያፋም ሊቃነ ካህናት ሳሉ፥ የእግዚአብሔር ቃል ወደ ዘካርያስ ልጅ ወደ ዮሐንስ በምድረ በዳ መጣ።

አንድ ሊቀ ካህናት መኖር ሲገባው ሁለት ናቸው ሐናና ቀያፋ::  በትክክለኛው በእግዚአብሔር የሚ ታወቀው ቀያፋ ነበረ ህዝብ ሁሉ ከሚጠፋ አንድ ሰው ስለህዝቡ ይሙት ብሎ ትንቢትን የተናገረ ነው:: ታሪክ እንደሚነግረን ግን ሮማዎች እንዲወርድ አስገድደውት ነው::

የእግዚአብሔር ቃል ወደ ዘካርያስ ልጅ ወደ ዮሐንስ በምድረ በዳ መጣ ይላል::  መጥምቁ ዮሐንስ ትልቅ አገልግሎት ይዞ የመጣ ነው:: ይህንንም እንዲፈጽም በመንፈስ ቅዱስ ተሞልቷል::  መንገዱን ለጌታ የሚያስተካክል ሰው ነበረ::  ከፍ ያሉትን ቃሉን እናውቃለን ከእኛ ሌላ ማን አለ የሚሉትን ዝቅ በሉ ዝቅ ያሉትን ቀራጭ የነበሩትን ለእናንተም ነው ጌታ የመጣው ተጠባበቁ:: ህይወታቸው የተበለሻሸውንም እንደነ መቅደላዊት ማርያም ያሉትን ጠብቁ መፍትሄ እየመጣ ነው ያለ ድምጽ ነው:: ድምጹም:- “ሥጋም የለበሰ ሁሉ የእግዚአብሔርን ማዳን ይይ፡”  አሜን!  እኛም አህዛቦች ይኸው ማዳንህን አየን! ተመስገን!

ሁሉን አንድ ሊያደርግ የመጣ ጌታ አይሁድ የለ አህዛብ ወይም ወንድ የለ ሴት ደግሞም ጨዋ የለ ባርያ! ሁሉም በክርስቶስ አንድ ነው::  የጥሉን ግድግዳ ሁሉ አፈረሰው:: 

ማነህ ሲባል ዮሐንስ:- ዮሐንስ መልሶ፦ “እኔስ በውኃ አጠምቃችኋለሁ፤ ነገር ግን የጫማውን ጠፍር መፍታት ከማይገባኝ ከእኔ የሚበረታ ይመጣል፤ እርሱ በመንፈስ ቅዱስና በእሳት ያጠምቃችኋል፤ መንሹም በእጁ ነው፥ አውድማውንም ፈጽሞ ያጠራል፥ ስንዴውንም በጎተራው ይከታል፥ ገለባውን ግን በማይጠፋ እሳት ያቃጥለዋል፡” አላቸው።

አባት ሆይ አንተ በመንፈስ ቅዱስና በእሳት አጠመከን::  ዮሐንስ የተላከበትን ስራውን በፍጹም ታዘዘና አገለገለህ::  እኛም የተጠራልነትን ስራህን እንድናገለግል እርዳን ጸጋ ይጨመርልን::  አሜን!

ሉቃስ 3: 21-38

21፤ ሕዝቡም ሁሉ ከተጠመቁ በኋላ ኢየሱስ ደግሞ ተጠመቀ። ሲጸልይም ሰማይ ተከፈተ፥ 22፤ መንፈስ ቅዱስም በአካል መልክ እንደ ርግብ በእርሱ ላይ ወረደ፤ የምወድህ ልጄ አንተ ነህ፥ በአንተ ደስ ይለኛል የሚል ድምፅም ከሰማይ መጣ።

ኢየሱስ ስለኃጥያት መጠመቅ አልነበረበትም እርሱ ግን ታዘዘና ተጠመቀ ትንቢቱ ይፈፀም ዘንድ::  በዚህ ጊዜ መንፈስ ቅዱስም በአካል መልክ እንደ ርግብ በእርሱ ላይ ወረደ፤ የምወድህ ልጄ አንተ ነህ፥ በአንተ ደስ ይለኛል የሚል ድምፅም ከሰማይ መጣ።

የምወድህ ልጄ አንተ ነህ፥ በአንተ ደስ ይለኛል ተባለ::  ይህንን ጌታ ልበሱት ተብለን ለበስነው አሁንም በአብ ፊት መታያችን እርሱ ነው::  አንድ ጊዜ አባቱንደስ አሰኝቷልና በእኛም ላይ ሲያየው ደስ ይለዋል::  እንጂ በአንዳች በስራችን ተቀባይነትን ያገኘን አይደለንም::

ኢየሱስም ሊያስተምር ሲጀምር ዕድሜው ሠላሳ ዓመት ያህል ሆኖት ነበር እንደመሰላቸው የዮሴፍ ልጅ ሆኖ፥ የኤሊ ልጅ አልነበረም::  እርሱ የእግዚአብሔር ልጅ ነው::  መንፈስ ቅዱስ በእርሱ ላይ ከመጣ በኃላ አገልግሌቱን ጀመረ::  እኛም መንፈስ ቅዱስ  እጅግ ያስፈልገናል ያለ እርሱ አንዳች ማድረግ አንችልም:: ኃይልን እስክትቀበሉ በእየሩሳሌም ቆዮ የተባሉትም ለዚሁ ነው ከመጣ በኃላ አገልግሎታቸውና ህይወታቸው እንዴት እንደተቀየረ እናውቃለን::

አባት ሆይ በመንፈስ ቅዱስ ኃይላችንን አድስ አንተን ደስ ማሰኘትና ማገልገል ይሁንልን::  አሜን!

ሉቃስ 4: 1-2

1፤ ኢየሱስም መንፈስ ቅዱስ መልቶበት ከዮርዳኖስ ተመለሰ፥ በመንፈስም ወደ ምድረ በዳ ተመርቶ፥ 2፤ አርባ ቀን ከዲያብሎስ ተፈተነ። በነዚያም ቀኖች ምንም አልበላም፥ ከተጨረሱም በኋላ ተራበ።

በዮሃንስ እጅ ዝቅ ብሎ ከተጠመቀ በኃላ መንፈስ ቅዱስ መልቶበት ከዮርዳኖስ ተመለሰ::   እንዲሁም በሐዋ. ሥራ 10:38፤ እግዚአብሔር የናዝሬቱን ኢየሱስን በመንፈስ ቅዱስ በኃይልም ቀባው፥ እርሱም መልካም እያደረገ ለዲያብሎስም የተገዙትን ሁሉ እየፈወሰ ዞረ፥ እግዚአብሔር ከእርሱ ጋር ነበረና፤ ይላል::

በመንፈስም ወደ ምድረ በዳ ተመርቶ፥  ሲወጣ የሆነው ነገር አልጋ ባልጋ አልነበረም::  የጠበቀው አርባውንም ቀን መፈተን ነው:: ቃሉም እንደሚል አርባ ቀን ከዲያብሎስ ተፈተነ።  ጌታ ሆኖ በመንፈስ ቅዱስ  ኃይልም ተሞልቶ እያለ ጠላት አልተኛም ስለዚህ በምናልፍበት በማንኛውም ፈተና ጌታ መፈተኑን እያየን እንበርታ::   በነገር ሁሉ የተፈተንና የሚራራ አምላክ ነው ያለን::

በነዚያም ቀኖች ምንም አልበላም፥ ከተጨረሱም በኋላ ተራበ። ጠላታችን ዲያቢሎስ የሚውጠውን ፈልጎ ያለ እረፍት ይዞራል ነገር ግን ጌታ ከእኛ ጋር ነውና አሸናፊዎች ነን::  ጠላት እንደሆነ መሞከሩን አይተውም  እኛም መታመናችንን አንተውም:: በፈተና የሚጸና  ብጹእ ነው እንደሚል እንጽና ጌታም መውጫውን ይሰጠናል አንደናገጥ አንርበትበት ከእኛ ጋር ያለውን እንወቅ::

ሉቃስ 4:3-4

3፤ ዲያብሎስም፦ “የእግዚአብሔር ልጅ ከሆንህ፥ ይህን ድንጋይ፦ ‘እንጀራ ሁን፡’ ብለህ እዘዝ፡” አለው። 4፤ ኢየሱስም፦ “ ‘ሰው በእግዚአብሔር ቃል ሁሉ እንጂ በእንጀራ ብቻ አይኖርም፡’ ተብሎ ተጽፎአል፡” ብሎ መለሰለት።

አርባውን ቀን ሁሉ በዲያቢሎስ ሲፈተን የቆየው ጌታ በነዚህ ቀናት ምንም አልበላምና ተራበ::  ሁሉን የፈጠረ ጌታ ተራበ?!  ይህንን ክፍተት ያወቀ ጠላት ቃል ይዞ ብቅ አለ:: ሄዋን ጋር  ተሳክቶለት ነበረና ይህንኑ ልምዱን ይዞ መጣ::  ይዞ የመጣው ቃል ጌታ እየሱስ ተጠምቆ ሲወጣ ድምጽ ከሰማይ መቶ ነበረና እሱኑ ይዞ መርዝ ቀላቅሎ መጣ::

የእግዚአብሔር ልጅ ከሆንህ፥ ይህን ድንጋይ፦ ‘እንጀራ ሁን፡’ ብለህ እዘዝ፡” አለው።  መርዙ ልጅ ከሆንክ ላይ ነው::  እንደሆነማ ተመሰከረ!  የሌላውን ማረጋገጫ ያላስፈለገው ጌታ ግን በኤፌሶን 6 ላይ እንደተማርነው ቃሉ የመንፈስ ሰይፍ ነውና አውጥቶ ተጠቀመበት:: ሰው በእግዚአብሔር ቃል ሁሉ እንጂ በእንጀራ ብቻ አይኖርም፡’ ተብሎ ተጽፎአል፡” ብሎ መለሰለት። አሜን! 

በጠላት ኃይል ሁሉ ላይ ስልጣን ተሰቶናል የሚጎዳንም የለም::  ጠላት የቀረለት ሽንገላ ነውና  ለዚህ ሽንገላው አንንበርከክ እናሳደው ከአሸናፊዎች በላይ ነንና በአይምሯችን መታደስ እንለወጥ ቃሉ ይለውጠው አስተሳሰባችንን::  መልክት ጌታ ሲናገር ጠላትም እየሰማ እንደሆነ እንወቅ::  እንንቃ ጠላት ዙሪያችንን የሚዞር ምንም ማድረግ የማይችል ነው እድል ካልሰጠነው::  ስለዚህ በቃሉ እውነት እንሞላ እንደቃሉም እናስብ::  የተቀበልነውን የተስፋ ቃል አጥብቀን እንያዝ እንዳያስጥለን:: የምንዋጋበትን የእግዚአብሔርን ቃል እንያዝ በዚህ ሁሉ ላይ  ደግሞ በጌታና በኃይሉ ችሎት እንበርታ!

ሉቃስ 4: 5-8

7፤ ስለዚህ አንተ በእኔ ፊት ብትሰግድ፥ ሁሉ ለአንተ ይሆናል፡” አለው። 8፤ ኢየሱስም መልሶ፦ “ ‘ለጌታ ለአምላክህ ስገድ እርሱንም ብቻ አምልክ፡’ ተብሎ ተጽፎአል፡” አለው።

አርባ ቀን ሙሉ ሲፈትነው የቆየው ዲያቢሎስ መቼም ኢችን ሶስት ሽንገላ ብቻ አይደለም ወደእርሱ ይዞ የመጣው ብዬ አስባለሁ::  ልጅ ከሆንክ የሚለው ወጥመዱ መክሸፉን ሲያይ ስገድልኝና ክብርን ሁሉ ልስጥህ ብሎ መጣ::

የሚገርመኝ ነገር የዓለምን መንግሥታት ሁሉ በቅጽበት አሳየው።  ይህ ሥልጣን ሁሉ ክብራቸውም ለእኔ ተሰጥቶአል፥ ለምወደውም ለማንም እሰጠዋለሁና ለአንተ እሰጥሃለሁ ማለቱ ነው:: ማን ሰጠውና? አዳምም አይደል?  አሁን መቀምያው እንደሆነ አላወቀ!  ለመስቀል ሞት በመታዘዝ ከስም ሁሉ በላይ የሆነ ስምን ሰቶን እናንበረክከዋለን ዛሬ::  በትንሳኤው ጉልበት ኢየሱስ ከሞት ተነስቶ የሞትና የሲኦልን ቁልፍ ይዟል::  ለዲያብሎስ የቀረ ስልጣን የለም ሁሉንም ተቀምቷል ያለው ሽንገላ ብቻ ነውና በቃሉ እውነት ተሞልተን ስራውን እናፍርስበት:: 

ሰው ዓለሙን ሁሉ ቢያተርፍ ነፍሱን ግን ቢያጣ ምን ይጠቅመዋል?!  መርዙ ቀላል አይደለም የሚመጣበት መንገድ ረሃብን እንዲሁም ብልጽግናንና ክብርን አስታኮ መጣ::  ድፍረቱ ለፈጠረው ጌታ ይህንን ሁሉ ክብር ስገድልኝ እንጂ እሰጥሃለሁ ይላል ::  በዙሪያችንም ስናይ ማን ለእርሱ ሰግዶ በሰላም ተቀመጠ?  ፍፃሜያቸውን አይተናል::  የእኛ ጌታ ግን እውነተኛ እረኛ የዓለምን ክብር ሳይሆን እራሱን ሰጠን ወደንና ፈቅደን ደስም ብሎን እንሰግድለታለን::

ኢየሱስም መልሶ፦ “ ‘ለጌታ ለአምላክህ ስገድ እርሱንም ብቻ አምልክ፡’ ተብሎ ተጽፎአል፡” አለው። አሜን!  ሊሰገድለትና ሊመለክ የሚገባው ለእርሱ ብቻ ለፈጠረን በደሙም ለዋጀን ለእውነተኛው ጌታ ብቻ ነው::  አሜን!!

አባት ሆይ እኔም ትውልዴም አንተን ብቻ እናመልካለን ለአንተም ብቻ እንሰግዳለን! አሜን! 

ሉቃስ 4:9-13

ሉቃስ 4:12፤ ኢየሱስም መልሶ፦ “ ‘ጌታን አምላክህን አትፈታተነው’ ተብሎአል፡” አለው።

ወድቀህ ብትሰግድልኝ ይህንን ሁሉ ክብር ለምወደው እሰጣለሁ ሲል ትንሽ ስቅጥጥ አይለውም ሲዋሽ::  ምን መውደድ አለው መግደልና ማጥፋት እንጂ! ይሄኛው ፈተናው ስለከሸፈበት ወደ ታች ራስህን ወርውር በሚለው ፈተና ተገለጠ:: 

ጠላት ያለውን ሁሉ ወርድሯል ከዚህ በላይ ምንም ማድረግ አይችልም ምክንያቱም ፍጥረት ነው ያልቅበታል::  ይዞ  የሚመጣውም ፈተና እስከአሁን የተጠቀመበትን ነው:: ብትወድቅ መልአክቱን ስለአንተ ያዝልሃል ሲለው ኢየሱስም መልሶ፦ “ ‘ጌታን አምላክህን አትፈታተነው’ ተብሎአል፡” አለው። በቃሉ መለሰለት እንጂ  ጌታችን በሌላ መልኩ ሲጋበዝ አናየውም ጀግና ጀግና መጫወት የለብንም::  ቃሉና ስሙ በቂ መዋግያ ነው::

በ1 ዮሐንስ 2:15-16፤ ዓለምን ወይም በዓለም ያሉትን አትውደዱ፤ በዓለም ያለው ሁሉ እርሱም የሥጋ ምኞትና የዓይን አምሮት ስለ ገንዘብም መመካት ከዓለም ስለ ሆነ እንጂ ከአባት ስላልሆነ፥ ማንም ዓለምን ቢወድ የአባት ፍቅር በእርሱ ውስጥ የለም። የጌታን መፈተን በዚህ ቃል ውስጥ እስኪ እንየው ያልተፃፈልን አቅጣጫ የለምና:- 

የሥጋ ምኞት የሚለውን ምሳሌው ድንጋዮን ዳቦ አድርግ ያለበት አይነት ነው::

የዓይን አምሮት – (ሄዋንንም የጣለበት) ወድቀህ ብትሰግድልኝ ይህንን ሁሉ ክብር እሰጥሃለሁ ያለው ነው::

ስለ ገንዘብም መመካት – ትምክህት/ትዕቢት ብዙ መገለጫ አለው  እኛ ግን የተባልነው ትሁት እንድንሆን ነው በፈተና  ከመውደቅ ይጠብቀናልና:: የሚመካ በጌታ ይመካ!

ስለዚህ በምናልፍበት ነገር አናድንቅ ለሁሉ ነውና ፈተና:: በ1 ቆሮንቶስ 10:13፤ ለሰው ሁሉ ከሚሆነው በቀር ምንም ፈተና አልደረሰባችሁም፤ ነገር ግን ከሚቻላችሁ መጠን ይልቅ ትፈተኑ ዘንድ የማይፈቅድ እግዚአብሔር የታመነ ነው፥ ትታገሡም ዘንድ እንድትችሉ ከፈተናው ጋር መውጫውን ደግሞ ያደርግላችኋል።

ዲያቢሎስም ፈተናውን ሁሉ ከጨረሰ በኋላ እስከ ጊዜው ከእርሱ ተለየ። በያዕቆብ 4:7፤ እንግዲህ ለእግዚአብሔር ተገዙ፤ ዲያብሎስን ግን ተቃወሙ ከእናንተም ይሸሻል::  ተመልሶ አይመጣም አልተባልንም ይሸሻል ወይም ለጊዜው ተለየ እንጂ::  እግዚአብሔር ማንንም አይፈትንም ዲያቢሎስ ነው የሚፈትነን በቃሉ ተሞልተን ጸንተን እንቃወም::  ነገራችንን ከሰው ጋር አናያይዝ ከኃላ ያለውን እንንቃበትና እንምታው! 

ሉቃስ 4: 1-13 (ክለሳ)

1፤ ኢየሱስም መንፈስ ቅዱስ መልቶበት ከዮርዳኖስ ተመለሰ፥ በመንፈስም ወደ ምድረ በዳ ተመርቶ፥

ይህንን ክፍል ትንሽ ደቆስ አድርገን እንጭመቀው ብዬ ነው እንደገና ያጠናሁት::  ምክንያቱም በተለያየ ፈተና እናልፋለንና ጠላት ምን ላይ እንደሚያተኩርና እኛስ ምን ማድረግ አለብን እንድናስተውል ነው::

ከሶስቱ ፈተናዎች ሁለቱ ልጅ ከሆንክ ነው የሚሉት::  ለምን ልጅነትን ይመታል? እሱን ከወሰደብን ሌላ የምንቆምበት መሰረት ያሳጣናልና ነው::  አንቺን ብሎ ክርስትያን ሲለን እውነትም ብለን ስብር እንልና ምህረትና ጸጋ እንዳለ እንረሳለን::  ያኔ ለእርሱ ይመቸዋል ከቅዱሳንና ከቤተክርስትያን  ያርቀናል ከዛማ ካልነቃን ከባድ ነገር ውስጥ ይከተናል::  ብንደክም ለጌታ ብንበረታ ለጌታ::  ለፈተናው መመለስ ያለብን እየሱስ ነው በእኔ ውስጥ ክርስትያን ድሮውንም በራሴ አልጸደኩ:: እንዲያውም ጠላቴ በድካሜ ጸጋውን ይሰጠኛል  በትከሻውም የሚሸከመኝ እረኛ አለኝ ሮጬ ወደ እርሱ እሄዳለሁ ይረዳኛል ብለን መመለስና መበርታት  ይገባናል:: በክርስቶስ ምን እንደሆንን ከቃሉ ጠንቅቀን እንወቅ::  

ምን እናድርግ:-

ወደ ፈተና እንዳትገቡ ትጉና ጸልዮ ተብለናል::  ፈተና የለም አላለንም አሸንፌያለሁ ብሎናል:: እራሱም እየሱስ በመጨረሻዋ ሰዓት ብቻውን ተጋ እንጂ ሐዋርያቱማ እንቅልፍ እንቅልፍ ብሏቸው ነበረና ጌታ ስለእነርሱም ማለደ::  ስለእራሳችን ብቻ ሳይሆን ስለቅዱሳንም መማለድን አንርሳ::  ፈተናው መጥቶ ሲመታን በአለቱ ላይ ቤታችንን ሰርተናልና ሰባብሮ ይዞን  አይሄድም::

እንዳንረታ በክርስትና ዋናው ሃብታችን መንፈስ ቅዱስ ነው::  ጌታ እየሱስ በመንፈስ ተሞልቶ ነው አርባውንም ቀን እየተፈተነ በርትቶ ለአንዱም የሰይጣን ፈተና ሳይወድቅ እኛን ተቤዥቶ ያለው:: ዛሬ የሚራራልን ሊቀ ካህናት ቢፈተንም ያልተረታ አለልን::  ስለዚህ ዕለት ዕለት በመንፈስ ተሞሉ እንደሚል ጠይቀን  እንሞላ::  እርሱ እንደሆነ በልግስና ሳይሰፍር መንፈሱን ይሰጠናል::  ስሙ ይባረክ! 

ሌላው ጌታ እየሱስ ከዲያቢሎስ ጋር አታካራ አልገባም ::  ይመልስ የነበረው የተጻፈው ቃል ነበረ:: ስለዚህ ዛሬም መዋጊያችን በሁለት በኩል የተሳለው የመንፈስ ሰይፍ ነው:: ቃሉን እንብላ እናሰላስለው ከእርሱም ፈቀቅ አንበል በጸሎትም እንትጋ:: 

ሉቃስ 4: 14-21

17-19፤ የነቢዩንም የኢሳይያስን መጽሐፍ ሰጡት፥

ኢየሱስም በመንፈስ ኃይል ወደ ገሊላ ተመለሰ፤ ስለ እርሱም በዙሪያው ባለችው አገር ሁሉ ዝና ወጣ።   ከአርባ ቀን ጾም በኃላ ኢየሱስ የበረታው  በመንፈስ ኃይል ነበረ::   የጌታ ዝና እየወጣ ሄደ በምኩራብም ያስተምር ጀመረ::  በዚህም ጊዜ ነው የኢሳያስን መጽሐፍ የሰጡትና አንብቦ ሳያብራራ የተቀመጠው:: ምን ማብራራት ያስፈልጋል በፊታቸው ቆሞ እየፈጸመው?!  ማስተዋል ይስጠን ከጌታ ጋር እንዳንተላለፍ::

ክፍሉም የሚለው: የጌታ መንፈስ በእኔ ላይ ነው፥ አሜን ይህ መንፈስ በእኛም ላይ ነው:: ምን ለማድረግ?

– ለድሆች ወንጌልን እሰብክ ዘንድ ቀብቶኛልና፤ 

– ለታሰሩትም መፈታትን 

– ለዕውሮችም ማየትን እሰብክ ዘንድ፥ 

– የተጠቁትንም ነጻ አወጣ ዘንድ 

– የተወደደችውንም የጌታን ዓመት እሰብክ ዘንድ ልኮኛል፡:

የተላከበትን ዓላማ ቁልጭ አድርጎ ነገራቸው::  እኛም የተላክነው ለዚሁ ነው:: እኛም የተላክነው ለድሆች: ለታሰሩ: ለዕውሮችና ለተጠቁት ነው::  ወንጌል ስለእየሱስ ነው ይህንን ሁሉ የሚያደርግና የሚሰራ እራሱ በመንፈሱ ነው:: እንዲሁም የተወደደችውንም የጌታን ዓመት ሰበከ ይህም ማለት እዮበልዮ ነው በዕዳ ሁሉ የተያዙት በየ50 ዓመቱ ነፃ የሚወጡበት ጊዜ ነውና የጌታ ዓመት ሲላቸው በደንብ ይገባቸዋል:: ማንም ዕዳ አይኖርበትም ብሎ አወጀ እኛም ነፃ ሆንን የሚከሰን እስከማይኖር ድረስ – ማንም በክርስቶስ ቢሆን ኩነኔ የለበትም:: ይህንን እንድንሰብክ ተጠርተናል::  ማለትም የእግዚአብሔር በግ እየሱስ ተገልጧል የዕዳው  ጽህፈት ተደምስሷል ሞትና ሲዖልም ድል ተነስተዋል አርነት ታውጇል ብለን እናውጃለን:: አሜን!

አባት ሆይ ስራችንን ችላ እንዳንል እርዳን! አሜን

ሉቃስ 4: 22-30

22፤ ሁሉም ይመሰክሩለት ነበር ከአፉም ከሚወጣው ከጸጋው ቃል የተነሣ እየተደነቁ፦ “ይህ የዮሴፍ ልጅ አይደለምን?” ይሉ ነበር።

ወንጌል ምን እንደህነና ለማን እንደሆነ ከትንቢቱ ነገራቸው:: ወንጌል ለድሆች: ለታሰሩት: ለዕውሮችና ለተጠቁት ነው::  ይህንን መስፈርት ስላሟላን ይህንን ጌታ አወቅን እንጂ አንዳች በእኛ ባልሆነ መንገድ ዳንን::  ይህንንም ወንጌል ልናደርስ አደራ ተሰጠን:: እንዲሁም የተወደደችውን የጌታን ዓመት ይኸውም የመምጣቱንና የመመለሱን ዜና እንድንናገር ተጠርተናል::ማራናታ!

ከልጅነቱ ጀምሮ ወዳደገበት ወደ ገሊላ መጥቶ ሲያስተምር ይህ የዮሴፍ ልጅ አይደለምን? ማለትን ጀመሩ ከአፉ ከሚወጣው ከጸጋው ቃል የተነሳ እየተደነቁ::  መተላለፍ ሆነባቸው ከእግዚአብሔር ልጅ ጋር የዮሴፍ ልጅ መስሏቸው::  ስለዚህም ይለይላችሁ ብሎ የኤልያስን ወደ ሰረፕታዋ መበለት መላክና ስለንዕማን ለምጽ ነገራቸው:: 

ብዙ መበለቶች በእስራኤል ቢኖሩም እንኳን የተላከው ወደ አህዛቢቷ ሴት ነበረ::  በእስራኤልም ብዙ ለምጻሞች እያሉ ከሩቅ መጥቶ ንዕማን ተፈወሰ::  ስለዚህ የእግዚአብሔርን ማዳን ካልተቀበላችሁ አሁንም ይኸው ነው የሚሆነው እያላቸው ነው::  በቅድሚያ ለጠፋው ለእስራኤል ነበር ወንጌል አልሰማም ሲሉ ወደ አህዛብ ደረሰ::  ይኸው ዛሬ የከበረውን ቃል እየተመገብን ከመንፈሱም እየጠጣን አለን::  እስራኤል ግን እስከዛሬ ጠፍታለች::  አቤቱ ለዚህ ህዝብ ወንጌል ይድረስ ደንዳናውን ልባቸውንም ፈስው:: አሜን!

ይህ ንግግሩ አስቆጥቷቸው ከከፍታ ላይ ሊጥሉት  ወሰዱት  እርሱ ግን ጊዜው አልደረሰምና  በመካከላቸው አልፎ ሄደ::  ሰው በዚህ እንኳን እንዴት አያስተውልም?!  በሌላ ስፍራ ካለማመናቸው የተነሳ ብዙ ማድረግ አልቻለም ነበር::  ነብይ በአገሩ አይከበርም::

አባት ሆይ እኛን የበረሃ ወይራ የነበርነውን አሰብከን በወይኑም ግንድ ላይ አደረከን ተመስገን::  ወንጌልን ይዘን እንሮጥ ዘንድ ልጆችህን እርዳን::  አሜን!

ሉቃስ 4: 31-37

32፤ ቃሉ በሥልጣን ነበርና በትምህርቱ ተገረሙ።

ባደገበት ከተማ የዮሴፍ ልጅ አይደለምን ብለው ሳይሰሙት ቀሩ:: ወደ ቅፍረናሆም ወርዶ ሲያስተምር ቃሉን በስልጣን ያስተምር ነበረና በትምህርቱ ተገረሙ::

እያስተማረም አጋንንት ያደረበት ሰው “ተው፥ የናዝሬቱ ኢየሱስ ሆይ፥ ከአንተ ጋር ምን አለን? ልታጠፋን መጣህን? ማን እንደ ሆንህ አውቄሃለሁ፥ አንተ የእግዚአብሔር ቅዱሱ፡” አለ። ኢየሱስም፦ “ዝም በል ከእርሱም ውጣ” ብሎ ገሠጸው። ጋኔኑም በመካከላቸው ጥሎት ሳይጐዳው ከእርሱ ወጣ።

ማን እንደ ሆንህ አውቄሃለሁ፥ አንተ የእግዚአብሔር ቅዱሱ::  አጋንንት በደንብ አውቀውታል የእግዚአብሔር ህዝብ ግን አላወቀም::  የጠላትን ምስክርነት አንፈልግም የልጅነት ስልጣን የተሰጠንና ከአሸናፊዎችም በላይ መሆናችንን ቃሉ መስክሮልናልና ሌላ ምስክር አያስፈልገንም:: ዛሬም ይህንን የተሸነፈ አጋንንት በስሙ ስልጣን እያወጣን ሰዎችን ለጌታ እንማርክ::  እርሱም ይወጣል! 

ከዚህ ተአምር በኃላ ዝናው  በዙሪያው ባለች አገር ወደ ስፍራው ሁሉ ስለ እርሱ ወጣ። ይህ እንዲሆን ቅናቴ ነው – የኢየሱስ ዝና ይውጥና ሰዎች ወደ እርሱ ይሰብሰቡ!  እኛን ሳይሆን እርሱ ይታይ! መዳን ይታወጅ!  ለታሰሩትና ለታወሩት ወንጌል ይድረስ::  አሜን!  አንብበንና ሰምተን እንድንሄድ ሳይሆን እንጸልይ የመከሩ ጌታ የመከሩን ሰራተኞች እንዲጨምርና እኛንም እንዲልከን:: 

አባት ሆይ እኔንም ላከኝ ወደ መከሩ ሰውን አጥማጅ አድርገኝ::  አሜን

ሉቃስ 4: 38-41

40፤ ፀሐይም በገባ ጊዜ በልዩ ልዩ ደዌ የተያዙ በሽተኞችን ሁሉ ወደ እርሱ አመጡአቸው፤ እርሱም በእያንዳቸው ላይ እጁን ጭኖ ፈወሳቸው።

በእያንዳቸው ላይ እጁን ጭኖ ፈወሳቸው።  እንዴት ደስ ይላል ባለመለየት ሁሉንም ፈወሰሰ:: ጌታ ኢየሱስ ዛሬም ይፈውሳል::  በመገረፉ ቁስል እኛ ተፈወስን::  መፈወሳችንም ደስ ያሰኘዋል የልጆችም እንጀራ ነው ብሎ ጠርቶታልና በአባታችን ቤት መብል አንከለከልም:: አጋንንትም በስሙ ይወጣል!

አባት ሆይ ስምህ ይባረክ!  ረውስን ለህዝብህ ሰተሃልና ዛሬም በህመም የሚሰቃዮ በኢየሱስ ስም ይፈወሱ::  አሜን!

ሉቃስ 4:42-44

43፤ እርሱ ግን፦ “ስለዚህ ተልኬአለሁና ለሌሎቹ ከተማዎች ደግሞ የእግዚአብሔርን መንግሥት ወንጌል እሰብክ ዘንድ ይገባኛል፡” አላቸው።

በጸባም ጊዜ ወጥቶ ወደ ምድረ በዳ ሄደ፤ ሕዝቡም ይፈልጉት ነበር፤ ምክንያቱም ፈውስንና የአጋንንትን መታዘዝ አይተው ነበረና  ወደ እርሱም መጡ፥ ከእነርሱም ተለይቶ እንዳይሄድ ሊከለክሉት ወደዱ። እዚህ ኑር አስተምረን ፈውሰን የትም አትሂድ ነው አባባላቸው::  

እርሱግን በየስፍራው ሁሉ የመንግስትን ወንጌል እየሰበከ ዞረ:: ዛሬም በስፍራ ሁሉ መሰበክ አለበት ጌታ ሊመጣ በደጅ ነውና ከወገን ከቋንቋ ሁሉ ሰዎች ወደ ኢየሱስ ዘወር እንዲሉ::  ጌታ ጸጋውን ያብዛልን ይህንን ወንጌል ይዘን እንድንሮጥ::

ሉቃስ 5: 1-3

3፤ ከታንኳዎቹም የስምዖን ወደ ነበረች ወደ አንዲቱ ገብቶ ከምድር ጥቂት ፈቀቅ እንዲያደርጋት ለመነው፤ በታንኳይቱም ተቀምጦ ሕዝቡን ያስተምር ነበር።

ጌታ ጴጥሮስን ጥቂት ፈቀቅ እንዲያደርጋት ለመነው::  ለመነው የሚለው ነገር ልቤን ነካው የለመነውም ሊያገለግልበት ነው ውስጡ ከገባ በኃላ::  እኛም ውስጥ የገባው ጌታ በሮሜ 12:1፤ እንግዲህ፥ ወንድሞች ሆይ፥ ሰውነታችሁን እግዚአብሔርን ደስ የሚያሰኝና ሕያው ቅዱስም መሥዋዕት አድርጋችሁ ታቀርቡ ዘንድ በእግዚአብሔር ርኅራኄ እለምናችኋለሁ፥ እርሱም ለአእምሮ የሚመች አገልግሎታችሁ ነው። ተብለናልና ለጌታ  ያለ ስስት እራሳችንን እናቅርብ!  ጌታ ሆይ ጸጋህ ያግዘን!

ሉቃስ 5 : 4-7

4: ነገሩንም ከጨረሰ በኋላ፥ ስምዖንን፦ “ወደ ጥልቁ ፈቀቅ በል መረቦቻችሁንም ለማጥመድ ጣሉ፡” አለው።

ለሊቱን ሙሉ ባለሙያ የሆኑት ዓሳ አጥማጆች ምንም እንዳልያዙ ቢነግሩትም እርሱ ግን ጣሉት አላቸው:: በቃሉ ሰማይና ምድርን የፈጠረው ጌታ ዛሬ ቢደግምስ መፍጠሩን?  እነሆም በቃሉ መሰረት መረቡን መተው ሞሉት::  ዛሬም ጌታ ይህንን ማድረግ ይችላልና ሁኔታን አይተን አንመላለስ የጌታን ፊት እንጂ!  እርሱ ተአምራትን ያደርጋል እውቀታችንን አንደገፍ::

ሉቃስ 5: 8-11

8 ስምዖን ጴጥሮስ ግን ባየ ጊዜ በኢየሱስ ጕልበት ላይ ወድቆ፦ “ጌታ ሆይ፥ እኔ ኃጢአተኛ ነኝና ከኔ ተለይ፡” አለው። 9 ስላጠመዱት ዓሣ እርሱ ከእርሱ ጋርም የነበሩ ሁሉ ተደንቀዋልና፥

ሲፈልጉ አድረው ያጡትን ዓሳ በቃሉ መረባቸውን በሞላ ጊዜ ጴጥሮስ ማለት የቻለው “ጌታ ሆይ፥ እኔ ኃጢአተኛ ነኝና ከኔ ተለይ፡” አለው። አሁን ስለ ኃጥያት ምን አመጣው?  የፈለገውን አገኘ ግን የእግዚአብሔርን ልግስና የማይገባኝ ነኝ እኔ ኃጥያተኛ ነኝ ከእኔ ራቅ አለ::  የጌታ መገኘት ማንነቱን አሳየው::  ጌታም አትፍራ ሰውን አጥማጅ አደርግሃለሁ ብሎ ወደ አገልግሎት ጠራው:: የኃጥያተኞች ወዳጅ የተባለው  ጌታ ማንንም ሳይለይ አጥቦ አንጽቶ ይጠቀምብናል::  ሃሌሉያ!!

ሉቃስ 5: 12-16

12 ከከተማዎችም በአንዲቱ ሳለ፥ እነሆ፥ ለምጽ የሞላበት ሰው ነበረ፤ ኢየሱስንም አይቶ በፊቱ ወደቀና፦ “ጌታ ሆይ፥ ብትወድስ፥ ልታነጻኝ ትችላለህ፡” ብሎ ለመነው። 13 እጁንም ዘርግቶ ዳሰሰውና፦ “እወዳለሁ፥ ንጻ፡” አለው፤ ወዲያውም ለምጹ ለቀቀው።

በብሉይ ኪዳን ለምፃምን መንካት ያረክሳል  ስለዚህ ማንም አይቀርበውም የተገለለ ነው::  የዚህ ሰው ጥያቄ ግን ይገርማል ምን ቢያይና ቢተማመን ነው አንፃኝ ብሎ የጠየቀው?! ጌታ ግን ሳይሸሸው እንዲያውም ዳሶ እወዳለሁ ንፃ ብሎ ፈወሰውና ራስህን ለካህን አሳይ አለው::  ዋዉ ጌታ መታሰባችንን ይወዳል ስሙ ይባረክ!

ምንም እንኳን አትናገር ቢለውም ዝናው ወጣ ብዙ ሕዝብም ሊሰሙትና ከደዌአቸው ሊፈወሱ ይሰበሰቡ ነበር::  ዝናው በወጣ ጊዜ ግን እርሱ ወደ ምድረ በዳ ፈቀቅ ብሎ ይጸልይ ነበር ይላል::  እኛስ?  ያውም ጌታ ስራውን ሲሰራ መቼም እኛ አይደለን የምንፈውስ ወዴት ይሆን የምንሮጠው?  ወደ እግሮቹ  ይሁንልን! ከፊቱ አንታጣ!  እርሱ ዛሬም ይሰራል::  ጌታዬ ሆይ ክብርህን ወደ ራሳችንም ይሁን ወደ ሌላ ስጋ ለባሽ በመውሰድ እንዳንበድልህ እርዳን!

ሉቃስ 5:17 አንድ ቀንም ያስተምር ነበር፤ ከገሊላና ከይሁዳ መንደሮችም ሁሉ ከኢየሩሳሌምም መጥተው የነበሩ ፈሪሳውያንና የሕግ መምህራን ይቀመጡ ነበር፤ እርሱም እንዲፈውስ የጌታ ኃይል ሆነለት።

እነዚህ ፈሪሳውያንና የሕግ መምህራን ሲያስተምር ሰምተው ስህተት ለማግኘትና እርሱን ለመክሰስና ነገር ን ለመፈለግ ነው የሚከታተሉት እንጂ ለመማር ወይም የእግዚአብሔርን ድንቅ ስራ ለማየት አይደለም::  ያም ሆነ ይህመምጣታቸው ጥሩ ነው ቢያንስ ኒቆዲሞስን ወደጥያቄ አምጥቶታልና::

ለጌታ እየሱስ እንዲፈውስ የጌታ ኃይል ሆነለት ይላል:: ምን እንዲያደርግ? እንዲፈውስ!!!  መፈወሳችንን የሚወድ ጌታ ስሙ ይባረክ!!  ዛሬም ይሄ ኃይል ይገለጥ በእያንዳንዳችን ምክንያቱም ብዙዎች ፈውስ ያስፈልጋቸዋልና:: ያቺ ሴት ስትፈወስ ኃይል ከእኔ ወጣ አለ ብዙዎች እያጋፉት እርስዋ ግን ተንጠራርታ የልብሱን ጫፍ በእምነት ነካችና ፈውስ ሆነላት:: 

አባት ሆይ ይህ ኃይል በእኛም ህይወት ይስራ::  አሜን

ሉቃስ 5:18 – 26

20 እምነታቸውንም አይቶ፦ “አንተ ሰው፥ ኃጢአትህ ተሰረየችልህ፡” አለው።

ይህንን ሰው ወደጌታ ይዘው የመጡ ሰዎች የሚገርሙና የመጡበትን ዓላማ ሳይፈጽሙ የማይመለሱ ናቸው:: በእነርሱ እምነት ይህ ሰው ተፈወሰ::  እኛም ዛሬ በእምነት ወድፊቱ የምናቀርበው ልመና ይመለሳል::  በሌላው አንፃር ይህንን ንግግሩን ያልወደዱለት ነበሩ::  ያለ አንዱ እግዚአብሔር በቀር ማን ኃጥያትን ማስተሰረየት ይችላል ብለው አሰቡ::  ጌታም በምድር ላይ ኃጢአት ሊያስተሰርይ ለሰው ልጅ ሥልጣን እንዳለው እንድታውቁ፡” ብሎ፥ ሽባውን፦ “አንተን እልሃለሁ፥ ተነሣ፥ አልጋህን ተሸክመህ ወደ ቤትህ ሂድ፡” አለው። ወድያውም እንደተባለው አደረገ ፈውሱንም ተቀበለ:: ሊቀ ካህናቱም ይሁን ማን ይህንን ማድረግ አይችሉም የታረደው በግ ግን ኃጥያትን ይቅር ማለና መፈወስ ይችላል::  አሜን!

ከዚህም የተነሳ ሁሉንም መገረም ያዛቸው፥ እግዚአብሔርንም አመስግነው፦ “ዛሬስ ድንቅ ነገር አየን፡” እያሉ ፍርሃት ሞላባቸው።

ሉቃስ 5: 27-32

31 ኢየሱስም መልሶ አላቸው፦ “ሕመምተኞች እንጂ ባለ ጤናዎች ባለ መድኃኒት አያስፈልጋቸውም፤ 32 ኃጢአተኞችን ወደ ንስሐ እንጂ ጻድቃንን ልጠራ አልመጣሁም።”

ወንጌል ዛሬም ይኸው ነው!  ለሕመምተኞችና ለኃጢአተኞች ነው ኢየሱስ የመጣው ሊፈርድባቸው ሳይሆን ሊያድናቸው ነው::  ማኅበረሰቡ ከሚለው ባህላችን ከሚለው የምድር ቀመሮች ከሚያወሩት ሁሉ ወተን ሰውን በሰውነቱ አይተን የእግዚአብሔርም ክብር እንደጎደለው አውቀን ክርስቶስን ባለማዳላት እንስበክ::  ከጌታ ጋር ታረቁ እንበል::  እንደባህሉ ቢሆንማ ማቴዎስ ደቀ መዝሙር ባልሆነም ነበር:: ጌታ ይርዳን!

ሉቃስ 5: 33-39

35 ነገር ግን ወራት ይመጣል፥ ሙሽራውም ከእነርሱ ሲወሰድ ያንጊዜ፥ በዚያ ወራት ይጦማሉ።” 36: ደግሞም ምሳሌ እንዲህ ሲል ነገራቸው፦ “የአዲስ ልብስ እራፊ ባረጀ ልብስ ላይ የሚያኖር የለም፤ ቢደረግ ግን አዲሱን ይቀደዋል ደግሞም አዲስ እራፊ ለአሮጌው አይስማማውም።

ጥያቄያቸው “የዮሐንስ ደቀ መዛሙርት ስለ ምን ብዙ ይጦማሉ ጸሎትስ ስለ ምን ያደርጋሉ፥ ደግሞም የፈሪሳውያን ደቀ መዛሙርት ስለ ምን እንደዚሁ ያደርጋሉ፤ የአንተ ደቀ መዛሙርት ግን ይበላሉ ይጠጣሉም?” ነበር::  እነርሱ የሚጾሙትና የሚጸልዮት አንዱ ምክንያት መሲሁ እንዲገለጥ ነበረ እርሱ በመካከላቸው ቆሟል::  ጊዜውን ያልዋጀ ነበረ (የልማድ)::  ጊዜያችንን እንድንዋጅ ጌታ ይርዳን ከጌታ ተረድተን የጊዜውን ማድረግና በሚያስፈልግ ጊዜ ጾምን ማወጅ:: በተመደው አካሄድ ከመሄድ በአዲሱ በመረቀልን መንገድ  የጌታን ፈቃድ እያወቁ ከአዲስ አሰራሩ ጋር ተዋህዶ በመንፈስ እየተመላለሱ መጾምና መጸለይ ይሁንልን::

ሉቃስ 6:1-5

5 የሰው ልጅ የሰንበት ጌታ ነው፡” አላቸውም።

ስለጾም አነሱ መለሰላቸው ጌታ የሚፈልገው ጾም ምን አይነት እንደሆነም አያውቁም::  ኢሳ 58:1-9 ያለውን አይነት ውጤት ያለው ጾም እንጂ ልማድን አይደለም የሚፈልገው::  

እዚህም ክፍል ላይ ሰንበትን አልጠበቁም በእርሻው መካከል ሲያልፉ እሸት ቀጥፈው በልተዋል ነው ክሱ:: የሰንበት ጌታ እንደሆነ አውጆ ክሱ ተቀባይነት አላገኘም ከዚህ የባሰ ዳዊት አድርጏል ብሎ ሻረው ቃሉን ማንበብና ማወቅ ይለያያል ያወቀ ይኖርበታል::  አቤት ትኩረታቸው ሁሉ ልምድ ላይ ነው::  እኛም ሳናስብ በልምድ ተይዘን ዋናውን የተጠራልለትን ሰውን መውደድና ወደ ጌታ ማምጣት አስትቶን እንዳይሆን ጌታ ሆይ እርዳንና ሰፊ ልብን ስጠን!

በሆሴዕ 6:6 ከመሥዋዕት ይልቅ ምሕረትን፥ ከሚቃጠልም መሥዋዕት ይልቅ እግዚአብሔርን ማወቅ እወድዳለሁና::  አሜን!

አባት ሆይ በልምና በባህል ተጠርዤ እንዳልገኝ እርዳኝ የመረጥከውን አይነት ህይወት እንድመላለስና ቃልህንና ኃይልህን እንዳልስት እርዳኝ::

ሉቃስ 6: 6-11

9 ኢየሱስም፦ “እጠይቃችኋለሁ፤ በሰንበት በጎ ማድረግ ተፈቅዶአልን ወይስ ክፉ? ነፍስ ማዳንን ወይስ መግደል?” አላቸው።

ጥያቄውን እንኳን ያስተዋሉ አይመስለኝም::  እነሱን የያዛቸው ነገር ሰንበት ተደፈረ ነው::  የሰንበት ጌታ እንደሆነ ከሳምንት በፊት ነግሯቸው ነበር እነርሱ ጋር  ግን ቃሉ ጠብ አላለምና እንደወጥመድ ሊጠቀሙበት ተነስተዋል::  ጌታ መሆን የማይገባው ጌታ ሆኖ ፈውስን ሊከለክል ነበረ::  ጌታ ግን ወደ ምኩራብም ሲመጣም ያንን እጁ የሰለለችን ሰው አይቶት እጎበኘዋለሁ ብሏልና አሳቡን አላስቀየሩትም በሰንበት በጎ አደረገ!  ፍቅሩ ብዙ የሆነ ጌታ ስሙ ይባረክ!

ሁላቸውንም ዙሪያውን አየና ሰውዬውን፦ “እጅህን ዘርጋ፡” አለው። እርሱም እንዲህ አደረገ፥ እጁም እንደ ሁለተኛይቱ ዳነች። አሜን!  ሰውን በማዳንና በመፈወስ ደስ የሚለው ጌታ ዛሬም አልተለወጠም በዚሁ አሳብ ላይ ነውና ወደፊቱ እንምጣና እንፈወስ ሌሎችንም እናምጣና የጌታችንን ማዳን እናሳይ! ሃሌሉያ!

ሉቃስ 6: 12-16

12 በነዚህም ወራት ይጸልይ ዘንድ ወደ ተራራ ወጣ፥ ሌሊቱንም ሁሉ ወደ እግዚአብሔር ሲጸልይ አደረ።

ሙሉ ለሊት መጸለይ?!  እንዴት ደስ የሚል ነገር ነው? ከእኛም የሚጠበቅ ነው ምክንያቱም ጸጋን በልግስና ይሰጣልና::  በራሳችን በተለያየ ዘዴ ለተወሰነ ሰዓት ለጸሎት መትጋት ይቻል ይሆናል በጸጋ ግን ሲሆን ቀላል ነው::  እንደፈቃዱ አንዳች ብንለምን ይሰማናልና ይህንን በፊቱ የምንተጋበትን  ጸጋ ያፍስስልን!  አሜን! 

ጌታለሊቱን ሙሉ ሲጸልይ አድሮ በማግስቱ ያደረገው ነገር ደቀመዛሙርትን መርጦ መጥራት ነበረ::  እነዚህ በዚህ ሁሉ ጸሎት ውስጥ የተመረጡ ናቸው ወንጌልን ለዓለም ያደረሱት:: ለመንግስቱ ስራ እንበርታ!

ሉቃስ 6:17-19

19 ከእርሱም ኃይል ወጥቶ ሁሉን ይፈውስ ነበርና ሕዝቡ ሁሉ ሊዳስሱት ይሹ ነበር።

ወደ ጌታ ኢየሱስ ይመጡ የነበረው ሊሰሙትና ሊፈወሱ ነበር::  ኃይልም ወጥቶ ሁሉን ይፈውስ ነበርና :: ከርኵሳንም መናፍስት ይሠቃዩ የነበሩት ተፈወሱ:: 

ለሐዋርያት ያላቸው ከመሄዱ በፊት ኃይልን እስክትቀበሉ ድረስ በእየሩሳሌም  ጠብቁ ነበረ::  ይህ ኃይል ዛሬም ያስፈልገናልና ለመቀበል በፊቱ እንገኝ:  

አባት ሆይ ኃይልህን ሙላንና በእኛ ተጠቀም:: አሜን!

ሉቃስ 6:20-26

22 ሰዎች ስለ ሰው ልጅ ሲጠሉአችሁ ሲለዩአችሁም ሲነቅፉአችሁም ስማችሁንም እንደ ክፉ ሲያወጡ፥ ብፁዓን ናችሁ። 23 እነሆ፥ ዋጋችሁ በሰማይ ታላቅ ነውና በዚያን ቀን ደስ ይበላችሁ ዝለሉም፤ አባቶቻቸው ነቢያትን እንዲህ ያደርጉባቸው ነበርና።

የእግዚአብሔር ነገር ተቃራኒ ነው ለድሃው ጽድቅን ይሰጣል::   ስለስሙ ስንጠላ  ብጹዓን ናችሁ ይለናል ዋጋችሁም በሰማይ ታላቅ ነውና በዚያን ቀን ደስ ይበላችሁ ዝለሉም ይለናል እንጂ ተክዙ አላለንም::  በስሜ የሚያፍርብኝን አፍርበታለሁ የማያፍረውን ደግሞ እመሰክርለታለሁ ብሎናልና በህይወታችን እርሱን እናሳይ ደግሞም እንመስክር::  ጥላቻ ከመጣም እንደሰት:: አንድ በህብረታችን ውስጥ የነበሩ አባት ወግ ደርሶኝ ከእድር ተባርሬአለሁና አመስግኑልኝ ያሉትን አልረሳውም:: የገባው እንደዚህ ይላል::

ሉቃስ 6: 27

27 “ነገር ግን ለእናንተ ለምትሰሙ እላችኋለሁ፥ ጠላቶቻችሁን ውደዱ፥ ለሚጠሉአችሁ መልካም አድርጉ፥

ጆሮ ያለው ይስማ:-

ከሰማን ጌታ ይናገራል ዙሩን እያከረረው ነው ያለው::  ጠላቶቻችሁን ውደዱ?! እንዴት ይቻላል?! ጠላት የተባለው በምክንያትም አይደለም እንዴ?  ጠላት እንዳለን ጌታም ያውቃል ግን ደግሞ ብቃትን ሰቶናልና የጌታ መልስ ለዚህ ጥያቄ በአዲሱ ሰው ይቻላል ነው በመንፈስ ተመላለሱ የሚል ነው::

ደቀመዝሙር  መሆናችን የሚታወቀው በፍቅራችን ነው የምንወደው ለይተን አይደለም የወዳጅና የጠላት የሚል ግሩኘ የለንም ሁሉ ወዳጅ ነው በጌታ ዲክሽነሪ:: ማስተዋል ይሁንልን እንደቃሉ እንድንመላለስ::  በክርስቶስም የተፈጠርነው መልካምን ለማድረግ ነውና ሰውን ሳንለይ መልካም እናድርግ::

ሉቃስ 6:28 የሚረግሙአችሁንም መርቁ፥ ስለሚበድሉአችሁም ጸልዩ።

የሚረግሙንን መመረቅ?  ቢያንስ መመረቁ ቀርቶ ዝም ብለን እንለፍ የሚለው ትንሽ ይሻላል የሰጡትን ሰፍሮ መመለስ ለሚያውቀው አእምሮ::  ነገር ግን በአእምሮ አንመራም የምንመራው በመንፈስ የምናመልከው በመንፈስ ነውና ልባችንን ወደ ጌታ እናንሳ::  ይህ የምንኖርበት አዲስ የህይወት መንገድና ዘይቤ ነው እንጂ ስንፈልግ ኦን ስንፈልግ ኦፍ የምናደርገው አይደለም::  እኛስ የክርስቶስ ልብ አለን:: ሰው በደህናው ክፉ አይሆንምና ክርስቶስን እንዲያውቁ እየባረክን እንጸልይላቸው  ለክፉ ንግግራቸውም እግዚአብሔር ይባርካችሁ እንበል:: ጠላት አንዳች እንዳያገኝ በድል መመላለስ እንዲሆንልን እራሳችንን በቃሉ እንፈትሽ! 

ስለሚበድሉአችሁም ጸልዮ ሲለን ጌታ ከዚህ በላይ ኖሮ ነው:: ለገረፉት ለተፉበት ለሰቀሉት የሚያደርጉትን አያውቁምና ይቅር በላቸው  ብሎ ጸልዮ አሳይቶን ነው::  ማንም ጸጋ ቢጎድለው በልግስና የሚሰጠውን ጌታን ይጠይቅ እንደሚል ቃልህ ጌታዬ ሆይ ሁሉን እየወደድን የምንጸልይበትን ጸጋ ስጠን በመንፈስ ቅዱስ በልባችን የፈሰሰውን ፍቅር  አያሳፍርምና ግለጠው:: አሜን!

ሉቃስ 6:29 “ጕንጭህን ለሚመታህ ደግሞ ሁለተኛውን ስጠው፥ መጐናጸፊያህንም ለሚወስድ እጀ ጠባብህን ደግሞ አትከልክለው።

ይሄ መቼም በእርግጥ መምታት ብቻ አይደለም ለምሳሌ:- ጌታ ኢየሱስን “ጋኔን አለበት፡ አብዶአልም፤ ስለ ምንስ ትሰሙታላችሁ?”   እንዲሁም “በአጋንንት አለቃ አጋንንትን ያወጣል” ሁሉ ይሉት ነበረ:: እርሱ ለዚህ ስድባቸው ሲመልስና ለእራሱ ሲከራከር አናይም::  በዘመናችን ዱላን ብዙም ላንቀምስ እንችላለን ስድብና ማሽሟጠጥ ግን አይቀሩም::  ይሉኝን (ይሉኝታን) አውጥተን ጥለን ፍቅርን ተሞልተን በመልካም ልብ ሳንፈርድ ቁጣም ሳይሞላን እንመላለስ::  ለሁሉ ፍቅርን እንስጥ:: የጌታ ጸጋ በዛ ውስጥ ይገለጣል::

እርሱ ህይወቱን እንደሰጠን እያሰብን ማካፈልንና መስጠትን እንድንለማመደው ጌታ ይርዳን::  ሌሎችን በመባረክ ደስ ይበለን:: ህይወትን እንኑሩው እንጂ ማንበብ ብቻ አይሁንብን::  

ጌታ ሆይ እንድንዘረጋ ወደምትፈልገው ሁሉ እንዘረጋ ዘንድ ጸጋህን ስጠን በውስጣችንም ያለው ፍቅር ወጥቶ ይውደድ – እኛ የምንሰጠው የለንምና! ተባረክ::  አሜን!

ሉቃስ 6: 30-31

30 ለሚለምንህ ሁሉ ስጥ፥ ገንዘብህንም የሚወስድ እንዲመልስ አትጠይቀው። 31 “ሰዎችም ሊያደርጉላችሁ እንደምትወዱ እናንተ ደግሞ እንዲሁ አድርጉላቸው።

ሰውን በለመስጠት ለመባረክ የሚያስፈልገን ከገንዘቡ በላይ ፍቅር ነው::  ፍቅር ካለ መስጠት ይቀላልና የተቸገሩትን ለማሰብ የክርስቶስ ፍቅር ይሙላን::

ሰዎችም ሊያደርጉላችሁ እንደምትወዱ ማድረግ የሚለው እራሳችንን እንድናይ የሚያደርገን ሚዛን ነው::  ይህንን ምክር ወርቃማው ህግ ብለው ይጠሩታል::  እንዲድረግብን የማንፈልገውን አናድርግ:: በማስተዋል እንመላለስ ለሌሎችም እንቅፋት እንዳንሆን::  

አባት ሆይ በልግስና ያለ ስስትእንድንሰጥናሌሎችን ልክ አንተ እንደወደድካቸው መውደድ እንድችል እርዳኝ::  አሜን!

ሉቃስ 6: 32-33

32 የሚወዱአችሁንማ ብትወዱ፥ ምን ምስጋና አላችሁ? ኃጢአተኞች ደግሞ የሚወዱአቸውን ይወዳሉና። 33 “መልካምም ለሚያደርጉላችሁ መልካም ብታደርጉ፥ ምን ምስጋና አላችሁ? ኃጢአተኞች ደግሞ ያን ያደርጋሉና።

የአዲሱ ኪዳን ህይወት ከብሉይ ይለያል::  ጥሩ ተብለው የሚባሉትን ሁሉ የሚቀይር ነው::  የሚወዱንን መውደድ ወይም መልካም ላደረጉልን መልካም መመለስ ጥሩ ነው  ምን ክፋት አለው? እንል ይሆናል::  ነገር ግን በውስጣችን እየኖረ ያለው ፍቅር የሆነ ጌታ ለዚህ አይደለም የመጣሁት እያለ ነው:: ይህንንማ ሰው ሁሉ ማድረግ ይችላል::  የእኔ ደቀ መዝሙር ግን በፍቅሩ ይታወቃል ስለተደረገለት ወይንም ወሮታን ለመመለስ አይደለም የሚወደው ነገር ግን እግዚአብሔር ሰውን በወደደበት መውደድ እየወደደ ምላሽን ሳይጠበቅ የእግዚአብሔርን ፈቃድ ማገልገል ነው::  እግዚአብሔር ይርዳን የሰው ልጆችን ሁሉ ሳንለይ እንድንወድድና መጥፋታቸው ግድ ብሎን የምስራቹን እንድንመሰክር:: ከፍቅርም በቀር ሌላ  እዳ  አይኑርብን:: ያለዛ ግን እንደሚሿሿ ፀናፅል ነን ከድምጽ ውጪ ምንም ፍሬ የሌለው ማለት ነው::  ጆሮ ያለው ይስማ! ሁሉን በጸጋው ለሚያደርገው እረኛ እራሳችንን እናቅርብ!

ሉቃስ 6: 34-36

35 “ነገር ግን ጠላቶቻችሁን ውደዱ፤ መልካም አድርጉ፤ ምንም ተስፋ ሳታደርጉም አበድሩ፥ ዋጋችሁም ታላቅ ይሆናል፥ የልዑልም ልጆች ትሆናላችሁ፥ እርሱ ለማያመሰግኑ ለክፉዎችም ቸር ነውና። 36 አባታችሁ ርኅሩኅ እንደ ሆነ ርኅሩኆች ሁኑ።”

ዋጋችሁም ታላቅ ይሆናል፥ የልዑልም ልጆች ትሆናላችሁ ያስባለው ነገር እየሱስን እየመሰሉ መመላለሱ ነው::  አምላካችን ለማያመሰግኑ ለክፉዎችም ቸር  ነውና ከእኛም ይህ አባታችንን መምሰል ይጠበቅብናል::  ጠላትን እንደ ክርስቶስ በመውደድ ፤ እንዲሁም በክርስቶስ የተፈጠርነው መልካም ለማድረግ ነውና መልካምን እያደረግንና ምንም ተስፋ ሳናደርግ  ማበደርን እየተለማመድንጌታን እናሳይ:: አባታችን  ርኅሩኅ እንደ ሆነ እኛም ርኅሩኆች እንሁን። ልክ እንደ አባታችን የሰው ልጅ ሁሉ ያሳዝነን የምንራራም እንሁን::  ጌታ ማስተዋልን ይስጠን!

ሉቃስ 6:37 “አትፍረዱ አይፈረድባችሁምም፤ አትኰንኑ አትኰነኑምም። ይቅር በሉ ይቅርም ትባላላችሁ።

የእግዚአብሔርን ርኅራኄ የቀመስንና ያስተዋልን እኛ እንጂ  ዓለም አይደለችም:: ርኅራኄውን እንደቀመሰ ሰው ስንመላለስ በሌሎች ላይ እንዳንፈርድ ፤  እንዳንኮንንና ይቅርታን እንዳንነፍግ::  ይልቁንም ሰፊ ልብ ይዘን ሌሎችን ማቀፍና የቀመስነውን ጌታ መስለን መማረክ ይሁንልን::  

ጌታ ይቅር በሉ ሲለን ሳያልፍበት ቀርቶ አይደለም::  ማንም በማይቀርበው ብርሃን ይኖራል የተባለው ጌታ ሲመቱት ፤  ሲገርፉት ፤  ሲተፉበትና ሲሰቅሉት  ይቅር አላቸው:: ከማን እንማር ታድያ ይቅርታችን በአጭር የቀረ አይሁን እንደተቀበልን በልግስና እንስጥ:: ጌታ ይርዳን! ቃሉን እንኑርበት እንጂ አንብበን አንለፈው እራሳችንን እንይበት በዚህ መስታወት::  

አባት ሆይ እንዳን ከፍቅር በቀር ሌላ ዕዳ አይኑርባችሁ ስትለን በሌላ ዕዳ ውስጥ ተይዘን እንዳንገኝ ዓይኖቻችንን ክፈትልን::  አሜን!

ሉቃስ 6:37 “አትፍረዱ አይፈረድባችሁምም፤ አትኰንኑ አትኰነኑምም። ይቅር በሉ ይቅርም ትባላላችሁ።

የእግዚአብሔርን ርኅራኄ የቀመስንና ያስተዋልን እኛ እንጂ  ዓለም አይደለችም:: ርኅራኄውን እንደቀመሰ ሰው ስንመላለስ በሌሎች ላይ እንዳንፈርድ ፤  እንዳንኮንንና ይቅርታን እንዳንነፍግ::  ይልቁንም ሰፊ ልብ ይዘን ሌሎችን ማቀፍና የቀመስነውን ጌታ መስለን መማረክ ይሁንልን::  

ጌታ ይቅር በሉ ሲለን ሳያልፍበት ቀርቶ አይደለም::  ማንም በማይቀርበው ብርሃን ይኖራል የተባለው ጌታ ሲመቱት ፤  ሲገርፉት ፤  ሲተፉበትና ሲሰቅሉት  ይቅር አላቸው:: ከማን እንማር ታድያ ይቅርታችን በአጭር የቀረ አይሁን እንደተቀበልን በልግስና እንስጥ:: ጌታ ይርዳን! ቃሉን እንኑርበት እንጂ አንብበን አንለፈው እራሳችንን እንይበት በዚህ መስታወት::  

አባት ሆይ እንዳን ከፍቅር በቀር ሌላ ዕዳ አይኑርባችሁ ስትለን በሌላ ዕዳ ውስጥ ተይዘን እንዳንገኝ ዓይኖቻችንን ክፈትልን::  አሜን!

ሉቃስ 6:38 ስጡ ይሰጣችሁማል፤ በምትሰፍሩበት መስፈሪያ ተመልሶ ይሰፈርላችኋልና፥ የተጨቈነና የተነቀነቀ የተትረፈረፈም መልካም መስፈሪያ በእቅፋችሁ ይሰጣችኋል።”

ከላይ ያነበብነው አታድርጉ የተባልነውን ነው:- አትፍረዱ፤  አትኮንኑና ይቅር በሉ::  ቀላል ይመስላል ስናነበው ስናልፍበት ግን እንዴት እንሆን?  ይህንን ሁሉ ነገር የምናደርገው ለራሳችን ስንል ነው ሲደርስብን አንወደውም ያመናል ሲፈረድብን ስንኮነን  ስንቀምሰው መራራ ነውና እናስወግደው::  

አሁንም ስጡ እየተባልን ነው::  የምንሰጠው ስለሚሰጠን ሳይሆን ርኁሩኅ የሆነውን አባታችንን እንድንመስል ብለን ነው::  እርሱ ለኃጥያተኛም ለፃድቁም እኩል ፀሐይን ያወጣልና::  ስንሰጥም በልግስና ደስ እያለን እንስጥ::  እርሱ ታማኝ ነውና በሰጠነው መስፈርያ ይሰፍርልናል:: መስጠት ይዋሃደን ዘንድ ጌታ ይርዳን::  ሰውን በችግሩ መድረስ እንድንችል ጌታ ዓይናችንን ይክፈትልን ጸጋውንም ያብዛልን::

ሉቃስ 6: 39-40

39 ምሳሌም አላቸው፦ “ዕውር ዕውርን ሊመራ ይችላልን? ሁለቱ በጕድጓድ አይወድቁምን? 40 ደቀ መዝሙር ከመምህሩ አይበልጥም፤ ፈጽሞ የተማረ ሁሉ ግን እንደ መምህሩ ይሆናል።

የሚመራን ማን እንደሆነ ውሳኔው የእኛ ነው እውር እንዳንከተል በቃሉ እውነት መርምረን የህይወትንም ፍሬ እያየን መሆን አለበት::

እረኛችን ግን ሲያስተምረንና ሲቀርጸን እርሱን እንድንመስል ነው::  ይኸው ነው የተወሰነው በሮሜ 8:29 . . . አስቀድሞ ያወቃቸው የልጁን መልክ እንዲመስሉ አስቀድሞ ደግሞ ወስኖአልና::  በኃላም ስንገለጥ እርሱን እንመስላለን:: እውር ያስተማረው ጥሩ እውር ይሆናል ከጌታም የተማረ ጌታን እየመሰለ ይመጣል::  እርሱን የምንመስለው እንዴት ነው?  በፍቅራችን፤ በትህትና፤ በርኅራኄና በመንፈሳዊ ፍሬዎች ሁሉ በማሸብርቅ ነው::  እነዚህን የሚቃወም የዓለምም ህግ የለም::  እግዚአብሔር ትልቅ ነው!!

ሉቃስ 6: 41-42

41 “በወንድምህም ዓይን ያለውን ጉድፍ ስለ ምን ታያለህ፥ በራስህ ዓይን ግን ያለውን ምሰሶ ስለ ምን አትመለከትም?

ሌሎችን መርዳትን አይደለም ጌታ እየተቃወመ ያለው ነገር ግን እራስህንም መርምር በሌላው ከምታየው የበለጠ በአንተ እንዳይገኝ ነው::  ዳዊት አንዲት በግ የነበረችው ታረደችበት የሚለውን ታሪክ ሲሰማ ቡራ ከረዮ አለ እርሱ መሆኑን ባለማወቁ::  ማለት የነበረበት:- እኔም ወድቄያለሁና ንስሃ ልግባና ከዚህ ሰው ጋር ከዛ በኃላ እነጋገራለሁ ማለት ነበረበት::  ያችም ስታመነዝር የተገኘች ሴት ከሳሾችዋ በሙሉ ባለ ምሰሶ ሆነው ተገኙ::  እራሳችንን ብንመረምር ባልተፈረደብን ነበር::  ሌሎችን እዮ የተባልነው በክርስቶስ ውስጥ ነውና እያንዳንዱን ቅዱሳን ስንመለከት ክርስቶስን እንይና ከእኛ እንደሚበልጡ እንረዳ ድሮስ እንዴት ከእየሱስ እንወዳደር? ትህትናን ለብሰን በእውነት ገብቶን እንመላለስ:: 

ሉቃስ 6: 43-45

43 “ክፉ ፍሬ የሚያደርግ መልካም ዛፍ የለምና፥ እንዲሁም መልካም ፍሬ የሚያደርግ ክፉ ዛፍ የለም።

ዛፍ ስም የሚወጣለት በፍሬው ነው::  የብርትኳን ዛፍ ወይም የማንጎ ዛፍ ያስባለው ከሚያፈራው ፍሬ የተነሳ ነው::  እንግዲህ እናስተውል አፍሩ የተባልነው የመንፈስ ፍሬ ነው::  ሐዋርያቱ ምንም ያልተማሩ ነበሩና ከእየሱስ ጋር እንደነበሩ አወቋቸው:: ውሎ አዳራችን ከእየሱስ ጋር ከሆነ እየሱስን እንመስላለን:: የህይወት ቃል አለህ ወዴት እንሄዳለን ብለዋልና:: ይህ ቃል መንፈስ ነው እውነትም ነውና መልካም መሬት ሆነን እንቀበለው እርሱም ያፈራል::

በልብ ሞልቶ ከተረፈው አፉ ይናገራልና መልካም ሰው ከልብ መልካም መዝገብ መልካሙን ያወጣል፥ ክፉ ሰውም ከልብ ክፉ መዝገብ ክፉውን ያወጣል። የተሞላነው ምንድነው?  ቃሉን?  ዕለት ዕለት በመንፈስ ቅዱስ ተሞሉ ተባልን አለዚያ ዓለም ክፍተቱን ተጠቅማ መራራውን እውቀት ትሞላናለችና::  ክርስቶስን ወደ መምሰል አንመጣም:: ቃሉን ስናሰላስል እንዋል እርሱ ነው በአእምሯችን መታደስ የሚለውጠን:: የእግዚአብሔር እርሻ ነንና ልባችን በቃሉ ይሞላና የምንናገረው ቃል ሰውን የሚያንጽ የጥበብ ቃል ይሁን::  ቃሉ በሙላት ይኑርባችሁ ተብለናልና ለቃሉ ጊዜና ክብር ይኑረን! 

ሉቃስ 6: 46-49

46 “ስለ ምን፦ ‘ጌታ ሆይ፥ ጌታ ሆይ፥’ ትሉኛላችሁ፥ የምለውንም አታደርጉም?

ጥያቄውን መመለስ የእያንዳንዳችን ግዴታ ነው::   ለምን በአፋችን ብቻ ጌታ ሆይ ጌታ ሆይ ማለት እንዳይሆንብን ህይወታችንን በቃሉ ላይ መስርተን እንኑርበት::  ጌታ ሶስት ነገሮችን እየነገረን ነው:- 

1. ወደ እኔ የሚመጣ ሁሉ – እራስን መካድ: ማስገዛትና ጌታን መከተል

2. ቃሌንም የሚሰማ – ደቀ መዝሙር መሆን

3. የሚያደርገው፥ – መታዘዝ

በዚህ መልኩ የሚከተል ማንን እንዲመስል አሳያችኋለሁ ብሎ:-  ቤት ሲሠራ አጥልቆ የቆፈረ በዓለት ላይም የመሠረተ ሰውን ይመስላል፤ ጐርፍም በመጣ ጊዜ ወንዙ ያን ቤት ገፋው፥ በዓለት ላይም ስለ ተመሠረተ ሊያናውጠው አልቻለም። እምነታችንን የሚፈትን መከራ መምጣቱ አይቀርም ያኔ እንጸናለን ወይንስ ትተን እንሄዳለን?

ይህንን ያላደረገው ደግሞ ያለ መሰረት (እናስምርበት) ቤቱን የሰራ ነው አይጸናም:: ክርስትና ክርስቶስን መምሰል እንጂ በአፍ ብቻ መከተል አይደለም በቃሉ ላይ እንደግ እንመስረትበትም::

ከ12  አንዱ ሲክደው ምንም ምልክትን አላሳየም ሌሎቹ አላወቁበትም ጌታ እንጂ::  እነሱኑ ነበር የሚመስለው ጠላት አሳብ አስገባበት እርሱም አስተናገደው::  ከውጪ ጥሩ ክርስትያን መምሰልና ሰውን ማታለል ይቻላል በጌታ ፊት ግን ሁሉ የተራቆተ ነው::  በመጨረሻው ጌታ ጌታ ሆይ ሲሉት አላውቃቸውም ከሚባሉት ውስጥ በስምህ አጋንንት አላወጣንም እንደዛና እንደዚህ አላደረግንም የሚሉ አሉበት:: እራሳችንን በቃሉ ብርሃን እንመርምር  አገልግለን የተጣልን እንዳንሆን::

ሉቃስ 7: 1-7

7 ስለዚህም ወደ አንተ ልመጣ እንዲገባኝ ሰውነቴን አልቈጠርሁትም፤ ነገር ግን ቃል ተናገር፥ ብላቴናዬም ይፈወሳል።

ቃል የገባው ይህንን ይላል!  ጌታ እየሱስን ስለቃል በደንብ አድርጎ ሰበከው::   ይህ ሰው የተመሰከረለት ጥሩ ሰው ነው ህዝቡን የሚወድና ምኩራብም የሚሰራ በኢየሱስ ፊት ግን ለመቆም ወይም ወደ ቤቱ እንዲገባ እራሱን የተገባው አድርጎ አልቆጠረምና መልክተኞችን ላከ::  መሲሁን ከሚጠባበቁት ይልቅ ይህ ምንም የማያውቅ አህዛብ ጌታን በግርማው ተቀበለው:: 

ዛሬም የሚያስፈልገን ይህ ህያው  ቃል ነው ለቃሉ ክብር ይኑረን::  ቃሉ በከበረበት ጌታም ይገኛል::

ሉቃስ 7: 8-10

9 ኢየሱስም ይህን ሰምቶ በእርሱ ተደነቀ፥ ዘወርም ብሎ ለተከተሉት ሕዝብ፦ “እላችኋለሁ፥ በእስራኤልስ እንኳ እንዲህ ያለ ትልቅ እምነት አላገኘሁም፡” አላቸው። 10 የተላኩትም ወደ ቤት ተመልሰው ባሪያውን ባለ ጤና ሆኖ አገኙት።

ይህ ሰው መልካም እንደሆነ መስክረውለታል ከስራውም ማየት ይቻላል  ለልጁ አይደለም  እንደዚህ  የተጋው:: ኢየሱስንና በአካባቢው ላሉት ሁሉ የባለስልጣን ቃል ምን ማለት እንደሆነ ሰበካቸው:: ይህንን ሁሉ የሚመላለሰው በመልክተኛ ነው ፊቱ ለመቆምማ አልደፈረም::  የጌታ ቃል ስልጣኑ ይግባን!!  ሁሉን ወደመኖር ያመጣው በቃሉ ነው::  አሁንም የምንኖርባትን ትልቁን ዓለም ያጸናት ጥሩ በሆነ መሰረት ላይ መስርቶ ሳይሆን በቃሉ ነው ደግፎ የያዘው!  ሃሌሉያ! 

እስራኤሎች ይህንን ቢሉ አይደንቅም ብዙ የአምላካቸው አሻራ አለና በዙሪያቸው::  ሙት ከሆነው አብረሃም የተገኙ:  ቀይባህርና ዮርዳኖስ የተከፈለላቸው: እያሪኮ በመዞር ብቻ የፈረሰላቸው:  ያልገነቡትን ከተማ የወረሱ: ብዙ ነገስታትን ድል የነሱ ብዙ ብዙ መጥቀስ  ይቻላል:: እነሱ ተለማምደውታልና ብዙም አልታያቸው::  እኛስ እንዳንለምደውና ታላቅነቱ እንዳይደበዝዝብን! 

ጌታ ኢየሱስም ተገርሞበት እላችኋለሁ፥ በእስራኤልስ እንኳ እንዲህ ያለ ትልቅ እምነት አላገኘሁም አለ:: ምን አይነት እምነት? ትልቅ! ጌታ እየሱስ ምንም አላለም ነገር ግን መልክተኞቹ ሲመለሉ ባርያውን ድኖ አገኙት!!!!  ሃሌሉያ ክብር ይሁንለት!!  ጆሮ ያለው ይስማ!!  ቃሉ ህያው ነው በሁለት በኩልም የተሳለ ነው!! ይሰራል ሳይሰራም አይመለስም! ቃል!  ቃል!  ቃል! 

ሉቃስ 7: 11-15

13 ጌታም ባያት ጊዜ አዘነላትና፦ “አታልቅሽ፡” አላት። 14 ቀርቦም ቃሬዛውን ነካ፥ የተሸከሙትም ቆሙ፤ አለውም፦ “አንተ ጐበዝ፥ እልሃለሁ፥ ተነሣ።” 15 የሞተውም ቀና ብሎ ተቀመጠ ሊናገርም ጀመረ፥ ለእናቱም ሰጣት።

ናይን ወደምትባለው ከተማ በአጋጣሚ አልመጣም ቀኑን የትና እንዴት እንደሚውል የሚያውቅ ጌታ::  ቀጥታ እርሰዋን ሊረዳት መጣ ስለታሪክዋ የነገረው የለም ግን አያትና አዘነላት አንድ ልጅዋን አታለችና:: 

ጸሎትን ከጌታ እንማር እርሱ ነገሮችን ያዛል ::  ከየት እንዳመጣነው የማይገባኝ ድምፃችንን ሁሉ ለውጠን የለቅሶ ዘይቤ አስይዘን እንጸልያለን ወይም ደግሞ እርሱ መረጃ የጎደለው ይመስል እንወተውታለን::  ማንም ምንም ሳይነግረው አውቆ አዘነላትና ልጅዋን በሰውኛ ሬሳ የሆነውን እርሱ ግን አናገረው አንተ ጎበዝ ብሎ ጠርቶ ተነሳ አለው እርሱም ተነስቶ ተቀመጠ ለእናቱም ሁለተኛ ሰጣት ድሮውንስ ልጅ የሚሰጥ እርሱ አይደለምን?!  በአላዛርም ይህንኑ ነው ያደረገው::

የሞተም ይሰማዋል!  እኛም ስንጸልይ ጉዳዮን አድሬስ እናድርግ እንጂ አንዘብዝብ::  ስትጸልዮ እንደአህዛብ አትሁኑ ተብለናል:: እግዚአብሔር መንፈስ ነው!  እንወቀው ሰምቶ የሚመልስ ነው የለመነውን እንደተቀበልን ብንቆጥር ለእኛ ይሆናል::  የጌታን የሚያዝን ልብ ይስጠን ሌሎች ሲያዝኑ አብሮ የሚያዝንና የሚጸልይ ማንነትን ያብዛልን::

ሉቃስ 7: 16-17

16 ሁሉንም ፍርሃት ያዛቸውና፦ “ታላቅ ነቢይ በእኛ መካከል ተነሥቶአል፥” ደግሞ፦ “እግዚአብሔር ሕዝቡን ጐበኘ፡” እያሉ እግዚአብሔርን አመሰገኑ።  17 ይህም ዝና ስለ እርሱ በይሁዳ ሁሉ በዙሪያውም ባለች አገር ሁሉ ወጣ።

ሁሉንም ፍርሃት ያዛቸው ይላል ቃሉ::  ለምን?! እንደዚህ አይነት ነብይ በህይወት ዘመናቸው ያላዮና የነብያትን አገልግሎት በዝና እንጂ በተግባር ያላዮ ትውልድ ናቸው:  ይህንን ያደረጉት ነብያት እነኤልያስና ኤልሳዕ ነበሩ::  ኢየሱስ ግን ከነብያትም የሚበልጥ የእግዚአብሔር ልጅ የሚጠብቁት መሲህ መሆኑን አልተረዱም::  መሲሑ ሲመጣ የሚያደርገውን ተአምራት እያደረገ ነውና::  እነርሱ ግን ታላቅ ነቢይ በእኛ መካከል ተነሥቶአል፥” ደግሞ፦ “እግዚአብሔር ሕዝቡን ጐበኘ፡” አሉ::  ይህንን ያሉት ከሮም አገዛዝ ያወጣናል ብለው ነበረ እንጂ የእግዚአብሔር እቅድ ዓለምን ሁሉ ለማዳንና የሰይጣንን መንግስት ለመጣል እንደሆነ በጥልቀቱ አልተረዱትም::

ተአምራት ሲደረግ የጌታ ስም ይገናል ዝናውም ይወጣል ብዙዎችንም ወደ እግዚአብሔር መንግስት ያመጣል::  እነዚህ ጸጋዎች በቤተክርስቲያን እንዲገለጡ እንጸልይ:: ብዙዎች እያነከሱ በቤቱ እየተመላለሱ ነው ያሉት::  የዚህች ሴት መጎብኘት ደስ አይልም? አንድ ልጅዋን መልሶ ሰጣት! አሜን! ይህንን ክብሩን ያሳየን::

ሉቃስ 7: 18-20

20 ሰዎቹም ወደ እርሱ መጥተው፦ “መጥምቁ ዮሐንስ፦ ‘የሚመጣው አንተ ነህን ወይስ ሌላውን እንጠብቅ?’ ብሎ ወደ አንተ ላከን፡” አሉት።

ይህንን ጥያቄ ከመጥምቁ ዮሃንስ መስማት ያስገርማል::  ምክንያቱም ሲያጠምቀው መንፈስ ቅዱስ በእርግብ መልክ መጥቶ  ሲቀመጥበት በአይኖቹ አይቶ እንደዚሁም ከአብ ዘንድ ድምጽን ሰምቶ ነበረና ነው::  በእርግጠኝነትም ይህ የእግዚአብሔር በግ እያለም አውጆለት ሲያበቃ ይህንን መጠየቁ ነው ያስገረመኝ::

አንዳንዴ ግራ ሲገባኝ እነዮሃንስም ያንን ሁሉ ምልክት ተሰቷቸው ጥያቄ ጠይቀዋል ብዬ  እጽናናለሁ::  ስለዚህ  እኛ ብቻ አይደለንም ግራ የሚገባን ከሴቶች ሁሉ ከተወለዱት ይበልጣል የተባለውም ወሳኙ ነብይ ጠይቋል::  ደስ የሚለው ጌታ አይታዘበን ወይንም አይቆጣን በነገር ሁሉ የተፈተነው ካህን ይረዳናል::  በድካማችን ኃይሉ ይገለጣል ደግሞም ጸጋን ይሰጠናል::  አሜን!!  ሃሌሉያ!

ሉቃስ 7: 21-23

ዮሃንስ ለላከው ጥያቄ በቃል ወይም በንግግር አልመለሰም ያላቸው ያያችሁትን የሰማችሁትንም አውሩለት ነበረ::  ወንጌል የሚታይና የሚሰማ ነው::  በኢሳያስም መጽሐፍ በትንቢት እንደተነገረው:-

ዕውሮች ያያሉ፥ 

አንካሶችም ይሄዳሉ፥ 

ለምጻሞችም ይነጻሉ፥ 

ደንቆሮዎችም ይሰማሉ፥ 

ሙታንም ይነሣሉ፥ 

ለድሆችም ወንጌል ይሰበካል፤

ይህ መሲሁ ሲመጣ የሚሰራው ነውና ስራው እየተሰራ ነው::  ዮሃንስን የገረመው ለምን እስከአሁን ቆየህ ነፃ አውጣን ነበረ::  ለምን በእስር ቤትስ እቆያለሁ ቶሎ መንግስትህን መስርት ነው ጥያቄው::  ኢየሱስ የመጣው የሰማይን መንግስት ለመመስረት ነው::  የሐዋርያቱም ጥያቄ ሊያርግ ሲል ይኸው ነበረ:: 

ስለዚህ ብዙዎች በዚህ ይሰናከላሉ ምክንያቱም የሚፈልጉት የእስራኤልን መንግስት እንጂ የማይታየውን የእግዚአብሔርን መንግስት አይደለም:: ንጉስ  አንግስልን አሉት በሳሙኤልም ዘመን ጌታም እኔን ነው የናቁት አለ::  እነርሱ የፈለጉት  እንደ አህዛብ  ያለ በፊታችን የሚሄድ ንጉስ ነበረ:: እግዚአብሔር ግን በቀን በደመና በለሊትም በእሳት አምድ እየመራቸው ነበረ::  ንጉሳችን እግዚአብሔር ነው!

ዛሬም ኢየሱስ በእኛ ውስጥ እየኖረ ስለሆነ እነዚህ ተአምራት ይቀጥላሉ::  ኃይሉን እንጠማ!!!

ሉቃስ 7: 24-28

ዮሃንስ ከሴቶች ከተወለዱት መካከል እንደሚበልጥ ጌታ መሰከረ ምክንያቱም  ሌሎቹ ነብያት ይመጣል ብለው አንዳንዶችንም ከሩቅ ተሳለሙት ሲል ዮሃንስ ግን ይኸው ብሎ ማወጅና ይመጣል የተባለውን መሲህ ማየት ሆነለት::   

የብሉይ ኪዳን አገልጋይ ሆኖ ሳለ ኢየሱስን ማየት ብቻም ሳይሆን ስለእርሱ ሲመሰከር በጆሮው የእግዚአብሔርን ድምጽ ሰማ መንፈስ ቅዱስም ሲወርድ አየ!   ዮሃንስ ማለት በመልአክ መልክት ይመጣል ተብሎ  የመጣ ፥  በበረሃ የኖረ ፥  ከሰው የማይነካካ የሚበላውና የሚለብሰው ሁሉ የተለየ ፥ እራሱን ሙሉ በሙሉ ለተላከለት አገልግሎት የሰጠ ነው::   ይህ ሁሉ ቢሆንም ቅሉ  በክርስቶስ የጸደቀ ግን ይበልጠዋል::  ምክንያቱም እርሱን ለብሰን፥  በደሙ ታጥበን ፥  እርሱን በልባችን ሾመን ፥  በእርሱ ተሞልተናልና ነው::  አሜን!  መዳናችን እጅግ ክቡር ነውና  ይህንን ሁሉ ሳናደርግ ድነናልና ይህንን ህይወት አንለማመደው በየዓለቱ እንደነቅ!

ሉቃስ 7: 29-30

ዮሃንስ የጌታን መንገድ ሊያቀና ከፊቱ የተላከ ነበረ::  ህዝቡን ወደ ንስሃ የሚያመጣ ከፍ ያለውን የትቢት ልብ ዝቅ የሚያደርግ አልበቃም ብሎም ዝቅ ያለውን ከፍ አድርጎ ልብን ሁሉ አደላድሎ የሚጠብቅ ነብይ::  ነገር ግን ህዝቡ ሁሉ ቀራጮች እንኳን ሳይቀሩ መተው ተጠምቀው ሲጠብቁት አውቀናል የሚሉት ፈሪሳውያንና ሕግ አዋቂዎች ግን በእርሱ አልተጠመቁምና የእግዚአብሔርን ምክር ከራሳቸው ጣሉ። እንዴት ከባድ ንግግር ነው? ! የእግዚአብሔርን ምክር ከራሳቸው መጣል? የጌታ ምክር በይወታችን ይጽና!  እግዚአብሔር ፈቃድ አለው ምንድነው ፈቃዱ በህይወታችን? እርሱን እንወቅና ፈቃዱን እንፈጽም እንጂ ሞኞች አንሁን::

ይህ ሰው ተራ ሰው እንዳልሆነ ያውቃሉ ብዙም ጊዜ አንተ እርሱ ነህን ብለው ጠይቀውታል እርሱም እኔ እርሱ አይደለሁም መንገድን የማዘጋጅ ነኝ ብሏል ልብ አላሉምና አለፋቸው::  ጌታም ሲመጣ አልተዘጋጁምና አልተጠቀሙበትም::  ጥምቀት በብሉይ ኪዳን አይታወቅም ግን ዮሃንስ አጠመቀ በኤልያስም መንፈስ ተገለጦ እንደ ትንቢቱ አገለገለ::

ሉቃስ 7: 31-35

32 በገበያ የሚቀመጡትን ልጆች ይመስላሉ፥ እርስ በርሳቸውም እየተጠራሩ እንዲህ ይላሉ፦ ‘እንቢልታ ነፋንላችሁ አልዘፈናችሁምም፤ ሙሾ አወጣንላችሁ አላለቀሳችሁምም’።

ይህንን ምሳሌ ሲናገር ጌታ የመጥምቁን የዮሐንስና የራሱን አገልግሎት ለማለት ነው:- ሙሾ አወጣንላችሁ አላለቀሳችሁምም’። ዮሃንስ ንስሃ ግቡ እናንተ የእፉኝት ልጆች ይላቸው ነበረ::  አኗኗሩ ሁሉ የተለየ ሲሆንባቸው ጋኔን አለበት አሉት::  

በሌላ አንፃር እግዚአብሔር ጌታ የሱስን ላከ  የምስራቹን ይዞ መጣ:- እንቢልታ ነፋንላችሁ አልዘፈናችሁምም::  የተገፉትንና የተጣሉትን ሁሉ ወደ መንግስቱ የሚያስገባ የኃጥያተኞች ወዳጅ የሆነ የእግዚአብሔር በግ::  ለእርሱም ምላሽ አልሰጡምና፤ እግዚአብሔር በምንም አይወቀስም::  ጥበብም ለልጆችዋ ሁሉ ጸደቀች አላቸው::  ጥበብ በብዙ ተጣርታለች ምክሩን ያልጣሉት ግን የእግዚአብሔር ጥበብ የሆነውን እየሱስን አወቁ::  እኛም አወቅን! ተመስገን ጌታ ሆይ!

ሉቃስ 7: 36-39

36 ከፈሪሳውያንም አንድ ከእርሱ ጋር ይበላ ዘንድ ለመነው፤ በፈሪሳዊው ቤትም ገብቶ በማዕድ ተቀመጠ።

ልመናን የማያልፍ ጌታ በዚህ ፈሪሳዊ  ቤት ለመስተናገድ መጣ::  ይህ ሰው የጋበዘው ነብይ መስሎት ነው ምክንያቱም ነብይ ቢሆን ኖሮ ይህችን ሴት ባወቃት ነበር አለ::  ከነብይነትም አወረደው::  እርሱ ግን በቤቱ ጋብዞ በሰው ላይ ይፈርዳል የሚገርመው ነገርና ያላወቀው ፈራጅ የሆነው ጌታ በዚያ በቤቱ ተቀምጦ ነበር::   ዛሬስ እኛ እንዴት ነን በጉባኤ መካከል በእህት ወንድሞቻችን መካከል ከፍቅርና እርስ በእርስ ከመቀባበል ባለፈ የፍርድ ልብ እንዳንይዝ እናስወግድ ወይም ስህተትን ካየን እንጸልይላቸው:

እርስዋ ግን ሰውየው ያሰበውን ሳታውቅ በቤቱ ገብታ ሳትጋበዝ ይሉኝታም ሳይዛት አገልግሎትዋን ቀጠለች አካሉን ለቀብር ማዘጋጀት ይህንን ወግ ጌታ አያገኝምና:: 

ያደረገችውም:-

– ሽቱ አምጥታ

– በእግሩ አጠገብ በመሆን እራስዋን ዝቅ አድርጋ: 

– ከፍቅርዋ የተነሳ እያለቀሰች 

– በእንባዋ እግሩን እያራሰች

– በራስ ጠጕርዋም እያበሰች  እራስዋን አዋርዳ 

– እግሩንም በመሳም ፍቅርዋን እየገለጠች 

– ሽቱ ቀባችው::

አገልግሎታችን ምንድነው? ማንም አይሰራልንምና ተነስተን እናገልግል የጌታ ውለታ የበዛብን ነን! 

ሉቃስ 7: 40-50

47 ስለዚህ እልሃለሁ፥ እጅግ ወዳለችና ብዙ ያለው ኃጢአትዋ ተሰርዮላታል፤ ጥቂት ግን የሚሰረይለት ጥቂት ይወዳል።”

ይሉኝታ ሳይዛት ሰው ሁሉ ለመብላት ተሰብስቦ ባለበት እርስዋ ግን አሳብዋንም ዓይንማንም በጌታ ላይ አድርጋ ለማምለክ ተገኝታለች::  አካባቢውን ሁሉ በዚህ ውድ ሽቶ አውዳ አመለከችው::

ስምዖን ግን ጌታን በልቡ እያማ ነው ማንነትዋን ነብይ ቢሆን ኖሮ ያውቅ ነበረ እያለ ባለበት ጌታ የልቡን አሳብ አውቆ መመለስ ጀመረ::  ለምን እንደዚህ እየሆነች እንዳለች ገለጸለት::  እርሱ ምንም አላደረገለትም እርስዋ ግን ብዙ ተትቶላታልና ብዙ ወደደች ፍቅርዋንም በተግባር ገለጸች:: እርስዋንም፦ “ኃጢአትሽ ተሰርዮልሻል፡” ብሎ ገበናዋን ሳይገልጥ ይቅር አለላት:: በነገር ሁሉ የተፈተነና ምንም ኃጥያት ያልተገኘበት ሊቀ ካህን ዛሬም ይራራል ይቅርም ይላል::ስምዓን ቤት ስትገባ ስብር ብላ እንደነበረችው አይደለም ስትወጣ ቀና ብላ ወጣች እዳዋ ሁሉ ተከፍሎ::  

እኛንም ቀና ያደረገን አባ አባ እንድንል ያደረገን በከበረ ደሙ አንጽቶናን ለመንግስቱ ዋጅቶ ነውና ስሙ ይባረክ! የሚያጸድቅ እርሱ የሚኮንን ማነው?!

ሉቃስ 8: 1-3

1 ከዚህም በኋላ እየሰበከና ስለ እግዚአብሔር መንግሥት የምሥራች እየተናገረ በየከተማይቱ በየመንደሩም ያልፍ ነበር፤

በብዙ መንገድ እግዚአብሔር ተናግሮ ነበረ አሁን ግን ልጁ ስለ እግዚአብሔር መንግሥት የምሥራች እየተናገረ ዞረ::  አሜን!!  የሚናገረው የምስራች ነው!  ምንድነው ይህ የምስራች?!  እውቀት ደብቀኸናልና የእባቡ ምክር ይሻላል አንፈልግህም ብላችሁ ጥላችሁት ወደ መከራ ከገባችሁበት የምርጫሁ መከራና ጨለማ  ሊያወጣችሁና ሊታረቃችሁ ፈጣሪያችሁ መጥቷል ይመስለኛል በቀላል ቋንቋ:: ዛሬም ዝናው በምድር ነገዶች ሁሉ ዘንድ ይሰማል::

ጌታ ሲወለድ መልአኩ ለእረኞቹ ያላቸው ታላቅ የምስራች እነግራችኋለሁ ነበረ::  ዛሬም ይህ ለሰው ልጆች ሁሉ የሚሆን የምስራች ይሰበካል!!  የምስራች አለን! የእግዚአብሔር  በግ ተገልጧል እንታረቅም ይላል ብለን የምንሰብክ አምባሳደሮች ነን!!

በዚያ ዘመን የነበሩ አገልጋዮች ሴቶችን ከእቁብ አያስገቡም ነበር  ጌታ ግን ሁሉ ያለው የሁሉ ፈጣሪ በገንዘባቸውም እንዲያገለግሉት ፈቀደ እንዲሁም  ከ12 ጋር አብረው ነበሩ::  “እምነትሽ አድኖሻል፤ በሰላም ሂጂ፡” ያላት ብዙ ወዳለች የተባለችው የሽቶዋ ባለቤት መቅደላዊት ማርያምም አንድዋ አገልጋይ ነበረች:: በገላትያ 3:28 አይሁዳዊ ወይም የግሪክ ሰው የለም፥ ባሪያ ወይም ጨዋ ሰው የለም፥ ወንድም ሴትም የለም፤ ሁላችሁ በክርስቶስ ኢየሱስ አንድ ሰው ናችሁና። አሜን አንድ ነን በሁሉም ጌታ ይጠቀማል!  እናገልግለው!

ሉቃስ 8: 4-15

10 እርሱም እንዲህ አለ፦ “ለእናንተ የእግዚአብሔርን መንግሥት ምሥጢር ማወቅ ተሰጥቶአችኋል፤ ለሌሎች ግን እያዩ እንዳያዩ እየሰሙም እንዳያስተውሉ በምሳሌ ነው።” 11 “ምሳሌው ይህ ነው። ዘሩ የእግዚአብሔር ቃል ነው።

ጌታ በዚህ ስፍራ ላይ ስለዘሪው ሲያስተምርና ፍቺውንም ለሐዋርያቱ ሲነግራቸው እናያለን::   ዘሩ ቃሉ ነው የሚዘራውም በተለያየ አይነት ልብ ላይ ነው::  የሰውን የልብ አይነት ማወቅ ለእኛ አልተሰጠንም  የተሰጠን መዝራት ነውና እንዝራ::  የሚያበቅል መንፈስ ቅዱስ ነው!  ተስፋ ሳንቆርጥ ሳንሰለች እንዝራ!  ሰይጣንም ይልቀመው:  በፈተና የሚከዱም ይሁኑ: በዓለም ነገር የተጠላለፉም ይሁኑ መቶ እጥፍም የሚያፈሩ ይሁኑ እኛ ልባቸውን ስለማናውቅ አምነን እየጸለይን እንዝራ::

የእግዚአብሔርን መንግሥት ምሥጢር ማወቅ ስለተሰጠን እንጂ እኛም ይህንን ሚስጥር ማወቅ አንችልም ነበረ:: 

ሉቃስ 8:16 “መብራትንም አብርቶ በዕቃ የሚከድነው ወይም ከአልጋ በታች የሚያኖረው የለም፥ የሚገቡት ሰዎች ብርሃኑን እንዲያዩ በመቅረዝ ላይ ያኖረዋል እንጂ።

በህይወታችን ላይ የነበረውን ጨለማ ገፎ በብርሃኑ ሞላው ::  በዓለም ስንመላለስ የዓለም ብርሃን የተባልነውም ለዚሁ ነውና ይህንን ጨለማ ዓለም ሳንሸማቀቅ እናብራው::  ባይመስለንም እንኳን የሰው ልጅ ክርስቶስን ካላወቀ  እርዳታ የሚያስፈልገው ምስኪን የሚጠፋ ፍጥረት እንደሆነ አውቀን በብርሃኑ ወደ ብርሃን እንምራው::  እንጂ ብርሃናችንን ደብቀን አብረን በጨለማ አንመላለስ::  ክፉን በክፉ አንመልስ:  የሚጠሉንን እንውደድ:  ለሚያሳድዱን እንጸልይ እና ሌላም ሌላም በውስጣችን የበራው ብርሃን ህይወትን በዓለም ቀመር እንዳንኖረው ግድ ይለናልና አዲሱ ሰው ክርስቶስ ህይወቱን በእኛ ይኑር:: አሜን!

ሉቃስ 8: 17-18

18 እንግዲህ እንዴት እንድትሰሙ ተጠበቁ፤ ላለው ሁሉ ይሰጠዋልና፥ ከሌለውም ሁሉ፥ ያው ያለው የሚመስለው እንኳ ይወሰድበታል።”

ተሰውሮ የሚቀር ነገር የለም ሁሉ በግልጥ ይታያል አንድ ቀን ስለዚህ ማንም አገልግሎ የተጣለ እንዳይሆን ይጠንቀቅ!

መስማት ለሰው አቅጣጫን የሚያስይዝ ነውና እንዴት እንድትሰሙ ተጠበቁ፤ እየተባልን ነው::  ጌታም ጆሮ ያለው ይስማ ይላል ደጋግሞ::  በጎቼ ድምጼን ይሰማሉ ተብለናልና ልባችንን መልካም መሬት አድርገን እንስማ! ከላይም እንዳለው ቃል የሰው ልብ የተለያየ ነው ቃሉን ሲሰማ መልካም መሬት ላይ ካላረፈ ቃሉ አያፈራም::  ለዚህም ነው በአእምሯችሁ መታደስ ተለወጡ እንጂ ይህንን ዓለም አትምሰሉ የተባልነው መለወጥና መታደስ የሚመጣው በቃሉ ነው:: አለበለዚያ አለን ብለን የምናስበውም ይወሰዳል::  ለጊዜው ተቀብያለብ ብለን ብናስብም::  የሎዶቅያ ቤተክርስቲያን ይህንኑ ብላ ነበረ ጌታ ግን በራእይ 3:17 ሀብታም ነኝና ባለጠጋ ሆኜአለሁ አንድም ስንኳ አያስፈልገኝም፡ የምትል ስለ ሆንህ፥ ጐስቋላና ምስኪንም ድሀም ዕውርም የተራቆትህም መሆንህን ስለማታውቅ ልተፋህ ነው ይላቸዋል::

ጌታ አስተውሎ መስማትን ይስጠን!

ሉቃስ 8: 19-21

21 እርሱም መልሶ፦ “እናቴና ወንድሞቼስ የእግዚአብሔርን ቃል ሰምተው የሚያደርጉት እነዚህ ናቸው፡” አላቸው።

ይህንን ማለቱ መቼም ቤተሰቡን መናቁ ወይም ችላ ማለቱ አይደለም::  ከላይ ጀምሮ ሲያስተምር የነበረውን ቃሌን በማስተዋል ስሙ ኑሩትን በቤተሰብ ምሳሌ አጠናቀቀው:: የእግዚአብሔር ቤተሰብ መሆን ምን ማለት እንደሆነ ገለጸልን ይኸውም ቃሉን መስማትና ማድረግን እንደሚጠይቅ አሳወቀን::  ቃሌ በእርሱ ዘንድ ያለችው የሚወደኝ እርሱ ነው ይልና ወደ እኛ እንደሚመጣና መኖርያም እንደሚያደርግ ይገልፃል እንዲሁም ጸሎታችን እንደሚሰማ ይናገር የለም በሌላ ስፍራም? ቃሉን ሰምተን ስንኖርበት እናተርፋለን!

ቃሉ በልባችን እርሻ ተዘርቶ ይብቀልና ይውረሰን::  ቃሉን እንዴት እንደምንሰማም እንጠንቀቅ በአውቃለሁ ሳይሆን ሁልጊዜ በትህትና ሊሆን ይገባል::  በቃሉ ይሰራናል ስንኖረውም የማን ወዳጅና ቤተሰብ እንደሆንን ያሳውቃል::  ጌታ ይርዳን ላይ ላዮን ሳይሆን ጠለቅ ብለን እንድንመላለስና ልጁን እንድንመስለው:: አሜን!

ሉቃስ 8: 22-25

25 እርሱም፦ “እምነታችሁ የት ነው?” አላቸው። ፈርተውም ተደነቁ፥ እርስ በርሳቸውም፦ “እንዲህ ነፋሳትንና ውኃን እንኳ የሚያዝ ለእርሱም የሚታዘዙለት ይህ ማን ነው?” አሉ።

እንሻገር ብሏቸው መንገድ ጀምረው ሳይጨርሱ ማዕበል መንገዳቸውን ያዘውና ያስጨንቃቸው ጀመር::  እነዚህ ሰዎች አብዛኞቹ በውሃ ላይ ልምድ ያላቸው ናቸው ታድያ ለምን እንደዚህ ደነገጡ ያልን እንደሆነ ምክንያቱ ይህ ዓውሎ ንፋስ አጥፊ እንደሆነና መውጫም የሌለው ገዳይ እንደሆነ ስለሚያውቁ ነው::  ከልምዳቸው ይልቅ አጠገባቸው ያለውን ጌታ ቢያዮ ይሻል ነበር::

ለሊቱን ሲጸልይ የሚያድረው ጌታ ቢተኛ አይደንቅም ጀልባዋ በውሃ እየተሞላች እርሱም በውሃው ውስጥ እንቅልፉን ቀጠለ::  ጠፋን ብለው ሲቀሰቅሱት እርሱም ነቅቶ ነፋሱንና የውኃውን ማዕበል ገሠጻቸው፤ ተዉም፥ ጸጥታም ሆነ። ፍጹም አምላክ ፍጥረትን ሁሉ የሚያዝ ፍጹም ሰው ደክሞት የሚተኛ  ነበረና::  

ከዚህ በኃላ እምነታችሁ የት ነው? ብሎ ጠየቃቸው በማዕበሉ ላይ ወይንስ በእኔ ላይ ነው? ነው ጥያቄው::  ዛሬ የት ነው እምነታችን ጌታ ያሻግራል!  ሲቀሰቅሱትም ተነሳና ረዳቸው  እኛም ዛሬ ስንጠራው በዙፋኑ ያለ የሚሰማ ሊቀ ካህናት አለን::  የገረመኝ ማዕበሉን ፈርተው ቀሰቀቁሱት ገስጾ ጸጥ ሲያደርገውም ፈርተውም ተደነቁ ይላል::  ደግሞም ይህ ማነው? አስባላቸው ይሄኛው ፍርሃታቸው ለየት ያለ ነው በጀልባ አብሯቸው የሚጏዘውን ገና በደንብ አላወቁትም ነበር:: እርሱ ግን የእግዚአብሔር ልጅ ኢየሱስ መሲህ ነው!    የተከተልነውማ ጌታ የጌቶችም ጌታ ነው::  አሜን! 

በእየሱስ ስም ያቆመን ማዕበል ሁሉ ከፊታችን ጸጥ ይበል!  ጸሎታችንንም የምንቀበልበት ቀን ይሁን!  ዓይናችንም በእርሱ ላይ ይጽና ሁሉን ጸጥ ያደርግና በሰላም ያሻግረናልና!  ሃሌሉያ!!!

ሉቃስ 8:26-35

35 የሆነውን ነገር ሊያዩ ወጥተውም ወደ ኢየሱስ መጡ፥ አጋንንትም የወጡለትን ሰው ለብሶ ልቡም ተመልሶ በኢየሱስ እግር አጠገብ ተቀምጦ አገኙትና ፈሩ።

ይህንን ሰው ሊረዳው የመጣለት እየሱስ ብቻ ነው::  ሰዎች የሚችሉትን ረዱት ይኸውም በብረት አስሮ ማስቀመጥ ነው እንጂ ከዛ ያለፈ አልቻሉም::  እየሱስ የመጣበት አንዱ አላማ የተጠቁትን ነፃ ማውጣት ነበረና በማዕበል ሊቋቋመው ቢነሳም እንኳን አላቆመውም::  አልፎ መጥቶ ነፃ አወጣው::  አጋንንቱ የሚወስደው ወደ መቃብር ስፍራ ነው ከሙታን መካከል እራቁቱን ሊያኖረው::  አዳምና ሄዋን በኃጥያት ሲወድቁ እራቁታቸውን መሆናችውን አወቁ እንደዛ ሊያዋርዳቸው ነበረ  ተሳካለት::  እየሱስ መቶ ታደገንና ወደ ክብራችን መለሰን::  

ጠላት ሞትን እንጂ ህይወትን አይሰጥም ህይወትን የሚሰጠው እየሱስ ነው::  ህይወት እንዲበዛልን መጣ!  ዛሬም ስሙ ከስም ሁሉ በላይ ነው!  ጌታ እየሱስ ክርስቶስ ትናንትናም ዛሬም እስከዘላለም ድረስ ያው ነው::  ሰውን ለመርዳት እንደእየሱስ ግድ ይበለን::  እርዳታ የሚያስፈልገውን ሰው ሁሉ ወደ እርሱ እናምጣ::  ዛሬም ነፃ ያወጣል ይረዳልና!  አምላካችን በስራ ላይነው!  አሜን! 

ሉቃስ 8: 36-39

39 “ወደ ቤትህ ተመለስ፥ እግዚአብሔር እንዴት ያለ ታላቅ ነገር እንዳደረግልህ ንገር፡” ብሎ አሰናበተው። ኢየሱስም እንዴት ያለ ታላቅ ነገር እንዳደረገለት በከተማው ሁሉ እየሰበከ ሄደ።

ይህ ሰው የሚታወቀው ታላቅ ነገር የተደረገለት ተብሎ ነው:: ይህ ሰውከእየሱስ ጋር መኖር ፈልጎ ነበር ምናልባትም እነዚያ አስጨናቂ መናፍስት ይመለሳሉ ብሎ ይሁን ወይንም ውለታው በዝቶብኛል ብሎ ይሆናል ጌታ ግን አልፈቀደም::  የእግዚአብሔር አሰራር ግን ለየት ስለሚል ወደ ቤትህ ሂድ አለው::  የከተማው ሰው ሁሉ ወተው ሂድልን ብለው ለመኑት ጸሎታቸውንም ሰማና ሄደላቸው::  ነገር ግን ወንጌላዊ ወደ ከተማቸው ማስገባቱን አላወቁም::  ሰውየውም በከተማው ሁሉ እየሰበከ ሄደ ይላል:: ይህንን ሰው ለመርዳት ተሻግሮ የመጣውጌታ ፍሬ እፍርቶ ተመለሰ የከሰረ ቢመስልም ሂድልን ሲሉት::  በመንፈስ ግን የተሰራ  ስራ አለ::  ሂድልን ሲሉት ሰውየውንም ይዞባቸው በሄደ ነበር ስለሚወዳቸው ግን እሱን ሰጣቸው በእርሱ ተጠቅሞ ይረዳቸዋልና::

ምንም እንኳን እነዚህ ሰዎች አህዛብ ናቸው ተብሎ ቢታሰብም የሰማርያ  ህዝብ ያችን ሴት ሰምተው ከእነርሱ ጋር እንዲቆይ ለመኑትና ከተማው ሁሉ ተከተለው በተቃራኒው::  የዛሬ ምኞቴ ለአገራችንም  ይኸው ነው እርሱን መከተልና መፈለግ ይሁንልን:: የእግዚአብሔር ፍቅር በምድራችን ይስራ!! አሜን!!

ሉቃስ 8:40-42

42 አሥራ ሁለት ዓመት የሆናት አንዲት ሴት ልጅ ነበረችውና፤ እርስዋም ለሞት ቀርባ ነበረች። ሲሄድም ሕዝቡ ያጨናንቁት ነበር።

በአጋንንት የተያዘውን ሰው ነፃ አውጥቶ የከተማውም ሰው ሁሉ ሂድልን ብለውት እየተመለሰ ነበር::  በተቃራኒው በዚህኛው የባህሩ በኩል ደግሞ ብዙ ህዝብ በጉጉት እየጠበቁት ነበር ከነዚህም አንዱ ይህ የምኩራብ አለቃ ነበረ::  እርሱም  እየሱስ እግር ላይ ወድቆ ወደ ቤቱ እንዲመጣና የታመመችውን ልጁን እንዲፈውስለት ለመነው::  እርግጠኛ መሆን የሚቻለው በዛ ያለው ሰው ሁሉ ያውቀዋል እንዴት እግሩ ስር ወደቀ? እየሱስን የሚያሳድዱት የእርሱ ቢጤዎች ናቸው ይሄ እንዴት ተለየ?  

ቸሩ ጌታ ለምን እንደ መቶ አለቃው አላመንክም ከዚሁ ቃል ብናገር ትድናለች አላለውም ይህችን ብላቴና እቤቱ ሄዶ ለመፈወስ ተስማምቶ  መንገድ ጀመረ::  ያለንበት ድረስ መቶ የሚገናኘን ጌታ አይፈርድብንም  ጸጋን ሰጥቶ ያቆመናል እርሱ እንደሰው አይደለምና በደረስንበት እምነት እንመላለስ::  የሚረዳንና የሚያዝንልን ሊቀ ካህናት አለን!! ሊቀ ካህኔ እየሱስ እኔን ልትረዳ ስለምትፈጥን ተመስገን!! እንደሰው ስላይደለህ ተመስገን!!  ስለምትረዳኝም ተመስገን!!

ሉቃስ 8: 43-48

46 ኢየሱስ ግን፦ “አንድ ሰው ዳስሶኛል፥ ኃይል ከእኔ እንደ ወጣ እኔ አውቃለሁና፡” አለ።

ሰው ሁሉ እያጨናነቁትና እያጋፋት ባለበት ውስጥ የዳሰሰኝ ማነው? ሲል ሐዋርያቱም ተገረሙ::  መዳሰሱንና በእምነት መነካቱን የሚያውቅ ጌታ ግን ማነው አለ::  አስራ ሁለት ዓመት የተሰቃየችበትን በቅጽበት ዳሰሳ የተገላገለችው ሴት እየተንቀጠቀጠች ተናዘዘች::  ፈውስዋንም አረጋገጠች::  የምናጋፋ ሳይሆን አስተውለን በእምነት የምንነካ ያድርገን::  ነገርዋን ለማንም ሳትነግር ከልብዋ  ጋር ተማክራ  በእምነት መጥታ ዳስሳው ፈውስዋን አገኘች::  እምነትን የማያልፍ ጌታ በዛ ሁሉ ፍትግጊያ  ውስጥ  ዳሰሳን ሰማ::  በፊቱ የምንለምነውን የሚሰማ ተራ ያዙ ቢዚ ነኝ የማይል ጌታ ስሙ ይባረክ!

እርሱም፦ “ልጄ ሆይ፥ እምነትሽ አድኖሻል፤ በሰላም ሂጂ፡” አላት። እንዴት ልብ ያረካል ንግግሩ ልጄ ሆይ ብሎ ጠርቶ ፈውሷን በአደባባይ አወጀው! ያለ እምነት እግዚአብሔርን ደስ ማሰኘትም ሆነ ከእጁ መቀበል አንችልም::  እምነትም የሚመጣው ህያው የሆነውን ቃል በመስማት ነው::  ይህች ሴት ብዙ ስለእየሱስ ሰምታለች ማለት ነው መጥታ የዳሰሰችው::  ባህሉ ባይፈቅድላትም የነካችው እንደሚረክስ ብታውቅም ቅሉ መጣች::  እየሱስ ይቀድሳል እንጂ በምንም አይረክስም!!  

ቅዱስ አባት ሆይ የጸሎታችንን ለሆሳስ እንኳን ታዳምጥና ትመልሳለህና ክብር ይሁንልህ!!!

ሉቃስ 8: 49-56

50 ኢየሱስ ግን ሰምቶ፦ “አትፍራ፤ እመን ብቻ ትድንማለች፡” ብሎ መለሰለት።

ልጅህ ሞታለች የሚል መርዶ ለደረሰው አባት አትፍራ!! እመን ብቻ ትድንማለች እንዴት ይባላል?  አባትየውማ የመጣው በህይወት እያለች ከመቼው ያንን ባህር ተሻግሮ ተመልሶ ብሎ በጉጉት ጠብቆ ሲያገኘው በእግሩ ወድቆ የለመነው ይህ እንዳይሆን ነበረ::  ነገር ግን የፈራው ደረሰ ጌታም ጊዜውን ወሰደ ሌላም ሴት ለመርዳት ቆየ::  የመጣበትን ሳያደርግ የማይመለስ ጌታ የጉብኝት ጊዜዋ ከዚህ በላይ እንዲቆይ አልፈለገምና አሰባት የደምዋም ምንጭ ደረቀ!  ሃሌሉያ!!

አርፋለች ለተባለው መልክት ትድናለች ብሎ ማለት ይገርማል::  ጊዜ በእርሱ ላይ ተጽዕኖ የለውም ከጊዜ ውጪ ይኖራል የእኛ ጌታ::  የዘገየብን የመሰለን ይመጣል ጌታ አይቀርም::  በኢያኢሮስ ቤትም ሲደርሱ ልምድ ያላቸው ነበሩና ይህ የህይወት ንጉስ አልሞተችም ሲላቸው ሳቁበት በኃላ ለማፈር::  አብርሃምም ይህንኑ ሆንዋል ምን ትሰጠኛለህ ያለልጅ እሄዳለሁ አለ ጌታም ሙት ከሆነው ማህጸን ውስጥ ይስሃቅን ሰጥቶ አሳቀው::  ጌታ በስራ ላይ ነው:: ወላጅዎችዋንና ከተወሰኑት ሐዋርያትን ብቻ ይዞ ገባ ክብሩን ለማየት ጥቂቶች ተመረጡ::  ጌታም እጅዋን ይዞ፦ “አንቺ ብላቴና፥ ተነሺ፡” ብሎ ጮኸ።ነፍስዋም ተመለሰች፥ ፈጥናም ቆመች፥ ወላጆችዋም ተገረሙ ይላል::  ከሞት ትነሳለች ብለው ጠብቀው ይሆን?! እንጃ!! ብቻ ግን ልጃቸው ተነሳች!  ምስጋና ይድረሰው!  የሞተብን፥ የተውነውና የረሳነው ነገር ሁሉ ህይወት ያግኝ!  በእየሱስ ስም አሜን! 

ሉቃስ 9: 1-6

1 አሥራ ሁለቱንም ሐዋርያት በአንድነት ወደ እርሱ ጠርቶ በአጋንንት ሁሉ ላይ ደዌንም ይፈውሱ ዘንድ ኃይልና ሥልጣን ሰጣቸው፤2 የእግዚአብሔርንም መንግሥት እንዲሰብኩና ድውዮችን እንዲፈውሱ ላካቸው፥

እግዚአብሔር አብርሃምን ሲጠራው የምድር ነገዶችን ሁሉ በአንተ እባርካለሁ ብሎት ነበር::  ከአብርሃም ይስሃቅ ከዛም ያዕቆብ ከእርሱም 12 ነገዶች ወጡ::  ይኸው እዚህ ቃል ላይ እዛው ተስፋ ላይ ሲመለስ እናያለን አሳቡን የማይቀይር ጌታ መልሶ 12ቱን ነገዶች አስነሳና ላካቸው::  ሲልካቸውም በአጋንንት ሁሉ ላይ ደዌንም ይፈውሱ ዘንድ ኃይልና ሥልጣን ሰጣቸው፤ የእግዚአብሔርንም መንግሥት እንዲሰብኩና ድውዮችን እንዲፈውሱ ላካቸው::  መንግስት የእርሱ ብቻ ነው የሰይጣን መንግስት መሸነፍና መልቀቅ መፍረስም አለበት::  ይኸው ተስፋ በእኛ ቀጥሏል ሊቀ ካህናችን እየሱስ እየማለደልን በአብ ቀኝ ነውና ዛሬም ድል የእኛ ነው::  እግዚአብሔር ዛሬም በጤና እንድንሆን ፈቃዱ ነው:: በመጀመርያ የእግዚአብሔርን መንግስት እንዲሰብኩ ላካቸው ይህ ዋናው የተላኩበት አገልግሎታቸው ነው ከዛም ደዌን መፈወስ እኛንም ልኮናል:: አሜን!

ሉቃስ 9: 7-9

7 አንዳንድ ሰዎች፡— “ዮሐንስ ከሙታን ተነሣ፥” 8 ሌሎችም፡— “ኤልያስ ተገለጠ፥” ሌሎችም፡— “ከቀደሙት ነቢያት አንዱ ተነሥቶአል፡” ይሉ ስለ ነበሩ፡ አመነታ።

ሄሮድስን ግራ ይግባው እንጂ ዝናው እየተሰማ ያለው ዮሃንስ ከሙታን ተነስቶ አይደለም፥ ኤልያስም አይደለም ወይንም  ከቀደሙት ነቢያት አንዱም አይደለም! እነርሱን አስቀድሞ የላከ ጌታ እንጂ የጫማውን ጠፍር እንኳን ለመፍታት የማይበቁ መሆናቸውን ያወቁ ባርያዎቹ ናቸው እነዚህ::

እግዚአብሔር ለአዳምና ለሄዋን ገና በኃጥያት ሲወድቁ ቃል የገባውን ለአብርሃምም እንደነገረው የዓለምን ሁሉ ነገዶች ሊታደግ የመጣው እራሱ ፈጣሪ የሆነው ታዳጊው አምላካችን ነው:: የእግዚአብሔር በግ ንጹህ በግ ስለኃጥያታችን ተላልፎ የሚሰጥ በግ ነው እየሱስ! እራሱን ያለስስት በእኔ እግር ገብቶ የተገኘ ወዳጅ!  ድንቅና ተአምራትን እያደረገ የተገለጠ ጌታ ሁሉን የፈወሰ የሞቱትን ያስነሳ ዛሬም ያልተቀየረ የሚሰራ ጌታ ነው!  አሜን

ሉቃስ 9:10 ሐዋርያትም ተመልሰው ያደረጉትን ሁሉ ነገሩት። ከእርሱ ጋርም ወስዶአቸው ቤተ ሳይዳ ከምትባል ከተማ አጠገብ ወደ ምድረ በዳ ለብቻው ፈቀቅ አለ።

ጌታ እየሱስ አሥራ ሁለቱን ሐዋርያት ጠርቶ በአጋንንት ሁሉ ላይ ደዌንም ይፈውሱ ዘንድ ኃይልና ሥልጣን ሰጥቶ ላካቸው::  ከተማሪነት አልፈው ወደ  ማገልገል መጡ:: ለማገልገል ሲወጡ ስንቅ ሳይሆን የያዙት ኃይልና ሥልጣን ነበረ የተቀበሉት::  ከአገልግሎትም መልስ የሆነውን  ሁሉ ነገሩት::  እርሱ ግን ወደ ምድረ በዳ ይዟቸው ሄደ::

ለምን ወደ ምድረበዳ ወሰዳቸው?  አገልግሎቱን አገልግለው የመጡት እርሱ በሰጣቸው ኃይልና ሥልጣን ነው በራሳቸው አይደለምና በፊቱ እርፍ ብለው ኃይላቸው እንዲያድሱና እንደገና በኃይል መውጣት ይሆንላቸው ዘንድ ነው:: አገልግለን የተጣልን እንዳንሆን እራሳችንን በእግሩ ስር ማድረግን እንማር::  እየሱስም ሲጠመቅ አብ ከመሰከረለትና መንፈስ ቅዱስም በእርሱ ላይ ካረፈ በኃላ የሄደው ወደ ምድረበዳ ነው ለብቻው ከአባቱ ጋር ለመቆየት::  እኛም ይህንን ወደ ጸጋ ዙፋኑ መቅረብን ልናዘወትር ይገባል::  

ይህንኑ ሐዋርያት ሲተገብሩት እናያለን እኛ ለቃሉና ለጸሎት እንተጋለን ሲሉ እንዲሁም በግልጥነት እንድንናገር  ስጠን ሲሉትና በኃይል ሲሞላቸው እናያለን::  እንትጋ!

ሉቃስ 9:11 ሕዝቡም አውቀው ተከተሉት፤ ተቀብሎአቸውም ስለ እግዚአብሔር መንግሥት ይነግራቸው ነበር፥ መፈወስ ያስፈለጋቸውንም ፈወሳቸው።

ወደ ምድረበዳ ሐዋርያቱን ለማሳረፍ ይዞ ቢወጣም ህዝቡ ግን ተከተሉት::  መልካሙ ጌታ አልመለሳቸውም እንደልማዱ ስለ መንግስቱ ይነግራቸው ነበረ::  በመጀመርያ ቃሉን ያስተምርና መንግስቱን ይገልጥ ነበር በቃሉ::  ዛሬም መንግስቱን በቃሉ ውስጥ ያስተምራል:: ቃሉን ካስተማረ እምነትም ከቃሉ ከተፈጠረ በኃላ መፈወስ ያስፈለጋቸውንም ፈወሳቸው። ከእምነታቸው የተነሳ የሰራበት ከእምነትም መጉደል የተነሳ ምንም ማድረግ ያልቻለበት አጋጣሚ አለ:: 

ያለ እምነት እግዚአብሔርን ደስ ማሰኘት አይቻልም!  እምነት ከመስማት የምንሰማውም የእግዚአብሔርን ቃል ነው::  ከቃሉ ውጪ እምነት ከየትም አይመጣምና!  ለቃሉ ጊዜ ይኑረን በእግሮቹ ስር ቁጭ ብለን እንደማርያም እንማር! ቃሉን ላከ ፈወሳቸው ከመከራቸውም አዳናቸው እንደሚል ጌታ ቃሉን ይልካል ካለንበትም ያወጣናል ይፈውሰንማል!  አሜን

ሉቃስ 9:  12-17

16 አምስቱንም እንጀራና ሁለቱን ዓሣ ይዞ፥ ወደ ሰማይ አሻቅቦ አየና ባረካቸው ቆርሶም ለሕዝቡ እንዲያቀርቡ ለደቀ መዛርሙርቱ ሰጠ።

እንደሐዋርያቱ ምክር ቢሆን ስለመሸ ባሰናበታቸው ነበረ::  እርሱ ግን ጥቂቱን ባርኮ አጠገባቸውና ተረፈ! የእኛ ምክር ይኸው ነው የእርሱ ግን ተፈጥሮን ሁሉ ያልፋልና እረፉ እኔም አምላክ እንደሆንኩ እወቁ ያለን ለዚሁ ነው::

ዛሬ እጃችን ላይ ምን አለ?  ያለውን እናቅርብለት በትንሽዬዋ አይምሯችን አስበን አውጥተን አውርደን አይሁን::  ያለንን በእምነት ወደ እርሱ ይዘን እንቅረብ አንዳንዴ ከምናልፍበት ነገር የተነሳ አምላካችን ማን እንደሆነ ይጠፋናል መሰለኝ::  እርሱ ሁሉን የፈጠረ ነው፥ በሁሉ ላይ ስልጣን ያለው፥  መንደርደርያና መነሻ አያስፈልገውም የሌለውን እንዳለ አድርጎ የሚጠራ ጌታ ነው! እንታመንበት ከስጋችን ሳንማከር ወደ እርሱ እንቅረብ  እርሱም እንደታላቅነቱ መጠን ይሰራል::

ሉቃስ 9: 18-20

20 “እናንተስ እኔ ማን እንደ ሆንሁ ትላላችሁ?” አላቸው። ጴጥሮስም መልሶ፡— “ከእግዚአብሔር የተቀባህ ነህ፡” አለ።

እየሱስ ጠፍቶት አይደለም ሌሎች ስለእኔ ምን ይላሉ ብሎ የጠየቃቸው ለሚቀጥለው ጥያቄ መንደርደርያ እንዲሆን እንጂ::  ለእናንተ ማን ነኝ?!  ዛሬም ይህንን ጥያቄ መመለስ አለብን::  ጴጥሮስም አንተማ ከእግዚአብሔር የተቀባህ መሲህ ነህ አለው:: 

ለእኔ?  የእግዚአብሔር በግ ነህ!  ስለዚህ ኩነኔ የለብኝም!  በሞትህም ሞቴ ተሻረ – አዳኜና ማምለጫዬ ነህ:: ዕዳዬን የከፈልክ! ቅድስናዬ ጽድቄ የዕዳው ጽህፈት የተሻረልኝ!! የእግዚአብሔር ወገን አደረከኝ! ከቁጣህም አዳንከኝ!  ወዳጅ ሆንኩኝ! እየሱስ ጌታዬና አምላኬ ነህ እገዛልሃለሁ!

ሉቃስ 9:21—22 እርሱ ግን፡— “የሰው ልጅ ብዙ መከራ ሊቀበል በሽማግሌዎችም በካህናት አለቆችም በጻፎችም ሊጣል ሊገደልም በሦስተኛውም ቀን ሊነሣ ይገባዋል፡” ብሎ ለማንም ይህን እንዳይናገሩ አስጠንቅቆ አዘዘ።

ማንነቱን ሲጠይቃቸው ከእግዚአብሔር የተቀባህ ብሎ ጴጥሮስ በመንፈስ ተረድቶ መለሰ::  ጌታም ከዚህም የበለጠ ስለእኔ እወቁ ብሎ በእርሱ ላይ የሚሆነውን  ገለጸላቸው::  

የሚደርስበትን ሲዘረዝር:-

መከራ እንደሚቀበል 

በሽማግሌዎችም በካህናት አለቆችም በጻፎችም ሊጣል – ግንበኞች የጣሉት የማዕዘን ራስ እየሱስ

ሊገደልም – ስለእኛ በደል ሙሉ ዋጋ ሊከፍል

በሦስተኛውም ቀን – የሞትንና የሲዖልን ቁልፍ ተቀብሎና መቃብሩን ፈንቅሎ ሊነሳ!!

ሊከብርና ሊገንን ይገባዋል!!  አሜን!

እነሱ የሚፈልጉትና የሚጠብቁት የምድር ንጉስ ከሮም አገዛዝ ነፃ የሚያወጣ እርሱ የሚለው እሞታለሁ::  በመጨረሻ ወደ ሰማይ ሊያርግ ሲል መንግስትን ለእስራኤል መቼ ትመልሳለህ ነበረ ጥያቄያቸው:: መንፈስ ቅዱስ ሲመጣ እንጂ ይህንን ጥልቅ እውነት የተረዱት ከዛ በፊት ምንም አልገባቸውም:: 

ዛሬም በመረዳት እንመላለስ የዳነው በስራ ሳይሆን በእርሱ መስዋትነት ነውና የምንመካበትም የለንምና ዝቅ ብለን በትህትና ጌታን እናገልግል ከማንም አንሻልም::  ይህንንም የመዳን እውነት ለፍጥረት እንንገር::

ሉቃስ 9:23 ለሁሉም እንዲህ አላቸው፡— “በኋላዬ ሊመጣ የሚወድ ቢኖር፥ ራሱን ይካድ መስቀሉንም ዕለት ዕለት ተሸክሞ ይከተለኝ።

የሚደርስበትን መከራ ነግሯቸው ሲያበቃ እነሱንም እንደሚጠብቃቸው ነገራቸው::  እነርሱ  እያዘኑ ያሉትና ልባቸው የከበደው ስለእርሱ ነበር ለካስ እነርሱም መስቀል መሸከም ይጠብቃቸዋል::

በዘመኑ መስቀል ተሸክሞ መሄድ እንጂ መመለስ የለምና የሚናገረው በዘመኑ የሮም አገዛዝ የሚፈጸም ቅጣት ስለሆነ ጠንቅቀው ያውቁታል::  የሚሰቀሉበትን መስቀል የመሸከም ግዴታ የሟቹ ነው::  ራስን ካልካዱ በስተቀር ወደዚህ ህይወት ማን ይገባል?!  ይህ መሸከም የሚቀጥል ነው በየዕለቱም ነው::  እኛ የራሳችን አይደለንም በዋጋ ተገዝተናል!

ሉቃስ 9:24-27

25 ሰው ዓለሙን ሁሉ አትርፎ ራሱን ቢያጠፋ ወይም ቢያጐድል ምን ይጠቅመዋል?

መስቀል ተሸክማችሁ ተከተሉኝ ያለውን ችላ ማለትና ለዓለም ትርፍ መሮጥም ሆነ በኃጥያት ማግበስበስ በምድር እንዲመቸን ሊያደርግ ይችል ይሆናል ነገር ግን ነፍሳችን የሚያስፈልጋትን አዳኝ ባታውቅ ምን ይጠቅማል?! የተከማቸው ኃብት ከስጋም ሆነ ከነፍስ መሞት አያስጥልም::

ዉደ ነፍሳችን እረኛ ዞር እንድንልና እንድናውቀው የረዳን ጌታ ይባረክ! መዳን ብቻ ሳይሆን የሚጠበቅብን በቃሉ አለማፈርም ነው:: በእኔና በቃሌ የሚያፍር ሁሉ፥ የሰው ልጅ በክብሩ በአባቱና በቅዱሳን መላእክቱ ክብርም ሲመጣ በእርሱ ያፍርበታል ይላልና በጌታና በቃሉ እንዳናፍር ጌታ ይርዳን!

አባት ሆይ ዕለት ዕለት መስቀላችንን ተሸክመን እንድንከተልህ እንዲሁም በአንተ ላይ ዓይናችንን እንድናደርግና በሙሉ ልባችን እንድንከተልህ ጸጋህን አብዛልን! 

ሉቃስ 9: 28-29

29 ሲጸልይም የፊቱ መልክ ተለወጠ፤ ልብሱም ተብለጭልጮ ነጭ ሆነ።

እናንተስ ማን ትሉኛላችሁ ያለው ጌታ ማንነቱን በመጠኑ ሊያሳያቸው ወደ ተራራ ወሰዳቸው::  ደግሞም ጌታ እውነት እላችኋለሁ፥ በዚህ ከሚቆሙት ሰዎች የእግዚአብሔርን መንግሥት እስኪያዩ ድረስ ሞትን የማይቀምሱ አንዳንድ አሉ እንዳለው ክብሩን አሳያቸው::  

አብሯቸው ቢበላና ቢጠጣ ቢመላለስም እርሱ ግን የተፈራውና የተከበረው ጌታና አምላካችን ነው::  ስለዚህም ያየነውንና ከገናና ክብሩ የሰማነውን የዳሰስነውን እናወራለን እንመሰክራለን ብለው ጻፉልን::  ሃሌሉያ! 

በዚያ ተራራ ላይ እየጸለየ ፊቱ ተለወጠ ይህንንም በሙሴ እናያለን አርባ ቀንና ለሊት ከጌታ ጋር ቆይቶ ሲወርድ ፊትህን ሸፍን እስኪሉት ደረሰ::  የእየሱስ ግን የፊቱ መለወጥ ብቻ ሳይሆን ልብሱም ተብለጨለጨ ወይም አጣቢ ሊያነፃው እስከማይችል የምድር ያልሆነ መዋብ ሆነባቸው:: ይህ ጌታ ዛሬ ከእኛ ጋር ነው የምናጋፋ ሳይሆን ክብሩን የምናይ ያድርገን::  አሜን!!!

ሉቃስ 9: 30-31

30 እነሆም፥ ሁለት ሰዎች እነርሱም ሙሴና ኤልያስ ከእርሱ ጋር ይነጋገሩ ነበር፤

ጌታ ክብሩን ሊያሳይ ይዟቸው በወጣበት ሁለት ሰዎች ማለትም ሙሴና ኤልያስ ከእርሱ ጋር ይነጋገሩ ነበር::  የእነዚህ ሰዎች ተጽዕኖ በእስራኤሎች ላይ ቀላል አይደለም::  ለምን እነዚህ ታዩ?  ለምን አዳም፤ ዳዊት ወይም ደግሞ አብርሃም አልታዩም? 

በጥቂቱ ለመጥቀስ ሙሴ ህግን ወክሎ ኤልያስ ደግሞ ነብያትን ወክሎ ቆመዋል::  ቃል እንደገባው አምላክ ሰው ሆኖ አዩ::  ይህ ተአምር  ነው!!!  በሙሴ ዘመን እስራኤላውያን እግዚአብሔር አይናገረን እንሞታለን አሉ::  ዛሬ እንደዛ የተንቀጠቀጡለት ጌታ በመካከላቸው ቆሞ አላወቁትም::  ክብሩ ሰማያትን ሸፍኗል!!  ይህ ትልቅ ጌታ ተላልፎ በሰው እጅ ለመሞት መጣ?!!!  እንዴት ጥልቅ ነው ደህንነታችን::  ከእነርሱም ጋር የተነጋገረው በኢየሩሳሌም ሊፈጽም ስላለው ስለ መውጣቱ ይናገሩ ነበር። ይደንቃል!  የተዋጀሁት በእንሰሳ ደም ሳይሆን ክብሩን ጥሎ በመጣውና እጅግ በወደደኝ ቅዱስና ኃያል አምላክ ነው!  መዳኔ ውድ ነውና ተመስገን!!

ሉቃስ 9: 32-33

33 ከእርሱም ሲለዩ ጴጥሮስ ኢየሱስን፡— “አቤቱ፥ በዚህ መሆን ለእኛ መልካም ነውና አንድ ለአንተ አንድም ለሙሴ አንድም ለኤልያስ ሦስት ዳሶች እንሥራ፡” አለው፤ የሚለውንም አያውቅም ነበር።

ጴጥሮስ የሚለውንም አያውቅም ነበረና ሶስት ዳስ ማቆም ፈለገ:: በእውኑ ኢየሱስ ከሙሴና ከኤልያስ መደዳ ነውን? ጌታም አልወቀሰውም ታገሰው:: የእኛ አምላክ በላይ በሰማይ በዙፋኑ ላይ የሚቀመጥ ጌታ ነው የሰው እጅ በሰራው ዳስ አይኖርም::

የእግዚአብሔር ዓላማ ምንድነው ይህንን ክብር ሲያሳያቸው? ክብሩን አይተው ምስክር ይሆኑ ዘንድ ነው:: ሶስቱን ብቻ መርጦ ነው ይዞ ወደ ተራራው የወጣው:: እነርሱም እንቅልፍ የከብዶባቸው ያለ ቢሆንም ግን ነቅተው ክብሩን አዩ:: የሚነጋገሩትንም ሰሙ ስለሚመጣው መከራውና በእየሩሳሌም ስለሚፈጸመው የሰው ልጆችን ነፃ የማውጣት ተልዕኮና ስለኢየሱስ ተላልፎ መሰጠት ነበር::

ክብሩን እንዳናይ ከሚከለክል ድካም ጌታ ያውጣንና ክብሩን እንይ:: ሐዋርያቱ አብረውት በጸሎት ተግተው ቢሆን ኖሮ ይህ ባልሆነ ነበር:: ዛሬም በጸሎት እንድንተጋና ክብሩን እንድናይ ጸጋው ይብዛልን:: አሜን!

የዮሐንስ ወንጌል

መግቢያ

የዮሐንስ ወንጌል ከሌሎቹ ወንጌሎች ለየት ይላል::  መለየቱም በጣም መንፈሳዊ ነው ማለትም አዲስ ኪዳናዊነቱ በጣም የጎላና የመንፈስ ቅዱስ እርዳታና መገለጥ ያለበት ጥልቅ እይታ ያለው ነው:: አንዳንዶች ስለዚህ ክፍል ሲናገሩ ሌሎቹን አንብቦ የጎደለውን ለመሙላት የተፃፈ ነው ይላሉ::  ከተደረጉት ተአምራት ሰባቱን ብቻ ነው የፃፈልን::  ሌሎቹ የተደረጉትን ነገሮች እንደሪፖርት ሲጽፉ እሱ ግን በእየሱስ አምላክነትና ሰው መሆንን ሊያሳየን ፃፈ::  የፍቅር ሰው ነው ምክንያቱም እራሱን ጌታ የሚወደው እያለ ይጠራል በሌሎቹ ወንጌላት አናገኘውም ይህም አልበቃውም በሌሎቹ መልእክቶቹም ፍቅርን በደንብ ገልጾ ጽፎልናል:: ስለእየሱስ አምላክነት ሲጽፍ ከስጋ ከትውልዱ አይደለም የጀመረው ከእግዚአብሔርነቱ ቃል እንደነበረ ቃልም በእግዚአብሔር ዘንድ እንደነበረና  ቃልም እግዚአብሔር እንደሆነ ይነግረናል:: ስለእየሱስ ሰው መሆን ደግሞ በተለያየ ታሪክ ውስጥ እናገኘዋለን::  ሳምራይቱን ሴት ሲያገኝ በምዕራፍ 4 ላይ ደክሞት እንደነበረ፤ ለአላዛር እንዳዘነና እንዳለቀሰ እንዲሁም በቤተመቅደስ ውስጥ ሲነግዱ ባገኛቸው ሰዎች እንደተናደደና ዱላ እንዳነሳም አሳይቶናል:: ጌታ ይረዳንና ይህንን ክፍል እናጠናለን:: 

ጸሎት:-አባት ሆይ አስተምረን ቃልህን በልባችን አትመው ውሃ የሌለው ደመና አይሁን ወደ ልባችን ወርዶ ያረስርሰን::  አሜን!

ዮሐንስ 1: 1-21፤

በመጀመሪያው ቃል ነበረ፥ ቃልም በእግዚአብሔር ዘንድ ነበረ፥ ቃልም እግዚአብሔር ነበረ።2፤ ይህ በመጀመሪያው በእግዚአብሔር ዘንድ ነበረ።

ዮሃንስ የሚጀምረው ከዘፍ 1:1 ነው::  በመጀመሪያ እግዚአብሔር ሰማይንና ምድርን ፈጠረ። ይህም ማለት የምጽፈውን ለመረዳት አዳም ጋር ወይም አብረሃም ጋር አይደለም የምጀምረው (የተቀሩት ወንጌላት ያንን አሳይተዋልና) ከዛ በፊት ምንም ፍጥረት ሳይኖር ዓለም ሳትሰራ መኖርያም ሳትሆን ማለቱ ነው:: ወንጌልን ሲጽፉ ሶስት ዓመት ሙሉ ከሰራውና ከኖረው  መርጠው ነው የፃፉት ሁሉ ቢፃፍ እንደማይቻልም ነግሮናል ዮሃንስ:: ከፍጥረት መጀመሪያ በፊት ይህ ቃል የተባለው በእግዚአብሔር ዘንድ ነበረ::  በፍጥረት አፈጣጠር ጥያቄ ካለ ይህም ቃል ተብሎ እየተጠራ ያለው ወልድ ተጠያቂ ነው::   ምክንያቱም ከእግዚአብሔር ጋር አብሮ ነበረና:: ይህም ቃል እራሱ እግዚአብሔር ነው ይለናል::  እኔን ያየ አብን አየ ብሎ የለም ጌታ እየሱስ::   በእቅፉ ያለ አንድያ ልጁ ተረከው እንደሚል አብሮ ስለነበረ መተረክ ይችላል ማሳየትና መናገርም ይችላል:: ሌላው አብርሃም ቀኔን ሊያይ ተመኘም ብሎ ነበር – አብርሃም ወንጌል ተሰብኮለታል በራሱ በጌታ:: እርሱ የነበረና ያለ ነው::  የእየሱስን ፍጥረት አለመሆንና ፈጣሪ መሆኑን የሚያሳይ ነው::  አልፋና ኦሜጋ! ሃሌሉያ!

ዮሐንስ 1: 3-53፤ ሁሉ በእርሱ ሆነ፥ ከሆነውም አንዳች ስንኳ ያለ እርሱ አልሆነም።4፤ በእርሱ ሕይወት ነበረች፥ ሕይወትም የሰው ብርሃን ነበረች።5፤ ብርሃንም በጨለማ ይበራል፥ ጨለማም አላሸነፈውም።

ይህ የሁሉ መገኛ የሆነው ጌታ ሁሉን አደረገ ሁሉን ፈጠረ::  ምንም ነገር ያለ እርሱ የሆነ የለም የፍጥረት ሁሉ መገኛ ነው እርሱ::  አምላክ መሆኑን ይገልፃል::ይህንን የህይወት ራስ ነው የሰው ልጅ አንገላቶ የሰቀለው እርሱም እንዳለ ነፍሴን በፈቃዴ አኖራታለሁ አለ::  አለበለዚያ ማንም ህይወትን ከእርሱ መንጠቅ አይችልም:: ወዶ ስለእኛ ዋጋ ከፈለ:: በጨለማችን ላይ ብርሃን ይብራ ያለ እርሱ ነው::  ጨለማውን አስወግዶ በብርሃን ተካው::  ጨለማም ብርሃንን አላሸነፈውም::  ለዘላለምም አያቨንፈውምም::  ዮሃንስ በእርሱ ህይወት ነበረች ሲለን የሚያወራው እስከሞት ያለውን በስጋ መኖርን አይደለም::  ስለዘላለም ህይወት ስለማይቋረጠው ህይወት ነው::  ይህ ህይወት የሆነው ጌታ በእኛ ውስጥ እየኖረ ነው ይህ ህይወት ደግሞ አይቋረጥም ለዘላለም ያኖረናል::

አባት ሆይ: አንተ የህይወት ምንጭ ነህ ይህንን ህይወት ስለሰጠኸኝ አመሰግንሃለሁ ማንም ከእጅህ መዳፍ አይነጥቀኝም ለዘላለም ልጅ ብለህ ተቀበልከኝ እኔም አባ ተመስገን እላለሁ::

ዮሐንስ 1: 6-10

6፤ ከእግዚአብሔር የተላከ ስሙ ዮሐንስ የሚባል አንድ ሰው ነበረ፤7፤ ሁሉ በእርሱ በኩል እንዲያምኑ ይህ ስለ ብርሃን ይመሰክር ዘንድ ለምስክር መጣ።8፤ ስለ ብርሃን ሊመሰክር መጣ እንጂ፥ እርሱ ብርሃን አልነበረም።9፤ ለሰው ሁሉ የሚያበራው እውነተኛው ብርሃን ወደ ዓለም ይመጣ ነበር።10፤ በዓለም ነበረ፥ ዓለሙም በእርሱ ሆነ፥ ዓለሙም አላወቀውም።

መጥምቁ ዮሃንስ ማን ይሆን የተባለ ህፃን ከውልደቱ ጀምሮ የሚጠብቁት አኗኗሩ በምድረ በዳ፤  ልብሱ ለምድ፤  ነገሩ ሁሉ ለየት ያለ ነበረ::  ድንገት መቶ ጥምቀት ማጥመቅ ሲጀምር ብዙዎች መጡ ለንስሃ:: ጥምቀት ብሉይ ኪዳናዊ ባይሆንም እንኳን ሰው ንስሃ እየገባ ለሚመጣው መሲህ ለመዘጋጀት እየተጠመቀ ነበረ:: እርሱንም  ማነህ ሲባል እኔ እርሱ አይደለሁም ብሎ ስለ ብርሃን ይመሰክር ነበር::  እንደጌታ ደቀ መዛሙርት ስለነበሩት አንድ እንዳይመስሏችሁ ነው የወንጌሉ መልክት::  ይህ ጠቋሚ ነው ሊመጣ ያለው ግን ለሰው ሁሉ የሚያበራው እውነተኛው ብርሃንና በግ መሲሁ  እየሱስ ነው። አሜን መጥምቁ ዮሃንስ በእግዚአብሔር የተላከ ሰው ነበረ::  ስራውም ይህንን ብርሃንና ህይወት የሆነውን ጌታ ሰዎች ያምኑ ዘንድ እንዲጠቁም እንጂ እርሱ አዳኝ አልነበረም::  ዛሬም  እኛ ከእግዚአብሔር ጋር ታረቁ የሚል አገልግሎት ተሰቶናል ወደዚህ ህይወት ወደሆነው ጌታ እንድንጠቁም::  

አባት ሆይ እራስህን ገልጠህልኝ አንተን አውቄ በቤትህ ተክለኸኛልና ተመስገን::  ሌሎችን ከአንተ ጋር የማስታረቅንም ጸጋ ስለሰጠኸኝ ተመስገን ሰዎች ስነግራቸው አንተን ማወቅ ይሁንላቸው::  አሜን!

ዮሐንስ 1: 11-13

11፤ የእርሱ ወደ ሆነው መጣ፥ የገዛ ወገኖቹም አልተቀበሉትም።12፤ ለተቀበሉት ሁሉ ግን፥ በስሙ ለሚያምኑት ለእነርሱ የእግዚአብሔር ልጆች ይሆኑ ዘንድ ሥልጣንን ሰጣቸው፤13፤ እነርሱም ከእግዚአብሔር ተወለዱ እንጂ ከደም ወይም ከሥጋ ፈቃድ ወይም ከወንድ ፈቃድ አልተወለዱም።

ጌታ ዋጋ ለመክፈል መምጣት ነበረበት ከአብርሃምም በቀር የታዘዘ አልነበረምና ለአዳም እንደገባው ቃል ወደ ሰው ልጅ ሁሉ በእስራኤል በኩል መጣ::  የፈጠረውና እንዲኖር ያደረገው ይህንን ዓለም እርሱ ሆኖ ሳለ ሲመጣ ግን ማንም አላወቀውም:: የሰው ልጅ ፈጣሪውን አለማወቁ  ደግሞ አለመቀበልን አስከተለ:: ባወቁትስ ኖሮ የህይወትን ራስ ባልገደሉት ነበረ እንደሚል ነው ቃሉ::  እርሱ ግን ለመሞት ቆርጦ መጣ:: ልጅነት በመቀበል የሚገኝ እንጂ ለሁሉ እንደራሽን የሚታደል አይደለም::  እርሱን ማወቅ  የእግዚአብሔር ልጅ እንደሆነና ከዛም ጌታዬ ነህ ስንለው ልጅነትን እናገኛለን::  ሌላ ነገር አድርጉም አልተባልንም::  ስለዚህም ከእግዚአብሔር ተወለዱ እንጂ ከደም ወይም ከሥጋ ፈቃድ ወይም ከወንድ ፈቃድ አልተወለዱም።  

አሜን

አባት ሆይ እንዳውቅህ ስለረዳኸኝ አመሰግንሃለሁ::   ከአንተ ተወልጃለሁኝ ይህንን ልጅነት ማንም አይነጥቀኝም::  ተመስገን!

ዮሐንስ 1: 14-18

14፤ ቃልም ሥጋ ሆነ፤ ጸጋንና እውነትንም ተመልቶ በእኛ አደረ፥ አንድ ልጅም ከአባቱ ዘንድ እንዳለው ክብር የሆነው ክብሩን አየን።15፤ ዮሐንስ ስለ እርሱ መሰከረ እንዲህም ብሎ ጮኸ፦ “ ‘ከእኔ በኋላ የሚመጣው እርሱ ከእኔ በፊት ነበረና ከእኔ ይልቅ የከበረ ሆኖአል፤’ ስለ እርሱ ያልሁት ይህ ነበረ።”16፤ እኛ ሁላችን ከሙላቱ ተቀብለን በጸጋ ላይ ጸጋ ተሰጥቶናልና፤ 17፤ ሕግ በሙሴ ተሰጥቶ ነበርና ጸጋና እውነት ግን በኢየሱስ ክርስቶስ ሆነ።18፤ መቼም ቢሆን እግዚአብሔርን ያየው አንድ ስንኳ የለም፤ በአባቱ እቅፍ ያለ አንድ ልጁ እርሱ ተረከው።

ይህ ቃል እግዚአብሔር ነው የተባልነው ቃል ያለ እርሱ ምንም አልሆነው የተባለው ቃል ምን ሆነ ይለናል? በእኛ መካከል እደረ ወይም ተወለደ ስጋን ለብሶ መጣ::  ሲመጣ ደግሞ ጸጋንና እውነትን ተሞልቶ ነው ምክንያቱም እርሱን አይቶ በህይወት የሚኖር የለምና – ጸጋ ተሞልቶ እውነትንም ሳይጥል አብሮ ይዞ መጣ:: የእርሱ ፍርድ ጽድቅና እውነት ነው አልተዛነፈም  ሊያመቻምችም አልመጣም የሐጥያት ደሞዙ ሞት ነው:: እንድንኖር ጸጋን ሰጠን ይህ ቅዱስ ጌታ::  ዮሃንስ ግን መሰከረ ከእኔ በኋላ የሚመጣው እርሱ ከእኔ በፊት ነበረና ከእኔ ይልቅ የከበረ ሆኖአል፤’ ስለ እርሱ ያልሁት ይህ ነበረ።” ዋዉ እርሱ ትልቅ ነው ከሁሉ የከበረ::  እኛ ሁላችን ከሙላቱ ተቀብለን በጸጋ ላይ ጸጋ ተሰጥቶናልና፤  በጸጋ ላይ ጸጋ እንጂ እንደገና በሙሴ የተሰጠውን ህግ አይደለም ይዞልን የመጣው:: እግዚአብሔር ለእኛ ያለውን ፍቅር በዚህ አሳየ ጸጋን ሰቶ እውነትንም ሳያዛንፍ ዋጋ ከፍሎ አዳነን::  አሜን! ስለዚህም እየሱስ ጸጋንና እውነትን ተሞልቶ መቶ የአባቱን ማንነት አሳየን::  መቼም ቢሆን እግዚአብሔርን ያየው አንድ ስንኳ የለም፤ በአባቱ እቅፍ ያለ አንድ ልጁ እርሱ ተረከው። አሜን

አባት ሆይ ተመስገን ከሙላትህ ስለሞላኸን ዛሬም በጸጋ ላይ ጸጋ ስለሰጠኸን ክበር::  በእኔ ዛሬ ማንነትህ ሰውን መውደድህ ይታይ::  አሜን

ዮሐንስ 1: 19-28

19፤ አይሁድም፦ “አንተ ማን ነህ?” ብለው ይጠይቁት ዘንድ ከኢየሩሳሌም ካህናትንና ሌዋውያንን በላኩበት ጊዜ፥ የዮሐንስ ምስክርነት ይህ ነው።20፤ መሰከረም አልካደምም፤ “እኔ ክርስቶስ አይደለሁም” ብሎ መሰከረ።21፤ “እንኪያስ ማን ነህ? ኤልያስ ነህን?” ብለው ጠየቁት። “አይደለሁም፡” አለ። “ነቢዩ ነህን?” “አይደለሁም፡” ብሎ መለሰ።22፤ “እንኪያስ፦ ማን ነህ? ለላኩን መልስ እንድንሰጥ፤ ስለራስህ ምን ትላለህ?” አሉት።23፤ እርሱም፦ “ነቢዩ ኢሳይያስ እንዳለ፦ ‘የጌታን መንገድ አቅኑ፡ ብሎ በምድረ በዳ የሚጮኽ ሰው ድምፅ፡’ እኔ ነኝ፡” አለ።

አይሁድ የዮሐንስ ዝና ስለወጣ ማንነቱን ለማጣራት መልክተኞችን ላኩ::  የተላኩትም ካህናትንና ሌዋውያን ነበሩ ላኪዎቹም አይሁድ ናቸው::   ማነህ ነው? ብለው ሶስት ምርጫ ነው ይዘው የመጡት:- መሲህ ፤ ኤልያስ ወይስ ነብዮ ነበር ጥያቄው::  ሌዋዉያን የተላኩት የህጉን ክፍል ጠንቅቀው ስለሚያውቁም ይሆናል:: መጽሐፍት ትመረምራላችሁ  እነርሱም ስለእኔ ይናገራሉ ግን ትስታላችሁ እንዳለ ጌታ እንደዛው ሆነባቸው:: ያልጠቀሱት ወይም ቸል ያሉት እውነት ቢኖር የጌታን መንገድ አቅኑ፡ ብሎ በምድረ በዳ የሚጮኽ ሰው ድምፅ፡ ነበረ ዮሃንስ::  መሲህ  ከመገለጡ በፊት ኤልያስ ይመጣል ብለው ይጠባበቁ ነበር::  ነገር ግን ኤልያስን ኤልያስ ያደረገው መንፈስ በዮሐንስ መገለጡን አላወቁም::  ስለዚህም ሳቱ! ዮሃንስ የተገለጠው በኤልያስ ኃይልና መንፈስ ነው::  መሲሁን እየጠበቁ እንደሆነ ያሳያል ግን ዮሃንስ እንዳለ እናንተ የማታውቁት በመካከላችሁ ቆሟል!  ዋዉ እኛ ግን ረድቶን አወቅነው ስሙ ይባረክ::  ዮሃንስም መሰከረ  ነብዮም አይደለሁም አለ::  ይህ ነብይ የሚሉት ማንን ነው? ሙሴ በመካከላችሁ እንደእኔ ያለ ነብይ ያስነሳል ያለውን ነው የሚጠብቁት::ዮሐንስ ግን ስለእየሱስ መሰከረ አልሸሸገምም የጊዜውም ዝና ከእውነት አላራቀውም ሊሸፍነውም አልደፈረ በግልጥ፦ “እኔ በውኃ አጠምቃለሁ፤ ዳሩ ግን እናንተ የማታውቁት በመካከላችሁ ቆሞአል፤ እኔ የጫማውን ጠፍር ልፈታ የማይገባኝ፥ ከእኔ በኋላ የሚመጣው ከእኔ ይልቅ የሚከብር ይህ ነው፡” አላቸው። አሜን የከበረ ጌታ ነው ስሙ ይባረክ! አዋቂዎች ያላወቁት/የናቁት የማእዘን ራስ እየሱስ ለዓለም ምናምንቴ እራሱን ገለጠ ይገርማል::  ምን እላለሁ ጌታዬ ክበር::

ዮሐንስ 1: 29-31

29፤ በነገው ዮሐንስ ኢየሱስን ወደ እርሱ ሲመጣ አይቶ እንዲህ አለ፦ “እነሆ የዓለምን ኃጢአት የሚያስወግድ የእግዚአብሔር በግ።30፤ ‘አንድ ሰው ከእኔ በኋላ ይመጣል፥ ከእኔም በፊት ነበርና ከእኔ ይልቅ የከበረ ሆኖአል፡’ ብዬ ስለ እርሱ ያልሁት ይህ ነው።31፤ እኔም አላውቀውም ነበር፥ ዳሩ ግን ለእስራኤል ይገለጥ ዘንድ ስለዚህ በውኃ እያጠመቅሁ እኔ መጣሁ።”32፤ ዮሐንስም እንዲህ ብሎ መሰከረ፦ “መንፈስ ከሰማይ እንደ ርግብ ሆኖ ሲወርድ አየሁ፤ በእርሱ ላይም ኖረ።33፤ እኔም አላውቀውም ነበር፥ ዳሩ ግን በውኃ አጠምቅ ዘንድ የላከኝ እርሱ፦ ‘መንፈስ ሲወርድበትና ሲኖርበት የምታየው፥ በመንፈስ ቅዱስ የሚያጠምቅ እርሱ ነው፡’ አለኝ።34፤ እኔም አይቻለሁ እርሱም የእግዚአብሔር ልጅ እንደ ሆነ መስክሬአለሁ።”ምን አይነት ምስክርነት ነው?! እነሆ አለ ዮሃንስ እየሱስን ሲያስተዋውቅ:1.  የእግዚአብሔር በግ – የዓለምን      ኃጢአት የሚያስወግድ:: 2. ከእኔም በፊት ነበርና ከእኔ ይልቅ የከበረ      ሆኖአል – ያለና የነበረ 3. መንፈስ ከሰማይ እንደ ርግብ ሆኖ     ሲወርድ አየሁ – በመንፈስ ቅዱስ     የሚያጠምቅ እርሱ ነው፡4. የእግዚአብሔር ልጅ እንደ ሆነ      መስክሬአለሁይህንን ምስክርነት ዮሃንስ  እየሰጠ ያለው እየሱስ ከመጠመቁ በፊት ሳይሆን ተጠምቆ በመንፈስ ቅዱስ ተሞልቶ በምድረ በዳ 40 ቀናትን ጾሞና ጸልዮ በሰይጣንም ተፈትኖ ሲመለስ ነው:: አያይዞም እኔም አላውቀውም ነበር አለ እርሱ ብቻ ሳይሆን መጽሐፉን እናውቃለን የሚሉትም እስከመጨረሻው አላወቁትም፥::  ዳሩ ግን ለእስራኤል ይገለጥ ዘንድ ስለዚህ በውኃ እያጠመቅሁ እኔ መጣሁ። ዋናው ስራ የዮሐንስ ሲመጣ መሲሁ መግለጥ ነበረና ገለጠው ክብርንም አልወሰደም ይኸው እናንተ የማታውቁት በመካከላችሁ ቆሟል አለ::ይህ በግ ንጹ የሆነ በምንም ያልተበከለ የዓለምን ኃጥያቶች ሳይሆን ኃጥያት ተብሎ በነጠላ ቁጥር ተጠቅልሎ እንደቀላል የተሰጠው ነው::   ይህ በግ በሸላቶቹ  ፊት ዝም አለ፤  የደም ላብ አላበው በጌቴሰማኒ የመጣበትን ጽዋ ለመጠጣት አባት ሆይ ከእኔ ይህ ጽዋ ይለፍ እስኪልና በመስቀልም ከፍሎ እስኪጨርስ ድረስ አብ አባት ተወው::  ዋው የእግዚአብሔር በግ!!! ተመስገን ጌታዬ!ከእኔም በፊት ነበርና ከእኔ ይልቅ የከበረ ሆኖአል  ሲል ዮሃንስ አንዳንዱ አንተ በወራት ትበልጠዋለህ  ብሎ ሊያርም ይነሳ ይሆናል::  ነገር ግን እርሱ ከሁሉ በፊት የኖረ የሁሉ መገኛ እንዲሁም እንደከበረ የሚኖር አልፋና ኦሜጋ ነው::እዚህ  በግ ላይ መንፈስ ከሰማይ እንደ ርግብ ሆኖ ሲወርድ አየሁ  በመንፈስ ቅዱስ የሚያጠምቅ እርሱ ነው አለኝ ብሎ አላበቃም የእግዚአብሔር ልጅ እንደ ሆነ መስክሬአለሁ አለን ዮሃንስ::  ይህ የእግዚአብሔር ልጅና በግ የሆነው እየሱስ እኛን ፍለጋ መጣ ዋጋንም ከፍሎ ዋጀን::  በምስጋና ላይ ምስጋና ይብዛልህ አሜን

ዮሐንስ 1: 36-42

36፤ ኢየሱስም ሲሄድ ተመልክቶ፦ “እነሆ የእግዚአብሔር በግ፡” አለ።37፤ ሁለቱም ደቀ መዛሙርት ሲናገር ሰምተው ኢየሱስን ተከተሉት።38፤ ኢየሱስም ዘወር ብሎ ሲከተሉትም አይቶ፦ “ምን ትፈልጋላችሁ?” አላቸው። እነርሱም፦ “ረቢ፥ ወዴት ትኖራለህ?” አሉት፤ ትርጓሜው፡ “መምህር ሆይ፡” ማለት ነው።39፤ “መጥታችሁ እዩ፡” አላቸው። መጥተው የሚኖርበትን አዩ፥ በዚያም ቀን በእርሱ ዘንድ ዋሉ፤ አሥር ሰዓት ያህል ነበረ።41፤ እርሱ አስቀድሞ የራሱን ወንድም ስምዖንን አገኘውና፦ “መሢሕን አግኝተናል” አለው፤ ትርጓሜውም “ክርስቶስ” ማለት ነው።መጥምቁ ዮሃንስ እየሱስን ባየው ቁጥር የሚጠራው የእግዚአብሔር በግ እያለ ነው::  ተከታዮቹም እየሱስን ሲከተሉ አልተቃወመም::  ሁልጊዜ የሚያመለክተው ወደ እየሱስ ነው::  የእኛም ህይወት ወደዚህ ጌታ የሚጠቁም መሆን አለበት::እየሱስ ሲከተሉት አይቶ ፦ “ምን ትፈልጋላችሁ?” አላቸው::  ለእኛም ዛሬ ጥያቄው ምን ትፈልጋላችሁ ነው::  ምንድነው የምንፈልገው?  እየሱስ እራሱን ወይስ ስጦታውን? ምቾትን? የዚህን ዓለም ብልጽግና ወዘተ::  መልስ እንስጥ::  እኛስ የተሰቀለውን እየሱስን እንሰብካለን አሜን::  የምድር ነገር ይዞ አያንገላታንም ዓይናችን በንጉሱ ላይ ይጽኑ::  እየሱስን ስንፈልገው ሌላው እኛን እየፈለገ ይመጣል::  አስቀድመን መንግስትና ጽድቁን እንፈልግ::  ጌታም ወዴት ትኖራለህ ሲሉት ወታችሁ እዩ አላቸው እነርሱም ከእሱ ጋር ዋሉ ይላል::  የጌታ መሆን ከጌታ ጋር መዋልን ይጠይቃል::  ጊዜያችን እንዳይባክን በፊቱ የምንሆንበትን ያብዛልን::እንድርያስ ወድያው ስራውን ጀመረ ሰውን ወደ እየሱስ ማምጣት የመጀመርያው ጴጥሮስ ነበረ መሲሁን አግኝተናል ብሎ ይዞት መጣ::  የቤተክርስቲያን መሪ የሆነውን ደቀ መዝሙር ጌታም ስሙንም ቀየረው::  ለእኛም መልእክቱ ከቤተሰባችን ጀምረን ዙሪያችን ላሉት ሁሉ ወንጌልን ማድረስ ነው::   መቀየርና ገንዘቡ ማድረግ ግን የጌታ ስራ ነው::  ጌታ ድፍረትንና ተደማጭነትን ይስጠን:: አሜን!

ዮሐንስ 1: 43-51

43፤ በነገው ኢየሱስ ወደ ገሊላ ሊወጣ ወደደ፥ ፊልጶስንም አገኘና፦ “ተከተለኝ፡” አለው።47፤ ኢየሱስ ናትናኤልን ወደ እርሱ ሲመጣ አይቶ ስለ እርሱ፦ “ተንኰል የሌለበት በእውነት የእስራኤል ሰው እነሆ፡” አለ።49፤ ናትናኤልም መልሶ፦ “መምህር ሆይ፥ አንተ የእግዚአብሔር ልጅ ነህ፤ አንተ የእስራኤል ንጉሥ ነህ፡” አለው።51፤ “እውነት እውነት እላችኋለሁ፥ ሰማይ ሲከፈት የእግዚአብሔርም መላእክት በሰው ልጅ ላይ ሲወጡና ሲወርዱ ታያላችሁ፡” አለው።በዝች አንድ ምዕራፍ ውስጥ ዮሃንስ ለእየሱስ ሰባት ስሞች እንደተሰጡት ያሳየናል:: 1. ዮሃንስ: የእግዚአብሔር በግ 2. የዮሃንስ ደቀመዛሙርት: መምህር (ቁ 38)3. እንድርያስ: መሲህ (ቁ 41)4. እንድርያስ: የናዝሬቱ እየሱስ (ቁ 45)5. እንድርያስ: የሰው (የዮሴፍ) ልጅ (ቁ 45)6. ናትናኤል: የእግዚአብሔር ልጅ (ቁ 49)7. ናትናኤል:  የእስራኤል ንጉስ  (ቁ 49)ጌታ እየሱስ ሶስተኛውን ደቀ መዝሙር ፊልጶስን ከቤተ ሳይዳ መረጠና ተከተለኝ አለው::  ጴጥሮስምና ወንድሙ እንድርያስም ከቤተሳይዳ ነበሩ::  እርሱም መከተል ብቻ ሳይሆን ስለእየሱስ መመስከር ጀመረ::ፊልጶስም የመሰከረው ለናትናኤል ነበረ::  ናትናኤል ግን የመለሰው የሚገርም ነው ከናዝሬት “ከናዝሬት መልካም ነገር ሊወጣ ይችላልን?” አለው። ፊልጶስ፦ “መጥተህ እይ፡” አለው። ስለየሱስ ሰዎች እራሳቸው መተው የሚያዩት ነው እኛ ማድረግ ያለብን ማመልከት እራሱን ግን የሚገልጥ እራሱ ነው::  ናትናኤል ብዙም ሳያምንበት ነበረ የመጣው ሲመጣ ግን የገጠመው ያልጠበቀው ነው ናትናኤል ብቻ ነው የሚያውቀው ከበለሱ በታች ምን እንደነበረ::  ስለዚህም ተነክቶ የእግዚአብሔር ልጅ ነህ ንጉስም ነህ አለው::  የናትናኤል ልብ ግን ደስ ይላል  ተንኮል የሌለበት እንደሆነ ጌታ መስክሯልና::  በዝችው የረካውን ናትናኤልን “ከዚህ የሚበልጥ ነገር ታያለህ፡” አለው።  የሚያየውም “እውነት እውነት እላችኋለሁ፥ ሰማይ ሲከፈት የእግዚአብሔርም መላእክት በሰው ልጅ ላይ ሲወጡና ሲወርዱ ታያላችሁ፡” አለው።አሜን የከበረ ተስፋ ያለን ነን ጌታ እራሱን ይግለጥልን::

ዮሐንስ 2: 1-12

1፤ በሦስተኛውም ቀን በገሊላ ቃና ሰርግ ነበረ፥ የኢየሱስም እናት በዚያ ነበረች፤3፤ የወይን ጠጅም ባለቀ ጊዜ የኢየሱስ እናት፦ “የወይን ጠጅ እኮ የላቸውም፡” አለችው።4፤ ኢየሱስም፦ “አንቺ ሴት፥ ከአንቺ ጋር ምን አለኝ? ጊዜዬ ገና አልደረሰም፡” አላት።5፤ እናቱም ለአገልጋዮቹ፦ “የሚላችሁን ሁሉ አድርጉ፡” አለቻቸው።7፤ ኢየሱስም፦ “ጋኖቹን ውኃ ሙሉአቸው፡” አላቸው። እስከ አፋቸውም ሞሉአቸው።8፤ “አሁን ቀድታችሁ ለአሳዳሪው ስጡት፡” አላቸው፤ ሰጡትም።ኢየሱስ ይህን የምልክቶች መጀመሪያ በገሊላ ቃና አደረገ፤ ክብሩንም ገለጠ፥ ደቀ መዛሙርቱም በእርሱ አመኑ።  ይህ ሰርግ የገጠመው ችግር በዘመኑ በጣም አሳፋሪ የሆነ ነገር ነው::  እንደው የምታደርገውን ነገር ብታጣነው ማርያም ወደ እርሱ የመጣችው::  ይህ መቼም ለእርስዋ የመጀመርያ ነው ብዬ ባይፃፍም ለማመን ይቸግረኛል::  ብትለማመደው ነው ችግሩን ነግራው ብቻ የሄደችው ከተፈጸመም በኃላ አሳላፊው ከየት እንደመጣ አላወቀም የመሰከረው ግን እነሱ የለፉበትን መናኛ ጌታ የፈጠረውን ግን ምርጥ አለው ባይገባውም እንኳን::  ባህርይዋም ስለእርሱ ሲነገር በልብዋ ትጠብቀው ነበረ ነው የሚለን ቃሉ እንጂ እወቁኝ እወቁኝ የምትልም አይደለችም::  አስቸጋሪ ነገር ስለሆነባት ወይን አልቆባቸዋል እንጂ ያለችው ምን ማድረግ እንዳለበት አልነገረችውም::  ከዛም በመቀጠል የሚላችሁን አድርጉ ወይም አንዳች ጥያቄ አትጠይቁ ምክንያቱም የሚያደርገው ነገር ከተፈጥሮ አሰራር ውጪ እንደሆነ ተረድታለችና::  የእኛ የጸሎት ርእስ እንዴት ነው?  እንዴት እንደሚያደርገው ሁሉ የሱን ስራ ለማቅለል ይመስል መመሪያ ያለው ነው::  የታመነ ሰው ልመና ግን ለየት ይላል ነገሩን ማሳየትና ቻሌንጅ ሲመጣም ቆሞ መጠበቅ ነው::  ይህን እንደዚህ ወይም እንደዛ አድርግ አይባልም እርሱ ፈጣሪ ነው::ሰዎቹም ይገርማሉ ውሃ ሙሏቸው ጋሎኖቹን ሲባሉ እሺ ብለው ሞሉ መቼም የተዋጠላቸው አይመስለኝም::  አሁን ይባስ አትሉም ቀድታችሁ ስጡ!  ምን?!! አሁን አይደል እንዴ ውሃውን የሞላንበት?! የጌታ አሰራር ይገርማል ዛሬም አልደከመም አልተቀየረምም!!  ልመናችንን በፊቱ ከምስጋና ጋር እናስታውቅ እንጂ በአንዳች አንጨነቅ እርሱ መልስን ሲመልስ ነገሩ ቀላል ነው ለእኛ የሚቀረው ውሃውን መቅዳት ብቻ ይሆናል::  ስናስበው ይህንን ወይን ለሰርጉ ለመጥመቅ ስንት ጊዜ ጉልበትና ገንዘብ አፍሰው ይሆን?  ለዛውም እንደዚህ አንሶ ሊያሳፍራቸውና መናኛ ተብሎ ሊፈረጅ::  ለጌታ ግን የደቂቃዎች ጉዳይ ነው አትረፍርፎና አሳምሮ ለመስጠት:: አሜን!አባት ሆይ አንተ የታመንክ አምላክ ነህ ዛሬም ክንድህ አልደከመም ትሰራለህ!!  በአንተ እታመናለሁ ይህ ጎደለ ብቻ ማለት ሲገባኝ እንዴት እንድታደርገው በነገርኩህ ይቅር በለኝ::  አባቴ ሆይ ተ መ ስ ገ ን!!  አሜን!

ዮሐንስ 2: 13-25

13፤ የአይሁድ ፋሲካም ቀርቦ ነበር፥ ኢየሱስም ወደ ኢየሩሳሌም ወጣ።14፤ በመቅደስም በሬዎችንና በጎችን ርግቦችንም የሚሸጡትን ገንዘብ ለዋጮችንም ተቀምጠው አገኘ፤16፤ ርግብ ሻጪዎችንም፦ “ይህን ከዚህ ውሰዱ፤ የአባቴን ቤት የንግድ ቤት አታድርጉት፡” አላቸው።19፤ ኢየሱስም መልሶ፦ “ይህን ቤተ መቅደስ አፍርሱት፥ በሦስት ቀንም አነሣዋለሁ፡” አላቸው።ይህ የፋሲካ በዓል ለ7 ቀን የሚከበር ከግብጽ የወጡበትን ድንቅ የሚያስቡበትና ወንዶች ሁሉ በእግዚአብሔር ፊት የሚታዩበት ነው::  በግብጽ ምድር ቀሳፊው ሲያልፍ የሚያየው የበጉን ምልክት ነበረ ነገር ግን ማንም ከቤቱ ውጪ ቢገኝ በራሱ ላይ ነበረ እግዚአብሔር አይጠየቅም::  ዘጸአት 12:27፤ እናንተ፦ ‘በግብፅ አገር በእስራኤል ልጆች ቤቶች ላይ አልፎ ግብፃዊያንን በመታ ጊዜ፥ ቤቶቻችንን ያዳነ የእግዚአብሔር የማለፉ መሥዋዕት ይህች ናት፡’ ትሉአቸዋላችሁ።” ሕዝቡም ተጎነበሰ ሰገደም።ይህንንም በዓል ማክበር ቀጠሉ ለልጆቻቸውም አስተላለፉ::  በዓሉ ግን ለሚመጣው እውነተኛ በግ ስፍራውን የሚለቅ ጥላ ሆኖ ሳለ እነርሱግን አላወቁትም::በዓሉ በደረሰ ጊዜ ነው ወደ እየሩሳሌም የወጣው ሰው ሁሉ ያንን በግ እየፈለገ ነው ለበዓሉ::  የእግዚአብሔር በግ ግን በመካከላቸው ቆሞ ነበረ!   ወይ መተላለፍ!  የቤትህ ቅናት ይበላኛል ብሎ እነዚህን ነጋዴዎች እየገረፈ አባረረ::  ማንም ቆሞ ንብረቱ ሲወድም ወፎቹንም ሲለቅ ገበታውንም ሲገለባብጥ አንድ ሰው ነው ተሰብስበው እንኳን ሊመጡበት አልቻሉም::  አምላካዊ ቁጣ መሆን አለበት::  ዮሃንስ ይህንን የዘገበው ገና አገልግሎት ሲጀምር የመጀመርያው ቤቱን ማፅዳት እንደሆነ ሲሆን ሎሌቹ ግን የዘገቡት በስተመጨረሻ ነው ከአንድ ጊዜ በላይ አድርጎት ይሆን? አንድ ጥያቄ አይሁድ ጠየቁት፦ “ይህን ስለምታደርግ ምን ምልክት ታሳየናለህ?” አሉት። የምን ምልክት ነው የሚፈልጉት መሆን የሌለበትን ነገር ስላስወጣ? እርሱ ግን ይህን ቤተ መቅደስ አፍርሱት፥ በሦስት ቀንም አነሣዋለሁ፡” አላቸው።  የፈጀው እኮ 46 ዓመት ነው እንዴት በ3 ቀን ታነሳዋለህ ብለው በዓለቱ እንደገና ተደናቀፉበት::  እርሱ ግን ስለትንሳኤው ተናገረ::ዛሬም ጌታ ይናገራል መንፈስ ቅዱስ ያብራልን እኛም ስንስት እንዳንገኝ::  ውስጣችን ነው የጌታ መቅደስ ኮተት ሞልቶት እንዳይሆንም እናጽዳው::  ቤቱ የፀሎት ቤት ነው::  በቃሉና በመንፈሱ ነው ሊሞላ የሚገባው::አባት ሆይ እየኝ ፈትሸኝ የዓለምን አመለካከት ከቃልህ በላይ በውስጤ አከማችቼ እንዳይሆን መርምረኝ የልቤንም ጉርጆ አገላብጠው ይቅርም በለኝ ከንቱ የሆነውን ሁሉ ከእኔ አውጣውና በመንፈስህና በቃልህ ሙላኝ::  መራራ ስር በእኔ እንዳያድግ  ንቀልልኝ!  እየኝ አባ:  ማረኝም በእየሱስ ደም እጠበኝ!  አሜን!

ዮሐንስ 3: 1-31፤ ከፈሪሳውያንም ወገን የአይሁድ አለቃ የሆነ ኒቆዲሞስ የሚባል አንድ ሰው ነበረ፤2፤ እርሱም በሌሊት ወደ ኢየሱስ መጥቶ፦ “መምህር ሆይ፥ እግዚአብሔር ከእርሱ ጋር ከሆነ በቀር አንተ የምታደርጋቸውን እነዚህን ምልክቶች ሊያደርግ የሚችል የለምና፡ መምህር ሆነህ ከእግዚአብሔር ዘንድ እንደ መጣህ እናውቃለን፡” አለው።3፤ ኢየሱስም መልሶ፦ “እውነት እውነት እልሃለሁ፥ ሰው ዳግመኛ ካልተወለደ በቀር የእግዚአብሔርን መንግሥት ሊያይ አይችልም፡” አለው።ይህ ሰው ፈሪሳዊ እንደዚሁም  የአይሁድ አለቃ ነው::  ከእየሱስ ጋር በግል ጊዜ ለማሳለፍና ጥያቄ ለመጠየቅ ነው የመጣው::  ፈሪሳውያን ለእግዚአብሔር የቀኑ ሰውን ሁሉ የሚያስጨንቁ በተለያየ እራሳቸው ባመጡት ህግ የተተበተቡ ናቸው::  ምክንያታቸውም እስራኤል እግዚአብሔርን እያሳዘነ ነው ለምርኮ ተላልፎ የሚሰጠው ስለዚህ ሁሉምያለ ኃጥያት መኖር አለበት የሚሉ እስራኤል ከስደት ሲመለሱ የተፈጠሩ ግሩፖች ናቸው::  በብሉይ ኪዳን ላይ አናያቸውም::ኒቆዲሞስ ግን ለየሱስ ያለው ነገር እግዚአብሔር ከአንተ ጋር ነው እንጂ ያለበለዚያ እንዴት ይህንን ሁሉ ተአምራት ማድረግ ትችላለህ?  ይህ ተአምር  የማድረጉ ጉዳይ ነው ወደ እየሱስ ያመጣው::  ምዕራፍ ሁለትን ሲዘጋ ዮሃንስ ያለን ነገር ቢኖር ዮሐንስ 2:23፤ በፋሲካ በዓልም በኢየሩሳሌም ሳለ፥ ያደረገውን ምልክት ባዩ ጊዜ ብዙ ሰዎች በስሙ አመኑ፤ 24-25፤ ነገር ግን ኢየሱስ ሰዎችን ሁሉ ያውቅ ነበር፤ ስለ ሰውም ማንም ሊመሰክር አያስፈልገውም ነበርና አይተማመናቸውም ነበር፤ ራሱ በሰው ያለውን ያውቅ ነበርና። ብዙዎች አመኑበት ተአምራትን ስላደረገ ምንም እንኳን ተአምራቶቹን ዮሃንስ ባይዘግበውም::  እነዚህ ተአምራት የሳቡት የነኒቆዲሞስንም ቀልብ ነው::  እየሱስ ግን አይተማመንባቸውም ነበር ምክንያቱም በመስቀል ላይ ብቻውን እንደሚሆንና ስቀለው ስቀለው የሚሉ እንደሚሆኑ ያውቃል::  የጊዜውን ተአምር ግን አግኝተው ወደ ቤታቸው ተመልሰዋል::እየሱስን የምንከተለው ይህንና ያንን አድርግልን ለማለት ለምድር ነገር ከሆነ እናሳዝናለን::  እርሱ የዘላለምን ህይወት ሊሰጠን መጣ ከጥፋት ሊያድነን በደሙ ገዛን::  እኛ የእርሱ ነን በከፍታም በዝቅታም ጌታ ጌታ ነው በህይወታችን::  እንድናስተውል ይርዳን::  አሜን!

ዮሐንስ 3: 3-8

3፤ ኢየሱስም መልሶ፦ “እውነት እውነት እልሃለሁ፥ ሰው ዳግመኛ ካልተወለደ በቀር የእግዚአብሔርን መንግሥት ሊያይ አይችልም፡” አለው።4፤ ኒቆዲሞስም፦ “ሰው ከሸመገለ በኋላ እንዴት ሊወለድ ይችላል? ሁለተኛ ወደ እናቱ ማኅፀን ገብቶ ይወለድ ዘንድ ይችላልን?” አለው።5፤ ኢየሱስም መለሰ፥ እንዲህ ሲል፦ “እውነት እውነት እልሃለሁ፥ ሰው ከውኃና ከመንፈስ ካልተወለደ በቀር ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ሊገባ አይችልም።6፤ ከሥጋ የተወለደ ሥጋ ነው፥ ከመንፈስም የተወለደ መንፈስ ነው።7፤ ‘ዳግመኛ ልትወለዱ ያስፈልጋችኋል’ ስላልሁህ አታድንቅ።8፤ ነፋስ ወደሚወደው ይነፍሳል፥ ድምፁንም ትሰማለህ፥ ነገር ግን ከወዴት እንደ መጣ ወዴትም እንዲሄድ አታውቅም፤ ከመንፈስ የተወለደ ሁሉ እንዲሁ ነው።”ኒቆዲሞስ ስለእግዚአብሔር አብሮነት ለእየሱስ መሰከረ:: እየሱስ ግን ልክ ነህ አንተ ልባም ወይም እንደዚህ አይነት ነገር አይደለም ያለው ዳግመኛ ተወለድ ብሎ ነው የነገረው::  ኒቆዲሞስ የሚያወራው ሌላ እየሱስ የሚያወራው ሌላ!  ማስተዋል ይስጠን ጉድለታችንን አይቶ ሲናገር የነቃ መንፈስ ይስጠን::  የእስራኤል መምህር የተባለው ሰው ጭራሽ ግራ ገባው ዳግም ስለመወለድና እንደገና እናቴ ማህፀን ልመለስ ነው?  ብሎ ጠየቀ::  እርሱ የሚያውቀው መወለድ ይኼኛው ብቻ ነውና::  ስለአዲስ መወለድ በመንፈስ ስለመወለድ ምንም አያውቅም::  ምናልባትም ከማውቀው እውቀት ምን የተለየ ይነግረኛል ብሎ ይሆናል የመጣው::  ነገር ግን የማያውቀው እውቀት ተገናኘው::እየሱስ ያስረዳው ጀመረ እውነት እውነት እልሃለሁ፥  ሰው ከውኃና ከመንፈስ ካልተወለደ በቀር ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ሊገባ አይችልም። ከሥጋ የተወለደ ሥጋ ነው፥ ከመንፈስም የተወለደ መንፈስ ነው።ዳግመኛ ልትወለዱ ያስፈልጋችኋል’ ስላልሁህ አታድንቅ። ይህ ሰው የሚያውቀው አንድ አይነት መወለድ ነው እርሱም  ወደዚህ ዓለም መምጫውን እንጂ ወደ እግዚአብሔር መንግስት መግቢያውን አይደለም::  ግራ ግብት ብሎ ከብዶታል ለዚህም ነው ጌታ አታድንቅ የሚለው::  ዳግም መወለድ ልክ ንስር እራስዋን እንደምታድሰው ለብቻዋ ሄዳ ጥፍርዋን መብያ አፍዋን ሁሉ እያደቀቀች ከላይዋ በወራት ውስጥ እንደምታራግፈው አይነት ቢሆን ሳይቀለው አይቀርም::  ዛሬም ሰዎች ይህ ነው የሚከብዳቸው ስራ ቢኖረው ግን ሁሉ ሮጦ አድርጎት ነበረ::   ለተቀበሉት ግን በስሙ ለሚያምኑት ለእነርሱ የልጅነት ስልጣንን ሰጣቸው ከእግዚአብሔር ተወልደዋል::  አጭርና ግልጽ!!!  ስሙ ይባረክ ደካሞችን ያሰበና በስብከት ሞኝነት በማመን መዳንን ያደረገው ጌታ ስሙ ይባረክ::ለዚህ አእምሮ አይመችም ጌታም እንዳለው ነፋስ ወደሚወደው ይነፍሳል፥ ድምፁንም ትሰማለህ፥ ነገር ግን ከወዴት እንደ መጣ ወዴትም እንዲሄድ አታውቅም፤ ከመንፈስ የተወለደ ሁሉ እንዲሁ ነው። አሜን!  ስራው በእኛ ላይ ተሰርቶ ተለውጠን እራሳችንን አግኝተናል::  እንዴት ቢባውል ከየት ወዴት እንደነፈሰ የማናውቀው ያ የእግዚአብሔር መንፈስ ወለደንና ለወጠን!!  ክብር ይሁንለት!  አሜን

ዮሐንስ 3: 9-13

9፤ ኒቆዲሞስ መልሶ፦ “ይህ እንዴት ሊሆን ይችላል?” አለው።10፤ ኢየሱስም መልሶ እንዲህ አለው፦ “አንተ የእስራኤል መምህር ስትሆን ይህን አታውቅምን?11፤ እውነት እውነት እልሃለሁ፥ የምናውቀውን እንናገራለን ያየነውንም እንመሰክራለን፥ ምስክራችንንም አትቀበሉትም።12፤ ስለ ምድራዊ ነገር በነገርኋችሁ ጊዜ ካላመናችሁ፥ ስለ ሰማያዊ ነገር ብነግራችሁ እንዴት ታምናላችሁ?13፤ ከሰማይም ከወረደ በቀር ወደ ሰማይ የወጣ ማንም የለም፥ እርሱም በሰማይ የሚኖረው የሰው ልጅ ነው።እንደዚህ እያስረዳውም ኒቆዲሞስ ሊገባው አልቻለም  የዳግም መወለድ ሚስጥር: :  ጌታም አንተ የእስራኤል መምህር ስትሆን ይህን አታውቅምን? ይህ ሰው የአይሁድ ሁሉ አለቃና መምህር ነው ከመምህራን አንዱ ሳይሆን ዋናው ነው ማወቅ ነበረበት::  ጌታ  በቃሉ ላይ ያለውን ሊፈጽም መጣ እንጂ ዱብ እዳ አይደለም የሆነው ቀድሞ በነብያቱ ተነግሯል::  እንደሚመጣ እየተጠባበቁት ነበር ነገር ግን ተሸዋወዱ ዮሃንስ መጥምቁ  እንዳለው እናንተ የማታውቁት በመካከላችሁ ቆሟል አላቸው ግን አላወቁትም!  ግንበኞች የናቁት የማዕዘን ራስ እየሱስ!!ይህ ዋና የእስራኤል መምህር ሕዝቅኤል 36:26፤ አዲስም ልብ እሰጣችኋለሁ አዲስም መንፈስ በውስጣችሁ አኖራለሁ፤ የድንጋዩንም ልብ ከሥጋችሁ አወጣለሁ፤ የሥጋንም ልብ እሰጣችኋለሁ። የሚለውን አንብቧል ግን አልገባውም እፊቱ የእግዚአብሔር በግ ቆሞ በብዙ የዮሐንስ ምስክር እየፀና አዋቂ ነን የሚሉት ግን በእውቀት ተኮፍሰው ከእኛ ምን ያመልጣል ብለው ተላለፉ::  ጌታ ይጠብቅ በዝች ትንሽ ጭንቅላታችን ይህንን ፈጣሪ ለማወቅ መነሳት የማይሆን ነው በመንፈሱ ግንማንነቱን ይገልጥልናል::ይህ ከሰማይ የመጣው ጌታ እውነት እውነት እልሃለሁ፥ የምናውቀውን እንናገራለን ያየነውንም እንመሰክራለን፥ ምስክራችንንም አትቀበሉትም። እርሱ የሚለንን እንስማ!  ስለ ምድራዊ ነገር በነገርኋችሁ ጊዜ ካላመናችሁ፥ ስለ ሰማያዊ ነገር ብነግራችሁ እንዴት ታምናላችሁ? መንፈስ ቅዱስ ነው አስተማሪው ስለምናውቅ አንናገር ይህ የከበረ ህያው የሆነ ቃል ነው::  እርሱ  ሲያስተምረን እንደነቃለን:: ይህ ንጉስ ክብሩን ገለጠልን ማንም ከምድር ወደ ሰማይ የሄደ የለምና እርሱ ግን ሁሉን ነገረን::  የመንፈስ ነገር በመንፈስ ይታወቃል አሁንም ጳውሎስ የፀለየውን እንፀልይ:- እርሱን በማወቅና በመገለጥ መንፈስ ይሙላን:: አሜን!!  ለመማርም የቀናን በትህትና የምንመላለስና ዝቅ ያለ መንፈስን ይዘን ወደፊቱ እንቅረብ::  ለትሁታን ፀጋን ይሰጣል::  አሜን  አባት ሆይ እርዳን! 

ዮሐንስ 3: 8-9 ይህንን ክፍል እንደገና እንድናተኩርበት በሚል ደግሜዋለሁ::  ጌታ እየሱስ የሚናገረው ስለሰማያዊዉ አሰራር ኒቆዲሞስ የሚያወራው ስለምድራዊዉ::  በዚህ ምክንያት ተላለፉ::  ኒቆዲሞስ እውቀት አላነሰውም መጽሐፍትን ጥጥት አድርጎ ነው ያጠናውና የሚያውቀው::  ያው የጭንቅላት እውቀት ማለት ነው:: ጌታ የሚለው ነፋስ ወደሚወደው ይነፍሳል፥ ድምፁንም ትሰማለህ፥ ነገር ግን ከወዴት እንደ መጣ ወዴትም እንዲሄድ አታውቅም፤ ከመንፈስ የተወለደ ሁሉ እንዲሁ ነው።” ሲለውኒቆዲሞስ ደግሞ የሚለው፦ “ይህ እንዴት ሊሆን ይችላል?” አለው።የመንፈስ አሰራር ሊገባን ይገባል አለበለዚያ ግን ጸሎታችን ሁሉ እንዴት ይሆናል በሚል ልባችን ተሞልቶ አፋችን ግን እየለመነ ይሆናል: ያለማመን ጠንቅ! ውስጣችንና አንደበታችን በአንድ አሳብ ይስማማ::  ይህ እንዲሆን የመንፈስ እርዳታ ያስፈልገናል::  ማነኝ ሲል አንተ የእግዚአብሔር ልጅ ነህ ብሎ መመለስ የሚቻለው  በመንፈስ ብቻ ነው::ባጭሩ በጌታ ፊት እንጸልይ ዛሬን እራሳችንን በፊቱ እናቅርብ በመንፈሱ ማንነቱን ያሳውቀን ቃሉንም ያብራልን! አባት ሆይ እራሳችንን በፊትህ ለማሳየት መተናል ሩጫችን በስጋ ይሆን? መርምረን ያለ አንተ አንዳች ማድረግ አንችልም የምንለው በአፋችን ብቻ ይሆንን?  መርምረን::  አንተን በማወቅና በመገለጥ ሙላን አለዚያ የማያምን ጠማማ ትውልድ እንዳንሆን አስበን:: በፊትህ ዛሬ የመንፈስ ቅዱስ እርዳታ በዳከርንበት ላይ ሁሉ ይምጣና ያብራልን::  መገለጥ ያስፈልገናል ጌታዬ ሆይ::  የሰው ልጅ ሲመጣ እምነትን ያገኝ ይሆንን ነበረ ጥያቄህ::  አባት ሆይ ዛሬ እርዳን እምነት ከመስማት ነውና የምንሰማውን ይህንን የምትሰጠንን ቃል አብራልን በመንፈስ እንረዳውና ከእኛ ጋር ይዋሃድ::  በእየሱስ ስም አሜን!

ዮሐንስ 3: 14-15

14-15፤ ሙሴም በምድረ በዳ እባብን እንደ ሰቀለ እንዲሁ በእርሱ የሚያምን ሁሉ የዘላለም ሕይወት እንዲኖረው እንጂ እንዳይጠፋ የሰው ልጅ ይሰቀል ይገባዋል።ጌታ እንዳለው ስለምድራዊው ነገር ስናገር ካልገባህ እንዴት ሰማያዊዉን ልንገርህ?  በንፋስ ሊያስረዳው ሞከረ ብዙም አልገባውም ስለዚህ ይህንን ታሪክ ይነግረው ጀመረ ከራሱ ጋር እያያያዘ::  ከላይ የተናገረው ካልገባው የበለጠ የሚገርመው የመንፈስ አሰራር በዚህ የናስ እባብ ላይ ታይቷል::  እንደው ስለተፃፈ ነበብ አድርገን ባናልፈው መልካም ነው ቆም ብለን የሆነውን እናስብ::  የሆነው ነገር እስራኤል በእግዚአብሔር ላይ እንጎራጉሮ እባቦች መተው ነደፏቸው::    ድሮም የጌታ ጥበቃ ነው እንጂ እኮ እባቦቹማ ነበሩ ወይም ሄዳችሁ ይህንን ህዝብ ንደፉ ብሎ  ለዚሁ ጥፋት የፈጠራቸው አይመስለኝም::  የሆነ ሆኖ እባቦቹ ህዝቡን ነድፈዋል::  ስለዚህ የህዝቡ ስቃይ ሲያሳዝነው ሙሴን የክፉ ምሳሌ የሆነውን እባብ ከብር ሰርተህ ስቀለው ተባለ::  የተሰቀለው አንድ እባብ ብቻ ሰውን የነደፉት ግን ብዙ እባቦች ለምን ታድያ ለእያንዳንዱ አንድ አልተሰቀለም?  ይህ ሰውኛ አሰራር ነው መንፈስ ለሆነው ለጌታ ግን አንዱ በቂ ነበር::  እየተሰቃየ ያለው ሰው የሚጠበቅበት ካለበት እሩቅም ይሁን ቅርብ የተሰቀለውን እባብ ማየት ብቻ ነው የነደፈው እባብ እንደተሰቀለ ሲያይ መርዙ በእርሱ ላይ ጉልበት ያጣል እናም ነፃ ይሆናል::  የነደፈኝ እባብ ተሰቀለ ብሎ ማየት እንዴት ያድናል ሄዶ መተሻሸት ወይም ቁስሉን ቢነካልኝ እንደዛና እንደዚህ ባደርግ ለአእምሮ ይመች ነበር::  ነገር ግን ጌታ በማየትና በማመን አደረገው አለበለዚያማ እየሱስ በየጊዜው እንድንነካውና እንድንድን እየተመላለሰ መሰቀል ሊኖርበት ነበረ::   ከሁሉም በላይ እየሱስ መቶ በሁላችን ውስጥ ያለውን የእባቡን መርዝ አንድ ጊዜ ተሰቅሎ ባመነው ጊዜ ነቅሎታል ::  ብሉይ ኪዳን የአዲስ ኪዳን ጥላው አይደለምን?  ይህ የአይሁድ መምህር ግን የገባውም አይመስለኝም ተአምራትን እዩ አባቶቻችን ብሎ አልፎት ይሆናል እንጂ አዲስ ልብ የሚሰጠው የድንጋዩ ልብ የሚወጣው እንደ እባቡ ምሳሌ የሰው ልጅ የሆነው እየሱስ ተሰቅሎ ነው ብሎ ያገናዘበው አይመስልም::  ለእኛም ይህ የእግዚአብሔር መንፈስ ቃሎቹን እያገናኘ ሙሉ ስእሉን ይስጠን:: መቼም  አሁንም ቢሆን ለኒቆዲሞስ ከባድ ነው ተፅፎ አነበበው እንጂ አልተለማመደውምና::  እኛ ግን ተለማምደነዋል በስብከት ሞኝነት አምነነው ከዚህ እባብ ነፃ ሆንን አዲስ ፍጥረት የእግዚአብሔር ወገን ለርስቱ የተለየን ካህናቱ አደረገን:: በእርሱ በማመን የዘላለም ህይወትን አግኝተናል!!  አሜን!!!  እኛም ዛሬ ወደተሰቀለው እየስስ የምናሳይ ቀስት ሆነናል በዚህ ሞኝነት ውስጥ ሕይወትን ማግኘት:: አባት ሆይ ተመስገን አሰራርህ ድንቅነው ዛሬም በአንተ ላይ እንታመናለን በህይወታችን ያልከው ሁሉ ይሁን::  አሜን!

ዮሐንስ 3:16-18

16፤ በእርሱ የሚያምን ሁሉ የዘላለም ሕይወት እንዲኖረው እንጂ እንዳይጠፋ እግዚአብሔር አንድያ ልጁን እስኪሰጥ ድረስ ዓለሙን እንዲሁ ወዶአልና።17፤ ዓለም በልጁ እንዲድን ነው እንጂ፥ በዓለም እንዲፈርድ እግዚአብሔር ወደ ዓለም አልላከውምና።18፤ በእርሱ በሚያምን አይፈረድበትም፤ በማያምን ግን በአንዱ በእግዚአብሔር ልጅ ስም ስላላመነ አሁን ተፈርዶበታል።በእርሱ ለሚያምን ሁሉ የተደረገለት:-1.  ልጅ መሆን2.  የዘላለም ህይወት ማግኘት4.  አለመጥፋትና3.  ከፍርድ ማምለጥ (አይፈረድብንም)ቀላል ይመስላል የሆነው ነገር ስናድግም ስንሰማው ስለሆነ መደነቃችንን ሳይቀንሰውአልቀረም::  ዓለምን አብ የወደደው እንዲያው ነው እንጂ እንደው ይሄ ነገሩ ተብሎ የሰው ልጅ የሚወደድበት ነገርም የለውም መልካም ብለን የምናደርገው እንኳን እንደመርገም ጨርቅ ነው::  አብ ወደደንና ልጁን ላከልን ሲልከውም ብዙ ክፉ ታያለህ አትፍረድባቸው ግን ሞተህ የዘላለምን ይህወት ስጥ ተባለ::  ሃሌሉያ!!  በምድር ሲመላለስ ስለሰው ሊነገረው የማይፈልግ ጌታ ያችንም ሴት ከሞት አዳናት  ሐጥያት ያላደረገ ይውገራት ብሎ እርሱም በመጨረሻ አልፈርድብሽም ደግመሽ ኃጥያትን አታድርጊ አላት:: እሱን ያላወቀች ነፍስ ግን አሁን በፍርድ ውስጥ አለች::  ፍርድ አሁን አይደለም የፍርድ ጊዜ ይመጣል ሰው እንደማገዶ ወደ እሳት የሚጣልበት ጊዜስለዚህ እንመስክር::   ወንጌልን እንድናደርስ የተጠራን ነንና በእግዚአብሔር ቁጣ ስር መገኘት እንዴት ከባድ ነው?  እንራራላቸውና እንመስክር እንፀልይ!!ጌታ ሆይ እርዳን!

ዮሐንስ 3: 19-21

19፤ ብርሃንም ወደ ዓለም ስለ መጣ ሰዎችም ሥራቸው ክፉ ነበርና ከብርሃን ይልቅ ጨለማን ስለ ወደዱ ፍርዱ ይህ ነው።20፤ ክፉ የሚያደርግ ሁሉ ብርሃንን ይጠላልና፥ ሥራውም እንዳይገለጥ ወደ ብርሃን አይመጣም፤21፤ እውነትን የሚያደርግ ግን ሥራው በእግዚአብሔር ተደርጎ እንደ ሆነ ይገለጥ ዘንድ ወደ ብርሃን ይመጣል።”ይህ የዓለም ብርሃን ለእኛ ደግሞ የህይወት ብርሃን ከጨለማው ስልጣን እንደወደደ ሲያሽከረክረን ከነበረው ሊታደገን መጣ እርሱ ባይመጣና ባያወጣን በራሳችን አንድም ማድረግ አንችልም ነበረ::  ይህ ጌታ መቶም አልፈረደብንም ነገር ግን ህይወትን ሰጠን ይህም ህይወት የሰው ብርሃን ነው::  ደግሞም ጨለማ ብርሃንን አሸንፎ አያውቅም::  ዮሐንስ 1:4፤ በእርሱ ሕይወት ነበረች፥ ሕይወትም የሰው ብርሃን ነበረች።5፤ ብርሃንም በጨለማ ይበራል፥ ጨለማም አላሸነፈውም። አሜን!ሰው ስራው ክፉ ስለሆነ ወደዚህ ህይወት ወደሆነው ብርሃን መምጣትና ስራውን ማስመርመር አልፈለገም:: ክፉ ጨለማን ተገን አድርጎ ይሰራል እኛ ግን የብርሃን ልጆች ነን በብርሃን እንመላለሳለን የአምላካችንንም ስራ እንሰራለን:: ይህንን ህይወት ለሰጠን ብርሃኑን ላበራልን አዳኝ ክብር ይሁን::  ከጨለማ ጋር አልተባበርም በብርሃን እመላለሳለሁ::

ዮሐንስ 3: 22-30

27፤ ዮሐንስ መለሰ፥ እንዲህ ሲል፦ “ከሰማይ ካልተሰጠው ሰው እንዳች ሊቀበል አይችልም።ዮሐንስ 3:30፤ እርሱ ሊልቅ እኔ ግን ላንስ ያስፈልጋል።ዮሃንስ ስለራሱ ሲናገር እኔ ሚዜ እንጂ ሙሽራ አይደለሁም አለ::  ምንም አይነት ትኩረት አይስብም ስራውን ያውቆ ነበረ::  ወደ ከበረው ጌታ ብቻ መጠቆም ነበረ ስራው::  አገልግሎትህን ቀማህ ሰው ሁሉ ወደ እርሱ እየሄደ ነው ቢሉትም  እናንተ ምስክር ናችሁ እኔ እርሱ አይደለሁም ብያለሁኝ እያለ እማኝ ይጠራል::  ምን አይነት ትኩረት ነው ያለው ለተሰጠው አገልግሎት?  ቅናት በአገልግሎት ውስጥ መታየት የለበትም እህቴ በርቺ ወንድሜ በርታ  ተባብለን ንጉሱን በይህወታችን ማክበር ነው ያለብን::ስለዚህም “ከሰማይ ካልተሰጠው ሰው እንዳች ሊቀበል አይችልም።” ይህ ቃል በጣም ነው የነካኝ በዚህ ማለዳ:: አንብቤው ብቻ ማለፍ አልቻልኩም የጌታ መንፈስ በኃይል በላዬ ይመጣል:  እናንተንም ጌታ በመንፈሱ ይጎብኛችሁ::  ምን ተቀብለናል ከሰማይ?!  ከሰማይ የተቀበልነው እኮ እርሱን ልናገንበትና ልናሳይበት ነው::  አንዱም ለእኛ አልተሰጠም ለእርሱ ክብር ነው::  ሃሌሉያ!ይህ ጌታ በልግስና መንፈሱን በየዕለቱ ያፈሳል ደግሞም በለመለመ መስክ ያሳድረኛል፤ በዕረፍት ውኃ ዘንድ ይመራኛል። ነፍሴን መለሳት፥ ስለ ስሙም በጽድቅ መንገድ መራኝ። መዝሙር 23:2-3  አሜን!!!አባት ሆይ አንተ ከሰማይ የሰጠኸንን ለክብርህ እናውለው ::  ማስተዋልን ስጠን እርዳን!! አንተ ልትልቅ ይገባሃልና ልቀህ ታይ!

ዮሐንስ 3:31-33

31፤ ከላይ የሚመጣው ከሁሉ በላይ ነው፤ ከምድር የሚሆነው የምድር ነው የምድሩንም ይናገራል። ከሰማይ የሚመጣው ከሁሉ በላይ ነው።32፤ ያየውንና የሰማውንም ይህን ይመሰክራል፥ ምስክሩንም የሚቀበለው የለም።33፤ ምስክሩን የተቀበለ እግዚአብሔር እውነተኛ እንደ ሆነ አተመ።ወንጌላዊው ዮሃንስ እየሱስን ማሳየት የሚፈልገው ከላይ የመጣ አምላክ መሆኑን ነው::  መጥምቁ ዮሃንስ እየሱስን የእግዚአብሔር በግ እንዲሁም ሙሽራ እያለ ይጠራዋል:: ከላይ የመጣው እግዚአብሔር ነው አምላክነቱን እወቁ እያለ ነው::  ከሰማይ የሚመጣው ከሁሉ በላይ ነው ብሎ አወጀ። አሜን!እርሱም በላይ ያየውንና የሰማውን ተናገረ ያስተዋለ ወይም የተቀበለ ግን የለም::  ብዙዎች ያጋፉት ነበረ የዕለት ጥቅም ፍለጋ ፤  እንጀራን ፍለጋ ፤ ፈውስን ፍለጋ::  ያወቁት ደግሞ ጥቂቶች ያላቸውን ሁሉ ትተው ተከተሉት::  ምስክርነቱ እውነተኛ ነው ምስክሩን የተቀበለ እግዚአብሔር እውነተኛ እንደ ሆነ አተመ!  ይህንን እውነት ያመንን አምላካችን እውነተኛ ነው ብለን አውጀናል! አሜን አትመናል!!  ጌታችን እውነተኛ ነው መዳናችንም እውነት ነው ልጅ መሆናችንም እውነት ነው::አባት ሆይ ክብርንና ምስጋናን ወደ አንተ አመጣለሁ እውነተኛ እንደሆንክና እኛም በአንተ እንደተነካን እንመሰክራለን!  አሜን!

ዮሐንስ 3: 34-36

34፤ እግዚአብሔር የላከው የእግዚአብሔርን ቃል ይናገራልና፤ እግዚአብሔር መንፈሱን ሰፍሮ አይሰጥምና።35፤ አባት ልጁን ይወዳል ሁሉንም በእጁ ሰጥቶታል።36፤ በልጁ የሚያምን የዘላለም ሕይወት አለው፤ በልጁ የማያምን ግን የእግዚአብሔር ቍጣ በእርሱ ላይ ይኖራል እንጂ ሕይወትን አያይም።”ያየውንና የሰማውን እየሱስ መሰከረ እኛም ምስክሩን እውነት ነው ብለን ተቀበልንና አተምን::  አሜን እግዚአብሔር እውነተኛ ነው::  እውነትተኛነቱንም ያወቅቅነው ቃሉን ስለነገረን ነው ሲናገርም በመንፈስ ሆኖ ነው::  የብሉይ ኪዳን ነብያት በልክና በጊዜ የተወሰነ ነገር በመንፈስ ቅዱስ አድርገዋል::  በአዲስ ኪዳን ግን መንፈስ ቅዱስ ስራ ሰርቶ መሄድ ብቻ ሳይሆን ከመለኮቱ ኃይል ተካፋይ አፍርጎንማንነቱን በእኛ ውስጥ አድርጎ እየኖረ ነው ስለዚህ ምኑን ሰፈረው ማንነቱ ሁሉ በእኛ ውስጥ እየኖረ እራሱን ነው የሰጠን::  ስሙ ይባረክ!አብ ሁሉን ለእየሱስ ሰቶታል በልጁ የሚያምን የዘላለም ሕይወት አለው፤ እንደሚል እኛ የዘላለም ህይወትን የምናገኘው ሞተን መንግስተ ሰማያት ስንገባ ሳይሆን አሁን ወደ ፍቅሩ መንግስት አፍልሶናል::  በልጁ የማያምን ግን የእግዚአብሔር ቍጣ በእርሱ ላይ ይኖራል እንጂ ሕይወትን አያይም::  ይህ ማለት በክርስቶስ ስራ ከማመን በህግ እንሄዳለን ለሚሉት ነው እርሱምመጨረሻው ህይወትን አለማየት ነው:: በራእይ 20:13፤ ባሕርም በእርሱ ውስጥ ያሉትን ሙታን ሰጠ፥ ሞትና ሲኦልም በእነርሱ ዘንድ ያሉትን ሙታን ሰጡ፥ እያንዳንዱም እንደ ሥራው መጠን ተከፈለ።አባት ሆይ ስለሰጠኸኝ ህይወት አመሰግንሃለሁ::  ስለሚጠፉት ደግሞ የምፀልይበትን ፀጋ ስጠኝ አንብቤ ብቻ እንዳላልፍ ጌታዬ ሆይ መራራትን ስጠኝ::አሜን!

ዮሐንስ 4: 1 – 6

እንግዲህ፦ “ኢየሱስ ከዮሐንስ ይልቅ ደቀ መዛሙርት ያደርጋል፡ ያጠምቅማል፡” ማለትን ፈሪሳውያን እንደ ሰሙ ጌታ ባወቀ ጊዜ፥ ይሁዳን ትቶ ወደ ገሊላ ደግሞ ሄደ፤ ዳሩ ግን ደቀ መዛሙርቱ እንጂ ኢየሱስ ራሱ አላጠመቀም። በሰማርያም ሊያልፍ ግድ ሆነበት።ስለዚህ ያዕቆብ ለልጁ ለዮሴፍ በሰጠው ስፍራ አጠገብ ወደምትሆን ሲካር ወደምትባል የሰማርያ ከተማ መጣ፤ በዚያም የያዕቆብ ጕድጓድ ነበረ። ኢየሱስም መንገድ ከመሄድ ደክሞ በጕድጓድ አጠገብ እንዲህ ተቀመጠ፤ ጊዜውም ስድስት ሰዓት ያህል ነበረ።ፈሪሳውያን እየሱስ ከዮሃንስ የበለጠ ደቀ መዛሙርት ያደርጋልን እንደሰሙ ባወቀ ጊዜ ይሁዳን ትቶ ወደ ገሊላ መሄድን መረጠ::  አሁን ጊዜው አልነበረም ከነዚህ ባለስልጣናት ጋር ለመጨቃጨቅ::  ስለዚህም ወደ ሌላ ስፍራ ሄዶ አገልግሎቱን መቀጠል ነበረበት::  ወደ ገሊላም ሲያቀና በሰማርያ ማለፍ ግድ ሆነበት ይላል::  ወደ ገሊላ ለመሄድ አጭሩ መንገድ ነበረ::  እስራኤሎች ግን ከሰማርያውያን ጋር ስለማይተባበሩ በከተማቸውም ማለፍን አይፈልጉምና በረጅም መንገድ ዙሪያውን ነበረ የሚሄዱት:: እየሱስ ደክሞት እንደነበረ ዮሃንስ ይነግረናል::  አምላክ እንደሆነ ሁሉ እንደሰውም ይደክመዋል::  እራሱን ዝቅ አድርጎ ነው የመጣው ስሙ ይባረክ::እየሱስን ግን ወደዚህ ስፍራ እንዲመጣ ግድ ያለው አንዱ ምክንያት ይህ ስፍራ አብርሃምንም ያዕቆብንም የተገናኘበትና እነርሱም መሰዊያን ሰርተው የሰውበትና ያመለኩበት ስፍራም ነው::  ሌላው አንዲትን ሴት ለማግኘትና ከተማዋን ሁሉ በአንድ ጊዜ መድረስ ነበረ::  የሰማርያ ህዝብ ከአህዛብ የተቀላቀለ ስለሆነ በእስራኤሎች ዘንድ ይገፋሉ::  ይህንንየተገፋና በተመረጡት ዘንድ ስፍራ ያልተሰጠውን ማህበረሰብ ፈልጎ መጣ:: አገልግሎታችን በፍቅር ያለ አድልዎ ለሰው ልጅ ሁሉ መሆን አለበት ::  ጌታ ይርዳን::ዘፍጥረት 12:6፤ አብራምም እስከ ሴኬም ስፍራ እስከ ሞሬ የአድባር ዛፍ ድረስ በምድር አለፈ፤ የከነዓን ሰዎችም በዚያን ጊዜ በምድሩ ነበሩ። 7፤ እግዚአብሔርም ለአብራም ተገለጠለትና፦ “ይህችን ምድር ለዘርህ እሰጣለሁ፡” አለው። እርሱም ለተገለጠለት ለእግዚአብሔር በዚያ ስፍራ መሠውያን ሠራ።ዘፍጥረት 33:18፤ ያዕቆብም ከሁለት ወንዞች መካከል በተመለሰ ጊዜ በከነዓን ምድር ወዳለችው ወደ ሴኬም ከተማ በደኅንነት መጣ፤ በከተማይቱም ፊት ሰፈረ። 19፤ ድንኳኑን ተክሎበት የነበረውንም የእርሻውን ክፍል ከሴኬም አባት ከኤሞር ልጆች በመቶ በጎች ገዛው። 20፤ በዚያም መሠውያውን አቆመ፥ ያንም ኤል ኤሎሄ እስራኤል ብሎ ጠራው።

ዮሐንስ 4: 7-12

7፤ ከሰማርያ አንዲት ሴት ውኃ ልትቀዳ መጣች። ኢየሱስም፦ “ውኃ አጠጪኝ፡” አላት፤8፤ ደቀ መዛሙርቱ ምግብ ሊገዙ ወደ ከተማ ሄደው ነበርና።10፤ ኢየሱስ መልሶ፦ “የእግዚአብሔርን ስጦታና፦ ‘ውኃ አጠጪኝ፥’ የሚልሽ ማን መሆኑንስ ብታውቂ፥ አንቺ ትለምኚው ነበርሽ፡ የሕይወትም ውኃ ይሰጥሽ ነበር፡” አላት።እየሱስ በሰማርያ ለማለፍና ይህንን መሰዊያ የነበረበትን ስፍራ ለመጎብኘት የተገኘ ይመስላል::  አብርሃምም ያዕቆብም እዚሁ ስፍራ ላይ መሰዊያን አድርገው ነበረና::  በስፍራው ላይ ሲመጣ ግን የተገኘችው ይህች ምስኪን በጥያቄ የተሞላች ሳምራዊት ነበረች::  በዘመኑ እስራኤላውያንና ሳምራውያን አይተባበሩም ነበረ::  እየሱስ ግን የተናቀችውን ለመገናኘት ጊዜውንና ቦታውን አስተካክሎ ተገናኛት::  እኛንምበጨለማው ውስጥ ስንደናበር ተገናኝቶን እራሱን ገልጦልን ተከተልነው::ሴቲቱን ኢየሱስም፦ “ውኃ አጠጪኝ፡” አላት፤ ይህ የማይታመን ጥያቄ ነው አይሁዳዊ ሰማርያዊትን? እርሱ ግን የሚያደርገውን ያውቅ ነበረ:: እርስዋም ገርሟታል መልሶም እንድትለምነው ስለፈለገ መንገዱን እያሳያት ነበር::  ጥያቄ የሚፈጥርን ነገርም ተናገራት:- የእግዚአብሔርን ስጦታና፦ ‘ውኃ አጠጪኝ፥’ የሚልሽ ማን መሆኑንስ ብታውቂ፥ አንቺ ትለምኚው ነበርሽ፡ የሕይወትም ውኃ ይሰጥሽ ነበር፡” ሲላት ከውሃው አሳብ ወጣችና ማወዳደር ጀመረች::  ማን ቢሆን ነው ብላ ከያዕቆብ ጀመረች::እራሱንየጠራው የእግዚአብሔርን ስጦታ ብሎ ነው::  እየሱስ ለእኛ ስጦታ ነው::  የሕይወትም ውኃ ይሰጥሽ ነበር አላት እኛምተቀብለናል ይህንን የህይወት ውኃ ጥማችንን የሚያረካ ከእርሱ በቀር ሌላው ሁሉ እያለቀ ያስጠማናል እየሱስ ግን ጥማትን የሚያረካ ነው ለዘላለም:: ሃሌሉያ!  ጥያቄያችንን ሁሉ የሚመልስ ጌታ በዙፋኑ ላይ ነው::

ዮሐንስ 4: 13-19

13፤ ኢየሱስም መልሶ እንዲህ አላት፦ “ከዚህ ውኃ የሚጠጣ ሁሉ እንደ ገና ይጠማል፤14፤ እኔ ከምሰጠው ውኃ የሚጠጣ ሁሉ ግን ለዘላለም አይጠማም፥ እኔ የምሰጠው ውኃ በእርሱ ውስጥ ለዘላለም ሕይወት የሚፈልቅ የውኃ ምንጭ ይሆናል እንጂ።”19፤ ሴቲቱ፦ “ጌታ ሆይ፥ አንተ ነቢይ እንደ ሆንህ አያለሁ።ይህች ሴት እየሱስን ከያዕቆብ ጋር እያወዳደረች ነበረ::  ኒቆዲሞስም ሆነ ይህች ሴት እየሱስ እያወራ ያለውን መንፈሳዊ ነገር አልተገለጠላቸውም::  ይህችም ሴት የደረሰችበት እውቀት ይህንን ውሃ ስጠኝና ደግሜ እዚህ እንዳልመጣ ገላግለኝ አለችው::  ይሄኔ የመሰላት ጏሮዋ የውሃ ምንጭ ሊያፈልቅልኝ ይሆናል ብላ ነው እንጂ ገና የእርሱ ትምህርት ጥልቀቱ አልገባትም:: እየሱስ:- እኔ ከምሰጠው ውኃ የሚጠጣ ሁሉ ግን ለዘላለም አይጠማም፥ አላት:: ውሃ ይሰጠናል ከእኛ የሚጠበቀው ግን መጠማትና መጠጣት ነው::  ዕለት ዕለት በመንፈስ ተሞሉ ነው የተባልነው እንድንጠጣ ይሰጠናል የሚሰጠንም በልግስና ሳይሰስት ያረካናል ከእርሱ ውጭ የሚያረካ የለም::   የምንፈልገውን ሁሉ ብናገኝና ቢትረፈረፍ የዓለም ነገር ይሰለቸንና ሌላ ፍለጋ እንሄዳለን::  እርሱ ግን ለዘላለም የሚያረካ የህይወት ምንጭ ነው ምንም በእርሱ ላይ መጨመር አያስፈልገንም ከእርሱስ ወዴት እንሄዳለን?!ሌላው:- እኔ የምሰጠው ውኃ በእርሱ ውስጥ ለዘላለም ሕይወት የሚፈልቅ የውኃ ምንጭ ይሆናል አለ::  በእኛ ውስጥ የማይቋረጥ ህይወት ይፈሳል::  ህይወት እንዲበዛልንና እንዲትረፈረፍልን መቷል! አሜን!ታላቅ መንፈሳዊ ነገር ሲነግራት ብዙም ያልገባት ሴት ህይወትዋን ግን ሲገልጠው “ጌታ ሆይ፥ አንተ ነቢይ እንደ ሆንህ አያለሁ አለች።  ከያዕቆብ ያወዳደረችውን አሁን ደግሞ ነብይ ነህ አለችው::  የሚገርመኝ የዓለም ጌታና ንጉስ ቁጭ ብሎ ማኅበረሰብዋ እንኳን የማይፈልጋትን ሴት በትዕግስት ወደሚፈልገው አቅጣጫ እንድትደርስ ማስተማሩ::  እርሱ ማንንም አይንቅም አንዱንም ከአንዱ አያበላልጥም ለሁሉ እንደሚረዳው መጠን ዝቅ ብሎ ይገኛል::  እኛንም እንደዚሁ ታግሶ እዚህ አድርሶናል::  ፍቅሩ አይለወጥም ማንም ወደ እኔ ይምጣና ይጠጣ ብሎናል::  የጠራው ሁሉንም ነው:: እንጠጣ!!አባት ሆይ አንተ መልካም ነህ!!  እናመሰግንሃለን አንተ አትለወጥም ዛሬ በመንፈስህ ሙላን::  ልክ እንደአንት የተጠሉትንና የማይፈለጉትን መፈለግና ወደ መንግስትህ ማምጣት ይሁንልን:: ዓይኖቻችን ይከፈቱና የምታሳየንን ማየትና መታዘዝ  ይብዛልን::  አሜን!

ዮሐንስ 4: 20-27

20፤ አባቶቻችን በዚህ ተራራ ሰገዱ፤ እናንተም፦ ‘ሰው ሊሰግድበት የሚገባው ስፍራ በኢየሩሳሌም ነው፡’ ትላላችሁ፡” አለችው።21፤ ኢየሱስም እንዲህ አላት፦ “አንቺ ሴት፥ እመኚኝ፥ በዚህ ተራራ ወይም በኢየሩሳሌም ለአብ የማትሰግዱበት ጊዜ ይመጣል።22፤ እናንተስ ለማታውቁት ትሰግዳላችሁ፤ እኛ መዳን ከአይሁድ ነውና ለምናውቀው እንሰግዳለን።23፤ ነገር ግን በእውነት የሚሰግዱ ለአብ በመንፈስና በእውነት የሚሰግዱበት ጊዜ ይመጣል አሁንም ሆኖአል፤ አብ ሊሰግዱለት እንደ እነዚህ ያሉትን ይሻልና፤24፤ እግዚአብሔር መንፈስ ነው፥ የሚሰግዱለትም በመንፈስና በእውነት ሊሰግዱለት ያስፈልጋቸዋል።”25፤ ሴቲቱ፦ “ክርስቶስ የሚባል መሲሕ እንዲመጣ አውቃለሁ፤ እርሱ ሲመጣ ሁሉን ይነግረናል፡” አለችው።26፤ ኢየሱስ፦ “የምናገርሽ እኔ እርሱ ነኝ፡” አላት።ነብይ ነው ብላ  ስላመነች በውስጥዋ የሚቃጠለውን እርሱም ሊመልስ የተገኘውን ጥያቄ ጠየቀች እርሱም ስለ አምልኮ ነበረ::  አባቶቻችን በዚህ ተራራ ሰገዱ፤ እናንተም፦ ‘ሰው ሊሰግድበት የሚገባው ስፍራ በኢየሩሳሌም ነው፡’ ትላላችሁ፡::  እውነቱን ንገረኝ የት ነው መመለክ ያለበት አለች?  አዲስ ኪዳን አልነበረምና የሚመለከውና የሚሰገደው በእየሩሳሌም ብቻ ነበረና ሰማርያውያን መተው ማምለክ አይችሉም ነበር:: ኢየሱስም እንዲህ አላት፦ “አንቺ ሴት፥ እመኚኝ፥ በዚህ ተራራ ወይም በኢየሩሳሌም ለአብ የማትሰግዱበት ጊዜ ይመጣል አሁንም ሆኖአል አላት::  ስለዚህም ጌታ ሲመልስላት እናንተስ ለማታውቁት ትሰግዳላችሁ፤ እኛ መዳን ከአይሁድ ነውና ለምናውቀው እንሰግዳለን አላት::  በተወሰነ ስፍራ መመለክ ነበረበት:: ይህንን አሰራር ሊሽረው የመጣ ጌታ ስሙ ይባረክ::  በእየሩሳሌም ብቻ የነበረውን አምልኮ ወደ እያንዳንዳችን ልብ አምጥቶ እግዚአብሔር መንፈስ ነው፥ የሚሰግዱለትም በመንፈስና በእውነት ሊሰግዱለት ያስፈልጋቸዋል ብሎ ደመደመው ምክንያቱም  አብ ሊሰግዱለት እንደ እነዚህ ያሉትን ይሻልና::  አሜን!ይህች ሴት ከውሃ ክርክር ወጥታ ከያዕቆብ ትበልጣለህ ወይ ስትለው ነበር ከዛም ደግሞ ነብይ ነህ አለችው በስተመጨረሻ ግን ተወው እንዲያውም ጥያቄዬን ሁሉ የሚመልስ የምጠብቀው አለኝ  አለች:: እንዲህ ስትል፦ “ክርስቶስ የሚባል መሲሕ እንዲመጣ አውቃለሁ፤ እርሱ ሲመጣ ሁሉን ይነግረናል፡” አለችው። ይህየሚራራ ንጉስ ግን ለእርስዋ ብቻ  የተናገረው ነገር ቢኖር “የምናገርሽ እኔ እርሱ ነኝ፡” አላት። ዋዉ!  ለዝች ሴት ጊዜውን ሰጥቶ ማንነቱን ገለጠላት::  ጥያቄዋን ሁሉ መለሰ::  ጠብቃው ነበረና መሲህ ይመጣል ብላ ለራሱ ነገረችዉ ምን አይነት ትጋት ነው?!  በተመረጡት እየተገፉ ተስፋ  አድርገው እርሱን መጠበቅ?! እርሱም ስለሚያውቅ የውስጥዋን ቁጭት አይቶ ለብቻዋ እንድታመልከና ጥማትዋን እንድትወጣ አደረጋት:: መሲህ እንደሆነ ገለጠላት: አባት ሆይ ክብር ለአንተ ይሁን ይህንን እውነት ስለገለጥክልን::   አንተን  በውስጣችን የትም ሳንሄድ በመንፈስና በእውነት እናመልክህ ዘንድ መቅደስህ ላደረከን ጌታ ክብር ይሁንልህ::  ለዘላለም ግዛን!  የምናመልክበትን መንፈስ አፍስስልን!  አሜን

ዮሐንስ 4: 28-30

28፤ ሴቲቱም እንስራዋን ትታ ወደ ከተማ ሄደች ለሰዎችም፦29፤ “ያደረግሁትን ሁሉ የነገረኝን ሰው ኑና እዩ፤ እንጃ እርሱ ክርስቶስ ይሆንን?” አለች።30፤ ከከተማ ወጥተው ወደ እርሱ ይመጡ ነበር።ኢየሱስ፦ “የምናገርሽ እኔ እርሱ ነኝ፡” ባላት ጊዜ እንስራዋን ትታ ወደ ከተማ ሄደች ስለ እየሱስ ለመመስከር::  ይህ ሰው ክርስቶስ ይሆንን? እያለች መሰከረች::  የመጣችበት በኃላ ላይ የሚያስፈልጋት ውሃም ትዝ አላላትም::  እየሱስ ሲመጣ ምን ይወዳደረዋል ይህንን ልጨምር በእርሱ ላይ አንልም ሁሉንም ጥለን ነው ተከትለነው የምንሮጠው:: በእውነት ዛሬ ተከትለን መሮጥ ይሁንልን እውቀታችን ልምዳችን ሳንል ህይወቴን የቀየረውን ኑና እዮ ማለት ይሁንልን::ጳውሎስም ምንም በገማልያ እግር ስር የተማረና ብዙ እውቀት የነበረው ቢሆንም ሁሉንም ጥሎ ባዶ እራሱን አድርጎ ነበረ::  1 ቆሮንቶስ 2:1፤ እኔም፥ ወንድሞች ሆይ፥ ወደ እናንተ በመጣሁ ጊዜ በቃልና በጥበብ ብልጫ ለእግዚአብሔር ምስክርነቴን ለእናንተ እየነገርሁ አልመጣሁም።  2፤ በመካከላችሁ ሳለሁ ከኢየሱስ ክርስቶስ በቀር እርሱም እንደተሰቀለ ሌላ ነገር እንዳላውቅ ቆርጬ ነበርና።ዛሬ መጣል ያልቻልነው ምንድነው? ሃብት: መልክ:  እውቀት:  ወገን:  ችሎታ:  ገቢያችን . . .  እየሱስ ሲመጣ ጥለን እንሮጣለን እርሱን እንጂ እራሳችንን አናሳይም::  እርሱን ያየ ያስታውቃል እየሱስን እዮ የሚል ቀስት ብቻ ይሆናል::  ጌታ ይገለጥልንና በእርሱ ላይ ጨምረን የያዝነውን አስጥሎ  እርሱን ብቻ የምናሳይ ያድርገን:: አባት ሆይ እርዳን! እራስህን ግለጥልን እንወቅህ::አሜን

ዮሐንስ 4: 31-38

31፤ ይህም ሲሆን ሳለ ደቀ መዛሙርቱ፦ “መምህር ሆይ፥ ብላ፡” ብለው ለመኑት።32ግንድ34፤ ኢየሱስም እንዲህ አላቸው፦ “የእኔስ መብል የላከኝን ፈቃድ አደርግ ዘንድ ሥራውንም እፈጽም ዘንድ ነው።37፤ አንዱ ይዘራል አንዱም ያጭዳል የሚለው ቃል በዚህ እውነት ሆኖአልና።38፤ እኔም እናንተ ያልደከማችሁበትን ታጭዱ ዘንድ ሰደድኋችሁ፤ ሌሎች ደከሙ እናንተም በድካማቸው ገባችሁ።”ከሳምራዊትዋ  ጋር  መነጋገሩን ሲጨርስ ደቀመዛሙርቱ ከሄዱበት ተመለሱ ያመጡትንም ምግብ ጋበዙት::  እርሱ ግን፦ “እናንተ የማታውቁት የምበላው መብል ለእኔ አለኝ አላቸው::  እርሱ ምግብ የሚለውና እነሱ ምግብ የሚሉት የተለያየ ነገር ሆነ::  ስጋውያን ነበሩና መንፈሳዊዉን አሳብ መረዳት አልቻሉም::  የእግዚአብሔርን አሳብ የምንረዳው በመንፈሱ ነው እንጂ በእኛ በራሳችን አይደልም::  ለሴቲቱ እንዳለው እርሱ በመንፈስና በእውነት የሚመለክ ጌታ ነው::መብሉ ምን እንደሆነ ባያብራራልን ኖሮ እኛም እንደነርሱ የሆነ ምክንያት ሰተን እናልፍ ነበር::  እየሱስ ግን  የእኔስ መብል የላከኝን ፈቃድ አደርግ ዘንድ ሥራውንም እፈጽም ዘንድ ነው።ይህ የመንግስቱ ስራ ነው እርሱን የሚያረካው::  ምግብን ስናስብ ጉልበት የሚሆነን:  የሚያረካን:  ስንጠግብም ሌላ እንዳንፈልግ የሚያደርግ ነው::  ይህንን ሁሉ ፈቃዱን በማድረግ ተካው:: ጀምሮም አልሄደ ብትወድ ይህች ጽዋ ከእኔ ትለፍ ብሎ ነበር ነገር ግን ለዚህ መጥቻለሁ ብሎ ፈቃድህ ይሁን እያለ እራሱን ስቶ የአባቱን ፈቃድ ፈጽሞ አከበረው::  በመስቀልም ላይ ተፈፀመ ብሎ አወጀ::  አሜን ተፈጸመ!በመስቀል ላይ ዋጋ መክፈሉ የሚያሳየው ያልደከማችሁበትን ታጭዱ ዘንድ ሰደድኋችሁ፤ ሌሎች ደከሙ እናንተም በድካማቸው ገባችሁ። እንዳለው እኛ ዛሬ የምናጭደው እርሱ የለፋበትን ስለእርሱ ሲናገሩና ሲመሰክሩ የነበሩት ነብያት የሞቱለትን ስራ ነው::  በዚህም ውስጥ የአካል ስራ ይታያል እርሱንም የሚሰራው በመንፈሱ ነው:: አንዱ ይዘራል አንዱም ያጭዳል የሚለው ቃል በዚህ እውነት ሆኖአልና።  አባት ሆይ ፈቃድህን ማድረግና መታዘዝ ይብዛልን አንተን እንዳረካህ እኛም በዚህ እንርካ  እንጂ ሌላ የሚያረካ ፍለጋ እንዳንባዝን የሚያስፈልገውን አንድ ነገር ስጠን በእግርህ ስር መገኘት!  አሜን!

ዮሐንስ 4: 39-42

39፤ ሴቲቱም፦ “ያደረግሁትን ሁሉ ነገረኝ፡” ብላ ስለ መሰከረችው ቃል ከዚያች ከተማ የሰማርያ ሰዎች ብዙ አመኑበት።

40፤ የሰማርያ ሰዎችም ወደ እርሱ በመጡ ጊዜ በእነርሱ ዘንድ እንዲኖር ለመኑት፤ በዚያም ሁለት ቀን ያህል ኖረ።

41፤ ስለ ቃሉ ከፊተኞች ይልቅ ብዙ ሰዎች አመኑ፤

42፤ ሴቲቱንም፦ “አሁን የምናምን ስለ ቃልሽ አይደለም፥ እኛ ራሳችን ሰምተነዋልና፤ እርሱም በእውነት ክርስቶስ የዓለም መድኃኒት እንደ ሆነ እናውቃለን፡” ይሉአት ነበር።

ሳምራይትዋ ሴት እየሱስን አስተዋውቃዋለች ሳታፍርና ሳትደብቅ::   “ያደረግሁትን ሁሉ ነገረኝ፡” እያለች ስለእርሱ መሰከረች::  እኛም ስላደረገልን ነገር መመስከርና እርሱን ማሳየት አለብን::

የሰማርያ ሰዎች እርስዋን ሰምተው የመጡ ቢሆኑም ቅሉ እራሳቸው ቁጭ ብለው ተምረው ስለእርሱ መሰከሩ::  ሴቲቱንም፦ “አሁን የምናምን ስለ ቃልሽ አይደለም፥ እኛ ራሳችን ሰምተነዋልና፤ እርሱም በእውነት ክርስቶስ የዓለም መድኃኒት እንደ ሆነ እናውቃለን፡” ይሉአት ነበር። እራሱን የሚያሳይ ጌታ ነው::

ሳምራውያኑ የተረዱበት አረዳድ

1.  በእውነት ክርስቶስ ነው

2.  የዓለም መድኃኒትነው

ከመጥምቁ ዮሃንስ ቀጥሎ ለዓለም እንደመጣ አወቁ::  እነርሱም በእስራኤሎቹ ተቀባይነት አልነበራቸውምና::  ጌታ ግን በእኛ ዘንድ ቆይ ሲሉት ሁለት ቀን አደረ::  በዘመኑ የነበሩት እስራኤሎች ግን እንኳን ሁለት ቀን ሊያድሩ ይቅርና በዛ በኩል አያልፉም ነበር ተጠይፈው::   እርሱ ግን የጥልን ግድግዳ አፍርሶ አንድን ሰው ለመፍጠር መጣ::  ሁሉ በክርስቶስ አንድ ነው::  አሜን! ፊሊጶስም ሲያገለግላቸው ከተማይቱ ተገለባበጠች የእርሱን ማዳን የተቀበሉ ነበሩና::

አአባት ሆይ ውጫዊ ማንነትን ሳናይ ዓይንህና ልብህ ባለበት የእኛም እንዲሆን ያደረክልንን ሁሉ እንድንመሰክር በኃይልና በግልጥነት እንድንመሰክርና እንድናገለግልህ እርዳን::  አሜን

ዮሐንስ 4: 43-45

43፤ ከሁለቱ ቀኖችም በኋላ ከዚያ ወጥቶ ወደ ገሊላ ሄደ።

44፤ ነቢይ በገዛ አገሩ እንዳይከበር ኢየሱስ ራሱ መስክሮአልና።

45፤ ወደ ገሊላም በመጣ ጊዜ፥ የገሊላ ሰዎች ራሳቸው ደግሞ ለበዓል መጥተው ነበርና በበዓል በኢየሩሳሌም ያደረገውን ሁሉ ስላዩ ተቀበሉት።

ሁለት ቀን በሳምራውያን ዘንድ ከቆየ በኃላ ወደ ገሊላ መጣ::  የገሊላ ሰዎች እየሱስን እንደመቀበል አድርጉ ምክንያቱም በኢየሩሳሌም ያደረገውን  ስላዩ::  ያደረገውም አንዱ ነገር ቤተመቅደሱን ማጥራት ነበር ቤቴን የወንበዴዎች ዋሻ አደረጋችሁ ብሎ በቁጣ አስወጥቶ ነበረ::  እንደዚሁም ደግሞ ያልተመዘገበ ተአምራትን አድርጎ ነበረና ነው:: በዮሐንስ 2:23፤ በፋሲካ በዓልም በኢየሩሳሌም ሳለ፥ ያደረገውን ምልክት ባዩ ጊዜ ብዙ ሰዎች በስሙ አመኑ::

በገሊላ ውሃውን የወይን ጠጅ አድርጎ ቀይሮ ነበረ ነገር ግን እንኳን ህዝቡ የድግሱ ባለቤት ሙሽራውም  አላወቀም ነበር::  እዚህ ላይም ሰው የተቀበለው ከእየሩሳሌሙ ተአምራት የተነሳ እንጂ በመካከላቸው ያደረገውን አያውቁም ነበረ አይ መተላለፍ:: እርሱ ብዙ ግርግር ሳያስነሳ ማገልገል ነበረ የሚፈልገው ስለዚህም ከስፍራ ወደ ስፍራ ይንቀሳቀስ ነበረ:: የገሊላ ሰዎች እንደመሲህ ለመቀበል ይከብዳቸዋል ምክንያቱም እንደማንኛውም ልጅ ሲያድግ ስላዮት እናትና አባቱን የምናውቃቸው አይደሉም እንዴ ወደ ማለት ነው የሚመጡት::  ነቢይ በገዛ አገሩ እንዳይከበር ኢየሱስ ራሱ መስክሮአልና።  ለእኛ ግን ይህ የከበረ ጌታ የሌለን እንዳለ አድርጎ የሚጠራ ጌታ ስለእኛ ዝቅ ብሎ ተዋርዶ እራሱን ባዶ አድርጎ እንደመጣ ያሳየናል::  እነርሱ ባይቀበሉት እኛ ግን የህይወታችን ጌታ ነው ብለን ይህንን መሲህና አዳኝ ሾመነዋል::  እንዳያረጅብን እርሱ ማለዳ ማለዳ አዲስ ነው ህይወት እንዲበዛልን መቷል::

አባት ሆይ እራስህን ባዶ አድርገህ የባርያን መልክ ይዘህ ስለመጣህና ስለታደገን ተመስገን!!  ሃሌሉያ!!

ዮሐንስ 4: 46-54

46፤ ኢየሱስም ውኃውን የወይን ጠጅ ወዳደረገባት ወደ ገሊላ ቃና ዳግመኛ መጣ። በቅፍርናሆምም ልጁ የታመመበት ከንጉሥ ቤት አንድ ሹም ነበረ።

47፤ እርሱም ኢየሱስ ከይሁዳ ወደ ገሊላ እንደ መጣ ሰምቶ ልጁ ሊሞት ስላለው ወደ እርሱ ሄደ ወርዶም እንዲፈውስለት ለመነው።

48፤ ስለዚህም ኢየሱስ፦ “ምልክትና ድንቅ ነገር ካላያችሁ ከቶ አታምኑም፡” አለው።

49፤ ሹሙም፦ “ጌታ ሆይ፥ ብላቴናዬ ሳይሞት ውረድ፡” አለው።

50፤ ኢየሱስም፦ “ሂድ፤ ልጅህ በሕይወት አለ፡” አለው። ሰውዬውም ኢየሱስ የነገረውን ቃል አምኖ ሄደ።

53፤ አባቱም ኢየሱስ፦ “ልጅህ በሕይወት አለ፡” ባለው በዚያ ሰዓት እንደ ሆነ አወቀ፤ እርሱም ከቤተ ሰዎቹ ሁሉ ጋር አመነ።

54፤ ይህም ደግሞ ኢየሱስ ከይሁዳ ወደ ገሊላ መጥቶ ያደረገው ሁለተኛ ምልክት ነው።

እየሱስ በገሊላ መሆኑን ሲሰማ  አንድ አህዛብ የሆነ የንጉስ ሹም ልጁ ስለታመመበት ወደ ጌታ መጣ::  ኢየሱስ፦ “ምልክትና ድንቅ ነገር ካላያችሁ ከቶ አታምኑም፡” አለው። ምክንያቱም ሰውየው የፈለገው እየሱስ አብሮት እንዲመጣ ነው::  የጨነቀው አባት ስልጣኑና ማዕረጉ ምንም የማይጠቅምበት አጣብቂኝ ሰዓት ላይ ነውና ደግሞ ለመነ ሊሞትብኝ ነውና እባክህ::  ያለን ነገር ገንዘብ ቢሆን ዝና ቢሆን ጤና ቢሆን ወገን ቢሆን ሌላም ሌላም የሚያስመካ አይደለም መታመን ያለብን በጌታ ብቻ ነው:: ዓይናችን በንጉሱ ላይ ይሁኑ::

በዚህ ስፍራ  እንደምናየው ብዙዎች መተው ተአምራት ሆኖላቸዋል የተአምራቱን ጌታ  ግን ሳይተዋወቁት ቀርተዋል:: ይህም ሰው የፈለገው የልጁን መዳን ብቻ ነው::  ነገር ግን እንደባለስልጣን ሆኖ አይደለም በጌታ ፊት የቀረበው እርዳታ እንደሚፈልግ የተጨነቀ አባት እንጂ::  የፈለገውም የልጁን መፈወስ ነው ጌታም በቃል ላይ ብቻ እንዲደገፍ ቃል ነው የሰጠው   “ሂድ፤ ልጅህ በሕይወት አለ” አለው። ሞትን በህይወት የሚለውጥ ጌታ!  ያለ እምነት እግዚአብሔርን ደስ ማሰኘት አይቻልም::

ሰውዬውም ኢየሱስ የነገረውን ቃል አምኖ ሄደ። ይህ ሰውአህዛብ ነው ግን አምኖ ሄደ?!  ይገርማል መታመኑ እንደዘመናችን ስልክ የለ ደወል አድርጎ አጣርቶ አያውቅ የሚሄደውም መንገድ ረጅም ነው::  ነገር ግን የተነገረውን ቃል አምኖ ሄደ እርሱም አላፈረም::  አባቱም ፈውሱ የሆነው ኢየሱስ፦ “ልጅህ በሕይወት አለ፡” ባለው በዚያ ሰዓት እንደ ሆነ አወቀ፤ ሳይዘገይ ቃሉ ገና  ከአፉ ሲወጣ ነው ፈውሱ የሆነው::  እርሱም ከቤተ ሰዎቹ ሁሉ ጋር አመነ።  ይህ ተአምር የዚህን ሰውና የቤተሰቡን ሁሉ እምነት በእየሱስ ላይ እንዲያደርጉ አደረጋቸው::

በገሊላ ይህ ሁለተኛ ተአምር ነው ይላል ቃሉ ከዚህ የበለጠ ማየት ሲችሉ የገሊላ ሰዎች ግን ይህንን ንጉስ አላወቁትም:: አምላካችን በስራ ላይ ነው:: ተአምራትን ማድረግ ሰዎችን ወደ ክርስቶስ ያመጣልና የተለያዩ ጸጋዎች በቅዱሳን መካከል መገለጥ አለባቸው:: 

አባት ሆይ አንተ ዛሬም ትፈውሳለህ ወደ ቤትህ ሰዎችን በየምክንያቱ ትጠራለህና እያንዳንዳችንን ተጠቀምብን በእኛ ውስጥ ያስቀመጥከው ጸጋ ይውጣና አንተ የህይወት ራስ  ብቻህን ታይ::  አሜን!

ዮሐንስ 5: 1-4

1፤ ከዚህ በኋላ የአይሁድ በዓል ነበረ፥ ኢየሱስም ወደ ኢየሩሳሌም ወጣ።

2፤ በኢየሩሳሌምም በበጎች በር አጠገብ በዕብራይስጥ ቤተ ሳይዳ የምትባል አንዲት መጠመቂያ ነበረች፤ አምስትም መመላለሻ ነበረባት።

3፤ በእነዚህ ውስጥ የውኃውን መንቀሳቀስ እየጠበቁ በሽተኞችና ዕውሮች አንካሶችም ሰውነታቸውም የሰለለ ብዙ ሕዝብ ይተኙ ነበር።

4፤ አንዳንድ ጊዜ የጌታ መልአክ ወደ መጠመቂያይቱ ወርዶ ውኃውን ያናውጥ ነበርና፤ እንግዲህ ከውኃው መናወጥ በኋላ በመጀመሪያ የገባ ከማናቸው ካለበት ደዌ ጤናማ ይሆን ነበር።

እየሩሳሌምን ስናስብ ጌታ የመሰረተው መንግስት የኖረበት፤ መስዋዕት  የሚቀበልበትና የሚናገርበት ቤተመቅደሱ ያለበት፤ በስጋም የተወለደበት፤ የኖረበት፤ የተቀበረበትና  ያረገበት ዳግምም የሚመጣበት ርንዲሁምቤተክርስትያን የተወለደችበት ስፍራ ነው::

በዓልን ለማክበር ሁሉም ወደ እየሩሳሌም ይሰበሰባል እየሱስም ለበዓል ወደ እየሩሳሌም ብቅ ይላል አብዛኛው እስራኤላዊ እንደሚያደርገው ሁሉ::  የእርሱ መምጣት ግን አንድም ቤተመቅደሱን ከወንበዴዎች ለማጽዳት ወይም ለማስተማርና ለመፈወስ ነው::

ይህ አምላክ ይገርማል በዚሁ በእየሩሳሌም ቤተ ሳይዳን አዘጋጅቷል::  ያዘጋጀበትም ምክንያት መፍትሄ  ለህዝቡ ለመስጠት ነው እንዲፈወስ::  አምላካችን ፈዋሽ ነው::  መልአኩ መጥቶ ሲያናውጠው ፈውስ ይሆናል::  ይህንን መጠመቅያ ሳያዳላ ለሁሉ ሰጠ ማንምቀድሞ ከገባ ከማንኛውም ህመም ይፈወሳል::  

አባት ሆይ አንተ ዛሬም ሳታዳላ የምትፈውስ የህዝህን ጭንቅ መገላገል የምትፈልግ ነህና ለዚህም ተገርፈሃል በመገረፍህም ቁስል ተፈውሰናል! ተመስገን!!

ዮሐንስ 5: 5-9

5፤ በዚያም ከሠላሳ ስምንት ዓመት ጀምሮ የታመመ አንድ ሰው ነበረ፤

6፤ ኢየሱስ ይህን ሰው ተኝቶ ባየ ጊዜ፥ እስከ አሁን ብዙ ዘመን እንዲሁ እንደ ነበረ አውቆ፦ “ልትድን ትወዳለህን?” አለው።

7፤ ሰውዩም፦ “ጌታ ሆይ፥ ውኃው በተናወጠ ጊዜ በመጠመቂያይቱ ውስጥ የሚያኖረኝ ሰው የለኝም ነገር ግን እኔ ስመጣ ሳለሁ ሌላው ቀድሞኝ ይወርዳል፡” ብሎ መለሰለት።

8፤ ኢየሱስ፦ “ተነሣና አልጋህን ተሸክመህ ሂድ፡” አለው።

9፤ ወዲያውም ሰውዬው ዳነ አልጋውንም ተሸክሞ ሄደ።

እየሱስ ወደዚህ መጠመቅያ ስፍራ ሲመጣ ቀጠሮው በዚያም ለሠላሳ ስምንት ዓመት ለታመመ አንድ ሰው ነበረ::  እስኪ ወደኃላ እናስበው ሰላሳ ስምንት ዓመት ምንምን አደረግንበት?  ስንት ቦታ ደረስን ስንቱን አደረግን::  እርሱ ግን እዛው አንድ ቦታ ሆኖ  ሌሎች ሲፈዉሱና እየተደሰቱ ሲሄዱ ነው የሚመለከተው::  እርሱ ገና ወደ ውሃው ለመሄድ ሲሞክር ሌሎች ገብተው ይፈወሳሉ::  እንዴት ተስፋ ቆርጦ ጥሎ አልሄደም?  ምናልባትም መሄጃ የለው ይሆናል ማንም የሚረዳውም የሌለው ለዛም ይሆናል::  በጌታ ፊት ግን ታሰበ ይህ ማንም ምንም የሌለው ሰው::

ኢየሱስ ይህን ሰው ተኝቶ ባየ ጊዜ፥ እስከ አሁን ብዙ ዘመን እንዲሁ እንደ ነበረ አውቆ፦ “ልትድን ትወዳለህን?” አለው። ምን አይነት ጥያቄ ነው? መቼም እዚህ እየጠበቀ ያለው ፈውስ ነው::  እየሱስም ጠፍቶት አይደለም ከውሃው ላይ ዓይኑን አንስቶ በእርሱ ላይ እንዲያደርግ ቢሆንም ሰውየው ግን ዓይኑ በውሃው ላይ ነበረና ሰውዩም፦ “ጌታ ሆይ፥ ውኃው በተናወጠ ጊዜ በመጠመቂያይቱ ውስጥ የሚያኖረኝ ሰው የለኝም ነገር ግን እኔ ስመጣ ሳለሁ ሌላው ቀድሞኝ ይወርዳል፡” ብሎ መለሰለት።

ኢየሱስ፦ “ተነሣና አልጋህን ተሸክመህ ሂድ፡” አለው። ከውሃው ላይ ዓይንህን አንሳ ውሃውን እንዲያናውጥ መልአኩን የሚልከው በአጠገብህ ቆሟል!!  ዛሬም እኛ ዓይናችን በምን ላይ ነው?!  በእየሱስ ላይ ይሁን::  መምጣቱንም እንደዚህ እንጠባበቅ::  እየሱስ ይመጣል!!

ወዲያውም ሰውዬው ዳነ አልጋውንም ተሸክሞ ሄደ።  ይህ ሰው ሲፈወስ ብዙዎች በዛ ነበሩ ዓይናቸው ግን በውሃ ላይ ሆኖ ይህንን የህይወት ጌታ አላዮትም! ያሳዝናል::  እኛ ከዝች ክፉ ዓለም ድነን ህይወትን ስናገኝ አጠገባችን ያሉት አላዮትም አሾፉብን አላገጡብን::  እኛስ የተገለጠልንን ይህንን  የህይወት ራስ አወቅን ዳንን እርፍ አልን::  ስሙ ይባረክ! ለጠፉት እንፀልይ!

አባት ሆይ ስምህ ይባረክ እኔን ፈልገህ ስለመጣህ አንተንም ማወቅ ስለሆነልኝ አመሰግንሃለሁ::  በዙሪያዬ ያሉትን አስብ ወደ መዳንም ይመጡ ዘንድ አንተን ማወቅ ይሆንላቸው ዘንድ እፀልያለሁ::

ዮሐንስ 5: 10-18

10፤ ያም ቀን ሰንበት ነበረ። ስለዚህ አይሁድ የተፈወሰውን ሰው፦ “ሰንበት ነው አልጋህንም ልትሸከም አልተፈቀደልህም፡” አሉት።

ዮሐንስ 5:11፤ እርሱ ግን፦ “ያዳነኝ ያ ሰው፦ ‘አልጋህን ተሸክመህ ሂድ፥’ አለኝ” ብሎ መለሰላቸው።

ዮሐንስ 5:12፤ እነርሱም፦ “ ‘አልጋህን ተሸክመህ ሂድ፡’ ያለህ ሰው ማን ነው?” ብለው ጠየቁት።

ዮሐንስ 5:13፤ ዳሩ ግን በዚያ ስፍራ ሕዝብ ሰለ ነበሩ ኢየሱስ ፈቀቅ ብሎ ነበርና የተፈወሰው ሰው ማን እንደ ሆነ አላወቀም።

ዮሐንስ 5:14፤ ከዚህ በኋላ ኢየሱስ በመቅደስ አገኘውና፦ “እነሆ፥ ድነሃል፤ ከዚህ የሚብስ እንዳይደርስብህ ወደ ፊት ኃጢአት አትሥራ፡” አለው።

ዮሐንስ 5:17፤ ኢየሱስ ግን፦ “አባቴ እስከ ዛሬ ይሠራል፡ እኔም ደግሞ እሠራለሁ፡” ብሎ መለሰላቸው።

ይህ በመጥመቅያው አጠገብ ለመፈወስ ሰላሳ ስምንት ዓመት ሲጠብቅ የነበረው ሰው መፈወሱ የአይሁድን አለቆች አልገረማቸውም  ወይም ከእርሱ ጋር ደስ አላላቸውም::  የፈወሰውን ግን ለማወቅ ፈለጉ ሊያደንቁትና አብረው ሊተባበሩ ሳይሆን ሊከሱት::  ህግ እንደዚህ ነው ርህራሄ የለውም እኛ ግን ከህግ ነፃ ወተን ከፀጋ በታች ሆነናል::  ህግ ይከሳል  ያሳጣል እንጂ አይረዳም ስራው ሁሉ መክሰስ ነው::  እነዚህ ሰዎች በህግ ታጥረው የህጉን ባለቤት እንኳን ማወቅ አልቻሉም::  ዓይናቸው በማይሆን ነገር ተይዟል:: ይህ ርህሩህ ጌታ ግን ይህንን ሰው አይቶት መጣ አጠገቡ ያልሉት እግዚአብሔርን እናገለግላለን ያሉት ግን ምንም ግድ አላላቸውም በመፈወሱም ባለመፈወሱም::  ጌታ ይባረክ የሚያየን ዛሬም እኛን ተጠቅሞ ለሌሎች መድረስ የሚፈልግ ጌታ:: 

እየሱስ እየሸሸ ያለው እነዚህን የህግ መምህራን ነው አላሰራ ስላሉት ከአንዱ ቦታ ወደ ሌላ እየሄደ ነው የሚያስተምረው::  እዚህ ስፍራ ላይ ይህንን ሰው ሲያገኘው የነገረው ነገር በኃጥያት እንዳትመላለስና የከፋ እንዳይገጥምህ ነው::  በፀጋ ዘመን ነው የምኖረውና ምናለበት እንደፈለኩ ብመላለስ ብሎ ነገር የለም:: እራሳችንን ለጌታ አስገዝተን እርሱን እያከበርን ዓለምን ንቀን እንመላለሳለን::

አምላካችን በስራ ላይነው: ኢየሱስ ግን፦ “አባቴ እስከ ዛሬ ይሠራል፡ እኔም ደግሞ እሠራለሁ፡” ብሎ መለሰላቸው።

አባት ሆይ ስለምህረትህና ርህራሄህ ተመስገን የእኛ ነገር ግድ ስለሚልህ ተባረክ:: የአንት ዓይን ባለበት የእኛም ይሁን::  አንተ በምትሰራበት ሰዓት እኛንም ገንዘቦችህ አድርገን::  አሜን

ዮሐንስ 5: 18-19

18፤ እንግዲህ ሰንበትን ስለ ሻረ ብቻ አይደለም፥ ነገር ግን ደግሞ ራሱን ከእግዚአብሔር ጋር አስተካክሎ፦ “እግዚአብሔር አባቴ ነው፡” ስላለ፥ ስለዚህ አይሁድ ሊገድሉት አብዝተው ይፈልጉት ነበር።

19፤ ስለዚህ ኢየሱስ መለሰ፥ እንዲህም አላቸው፦ “እውነት እውነት እላችኋለሁ፥ አብ ሲያደርግ ያየውን ነው እንጂ ወልድ ከራሱ ሊያደርግ ምንም አይችልም፤ ያ የሚያደርገውን ሁሉ ወልድ ደግሞ ይህን እንዲሁ ያደርጋልና።

“እግዚአብሔር አባቴ ነው፡”  ብሎ ስላለ አይሁድ ሊገድሉት አብዝተው ይፈልጉት ነበር ይላል::  ለምን ቢባል አስርቱ ትዕዛዛት ለእነርሱ ከባድ ነገር ነውና::  አምላክህን ብቻ አምልክ ወይም እርሱን በፍፁም ማንነትህ  ውደድ በምንም ምስል እንዳትመስለው ተብለው እያለ ይህ ሰው እኔ የእግዚአብሔር ልጅ ነኝ ብሎ እራሱን ሲያቀራርብ አልዋጥላቸው አለ::  እንዲያውም ሊገድሉት ፈለጉ::  አይፈረድባቸውም በእነርሱ ቤት ለጌታቸው  መቆማቸውን ነው የሚያዩት:: በመካከላቸው የቆመው ማን እንደሆነ አላወቁም::

ስለዚህ ኢየሱስ መለሰ፥ እንዲህም አላቸው፦ “እውነት እውነት እላችኋለሁ፥ አብ ሲያደርግ ያየውን ነው እንጂ ወልድ ከራሱ ሊያደርግ ምንም አይችልም::  ይህ ማለት ግን  በዮሐንስ 15:5፤ እኔ የወይን ግንድ ነኝ እናንተም ቅርንጫፎች ናችሁ። ያለ እኔ ምንም ልታደርጉ አትችሉም ካለው ጋር እንዳናስተያየው ምክንያቱም በዮሐንስ 10:30፤ እኔና አብ አንድ ነን።” ብሏል::  ልጅ ነኝ በማለቱ የተቆጡት ሰዎች እርሱ እግዚአብሔር መሆኑን ባወቁ:: እግዚአብሔር መንፈስ ነው አብን ለብቻ ወልድን ለብቻ መንፈስ ቅዱስን ለብቻ እንዳናይ ምክንያቱም ለጭንቅላታችን ያ ይመቸዋል::  አምላካችን በሶስትነት የተገለጠ አንድ አምላክ ነውና::  ዛሬም በእኛ ውስጥ ያለው መንፈስ ቅዱስ እርሱ እግዚአብሔር ነው::  እርሱ በእኛ ውስጥ ሆኖ ተቀባይነትን እንዳገኘንና ልጅ እንደሆንን ይመሰክርልናል::  እርሱ ልጅ ካለን የሚሽር ማነው?! ግን ከአምላካችን ጋር አንስተያይም እንዳንዳንድ የስህተት ትምህርት::  የእርሱ በእኛ በመኖር  ነው ለውጥን ያመጣው::  እርሱን እናብለጭልጨው!  እየሱስ ይታይ መንፈስ ቅዱስም ይስራና ይግለጠው::  

አባት ሆይ በዚህ ምድር ያለነው የአንተን ስራ ለመስራት ነውና መንፈስ ቅዱስ በሙላት የመንግስትህን ዓላማ በእኛ ፈጽም:: እየሱስንም አክብረው ያለ አንተ አንዳች ማድረግ አንችልምና::

ዮሐንስ 5: 20-23

20፤ አብ ወልድን ይወዳልና፥ የሚያደርገውንም ሁሉ ያሳየዋል፤ እናንተም ትደነቁ ዘንድ ከዚህ የሚበልጥ ሥራ ያሳየዋል።

21፤ አብ ሙታንን እንደሚያነሣ ሕይወትም እንደሚሰጣቸው፥ እንዲሁ ወልድ ደግሞ ለሚወዳቸው ሕይወትን ይሰጣቸዋል።

22-23፤ ሰዎች ሁሉ አብን እንደሚያከብሩት ወልድን ያከብሩት ዘንድ፥ ፍርድን ሁሉ ለወልድ ሰጠው እንጂ አብ በአንድ ሰው ስንኳ አይፈርድም። ወልድን የማያከብር የላከውን አብን አያከብርም።

አብ ወልድን ይወዳልና እንደሚል ወልድን በወደደበት ፍቅር እኛንም ወደደን!  በዮሐንስ 17:26፤ እኔንም የወደድህባት ፍቅር በእነርሱ እንድትሆን እኔም በእነርሱ፥ ስምህን አስታወቅኋቸው አስታውቃቸውማለሁ።”

አብ ለወልድ የሚያደርገውንም ሁሉ ያሳየዋል፤ እናንተም ትደነቁ ዘንድ ከዚህ የሚበልጥ ሥራ ያሳየዋል። እኔና አብ አንድ ነን እኔን ያየ አብን አየ እያለን መልሶ ደግሞ እርሱ ነው የሚያሳየኝ ለምን ይላል?  እየሱስ እራሱን ባዶ አድርጎና የባርያን መልክ ይዞ ክብሩን ሁሉ ጥሎ መጣና ሰው ሆነ ስለዚህም በእግዚአብሔርና በሰው ፊት አደገ እንደሚል::  ምን አይነት ፍቅር ነው ሁሉን አስጥሎ የሚያስመጣ?  እየሱስ እግዚአብሔር ነው::   አብ የሚያደርገውን ሁሉ ወልድም ያደርጋል:: ህይወትን የሚሰጥ የህይወት ምንጭ ነውና::

ፍርድ ሁሉ  ለወልድ ተሰጠው በሰው ልጅ ላይ የሚፈርድ እርሱ ነው::  ከዚህም ፍርድ በደሙ ዋጅቶ አተረፈን የእርሱ ፅድቅ ለእኛ ተቆጠረ!!  በአጭሩ ወልድን የማያከብር የላከውን አብን አያከብርም። እርሱ ከአብ ተልኮ ወደእኛ መቷልና!

አባት ሆይ ተመስገን ስለእኛ ብለህ ክብርህን ጥለህ እራስህንም ባዶ አድርገህ በእንጨት ላይ ተሰቅለህ የእርግማንን ሞት  ስለእኛ ሞተህ የታደከን ከፍርድ ያስመለጥከን እጅግ የወደድከን ጌታ ነህና ተባረክ!!!!!

ዮሐንስ 5: 24-29

24፤ እውነት እውነት እላችኋለሁ፥ ቃሌን የሚሰማ የላከኝንም የሚያምን የዘላለም ሕይወት አለው፥ ከሞትም ወደ ሕይወት ተሻገረ እንጂ ወደ ፍርድ አይመጣም።

25፤ እውነት እውነት እላችኋለሁ፥ ሙታን የእግዚአብሔርን ልጅ ድምፅ የሚሰሙበት ሰዓት ይመጣል እርሱም አሁን ነው፤ የሚሰሙትም በሕይወት ይኖራሉ።

26፤ አብ በራሱ ሕይወት እንዳለው እንዲሁ ደግሞ ለወልድ በራሱ ሕይወት እንዲኖረው ሰጥቶታልና።

27፤ የሰው ልጅም ስለ ሆነ ይፈርድ ዘንድ ሥልጣን ሰጠው።

28-29፤ በመቃብር ያሉቱ ሁሉ ድምፁን የሚሰሙበት ሰዓት ይመጣል፤ መልካምም ያደረጉ ለሕይወት ትንሣኤ ክፉም ያደረጉ ለፍርድ ትንሣኤ ይወጣሉና በዚህ አታድንቁ።”

ቃሉ የከበረ ነው:: ቃሌን የሚሰማ የላከኝንም የሚያምን 

     የዘላለም ሕይወት አለው፥ 

     ከሞትም ወደ ሕይወት ተሻገረ 

     ወደ ፍርድ አይመጣም።

ይህ የሆነልን ነገር እንጂ ገና የሚህን ጊዜ የሚጠብቅ ነገር አይደለም:: ህይወት ተሰጠን ፍርድ ተነሳልን ሞትም ከእኛ ተለየ በስብከት ሞኝነት ቃሉን ሰምተን አምነን ተቀበልን!  ስሙ ይባረክ!

በዚህ ምድር የሚኖሩ ሰዎች ክርስቶስን ካላወቁ የእግዚአብሔር ቃል ሙታን ነው የሚይላቸው::  ስለዚህም ሙታን የእግዚአብሔርን ልጅ ድምፅ የሚሰሙበት ሰዓት ይመጣል እርሱም አሁን ነው፤ የሚሰሙትም በሕይወት ይኖራሉ። እርሱ ወደ ምድር በመምጣቱ ይህ ለውጥ መጣ::  ሙታን ድምጹን ሰምተው በህይወት መኖር:: ይህም የሆነው አብ በራሱ ሕይወት እንዳለው እንዲሁ ደግሞ ለወልድ በራሱ ሕይወት እንዲኖረው ሰጥቶታልና። ስለዚህ እየሱስ ህይወትን ሰቶን ሙታንን ወደእኔ አምጡ በህይወት እንዲኖሩ አለን::

እየሱስ ወደዝች ምድር የመጣው ሊፈርድ ሳይሆን ሊያድን ነው በማይቀበሉትላይ ግን በስራቸው ይፈርዳል የእግዚአብሔርን ደረጃ የሚያሟላ ስለማይኖር ሁሉ ወደ ሁለተኛ ሞት ይሄዳል::  እየሱስ የሰው ልጅም ስለ ሆነ ይፈርድ ዘንድ ሥልጣን ሰጠው። በስተመጨረሻ ክርስቶስን ያላወቀ ይፈረድበታል አሁንም ተፈርዶበታል ይላል ቃሉ::

በዚህም ፍርድ በመቃብር ያሉቱ ሁሉ ድምፁን የሚሰሙበት ሰዓት ይመጣል፤ መልካምም ያደረጉ ለሕይወት ትንሣኤ ክፉም ያደረጉ ለፍርድ ትንሣኤ ይወጣሉና በዚህ አታድንቁ።”

አባት ሆይ ከፍርድ ስላዳንከን ህይወትን ስለሰጠኸን ተመስገን!  ሙታን ለሆኑት ግን ላላወቁት አንተን ማሳየት ይሁንልን በአንድ ኃጥያተኛ መዳን አንተ ትደሰታለህና ምርኮን ስጠን::  የሚሰሙበትንም የተከፈተ ልብ ስጣቸው::  አሜን

ዮሐንስ 5: 30-32

30፤ “እኔ ከራሴ አንዳች ላደርግ አይቻለኝም፤ እንደ ሰማሁ እፈርዳለሁ ፍርዴም ቅን ነው፥ የላከኝን ፈቃድ እንጂ ፈቃዴን አልሻምና።

ዮሐንስ 5:31፤ እኔ ስለ እኔ ስለ ራሴ ብመሰክር ምስክሬ እውነት አይደለም፤

ዮሐንስ 5:32፤ ስለ እኔ የሚመሰክር ሌላ ነው፥ እርሱም ስለ እኔ የሚመሰክረው ምስክር እውነት እንደ ሆነ አውቃለሁ።

ጌታ የአብን ፈቃድ ነበረ ሲያደርግ  የነበረው ከእኛም የሚጠበቀው አንዳች ማድረግ የማንችል መሆናችንን አውቀን በእርሱ ላይ እንደገፍና ፈቃዱን እናድርግ::  ፍርድም ለእየሱስ ተሰቶታል ምክንያቱም የሰው ልጅ ስለሆነ የሚፈርደውም እሰማ ነው::  ይህ ማለት ግን እየሱስ አምላክ መሆኑን እንወቅ!!  እርሱ እግዚአብሔር ነው::  ሁሉን ማድረግ የሚችል ነው ሌሎች ኃይማኖቶች እየሱስ አምላክ አይደለም የሚሉት ከዚህ እየተነሱ ነው::  እኛም አስረግጠን ማወቅ ያለብን ስለእርሱ ስንመሰክር እራሱን ባዶ አድርጎ መምጣቱን ነው እንጂ እኔና አብ አንድ ነን ማለቱንም ማወቅ አለባቸው::

ስለራሱ ምንም አይመሰክርም አብ ስለወልድ ይመሰክራል ምስክሩም እውነተኛ ነው:: የሰው ምስክር እየሱስ አላስፈለገውም::  ማንም እንዲያጸድቅለት አገልግሎቱን አላስፈለገውም በ12 ሰዎች ዓለምን ገለባብጦ ሄደ::  የዘመኑ አገልጋዮች አልተቀበሉትም እርሱም አልጠበቀምም አላስፈለገውምም::  ዛሬም ሰዎች ባይቀበሉን የእነርሱን መስማማት ከመጠበቅ ከጌታ ጋር እንስማማ::  የማንም ምስክርነት አያስፈልገንም የሚያስፈልገን የሰማይ ምስክርነት ነው::  ከእርሱ ጋር ከተስማማንና ከታዘዝን በቂ ነው::  ለነገሩ ከሰራንም በራሳችን አንሰራ የሚሰራው መንፈስ ቅዱስ ነው::   በራሳችን አንዳች ማድረግ የማንችል በወይኑ ግንድ ላይ የተጣበቅን ቅርንጫፎች ነን::

አባት ሆይ ፈቃድህን በዘመኔ ሁሉ አደርግና እታዘዝ ዘንድ እርዳኝ::  የሰውን ምስክርነት ስፈልግ አንተ የሰጠኸኝን እንዳልጥል ጸጋ አብዛልኝ!  አሜን

ዮሐንስ 5: 33-42

ይህንን ሁሉ እየነገራቸው ያለው በመጠመቅያው ስፍራ ከፈወሰው ሰው በተነሳ ነው:: እየሱስ የሰው ምስክርነትን አይፈልግም አብ መስክሮለታል::  እናንተ ወደ ዮሐንስ ልካችኋል እርሱም ለእውነት መስክሮአል። እኔ ግን ከሰው ምስክር አልቀበልም፥ እናንተ እንድትድኑ ይህን እላለሁ እንጂ አላቸው። ምንም እንኳን ዮሃንስ የመሰከረ ቢሆንም ምስክርነቱንም አልተቀበሉም::  ሌላው የሚመሰክርለት ቃሉ ነው::  ሙሴ ጽድፎላቸዋልና በዘዳ 31 :21 

የአብ ምስክርነት የምወደው ልጄ በእርሱ ደስ የሚለምኝ ብሏል::  እየሱስ የመጣው ተልኮ አባቱን ደስ ለማሰኘትና እኛን ለመታደግ ነው::  የኖረው ሁሉ የአባቱን ፈቃድ በማድረግ ነው::  ይህች ጽዋ ከእኔ ትለፍ ብሎ ነበር ከፊቱ ያለው አስፈሪ ስለነበረ ነገር ግን የአንተ ፈቃድ ይሁን ብሎ ታዘዘ::

የሚገርመው እነዚህ ሰዎች ቃሉን ጥጥት አድርገዋል ነገር ግን ህይወት አልሆነላቸውም::  መጻሕፍትን ካላመናችሁ ግን ቃሌን እንዴት ታምናላችሁ?” ጌታም እንዳለው:- እናንተ በመጻሕፍት የዘላለም ሕይወት እንዳላችሁ ይመስላችኋልና እነርሱን ትመረምራላችሁ፤ እነርሱም ስለ እኔ የሚመሰክሩ ናቸው፤  ነገር ግን ሕይወት እንዲሆንላችሁ ወደ እኔ ልትመጡ አትወዱም።  ህይወት እንዲሆነን ወደ ህይወታችን የጋበዝነው ጌታ ስሙ ይባረክ እንደቃሉ ህይወትን ሰቶናልና::

እራሱን ዝቅ አድርጎ ስለመጣ የህይወትን ጌታ ሊያውቁት አልቻሉም::  ህይወትንም ፍለጋ ወደ እርሱ አልመጡም::  ዝቅ ብሎ ቢመጣም እንኳን ዛሬ መንፈስ ቅዱስ ከፍ ከፍ እያደረገው ስለእርሱ ብቻ ያሳያል::  

አባት ሆይ ክበር ተመስገን! ልትከብር የተገባህ ህይወትን የሰጠኸን ጌታ ዛሬም ክበር::  ጌታ የምትከበርበት ጊዜ ነውና ክበር::

ዮሐንስ 5:43 – 47

5:43፤  እኔ በአባቴ ስም መጥቻለሁ አልተቀበላችሁኝምም፤ ሌላው በራሱ ስም ቢመጣ እርሱን ትቀበሉታላችሁ።

5:44፤ እናንተ እርስ በርሳችሁ ክብር የምትቀባበሉ ከአንዱም ከእግዚአብሔር ያለውን ክብር የማትፈልጉ፥ እንዴት ልታምኑ ትችላላችሁ?

45፤ እኔ በአብ ዘንድ የምከሳችሁ አይምሰላችሁ፤ የሚከሳችሁ አለ፤ እርሱም ተስፋ የምታደርጉት ሙሴ ነው።

46፤ ሙሴንስ ብታምኑት እኔን ባመናችሁ ነበር፤ እርሱ ስለ እኔ ጽፎአ ልና።

47፤ መጻሕፍትን ካላመናችሁ ግን ቃሌን እንዴት ታምናላችሁ?”

ጌታ እየሱስ በምድር ሲመላለስ ያደረገው ሁሉ የአባቱን ፈቃድ ማድረግ ነበረ::  እኛም ከሁሉ በፊት ፈቃዱን መታዘዝ ይሁንልን::  ቃሉ ከእኛ ጋር በእምነት ይዋሃድ እንጂ እዚህ ክፍል ላይ እንደሚናገረው መጽሐፍትን ትመረምራላችሁ እነርሱም ስለእኔ ይናገራሉ ነገር ግን ሕይወት እንዲሆንላችሁ ወደ እኔ ልትመጡ አትወዱም  አላቸው::  እንዲያውም እኔ በአብ ዘንድ የምከሳችሁ አይምሰላችሁ፤ የሚከሳችሁ አለ፤ እርሱም ተስፋ የምታደርጉት ሙሴ ነው አላቸው::  ምን አይነት መተላለፍ ነው::  ዛሬም ልባቸው እስኪጠፋ የተከተሉት መስሏቸው የተላለፉ ስንቶች አሉ?  የእኛ ስራ ስለእነርሱ መፀለይ ነው::  መጋረጃው ይነሳላቸውና የክብርን ጌታ ይዮት::

ያልተላለፍን እኛ ወደ እርሱ በመጠጋት በቀንም በለሊትም ቃልና ህይወት ከሆነው ከእየሱስ ጋር ህብረትን ማድረግ ይሁንልን::  አለበለዝያ ግን ውሃ የሌለው ዳመና ከሆነብን ቃሉ ምን ያደርጋል? ቃሉ ዘንቦ የደረቀውን ካላጠጣና ህይወት ካላበበ?  ካለንበት ካላወጣን? ወይም ከመከራችን ካላዳነን? ከእኛ ጋር አልተዋሃደም ማለት ነው::  ስለዚህ ከወይኑ ግንድ ጋር እንጣበቅ እርሱ የሚሰጠውን ውሃ እንጠጣ  ዳግመኛም አንጠማም::  አሜን!

አባት ሆይ ጸጋን ስጠን ለሳቱት የምንማልድበትንና ፈቃድህን ማድረግ!

ዮሐንስ 6:1 -15

የፋሲካ በዓል ደርሶ እያለ ኢየሱስ ወደ ገሊላ ባሕር ማዶ ተሻገረ በዚያም  ብዙ ህዝብ ተሰበሰቡ::  እርሱም አስተማራቸው ፈወሳቸውና ሊመግባቸው ፈለገ::  ፊልጶስን፦ “እነዚህ እንዲበሉ እንጀራ ከወዴት እንገዛለን?” አለው። 

ፊልጶስም የተጠየቀው ከወዴት እንግዛ ነበረና ዋጋውን ማስላት ጀመረ::  ነገር ግን በቃና ዘገሊላ እብረውት ነበሩ ውሃውን ወይንጠጅ ሲያደርገው::  ቢያንስ አንተ ታውቃለህ ጥሩ መልስ ነበረ እርሱ ግን ያለውን ነገር የምድሩን ካልኩሌሽን ቀጠለና፦ “እያንዳንዳቸው ትንሽ ትንሽ እንኳ እንዲቀበሉ የሁለት መቶ ዲናር እንጀራ አይበቃቸውም፡” ብሎ መለሰለት። እየሱስ ግን ሊያደርግ ያለውን ያውቅ ነበርና ሊፈትነው ይህን ተናገረ።

የእኛስ መልስ ምን ይሆን? ፈተናውን እናልፍ ይሆን?  ጌታ አንዳች አጥቶ ከእኛ እርዳታ አይፈልግም አብረነው እንድንሰራ እንጂ::  ትላንትና ስንቱን አሻገረን?!  እርሱ አይለወጥም ዛሬም በስራ ላይ ነው::

ሰይጣን እየሱስን ፈትኖት ይህንን  ድንጋይ ዳቦ አድርግ ብሎት ነበረ እርቦት እያለ ለራሱ አላደረገም::  እዚህ ጋር ግን ህዝቡን ለመርዳት ተአምራትን አደረገ::  እጁ የገባው ዳቦና አሳ ነው::  ዳቦን ስናስበው እህሉ ወደ ዱቄትነት ተለውጧል ብንዘራው አይበቅልም አሳውም እንደዛው ከውሃ ወቶ ሞቷል::  ከህግ ውጪ ነው ይህንን ማብዛት::  ለእየሱስ ግን የተፈጥሮ ህግ ምንም አይደለምና ዳቦውንና አሳውን ቆርሶ አመስግኖ ሰጣቸው::  ልክ ሲሰጣቸው ተቆለለ አይልም ቃሉ ታድያ እንዴት በዛ?! እራሳችንን እንጠይቅ:  እያንዳንዱ ደቀ መዝሙር ቁራሽ ዳቦና ቁራሽ አሳ ነበረ  የደረሰው ለህዝቡ ለማደል::  አምነው ግን መስጠት ሲጀምሩ አላለቀም ለሁሉም አዳረሱ::  የእኛ አምላክ ህግ አይዘውም!!!!  እርሱ ዛሬም ድንቅንና ተአምራትን ያደርጋል ያለ እምነት ግን እግዚአብሔር ደስ ማሰኘት አይቻልም!  አሜን!

የተከተልነው አምላክ ትልቅ ነው በዝች ትንሽ አእምሯችን አናሳንሰው ሊያደርግ ያለውን ሁሉ ያድርግ!

አባት ሆይ እንዳትሰራ ባላመንኩትና ባገድኩህ ሁሉ ይቅር  በለኝ::  አንተ ያሰብከው ብቻ ይሁን ከአንተ ጋር እስማማለሁ::  ጸጋን ስጠን! 

ዮሐንስ 6: 16-21

ዮሐንስ 6:18፤ ብርቱ ነፋስም ስለ ነፈሰ ባሕሩ ተናወጠ።

ዮሐንስ 6:19፤ ሀያ አምስት ወይም ሠላሳ ምዕራፍ ከቀዘፉ በኋላም፥ ኢየሱስ በባሕር ላይ እየሄደ ወደ ታንኳይቱ ሲቀርብ አይተው ፈሩ።

20፤ እርሱ ግን፦ “እኔ ነኝ፤ አትፍሩ፡” አላቸው።

ወደ ባህርማዶ ተሻገሩ ብሎ እርሱ ግን ለፀሎት ወደኃላ ቀረ::  አብዛኛው ደቀመዛሙርቱ አሳ አጥማጅ ስለነበሩ ብዙም አላሳሰባቸው ወደ ማዶ መሻገሩ::   ብዙ ጊዜ ያጠመዱበት ባህር ነው ምን ይሆናልና ብሉው ይስጉ:: ትንሽ እንደቀዘፉ ማዕበል አስቸገራቸው::  ይህንንም ያይ ነበር ጌታእየሱስ እንዲያውም ማርቆስ እንደሚነግረን አልፎ የሚሄድ መሰለ ነው ያለው ምክንያቱም ተሻገሩ ብሏቸዋልና ይህ ማዕበል ግን ሲታገላቸው አደረ::  በምናልፍበት ሁሉ ጌታ በዛ አለ::  ከዚህ በፊት በጀልባው ውስጥ ተኝቶ ማዕበል ገጥሟቸው ነበረ ነገር ግን ንፋሱን ሲገስጽ ቆመ::  እዚህ ስፍራ ላይ ግን የተለየ ነው ያደረገው “እኔ ነኝ፤ አትፍሩ፡” ነው ያላቸው።  ያን ጊዜም ማዕበሉ ቆመ::

ሲመጣም ወደእነርሱ በባህር ላይ እየተራመደ ነው የመጣው እኛን የሚያስቸግር እርሱን አያስቸግረውም::  እኛን የሚቋቋም እርሱን አይቋቋምም::  እኔ ነኝ ሲል ሁሉ ይስተካከላል::  አንዳንዴ ፈቃዱን እያደረግን በመንገድ መዘግየት አለ::  ጠላት ይዋጋል ፈቃዱን ማድረግ መንገዳችንን አልጋ ባልጋ አያደርገውም:: ጳውሎስና ሲላስ ተገርፈው ከግንድም ተጠርቀው ያደሩት በፈቃዱ እየሄዱ ሳለ ነው::  ምን ጠላት ቢጠበብና ቢበረታ ድሉ የጌታ ነው ወዳለው ፈቃድ መድረሳችን አይቀርምና እንበርታ::  እርሱ ከአሸናፊዎች በላይ አድርጎናል::

አባት ሆይ በማልፍበት ሁሉ አንተ ከእኔ ጋር ስላለህ ተመስገን::  ስጋቴን ሁሉ በአንተ ላይ እጥላለሁ!  እሻገራለሁ ያየኸውንም እወርሳለሁ!

ዮሐንስ 6: 22-29

26፤ ኢየሱስም መልሶ፦ “እውነት እውነት እላችኋለሁ፥ የምትፈልጉኝ እንጀራን ስለ በላችሁና ስለ ጠገባችሁ ነው እንጂ ምልክቶችን ስላያችሁ አይደለም።

27፤ ለሚጠፋ መብል አትሥሩ፤ ነገር ግን ለዘላለም ሕይወት ለሚኖር መብል የሰው ልጅ ለሚሰጣችሁ ሥሩ፤ እርሱን እግዚአብሔር አብ አትሞታልና።”

29፤ ኢየሱስ መልሶ፦ “ይህ የእግዚአብሔር ሥራ እርሱ በላከው እንድታምኑ ነው፡” አላቸው።

በትናንትናው አገልግሎቱ እንጀራ ስላበላቸው ሁሉም ይፈልጉት ጀመር::  ፈልገው ፈልገው ሲያገኙት መቼ  ወደዚህ መጣህ አሉት በጀልባ  እንዳልተሳፈረ  አውቀው ነበረና::  መልሱም መሆን የነበረበት ልክ ነው እዛው ነበርኩኝ ኃዋርያት በማዕበል ሲጨነቁ አይቼ ልታደጋቸው በውሃው/ በማዕበሉ ላይ እየተራመድኩ ነው የመጣሁት ማለት ነበረበት::  እርሱ ግን የመለሰላቸው የምትፈልጉኝ እንጀራን ስለ በላችሁና ስለ ጠገባችሁ ነው እንጂ ምልክቶችን ስላያችሁ አይደለም። እንዲያውቁ የፈለገውን ሙሉ ቀን ሲያስተምር የዋለውን ትተው የያዙት የሆዳቸውን ብቻ ነበረ:: ያ ሁሉ ፈውስና ተአምራት ሲደረግ የዋለውን መሲህ ብቻ የሚያደርገውን አላስተዋሉም::  ለእኛም ማስተዋልን ይስጠን በተደረገው ነገር ላይ ሳይሆን በአድራጊው ላይ አይናችን እንዲሆን::

ሌላው ጌታ እንዲያውቁ የፈለገው ለሚጠፋ መብል እንዳይሰሩ ነው::  አይናቸውን ወደ አዳኙ አድርገው  ለዘላለም ሕይወት ለሚኖር መብል የሰው ልጅ ለሚሰጣችሁ ሥሩ፤ እርሱን እግዚአብሔር አብ አትሞታልና።” አላቸው::  ስራ ብሎ ስላለ ምን እንስራ አሉ ቶሎ ምክንያቱም ሰርቶ መፅደቅ ነው ሰው ሁሉ የሚፈልገው:: እርሱ ግን  “ይህ የእግዚአብሔር ሥራ እርሱ በላከው እንድታምኑ ነው፡” አላቸው። እኛም የዳነው እርሱ በላከው በማመን ነው:: 

አባት ሆይ በአንተ በማመን መዳንን አገኘን በጨለማ ላሉት ሳንፈርድ ወንጌልን እናደርስ ዘንድ እርዳን! አሜን

ዮሐንስ 6: 30-34

30፤ እንግዲህ፦ “እንኪያ አይተን እንድናምንህ፡ አንተ ምን ምልክት ታደርጋለህ? ምንስ ትሠራለህ?

31፤ ‘ይበሉ ዘንድ ከሰማይ እንጀራ ሰጣቸው፡’ ተብሎ እንደ ተጻፈ፡ አባቶቻችን በምድረ በዳ መና በሉ፡” አሉት።

32፤ ኢየሱስም አላቸው፦ “እውነት እውነት እላችኋለሁ፥ እውነተኛ እንጀራ ከሰማይ የሚሰጣችሁ አባቴ ነው እንጂ ከሰማይ እንጀራ የሰጣችሁ ሙሴ አይደለም፤

33፤ የእግዚአብሔር እንጀራ ከሰማይ የሚወርድ ለዓለምም ሕይወትን የሚሰጥ ነውና።”

35፤ ኢየሱስም እንዲህ አላቸው፦ “የሕይወት እንጀራ እኔ ነኝ፤ ወደ እኔ የሚመጣ ከቶ አይራብም፡ በእኔ የሚያምንም ሁልጊዜ ከቶ አይጠማም።

ይህ የእግዚአብሔር ሥራ እርሱ በላከው እንድታምኑ ነው፡” ስላላቸው ምልክትን አሳየን? ይበሉ ዘንድ ከሰማይ እንጀራ ሰጣቸው፡’ ተብሎ እንደ ተጻፈ፡ አባቶቻችን በምድረ በዳ መና በሉ፡” አሉት::  እየሱስን በማወዳደር ሳምራይቱም ጠይቃ ነበር  አንተ ይህንን ውሃ ከሰጠን ከያዕቆብ ትበለጣለህን? እዚህ ክፍል ላይ ደግሞ ከሙሴ ትበልጣለህን? እርሱ መናን ሰጠ ለአባቶቻችን አሉት:: እንጀራን በልተው ስለነበረ የተከተሉት ዛሬም በመገበን ብለው ይመስላል::  የሚያነሱትም ምሳሌ ምግብ ነው (መና) ነው:: 

እየሱስም ሲመልስ የጠየቁት ስለእንጀራ ነውና እውነት እውነት እላችኋለሁ፥ እውነተኛ እንጀራ ከሰማይ የሚሰጣችሁ አባቴ ነው እንጂ ከሰማይ እንጀራ የሰጣችሁ ሙሴ አይደለም፤ ያወዳደሩት ከሙሴ ጋር ነበረ::  ሙሴ ምንም አላደረገም ያንን መና በየጠዋቱ ይሰጣቸው የነበረው እግዚአብሔር ነው አላቸው::  ዛሬም  በእኛ ህይወት አምላካችን ብቻ ነው ረድኤታችን::

እንዲያውም ስለእንጀራ ካነሳችሁማ ይህንን እወቁ ብሎ:- የእግዚአብሔር እንጀራ ከሰማይ የሚወርድ ለዓለምም ሕይወትን የሚሰጥ ነው። አሜን! ሙሴ የሰጠው እንጀራ ለነገ አይሆንም ነገም ይርባል ይኼኛው ግን የህይወት እንጀራ ለዘላለም ነው:: ሁልጊዜ የሚያረካ!  ሃሌሉያ!

ይህንን እንጀራ ስጠን አሉት::  ሳምራይቱም ይህንኑ ብላለች ይህንን ውሃ ስጠኝ::  የሕይወት እንጀራ እኔ ነኝ፤ ወደ እኔ የሚመጣ ከቶ አይራብም፡ በእኔ የሚያምንም ሁልጊዜ ከቶ አይጠማም። አሜን እየሱሴ!  የህይወት እንጀራ ነው የምትፈልጉት እይኸው እኔ ነኝ አላቸው::  ስለማንነቱ ነገራቸው ስለመሲህነቱ የገባው ግን የለም::  እኔም ያወኩህ በራሴ ጥበብ ሳይሆን በመንፈስ ቅዱስ እርዳታ ነውና ተመስገንልኝ! ላልገባቸው የማስታረቅን አገልግሎት ሰተኸኛልና የምመሰክርበት ጸጋ ይብዛልኝ! 

አባት ሆይ አንተ የህይወት እንጀራዬ የህይወትም ውሃዬ ሆነሃል ተመስገን!  ከቶም አልራብም አልጠማምም!! ጽድቄ ፤  ቅድስናዬ፤  የለበስኩህ ልብሴ በአብ ፊት መታያዬ ፤ ህይወቴ ፤  ሁሉ በሁሉዬ ሆንክልኝ!!  እባርክሃለሁ!

ሃሌሉያ አሜን!!!

ዮሐንስ 6: 41-51

41፤ እንግዲህ አይሁድ፦ “ከሰማይ የወረደ እንጀራ እኔ ነኝ፡” ስላለ ስለ እርሱ አንጐራጐሩና፦

42፤ “አባቱንና እናቱን የምናውቃቸው ይህ የዮሴፍ ልጅ ኢየሱስ አይደለምን? እንግዲህ፦ ከሰማይ ወርጃለሁ፡ እንዴት ይላል?” አሉ።

43፤ ኢየሱስ መለሰ አላቸውም፦ “እርስ በርሳችሁ አታንጐራጕሩ።

44፤ የላከኝ አብ ከሳበው በቀር ወደ እኔ ሊመጣ የሚችል የለም፥ እኔም በመጨረሻው ቀን አስነሣዋለሁ።

ጌታ እየሱስ ደግሞ ደጋግሞ  የሚነግራቸው እውነት እዚህ ስፍራ ላይ እርሱ የህይወት እንጀራ እንደሆነ በእርሱም የሚሆን የዘላለም ህይወት እንደሚኖረው እንደማይጠፋና ለዘላለም እንደሚኖር ነው::  ይህም የአባቴ ፈቃድ ነው አላቸው የሰው ልጅ ሁሉ በእርሱ እንዲያምን ስለዚህም ይህንን የአብን ፈቃድ እያደረኩኝ ነው አላቸው::  እነርሱ ግን ይሰናከሉበት ጀመር::  አባቱንና እናቱን የምናውቃቸው ይህ የዮሴፍ ልጅ ኢየሱስ አይደለምን? እንግዲህ፦ ከሰማይ ወርጃለሁ፡ እንዴት ይላል?” አሉ። ተሰናከሉ::  በመካከላቸው የቆመው ማን እንደሆነም አላወቁም! ሁሉም ከእግዚአብሔር የተማሩ ይሆናሉ ተብሎ በነቢያት ተጽፎአል እንደሚክል ይህንን እውነት በራሳችን አላወቅንም በጌታ ጸጋ እንጂ! ከእግዚአብሔር ከሆነ በቀር፥ እርሱ አብን አይቶአል። ይላል ቃሉ በክርስቶስ ወደ አብ ቀረብን::

አብ ምን አደረገ ወልድስ?

አብ:-

የላከኝ አብ ከሳበው በቀር ወደ እኔ ሊመጣ የሚችል የለም፥- ወደ እየሱስ የሳበን አብ ይባረክ!!

ከአብ የሰማ የተማረም ሁሉ ወደ እኔ ይመጣል:- ወደ ህይወት ራስ የደረስነው ከአብ መስማት ስለቻልን ነው! ከእኛ የሆነ ምንም የለም!

ወልድ:-

እኔም በመጨረሻው ቀን አስነሣዋለሁ።

በእኔ የሚያምን የዘላለም ሕይወት አለው።

የሕይወት እንጀራ እኔ ነኝ

ሰው ከእርሱ በልቶ እንዳይሞት ከሰማይ አሁን የወረደ እንጀራ ይህ ነው።

ከሰማይ የወረደ ሕያው እንጀራ እኔ ነኝ፤

የሚበላ እንጀራ

ሰው ከዚህ እንጀራ ቢበላ ለዘላለም ይኖራል፤ እኔም ስለ ዓለም ሕይወት የምሰጠው እንጀራ ሥጋዬ ነው።” 

አሜን! 

አባቴ ሆይ የዘላለምን ህይወት ስለሰጠኸኝ አመሰግንሃለሁ!  የህይወት እንጀራ አንተ ነህ አንተን ወደ ህይወቴ አስገብቻለሁና ለዘላለም አልራብም አልጠማምም!

ዮሐንስ 6: 52-59

ስለዚህ ኢየሱስ እንዲህ አላቸው፦ “እውነት እውነት እላችኋለሁ፥

   * የሰውን ልጅ ሥጋ ካልበላችሁ 

     ደሙንም ካልጠጣችሁ በራሳችሁ  

     ሕይወት የላችሁም።

   * ሥጋዬ እውነተኛ መብል፡ ደሜም 

      እውነተኛ መጠጥ፡ ነውና።

  *  ሕያው አብ እንደ ላከኝ እኔም ከአብ 

     የተነሣ ሕያው ነኝ፥ እኛም ከእርሱ 

     የተነሳ ህያዋን ሆንን

ሥጋዬን የሚበላ ደሜንም የሚጠጣ :-

  – የዘላለም ሕይወት አለው፥ 

  – እኔም በመጨረሻው ቀን አስነሣዋለሁ

  –  በእኔ ይኖራል፡ 

  –  እኔም በእርሱ እኖራለሁ።

  –  የሚበላኝ ደግሞ ከእኔ የተነሣ ሕያው 

      ይሆናል።

  – ይህን እንጀራ የሚበላ ለዘላለም   

      ይኖራል።

ይህንን ከሰማይ የወረደ እንጀራ መብላት እንደእስራኤሎቹ ያለ መና አይደለም እነርሱ በልተው ሞቱ ይኼኛው ግን ህይወትን የሚሰጥ ነው::፤

የቀረልኝ:-

1. በራሴ ህይወት የለኝም

2. እውነተኛ መብልና መጠጥ ለህይወቴ 

    እየሱስ ነው

3. ለዘላለም እንድኖር ይፈልጋል

4. በእርሱ እኖራለሁ

5. ህያው ነኝ

6. ትንሳኤን ይሰጠኛል

አብ አባት ሆይ አመሰግንሃለሁ!  ልጅህን ልከህ ሞቴን ሞተልኝ::  የዘላለምንም  ህይወት አገኘሁ!  ተባረክ!!

ዮሐንስ 6: 60-71

62፤ እንግዲህ የሰው ልጅ አስቀድሞ ወደ ነበረበት ሲወጣ ብታዩ እንዴት ይሆናል?

63፤ ሕይወትን የሚሰጥ መንፈስ ነው፤ ሥጋ ምንም አይጠቅምም፤ እኔ የነገርኋችሁ ቃል መንፈስ ነው ሕይወትም ነው።

64፤ ነገር ግን ከእናንተ የማያምኑ አሉ።” ኢየሱስ የማያምኑት እነማን እንደ ሆኑ አሳልፎ የሚሰጠውም ማን እንደ ሆነ ከመጀመሪያ ያውቅ ነበርና።

65፤ ደግሞ አለ፦ “ስለዚህ አልኋችሁ፥ ከአብ የተሰጠው ካልሆነ ወደ እኔ ሊመጣ የሚችል የለም።”

ሕያው አብ እንደ ላከኝ እኔም ከአብ የተነሣ ሕያው እንደምሆን፥ እንዲሁ የሚበላኝ ደግሞ ከእኔ የተነሣ ሕያው ይሆናል ሲላቸው  ብዙዎች ተሰናከሉና ተመለሱ::  ጌታም ይህ ያሰናክላችኃል አላቸውና ይባስ ብሎ ወደ ሰማይ ሳርግ ብታዩ ምን ልትሉ ነው::  ማረጉንም  ቢሆን አይተዋል ከትንሳኤው በኃላ ነገር ግን ምንም ጭብጥ ያደረጉት ነገር አልነበረም:: 

ግራ የገባቸው ምክንያት መንፈሳዊዉን በስጋ ለመረዳት በመሞከራቸው ነው::  ስለዚህም ነው ጌታ ሕይወትን የሚሰጥ መንፈስ ነው፤ ሥጋ ምንም አይጠቅምም፤ እኔ የነገርኋችሁ ቃል መንፈስ ነው ሕይወትም ነው አላቸው:: ብዙዎች ግን ተሰናክለው ተመለሱ::  ዛሬም ሰዎች ይህንን እውነት መረዳት በስጋ ይሞክራሉ ይከብዳቸዋል::  እኛም ወደዛ እንዳንዳዳ በመንፈስ እንመላለስ – መንፈስ ህይወትን ይሰጣል::

ጴጥሮስም በመንፈስ ስምዖን “ጌታ ሆይ፥ ወደ ማን እንሄዳለን? አንተ የዘላለም ሕይወት ቃል አለህ፤ እኛስ አንተ ክርስቶስ የሕያው የእግዚአብሔር ልጅ እንደ ሆንህ አምነናል አውቀናልም፡” ብሎ መለሰለት። ሃሌሉያ!  በመንፈስ ትክክለኛውን ማንነቱን እናውቃለን አለበለዚያ ግን ግምት ነው የሚሆነው ከዚህ ደግሞ ያውጣን::  መንፈስ ዝግጁ ነው!

ስለዚህ አልኋችሁ፥ ከአብ የተሰጠው ካልሆነ ወደ እኔ ሊመጣ የሚችል የለም።” እኛ ከአብ ዘንድ ቸርነት ተደርጎልን በመንፈስ ማንነቱን ተረድተን ወደ እየሱስ መጣን እንጂ የተሻለ ማንነት ስላለን ወይም በሌላ ምክንያት አይደለም እርሱ ከሰማይ ቸርነትን ስላደረገልን ብቻ ነው::

ዮሐንስ 7: 1-9

6፤ ኢየሱስም እንዲህ አላቸው፦ “ጊዜዬ ገና አልደረሰም፥ ጊዜያችሁ ግን ዘወትር የተመቸ ነው።

ዮሐንስ 7:7፤ ዓለም እናንተን ሊጠላ አይቻለውም፤ እኔ ግን ሥራው ክፉ መሆኑን እመሰክርበታለሁና እኔን ይጠላኛል።

ዮሐንስ 7:8፤ እናንተ ወደዚህ በዓል ውጡ፤ እኔስ ጊዜዬ ገና ስላልተፈጸመ ወደዚህ በዓል ገና አልወጣም።”

የእየሱስ ወንድሞች አላመኑበትም ነበረና ለበዓሉ ውጣና ለዓለም እራስህን ግለጥ አሉት::  ግን እንዴት ከእየሱስ ጋር በአንድ ቤት አድጎ እርሱን አለማወቅ ይቻላል?!   ማርያም ግን የተነገራትን ሁሉ በልብዋ ትጠብቀው ነበር እንደሚል ለማንም አላካፈለችም ማለት ነው::  ይህ የሚያሳየው አብ ወደ ልጁ ካልሳበና መንፈስ ቅዱስ ካልገለጠልን በራሳችን እየሱስን ማወቅ  አንችልም::

ለወንድሞቹም ዓለም እናንተን ሊጠላ አይቻለውም፤ እኔ ግን ሥራው ክፉ መሆኑን እመሰክርበታለሁና እኔን ይጠላኛል። ይህ ነው የእኛም ስራ የዓለምን ክፉ ስራ መግለጥ ነው::  እኛ የዓለም ብርሃን ነን ከእየሱስ የተነሳ:: በዝች ጨለማ በወረሳት ዓለም ውስጥ ስንመላለስ ብርሃናችንን ከፍ አድርገን እያሳየን እንሂድ::  ብርሃንን አብርቶ ከአልጋ ስር ማድረግ የለም ጽድቅን እየገለጥን እንመላለስ::  በዚህ ምድር የመቆየታችን ሚስጥሩ ይግባን ይኸውም ብርሃኑን እንድናበራና የጨለማውን ስራ እንድንገልጥ ነው:: እንደ ቁጫጭዋ እንዳንሆን እኔና ዝሆን ድልድዮን ነቀነቅነው እንዳለችው::  እየሱስ ነው በእኛ ብርሃን ይብራ ብሎ እያበራ ያለው እርሱኑ እናሳይ::

አባት ሆይ

ተመስገን በእኔ ውስጥ የምታበራ ብርሃን ነህና::  አሁንም አንተን ለማብለጭለጭ ጸጋህን  ለኔና ለህዝብህ አብዛልን::

ዮሐንስ 7: 10-24

15፤ አይሁድም፦ “ይህ ሰው ሳይማር መጻሕፍትን እንዴት ያውቃል?” ብለው ይደነቁ ነበር።

16፤ ስለዚህ ኢየሱስ መለሰ፥ እንዲህም አላቸው፦ “ትምህርቴስ ከላከኝ ነው እንጂ ከእኔ አይደለም፤

23፤ የሙሴ ሕግ እንዳይሻር ሰው በሰንበት መገረዝን የሚቀበል ከሆነስ ሰውን ሁለንተናውን በሰንበት ጤናማ ስላደረግሁ ትቈጡኛላችሁን?

24፤ ቅን ፍርድ ፍረዱ እንጂ በመልክ አትፍረዱ።”

ወንድሞቹ ግን ወደ በዓሉ ከወጡ በኋላ በዚያን ጊዜ እርሱ ደግሞ በግልጥ ሳይሆን ተሰውሮ ወጣ ምክንያቱም አይሁድ ሊገድሉት ይፈልጉ ነበረና::  እየሱስ በራሱ  ጊዜ ወደ በዓሉ ታደመ::   በዛም ተገኝቶ ዝም ማለትና እንደሌላው መሆን አይችልምና ማስተማሩን ቀጠለ::

አይሁድም፦ “ይህ ሰው ሳይማር መጻሕፍትን እንዴት ያውቃል?” ብለው ይደነቁ ነበር። ያላወቁት እውነትቢኖር ቃሉን የሰጣቸው አምላኬ የሚሉት ጌታ በፊታቸው መቆሙን ነው:: ኢየሱስ መለሰ፥ እንዲህም አላቸው፦ “ትምህርቴስ ከላከኝ ነው እንጂ ከእኔ አይደለም::  ጌታ አያችሁ እኔ ከእናንተ የተሻለ አውቃለሁ እያለ አልሸለለም አብን አከበረ::  እኛም በህይወታችን የፈለገውን አይነት መገለጥ ቢኖረን ትንሽም ሽርፍ ሳናደርግ እየተደነቅን መንፈስ ቅዱስ ነው እንበል እንጂ ኮፈስ እንዳንል ጌታ ይርዳን!!!! የዘመኑ ችግር ይህ ነውና በእውነት ይርዳን በባዶ ሜዳ እንዳንኮፈስ::  ጸጋው የእርሱ ህይወቱ የእርሱ ከቶ ምን ልሁን ብዬ ቀና ቀና እላለሁ?! 

እነሱ ጥብቅና የቆሙት ለሙሴ ህግ ነው::  ህጉን የሰጠው ባለቤቱ እዛው ቆሞ ሊያርሙት ፈለጉ::  የቆሙለትንም ህግ ማድረግ በትክክል እንዳልቻሉ ነገራቸው::  እነርሱ ማሻሻያ አድርገው ነበረና በሰንበት ግዝረትን ማድረግ እንግዲያውስ ፈውስ ምን ችግር አለው አላቸው?!  እንደው የመቃወም አባዜና ቅናት ይዟቸው እንጂ አንዳችም እንከን የማይገኝበት  ጌታ ነው እርሱ::  ቅንን ፍርድ መፍረድ አልቻሉም እርሱም የአባቱን ፈቃድ ከማድረግ ወደኃላ አላለም::

አባት ሆይ ፍቃድህን አደርግ ዘንድና ሁልጊዜም አንተን ማሳየት ክብርህንም ወደ አንተ ማምጣት  ይሆንልኝ ዘንድ እርዳኝ!  አሜን!

ዮሐንስ 7: 25-31

28፤ እንግዲህ ኢየሱስ በመቅደስ ሲያስተምር እንዲህ ብሎ ጮኸ፦ “እኔንም ታውቁኛላችሁ፡ ከወዴትም እንደ ሆንሁ ታውቃላችሁ፤ እኔም በራሴ አልመጣሁም፡ ነገር ግን እናንተ የማታውቁት የላከኝ እውነተኛ ነው፤

29፤ እኔ ግን ከእርሱ ዘንድ ነኝ እርሱም ልኮኛልና አውቀዋለሁ።”

30፤ ስለዚህ ሊይዙት ይፈልጉ ነበር፤ ነገር ግን ጊዜው ገና ስላልደረሰ ማንም እጁን አልጫነበትም።

ወንድሞቹ ለዓለም እራስህን ግለጥ ቢሉትም እርሱ ግን እንዲህ አላቸው፦ “ጊዜዬ ገና አልደረሰም፥ ጊዜያችሁ ግን ዘወትር የተመቸ ነው አላቸውና እርሱ ግን በራሱ ጊዜና ሁኔታ ወደ በዓሉ ወጣ:: ሰው ባሰመረለት ሳይሆን በአባቱ ፈቃድ ይመላለስ ነበረና::

ህዝቡም ይህን ሰው እየፈለጉት አልነበረም በግልጥ እየሰበከ ነው ተቀበሉት እንዴ? እየተባባሉ ይነጋገሩ ነበር::  ይባስ ብለውም ይህን ከወዴት እንደ ሆነ አውቀናል አሉ ማለትም የዮሴፍና የማርያም ልጅ ብለው ነው አውቀነዋል የሚሉት::  ሲቀጥሉም ክርስቶስ ሲመጣ ግን ከወዴት እንደ ሆነ ማንም አያውቅም።” ብለው ደመደሙ::   ነገርግን መጽሐፍት ሁሉ ስለእርሱ ይናገራሉ::  በቃላቸው የሸመደዱት ብዙ ቃል አልገባቸውም::  መሲህ ከዳዊት ዘር በቤተልሔም እንደሚወለድ  ተጽፎላቸዋል ይህንኑም እውነት ለሄሮድስ ነግረውህፃናትም አልቀዋል::  እዚህ ጋር ግን ህዝቡ አያውቁም?! እኛም ያወቅነው በእውቀት ብዛት ወይም ፃድቅ ስለሆንን ሳይሆን እርሱ ስለገለጠልን ብቻ ነው!!!

ኢየሱስም በመቅደስ ሲያስተምር እንዲህ ብሎ ጮኸ፦ “እኔንም ታውቁኛላችሁ፡ ከወዴትም እንደ ሆንሁ ታውቃላችሁ፤ እኔም በራሴ አልመጣሁም፡ ነገር ግን እናንተ የማታውቁት የላከኝ እውነተኛ ነው::  በሌላ አባባል የምታውቁኝ መሰላችሁ እንጂ አታውቁኝም የላከኝንም አታውቁትም::  እያላቸው ቢሆንም እነርሱ ግን  የማንም ባርያ አይደለንም “እኛስ ከዝሙት አልተወለድንም አንድ አባት አለን እርሱም እግዚአብሔር ነው፡”  ይላሉ በባዶ ሜዳ ነገር ግን አባት ብለው የሚጠሩትን አያውቁትም::  ቃሉ አልጠቀማቸውም ስላልተዋሃደ::  ለእኛ እርሱን ማወቅ ሆነልን አባ አባት ብለን የምንጠራበት መንፈስ ተሰጠን:: 

ስለዚህ ሊይዙት ይፈልጉ ነበር፤ ነገር ግን ጊዜው ገና ስላልደረሰ ማንም እጁን አልጫነበትም። አሜን!  እርሱ ወዶ እንጂ ፍጥረት አስገድዶት  አያውቅም አይችልምም!! ነፍሱንም በፈቃዱ ሰጠን ይህ ጌታ ስሙ ይባረክ!!!  በዚህ ሁሉ መገፋትና ስድብ መንገላታት ውስጥ የገባው እኔን ለመታደግ ነው::  

አባት ሆይ ምን እላለሁ ተባረክ!! እራስህን ስለገለጥክልኝ አንተንም የሚያውቅ ማንነት ስለሰጠኸኝ ክበር ተመስገን::  ማንም ሳያስገድድህ ነፍስህን መስዋእት አድርገህም ስለታደከኝ ተመስገን!  ይህንን እውነት የማሳይበትንና የምመሰክርበትን ጸጋ ስጠኝ !  አሜን!!!

ዮሐንስ 7: 32-39

36፤ እርሱ፦ ‘ትፈልጉኛላችሁ አታገኙኝምም፡ እኔም ወዳለሁበት እናንተ ልትመጡ አትችሉም፡’ የሚለው ይህ ቃል ምንድር ነው?” ብለው እርስ በርሳቸው ተነጋገሩ።

37፤ ከበዓሉም በታላቁ በኋለኛው ቀን ኢየሱስ ቆሞ እንዲህ ብሎ ጮኸ፦ “ማንም የተጠማ ቢኖር ወደ እኔ ይምጣና ይጠጣ።

38፤ በእኔ የሚያምን መጽሐፍ እንዳለ፥ የሕይወት ውኃ ወንዝ ከሆዱ ይፈልቃል።”

ምንም እንኳን የካህናት አለቆችና ፈሪሳውያን  ሊይዙት ሎሌዎችን ቢልኩም ኢየሱስ ግን  “ገና ጥቂት ጊዜ ከእናንተ ጋር እቆያለሁ፡ ወደ ላከኝም እሄዳለሁ። ትፈልጉኛላችሁ፡ አታገኙኝምም፤ እኔም ወዳለሁበት እናንተ ልትመጡ አትችሉም።” ቢላቸውም አልገባቸውም::  እርሱ ከዚች ምድር አይደለምና ስለመጣበትና ተመልሶም ስለሚሄድበት ቢነግራቸውም እነርሱ ግን ሌላ ከተማ ወይም አገር ከእየሩሳሌም ወቶ የሚሄድ ነው የመሰላቸው::  ያላቸውን ኃይል ሁሉ አሰባስበው ቢመጡምያለ ጊዜው አይዙትም::

በነብዮ እዩኤል ሲነገርየነበረውን አሁን ደግሞ ባለቤቱ እየሱስ ከበዓሉም በታላቁ በኋለኛው ቀን ቆሞ እንዲህ ብሎ ጮኸ፦ “ማንም የተጠማ ቢኖር ወደ እኔ ይምጣና ይጠጣ። ግብዣው ለማንም ወይም ለሰው ልጆች በሙሉ ነው::  የተጠማ ሌላው መስፈርት ነው ስለዚህ የሚያስፈልገው ሰው መሆንና መጠማት ወደ እርሱም መቶ መጠጣት ነው ማለት ነው::  ዛሬም ግብዣው አልተለወጠም እየሱስ ከብሯልና መንፈስ ቅዱስ ወርዷል::  ወደ እርሱ መተን እንጠጣ!

በእኔ የሚያምን መጽሐፍ እንዳለ፥ የሕይወት ውኃ ወንዝ ከሆዱ ይፈልቃል።” አሜን!  ማንም በእርሱ ቢያምን ወደእርሱ ተጠምቶ ቢመጣ  እንደቃሉ የሕይወት ውኃ ወንዝ ከሆዱ ይፈልቃል::  አሜን

አባት ሆይ የህይወት ውሃ ወንዝ ከሆዴ ይፈልቃልና ተመስገን እኔን አረስርሶ ለሌላውም የሚደርስ ነውና ማንነትህ  ቅዱሱ የእግዚአብሔር መንፈስ ክበር:: በልግስና ሳትሰስት ትሰጣለህና ተባረክ::  አሜን!

ዮሐንስ 7: 40-53

ዮሐንስ 7:50፤ ከእነርሱ አንዱ በሌሊት ቀድሞ ወደ እርሱ መጥቶ የነበረ ኒቆዲሞስ፦

ዮሐንስ 7:51፤ “ሕጋችን አስቀድሞ ከእርሱ ሳይሰማ ምንስ እንዳደረገ ሳያውቅ በሰው ይፈርዳልን?” አላቸው።

ዮሐንስ 7:52፤ እነርሱም መለሱና፦ “አንተም ደግሞ ከገሊላ ነህን? ነቢይ ከገሊላ እንዳይነሣ መርምርና እይ፡” አሉት።

ከበዓሉም በታላቁ በኋለኛው ቀን ኢየሱስ ቆሞ እንዲህ ብሎ ጮኸ፦ “ማንም የተጠማ ቢኖር ወደ እኔ ይምጣና ይጠጣ። በእኔ የሚያምን መጽሐፍ እንዳለ፥ የሕይወት ውኃ ወንዝ ከሆዱ ይፈልቃል።” ሲላቸው በመካከላቸው ክርክር ሆነ::

የመከራከርያ ነጥባቸው ይህ ክርስቶስ ነው፡” አሉ፤ ሌሎች ግን፦ “ክርስቶስ በእውኑ ከገሊላ ይመጣልን?  ክርስቶስ ከዳዊት ዘር ዳዊትም ከነበረባት መንደር ከቤተ ልሔም እንዲመጣ መጽሐፍ አላለምን?” አሉ።  አይሁድም ግራ ገብቷቸዋል ‘ትፈልጉኛላችሁ አታገኙኝምም፡ እኔም ወዳለሁበት እናንተ ልትመጡ አትችሉም፡’ ብሏቸው ነበረና::  እርሱ ስለምድር አልተናገረም::  በዚህ ውስጥ ግን ያመኑበትም ነበሩ::

ቃሉ እንደሚለን ከእነርሱም አንዳንዶቹ ሊይዙት ወደዱ ነገር ግን እጁን ማንም አልጫነበትም።  አለቆችም ልከው ሎሌዎቹ ለመያዝ አልፈለጉም::  ያለ እርሱ ፈቃድ አንዳች አይሆንም::  በዚህም ጊዜ አለቆች ሕግን የማያውቀው ይህ ሕዝብ ርጉም ነው፡” ብለው ህዝቡን ረገሙ::  ምን አይነት ድፍረት ነው?  ምክንያታቸው ከአለቆች ወይስ ከፈሪሳውያን በእርሱ ያመነ አለን? ነበር::  እነርሱ ካላፀደቁ ህዝቡ ምንም ማድረግ አይችልም ማለት ነው?!  

በዚህ መሀል ግን ከእነርሱ አንዱ በሌሊት ቀድሞ ወደ እርሱ መጥቶ የነበረ ኒቆዲሞስ፦ “ሕጋችን አስቀድሞ ከእርሱ ሳይሰማ ምንስ እንዳደረገ ሳያውቅ በሰው ይፈርዳልን?” አላቸው። ቢነቅፉትም እንኳን በዚህ ንግግር ነገሩን አበረደው:: ይህ ሰው ከጌታ ጋር ጊዜ አሳልፏል በጥቂቱም ቢሆን ገብቶታል::  

በመካከላቸው የቆመው ይህ ጌታ እየጠበቁት ያለ መሲህ ሆኖ ሳለ አላወቁትም እርሱ ግን በነብያት የተናገረውን እያደረገ ነው የተገለጠው ምንም ያላሟላው ነገር የለም::  እናውቃለን ያሉት ግንበኞች የማዕዘኑን ራስ ናቁት:: ለእኔ ግን መዳኛዬ ሆነልኝ አልተደናቀፍኩበትም::

አባት ሆይ ከዓለም ጥበበኞች ይልቅ እኔን ምንም እውቀት የሌለኝን መንግስትህን መረዳት ስለሰጠኸኝ አመሰግንሃለሁ!  ከእኔ የሆነ ምንም የለም ሁሉ በአንተ ነውና ተመስገን::  አሁንም የክብር አባት ሆይ የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ አምላክ ሆይ አንተን በማወቅ የጥበብንና የመገለጥን መንፈስ ስጠኝ። አሜን!

ዮሐንስ 8: 1-11

10፤ ኢየሱስም ቀና ብሎ ከሴቲቱ በቀር ማንንም ባላየ ጊዜ፦ “አንቺ ሴት፥ እነዚያ ከሳሾችሽ ወዴት አሉ? የፈረደብሽ የለምን?” አላት።

ዮሐንስ 8:11፤ እርስዋም፦ “ጌታ ሆይ፥ አንድ ስንኳ” አለች። ኢየሱስም፦ “እኔም አልፈርድብሽም፤ ሂጂ ከአሁንም ጀምሮ ደግመሽ ኃጢአት አትሥሪ፡” አላት።

በደብረ ዘይት ጌታን የገጠመው ወጥመድ በዝሙት የተያዘችን ሴት አምጥተው መወገር  አለባት አንተ ግን ምን ትላለህ የሚል ነበረ::  ውገርዋት ቢል በሮም ሊያሲዙት አትወገር ቢል ህግን ይሽራል ሊሉ ተጠብበው ነበረ የመጡት ከአንድም ሁለት አማራጭ ይዘው::  እርሱ ግን አልተያዘም ሴቲቱንም ነፃ አደረጋት::  የሚገርመው ግን ሴቲቱ ከማን ጋር ነው ያመነዘረችው?  ህጉ የሚለው ሁለቱንም በድንጋይ መውገር ነው::  ታድያ የታለ ሰውየው?  በዘዳግም 22:22፤ ማናቸውም ሰው ከሌላ ሰው ሚስት ጋር ተኝቶ ቢገኝ፥ አመንዝራውና አመንዝራይቱ ሁለታቸው ይሙቱ፤ እንዲሁም ክፉውን ነገር ከእስራኤል ታስወግዳለህ።

ሁሉን በሚመረምርና ቅዱስ በሆነው  ጌታ ፊት ከነኃጥያታቸው መቆም አልቻሉም::  ኃጥያት የሌለበት ይውገራት ሲላቸው ሁሉም እየተወቀሱ ጥለው ሄዱ::  በመሬት ላይ የፃፈው ምን ይሆን?  ከዚህስ በፊት ጽፎ የነበረው መቼ ነበር? በዘጸአት 31:18፤ እግዚአብሔርም ከሙሴ ጋር በሲና ተራራ የተናገረውን በፈጸመ ጊዜ በእግዚአብሔር ጣት የተጻፈባቸውን ከድንጋይ የሆኑ ሁለቱን የምስክር ጽላቶች ሰጠው። አሁንም  ይህንኑ ህግ ይሆን የፃፈው? 

ሴቲቱንም አንቺ ሴት፥ እነዚያ ከሳሾችሽ ወዴት አሉ? የፈረደብሽ የለምን?” አላት። እርስዋም፦ “ጌታ ሆይ፥ አንድ ስንኳ” አለች። ምን አይነት ርህሩህ ጌታ! አዳናት::  ይህ ማለት ግን ኃጥያት በፊቱ ምንም አይደለም ማለት ነው?! በፍጹም ኃጥያት በፊቱ ኃጥያት ነው::ስለዚህም ነው “እኔም አልፈርድብሽም፤ ሂጂ ከአሁንም ጀምሮ ደግመሽ ኃጢአት አትሥሪ፡” ያላት። ደግመሽ ኃጥያት አትስሪ!! ኃጥያተኛን እንጂ ኃጥያቱን አይወድም::  የኃጥያተኞት ወዳጅ መድኃኒት እየሱስ ስሙ ይባረክ:: እኛም በዙሪያችን ያሉትን ከመውቀስ በቀና ልብ እውነትን በፍቅር ይዘን ሰዎችን ወደ ጌታ እናምጣ  እንጂ በማንም እንዳንፈርድ::  ፍርድ አልተሰጠንም ጌታም እንኳን እኔ በዓለም ልፈርድ አልመጣሁም ብሎ የለ:: ይህ ዘመን ኃጥያተኞችን ከየመንገዱ እየሰበሰብን ቤቱን የምንሞላበትጊዜ ነው:: መኽሩ ነጥቷል!

አባት ሆይ ከፈራጅነት ወጥቼ በርህራሄ ይህንን የደረሰውን አዝመራ ስትሰበስብ ገንዘብህ አድርገኝ::  በእየሱስም አሜን!

ዮሐንስ 8:12፤ ደግሞም ኢየሱስ፦ “እኔ የዓለም ብርሃን ነኝ፤ የሚከተለኝ የሕይወት ብርሃን ይሆንለታል እንጂ በጨለማ አይመላለስም፡” ብሎ ተናገራቸው።

እየሱስ የዓለም ብርሃን ነው!!  ጨለማ በፊቱ አይቆምም የእኛንም ጨለማ አጠፋው!!  ስንከተለውም የሕይወት ብርሃን ሆነልን እንጂ በጨለማ አንመላለስም::

ምን አይነት ህይወት ተሰጠን በጨለማ ከመደናበር አውጥቶ ወደ ፍቅሩ ልጅ መፍለስ::  ይህ ጨለማ ግን ብቻውን አይደለም ሰይጣን የሚሰለጥንበትና እንደወደደ  የሚያደርግበት ነው::  ነፃ የወጣነው ከጨለማውም ገዢ ነው:: እርሱ በእኛ ላይ አንዳች የለውም:: ብርሃናችን እየሱስ በርቶልናል!!

ዮሐንስ 8: 13-20

14፤ ኢየሱስ መለሰ አላቸውም፦ “እኔ ስለ ራሴ ምንም እንኳ ብመሰክር ከወዴት እንደመጣሁ ወዴትም እንድሄድ አውቃለሁና ምስክርነቴ እውነት ነው፤ እናንተ ግን ከወዴት እንደ መጣሁ ወዴትም እንድሄድ አታውቁም።

15፤ እናንተ ሥጋዊ ፍርድን ትፈርዳላችሁ፤ እኔ በአንድ ሰው ስንኳ አልፈርድም።

16፤ የላከኝ አብ ከእኔ ጋር ነው እንጂ ብቻዬን አይደለሁምና እኔ ብፈርድ ፍርዴ እውነት ነው።

17፤ የሁለት ሰዎችም ምስክርነት እውነት እንደ ሆነ በሕጋችሁ ተጽፎአል።

እየሱስ ከወዴት እንደመጣ ወዴትም እንዲሄድ ያውቃል ምስክርነቱ እውነት ነው፤ በዙሪያው ያሉት ግን ከወዴት እንደ መጣ ወዴትም እንዲሄድ አያውቁም። ምክንያቱም ስጋዊ ናቸውና የዮሴፍና የማርያም ልጅ እያሉ ነው የሚያውቁት ምንም እንኳን መሲህ ይመጣል ብለው በጉጉት እየጠበቁ ቢሆንም:: የማንንም ምስክርነት የማይፈልገው እየሱስ የአባቱን ምስክርነት አግኝቷል በእርሱ ደስ የሚለኝ የምወደው ልጄ እርሱ ነው ብሏልና::  የሰውም ምስክርነት በደንብ አግኝቷል በተለይ ከመጥምቁ ዮሃንስ ግን አልሰሙም::

እነርሱ ላይ እንፈርዳለን እንጂ እኛም ይህንን ጌታ ጌታችንና ንጉሳችን አዳኛችን መመክያችን ብለን ስናበቃ የምንመላለሰው እንዴት ነው? አሁን ጌታ ተናግሮን በቃሉ አጽናንቶን እረድቶን ተመልሰን እዛው ውስጥ እንገኝ የለም? እግዚአብሔር ይገስጸውና ይህ ጠላት የምድሩን እያሳየ ወደ ምድር ሊስበን ይፈልጋል::  ዛሬ ካለንበት እንውጣ በላይ ያለውን እንሻ ወዴት እንደምንሄድ የምናውቅ ነንና ብል በማይበላበት ነገራችንን እናከማች::  የከበበንን ሁሉ አልሰማህም በጌታዬ  እታመናለሁ! እንቢ እንበለው!!  በእየሱስ ስም ከበባ ሁሉ ይበተን!  አምላካችን የቅርብ አምላክ ነው ከምስጋና ጋር ልመናችንን እናሳውቅ እንጂ በአንዳች አንጨነቅ! እንድንጨነቅ አልተጠራንም እንድንከተለውና እንድናብለጨልጨው እንጂ::  ስለ እኔ የሚያስብ በሰማይ አለ!  አሜን!!

ዮሐንስ 8: 21-30

23፤ እንዲህም አላቸው፦ “እናንተ ከታች ናችሁ፥ እኔ ከላይ ነኝ፤ እናንተ ከዚህ ዓለም ናችሁ፥ እኔ ከዚህ ዓለም አይደለሁም።

24፤ እንግዲህ፦ ‘በኃጢአታችሁ ትሞታላችሁ፡’ አልኋችሁ፤ እኔ እንደሆንሁ ባታምኑ በኃጢአታችሁ ትሞታላችሁና።”

25፤ እንግዲህ፦ አንተ ማን ነህ? አሉት። ኢየሱስም አላቸው፦ “ከመጀመሪያ ለእናንተ የተናገርሁት ነኝ።

28፤ ስለዚህም ኢየሱስ እንዲህ አላቸው፦ “የሰውን ልጅ ከፍ ከፍ ባደረጋችሁት ጊዜ፡ እኔ እሆን ዘንድ አባቴም እንዳስተማረኝ፡ እነዚህን እናገር ዘንድ እንጂ ከራሴ አንዳች እንዳላደርግ፡ በዚያን ጊዜ ታውቃላችሁ።

29፤ የላከኝም ከእኔ ጋር ነው፤ እኔ ደስ የሚያሰኘውን ዘወትር አደርጋለሁና አብ ብቻዬን አይተወኝም።”

30፤ ይህን ሲናገር ብዙዎች በእርሱ አመኑ።

እኔ ከዚህ ዓለም አይደለሁም እያለ ቢነግራቸው ወይም በኃጢአታችሁ ትሞታላችሁ፡’ አልኋችሁ፤ እኔ እንደሆንሁ ባታምኑ በኃጢአታችሁ ትሞታላችሁና ቢላቸውም ሊገባቸው አልቻለም:: ምክንያቱም እነሱ ከዚህ ዓለም ናችሁ፥ እርሱ ግን ከላይ ነው፤ እንዴት ይግባቡ:: እኛም የገባን ጌታ ገልጦልን እንጂ በዝች አእምሮ ይህንን ጌታ መረዳት አይታሰብም::

በክርስቶስ ያሉት ኩነኔ የለባቸውም የተባለበት ምክንያት እኔ እንደሆንሁ ባታምኑ በኃጢአታችሁ ትሞታላችሁና የሚለውን አምነን ከኃጥያታችን በታች ከመሆን ስላመለጥን ነው::

የሰውን ልጅ ከፍ ከፍ ባደረጋችሁት ጊዜ፡ ብሎ ሲል ስለመስቀሉ እንጂ ስለ መሾም ወይም ስለመንገስ እንዳልሆነ ማን ያስተውላል::  እየሱስ በመስቀል ላይ ከፍ ከፍ ሲል እኛንም ወደእርሱ ሳበንና ዳንን:: እርሱ የኖረው አባቱን በመታዘዝና ደስ በማሰኘት ነው::  የላከኝም ከእኔ ጋር ነው፤ እኔ ደስ የሚያሰኘውን ዘወትር አደርጋለሁና አብ ብቻዬን አይተወኝም።” እኛም እርሱን እንታዘዝና ደስ እናሰኘው:: ትእዛዚቱም እርሱን እንድንወድ ሌሎችንም እንደራሳችን እንድንወድ ነውና::  ፍቃዱን ማድረግ ይሁንልን::

በዚህ ሁሉ ክርክር  ውስጥ በእርሱ የሚያምኑ ተገኙ::  ለሰዎች ስንመሰክር ቃሉ ምን አይነት ልብ ላይ እንደሚያርፍ አናውቅምና መመስከራችንን ከእግዚአብሔር ጋር ታረቁ ማለታችንን አንተው እንዲያውም አብዝተን እናድርግ አለበለዚይያ ግን በኃጥያታቸው ይሞታሉ እርሱን ካላወቁት::  ጌታ ይርዳን እንደ ሊድያም የተከፈቱ ልብ ያላቸውን ይስጠን! አሜን!

አባት ሆይበእኔ ስራ እየሱስ ይታይ!

አሜን

ዮሐንስ 8: 31-39

31፤ ኢየሱስም ያመኑትን አይሁድ እንዲህ አላቸው፦ “እናንተ በቃሌ ብትኖሩ በእውነት ደቀ መዛሙርቴ ናችሁ፤

32፤ እውነትንም ታውቃላችሁ እውነትም አርነት ያወጣችኋል።”

ደቀ መዝሙር የሚያደርገን በቃሉ ስንኖር ነው ቃሉም የሚነግረን እርሱን እንድንወድ የሰውንም ልጅ ሁሉ እንደራሳችን እንድንወድ ነው::  በዚህም ምልክት (በፍቅር ) ደቀ መዛሙርት መሆናችን ይታወቃል:: ቃሉም እውነት ነውና የሚያሸንፈው የለምና ስናውቀው አርነት ያወጣናል::

ይህንን ሲላቸው የዳኑትም ማፈግፈግ ያዙ የምን አርነት ነው የምትለን እኛ ባርያ አይደለንም አሉት በእነሱ አባባል መንፈሳዊዉን አይደለም የምድሩን ነው ነገር ግን በሮም አገዛዝ ስር ባርያ ነበሩ::  በግብጽም በሌሎችም ነገስታት ባርያ ሆነዋል::  የቱን ነው የሚያወሩት ግን?

ኢየሱስ መለሰ፥ እንዲህ ሲል፦ “እውነት እውነት እላችኋለሁ፥ ኃጢአት የሚያደርግ ሁሉ የኃጢአት ባርያ ነው። እየሱስ ስለኃጥያት ባርነት ያወራል እነሱ ስለዘር! ባርያም ለዘላለም በቤት አይኖርም፤ ልጁ ለዘላለም ይኖራል። እንግዲህ ልጁ አርነት ቢያወጣችሁ በእውነት አርነት ትወጣላችሁ።  ይህ እውነት የሆነ ቃል እየሱስ ማንም ማንፃት ከማይችለው ኃጥያት ከተባለ በሽታ ነፃ ያወጣል አለበለዚያ ግን በኃጥያት መሞት ነው የሚጠብቃቸው::

መልሰውም፦ “አባታችንስ አብርሃም ነው፡” አሉት። ኢየሱስም፦ “የአብርሃም ልጆች ብትሆኑ የአብርሃምን ሥራ ባደረጋችሁ ነበር።  አብርሃም ጌታን አምኖ ጽድቅ ሆኖ የተቆጠረለት እንዲሁም ደግሞ ወደ እርሱ ሲመጣ ምግብን አዘጋጅቶ ያቀርብ ነበር እንጂ ሊገድለው አልተነሳም ነበር:: ይህ ነበረ የአብርሃም ምሳሌ ማመንና ጌታን መቀበ::

እየሱስ አርነት ያወጣኸኝ እውነቴ ጌታዬና መድኃኒቴ እውነትም ህይወትም መንገድም አንተ ነህና እንዳውቅህ ስለረዳኸኝ ተመስገን!  እገዛልሃለሁኝ! እንዳዳንከኝም ምስክር እሆናለሁ!  ጸጋህ በሙላት በእኔና በህዝብህ ላይ ይገለጥ::  አሜን!!

ዮሐንስ 8: 40-47

42፤ ኢየሱስም አላቸው፦ “እግዚአብሔርስ አባታችሁ ከሆነ በወደዳችሁኝ ነበር፤ እኔ ከእግዚአብሔር ወጥቼ መጥቻለሁና፤ እርሱ ላከኝ እንጂ ከራሴ አልመጣሁምና።

43፤ ንግግሬን የማታስተውሉ ስለ ምንድር ነው? ቃሌን ልትሰሙ ስለማትችሉ ነው።

45፤ እኔ ግን እውነትን የምናገር ስለ ሆንሁ አታምኑኝም።

46፤ ከእናንተ ስለ ኃጢአት የሚወቅሰኝ ማን ነው? እውነት የምናገር ከሆንሁ እናንተ ስለ ምን አታምኑኝም?

47፤ ከእግዚአብሔር የሆነ የእግዚአብሔርን ቃል ይሰማል፤ እናንተ ከእግዚአብሔር አይደላችሁምና ስለዚህ አትሰሙም።”

እግዚአብሔርስ አባታችን ነውና እኛስ ጌታን እንወደዋለን!! ምክንያቱም ጌታ እየሱስ ከእግዚአብሔር ወጥቶ መቷልና፤ እርሱ ተልኮ እራሱን አዋርዶ መጣ  እንጂ በራሱ አልመጣም። ለእነርሱ ግን ንግግሬን የማታስተውሉ ስለ ምንድር ነው? ቃሌን ልትሰሙ ስለማትችሉ ነው:: ብሎ ጥያቄ ጠይቆ እራሱ መለሰው ቃሉን ማመንና ማስተዋል አልሆነላቸውም:: እኔ ግን እውነትን የምናገር ስለ ሆንሁ አታምኑኝም አላቸው። ለምን ንግግሩን እንደማያስተውሉ ይገርማል ወደ እርሱ የሚመጡትም አንዳች እንማራለን ወይም እርሱ መሲህ ይሆንን በሚል ሳይሆን እግረ መንገዳቸውን ወይም ጉዳያቸውን እያደረጉ ለመስማት ያህል እንጂ ህይወትን ፈልገው አይመስልም:: እየሱስ ግን እውነትን ይናገራል::  እርሱ እውነት ነውና ይዋሽ ዘንድ የሰው ልጅ አይደለም!  የሚሰማ ዛሬም ይስማ ይህ ቃል እውነት ነው! የሚሰራ ነው! መንፈስም ነው! 

ይህ አባባሉ ልቤን ይነካዋል ከእናንተ ስለ ኃጢአት የሚወቅሰኝ ማን ነው? እውነት የምናገር ከሆንሁ እናንተ ስለ ምን አታምኑኝም? እውነቱን ነው እኮ::  በእውነትና በጽድቅ እየተመላለሰ መሲሁ ሲመጣ የሚያደርጋቸውን ምልክቶች እያደረገ  ሊሰሙት አልቻሉም::  እንግዲህ ምን ያድርግ እውነትም ግራ ያጋባል ምን እንደሚፈልጉ!  ዛሬስ እኛ ቃሉን እንደ እግዚአብሔር ቃል አክብረን እንወስዳለን ወይስ ለመስማት ያህል ነው?  ይህ ጌታ የከበረ ቃሉም እውነት ነው እንመስረትበት እንደቃሉ እንጂ በሎጂክ አንመላለስ!

እናንተ ከአባታችሁ ከዲያብሎስ ናችሁ የአባታችሁንም ምኞት ልታደርጉ ትወዳላችሁ። እርሱ ከመጀመሪያ ነፍሰ ገዳይ ነበረ፤ እውነትም በእርሱ ስለ ሌለ በእውነት አልቆመም። ሐሰትን ሲናገር ከራሱ ይናገራል፥ ሐሰተኛ የሐሰትም አባት ነውና። ከእግዚአብሔር የሆነ የእግዚአብሔርን ቃል ይሰማል፤ እናንተ ከእግዚአብሔር አይደላችሁምና ስለዚህ አትሰሙም። አለቀ!! ከእግዚአብሔር የሆንን እኛ ግን እንሰማለን  ቃሉም ከእኛ ጋር ይዋሃዳል:: እግዚአብሔር በእውነት በጸጋው ይርዳን ይደግፈን!!  

አባት ሆይ ቃልህን መስማትና ማስተዋል ይብዛልን! አሜን!

ዮሐንስ 8: 48-59

56፤ አባታችሁ አብርሃም ቀኔን ያይ ዘንድ ሐሤት አደረገ፥ አየም ደስም አለው።”

58፤ ኢየሱስም፦ “እውነት እውነት እላችኋለሁ፥ አብርሃም ሳይወለድ እኔ አለሁ፡” አላቸው።

59፤ ስለዚህ ሊወግሩት ድንጋይ አነሡ፤ ኢየሱስ ግን ተሰወራቸው ከመቅደስም ወጥቶ በመካከላቸው አልፎ ሄደ።

ከእግዚአብሔር የሆነ የእግዚአብሔርን ቃል ይሰማል፤ እናንተ ከእግዚአብሔር አይደላችሁምና ስለዚህ አትሰሙም።” ሲላቸው ጋኔን አለብህ ብለው ለማለት ትንሽም አላፈሩ ነገር ግን ደፈሩ! ኢየሱስም መለሰ፥“እኔስ ጋኔን የለብኝም፡ ነገር ግን አባቴን አከብራለሁ፡ እናንተም ታዋርዱኛላችሁ።

እኔ ግን የራሴን ክብር አልፈልግም፤ የሚፈልግ የሚፈርድም አለ።  እኔ ራሴን ባከብር ክብሬ ከንቱ ነው፤ የሚያከብረኝ እናንተ አምላካችን የምትሉት አባቴ ነው:: ክብር የሚገባው አለ እርሱም አብ አባት ነው አላቸው! ዛሬ በህይወቴ አከብርሃለሁ! ጌታ እየሱስ ክብር አልፈልግም አለና እራሱን በመስቀል ሰጠ ያኔ ከሁሉ በላይ ከበረ ከስምም ሁሉ በላይ ስምን አገኘ! አሜን እየሱስ ክርስቶስ ጌታ ነው ለዚህ ስም ሁሉ ይንበረከካል!!  በአብ  ቀኝ በክብር ከፍ ብሎ ስልጣን ሁሉ በሰማይና በምድር ተሰቶት አለ!  እርሱ አልፋና ኦሜጋ ነው! አሜን

እየሱስም እንደዚህ አላቸውአብን አውቀዋለሁ። አላውቀውም ብል እንደ እናንተ ሐሰተኛ በሆንሁ፤ ዳሩ ግን አውቀዋለሁ ቃሉንም እጠብቃለሁ::  እውነት እውነት እላችኋለሁ፥ ቃሌን የሚጠብቅ ቢኖር ለዘላለም ሞትን አያይም።” በነገር ሁሉ እንድንመስለው የሚፈልግ ጌታ እኔ ቃሉን ጠብቄአለሁና እናንተም ቃሌን ጠብቁ ብሎ ህይወትን ሰጠን:: ይህንን ህይወት ማንም ከእኛ አይወስደውም ምክንያቱም ወደእኔ የመጡትን ወደ ውጪ አላወጣም ብሏልና::

አብርሃም ቀኔን ያይ ዘንድ ሐሤት አደረገ፥ አየም ደስም አለው።” ሲላቸው ግራ ገብቷቸው አንተ ሃምሳ አመት አልሞላህ አሉት እርሱ ግን ገና በሰላሳዎቹ መጀመርያ ነበረ::  ይህ ማለት ባየነውም ጊዜ ደም ግባት የለውም እንደተባለው በኢሳያስ መልክት ጌታ ከእድሜው በላይ ይመስል ይሆንን ብዬ አስባለሁ::   ኢየሱስም፦ “እውነት እውነት እላችኋለሁ፥ አብርሃም ሳይወለድ እኔ አለሁ፡” አላቸው። አሜን እርሱ የሁሉ ፈጣሪ የሁሉ መገኛ የዘላለም አምላክ ነው::  አሜን!

ስለዚህ ሊወግሩት ድንጋይ አነሡ፤ ኢየሱስ ግን ተሰወራቸው ከመቅደስም ወጥቶ በመካከላቸው አልፎ ሄደ። ፍጥረት ፍጥረትነቱን ሲረሳ እንደዚህ ይሆናል:: በእርሱ ላይ ያለጊዜው አንዳች ማድረግ አልቻሉም::  በጊዜው ግን እራሱን ሰጠ ነፍሱን በፈቃዱ አኖራት ስለ እኛ::  እሰይ መጣህልን ልትታደገን ማለት ሲገባው የሰው ልጅ ጭራሽ ከእሱ ጋር ክርክር ገባ ጌታም  ታህሶ የመጣበትን ፈጽሞ ሄደ ምን አይነት ጌታ ነው? ምን አይነትስ ፍቅር ነው? ዛሬ የትኛው ክብራችን ነው አሳዝኖን ከመመስከር ወደኃላ እንድንል የሚያደርገን?! ለጌታ እኛነታችን ይገባዋል እርሱ ክብሩን ትቶ ስለእኛ መቷልና እኛም ለእርሱ እንኑር::  

አባት ሆይ እራሴን በፊትህ ቅዱስና ህያው መስዋአት አድርጌ አቀርባለሁ ተጠቀምብኝ!!

ዮሐንስ 9: 1-5

3፤ ኢየሱስም እንዲህ ብሎ መለሰ፦ “የእግዚአብሔር ሥራ በእርሱ እንዲገለጥ ነው እንጂ እርሱ ወይም ወላጆቹ ኃጢአት አልሠሩም።

4፤ ቀን ሳለ የላከኝን ሥራ ላደርግ ይገባኛል፤ ማንም ሊሠራ የማይችልባት ሌሊት ትመጣለች።

5፤ በዓለም ሳለሁ የዓለም ብርሃን ነኝ።”

የቀደመውን ምዕራፍ የዘጋው ሊገድሉት ሲፈልጉ በመካከላቸው አልፎ እንደሄደ ነግሮን ነው::  ሲያልፍም ይህንን ሰው  አየው::  ግን ከነበረበት ሁኔታ ማድረግ የነበረበት ያንን አካባቢ ጥሎ መሄድ ነበር እርሱ ግን አሳቡ ሁሉ የመጣበትን ዓላማ መፈጸ ም ላይ ነበረ:: 

በሰውየው  በኩል ምንም አይነት  አስበኝ የሚልም ነገር የለውም የዕለት ተዕለት ተግባሩን እያከናወነ ነው::   ደቀ መዛሙርቱ ግን ምክንያቱን ማወቅ ፈለጉ ለምን እውር ሆኖ ተወለደ? የማን ኃጥያት ነው?  ኢየሱስም እንዲህ ብሎ መለሰ፦ “የእግዚአብሔር ሥራ በእርሱ እንዲገለጥ ነው እንጂ እርሱ ወይም ወላጆቹ ኃጢአት አልሠሩም። መፈላሰፍ አያስፈልግም የእግዚአብሔር ክብር መገለጥ ነው የሚያስፈልገው::  አንዳንዴ መውጫ የሌለው ቅርቃር ውስጥ እንገባለን በእንደነዚህ ባሉ ጥያቄዎች ተተብትበን:: ከመፍረድ ወተን አሁን መደረግ ያለበት ላይ ነው ትኩረታችንን ማድረግ ያለብን::

ጌታ እየሱስ የመጣበትን ዓላማ አስታወሳቸው:- ቀን ሳለ የላከኝን ሥራ ላደርግ ይገባኛል፤ ማንም ሊሠራ የማይችልባት ሌሊት ትመጣለች። በዓለም ሳለሁ የዓለም ብርሃን ነኝ አላቸው ::  ዛሬ ለእኛ ቀን ነው የተላክን ነንና የላከንን እናገልግል::  ክብሩን ለመግለጥ በእኛ ውስጥ እየሱስ አለ ይሰራል::  አባቴ ይሰራል እኔም እሰራለሁ እንዳለው የሚሰራ ጌታ ይዘን ቁጭ አንበል::  የዓለም ብርሃን አድርጎናል በዚህ ጨለማ በዋጠው ዓለም እያበራን በችግር ውስጥ ባሉትም ላይ ሳንፈርድ የዋልንበትም ቀን ሳይረብሸን (እየሱስ የሞት ሙከራ ነበር የተደረገበት ከደቂቃዎች በፊት) በፍቅርና በመራራት እናብራና እናብለጭልጨው::

አባትሆይ ፈቃድህን ፈጽሜ ልታዘዝህ የጊዜው ነገር ልቤን አይያዘው ልቤን በመንገዴ ላይ ላድርግ እርዳኝ::

ዮሐንስ 9: 6-7

6፤ ይህን ብሎ ወደ መሬት እንትፍ አለ በምራቁም ጭቃ አድርጎ በጭቃው የዕውሩን ዓይኖች ቀባና፦

7፤ “ሂድና በሰሊሆም መጠመቂያ ታጠብ፡” አለው፤ ትርጓሜው፡ “የተላከ፡” ነው። ስለዚህ ሄዶ ታጠበ፡ እያየም መጣ።

ቀን ሳለ የላከኝን ሥራ ላደርግ ይገባኛል፤ ማንም ሊሠራ የማይችልባት ሌሊት ትመጣለች ብሎ ይህንን ሰው አሰበው::  አዳምን ከአፈር ያበጀው ጌታ ይህ ሰው ዓይኑ እንዳልተፈጠረ አውቆ ልምድ ስላለው እንትፍ ብሎ አፈሩን ዓይን አደረገው!  ሃሌሉያ!!  ሳይንስ ምን ቢመራመር ከአፈር አንዳች ነገር አይሰራም እንዲያውም  አያስበውም::  ለሰርጀሪ እንኳን እንዴት እንደሚያጸዱ እናውቃለን::

ይህ ሰው ያልጠበቀው ነው የሆነለት ዛሬ የፈውሴ ቀን ነው ብሎ አላሰበም  ድንገት ግን ስለእርሱ ውይይት ተነሳ::  እየሱስ ፈጣሪው አጠገቡ መቆሙንም አላወቀም::  ማን እንደሆነም አላወቀውም የታለ ሲባልም እኔ እንጃ  ነበረ መልሱ::  እምነትም ልመናም አልነበረውምና ጭቃውን ከቀባው በኃላ አንድ ነገር አዘዘው ሂድና በሰሊሆም መጠመቂያ ታጠብ፡” አለው፤ ትርጓሜው፡ “የተላከ፡” ነው። ስለዚህ ሄዶ ታጠበ፡ እያየም መጣ። እምነቱ በመሄዱ ላይ ነበረ::  ያለ እምነት እግዚአብሔር ደስ ማሰኘትና ከእርሱም መቀበል አይቻልም:: ዛሬም ድንገት ወደ ነገራችንይህጌታ ይምጣ ጥያቄያችን ይመለስ::

አምላኩ አሰበውና ከወደቀበት ጨለማ ገላገለው::  እየሱስ አንድ አይነት ብቻ የፈውስ መንገድ አይከተልም ይሄኛው ደግሞ ከሁሉም በጣም የተለየየ ነው::  ይህ መሲህ ሲመጣ ከሚሆኑት ምልክቶች አንዱ ይህ ነው እውሮች ይበራሉ::  ጌታ እየሱስ እንዲታጠብ የላከው ቦታ “የተላከ”  ነው የተላከ መሆኑን እየጠቆመ ቢሆንም እንኳን ህግን እናውቃለን የሚሉትና የሚያዮት ታውረዋልና መሲሁን ጌታ አላወቁትም::

አባት ሆይ አንተን ማወቅ ሆኖልኛልና ተመስገን!! ጨለማዬን አብርተሀልና ተመስገን የህይወት ብርሃኔ እየሱስ ክበር! ዛሬም በስራ ላይነህና በጨለማ የሄደ ህዝብ ብርሃን ያይ ዘንድ የሰዎችን ልብ አብራ የሚድኑ ነፍሳትንም እንደሊድያ ልባቸውን እየከፈትህ ስጠን ::  አሜን!

ዮሐንስ 9: 8-34

17፤ ከዚህም የተነሣ ዕውሩን፦ “አንተ ዓይኖችህን ስለ ከፈተ ስለ እርሱ ምን ትላለህ?” ደግሞ፥ አሉት። እርሱም፦ “ነቢይ ነው፡” አለ።

25፤ እርሱም መልሶ፦ “ኃጢአተኛ መሆኑን አላውቅም፤ ዕውር እንደ ነበርሁ፡ አሁንም እንዳይ፡ ይህን አንድ ነገር አውቃለሁ፡” አለ።

27፤ እርሱም መልሶ፦ “አስቀድሜ ነገርኋችሁ አልሰማችሁምም፤ ስለ ምን ዳግመኛ ልትሰሙ ትወዳላችሁ? እናንተ ደግሞ ደቀ መዛሙርቱ ልትሆኑ ትወዳላችሁን?” አላቸው።

ዓይኖቹ በተከፈቱለት ሰው ምክንያት ብዙ ውዝግብ ነበረ አንዳንዶች  እሱ ነው ሲሉ ሌሎች እሱ አይደለም በሚል ሲሆን ሌላው ይህ ሰው ሰንበትን አያከብርምና ከእግዚአብሔር አይደለም፡” ሌሎች ግን፦ “ኃጢአትኛ ሰው እንደነዚህ ያሉ ምልክቶች ሊያደርግ እንዴት ይችላል?” አሉ። በመካከላቸውም መለያየት ሆነ።

አሁንም አሁንም ሲጠይቁት ሰውዬው መለሰ፥ እንዲህም አላቸው፦ “ከወዴት እንደ ሆነ እናንተ አለማወቃችሁ ይህ ድንቅ ነገር ነው፥ ዳሩ ግን ዓይኖቼን ከፈተ። አስተማሪና መሪ ነን የሚሉት እየሱስን አለማወቃቸው ገርሞታን እንደዚህ ያለ ነብይ መኖሩ እንዴት ጠፋቸው ብሎ ነው እየሱስ ለሱ ገና ነብይ ነው በዚህ ሰዓት:: እግዚአብሔርን የሚፈራ ፈቃዱንም የሚያደርግ ቢኖር ያንን እግዚአብሔር ይሰማዋል እንጂ ኃጢአተኞችን እንዳይሰማ እናውቃለን። ዕውር ሆኖ የተወለደውን ዓይኖች ማንም እንደ ከፈተ ዓለም ከተፈጠረ ጀምሮ አልተሰማም፤ ይህ ሰው ከእግዚአብሔር ባይሆን ምንም ሊያደርግ ባልቻለም ነበር አላቸው:: እንደዚህ ያለ ስብከት በፈሪሳውያን ፊት የሚገርምና ያለውን ውጥረት ያገናዘበ አይመስልም ሰውየው::እውነቱን ነው ማንም እንደዚህ አይነት ምልክት አድርጎ አያውቅም ነበረ:: 

እነርሱም “አንተ ሁለንተናህ በኃጢአት ተወለድህ፥ አንተም እኛን ታስተምረናለህን?” አሉት። ወደ ውጭም አወጡት። ስለ እየሱስ ስለመሰከረ አውጥተው ጣሉት በባዶ ቅናት::  አንዳንዶቻችን እንደዚህ ነበርን በባዶ ቅናት የምንመላለስ  ዛሬ ግን ብርሃን በርቶልን እየሱስ ጌታ ነው እንላለን የምንመላለሰውና የምናመልከው በመንፈስ ሆነልን! ስሙ ይባረክ!  በተራ ክርክር ውስጥ ላሉት ታግሰን በፍቅር ወደ እየሱስ ማምጣት ይሁንልን::

አባት ሆይ ዓይኖቻችንን አብርተህ ወደ ፍቅርህ ልጅ ስላፈለስከን ተመስገን::

ዮሐንስ 9: 35-41

35፤ ኢየሱስም ወደ ውጭ እንዳወጡት ሰማ፡ ሲያገኘውም፦ “አንተ በእግዚአብሔር ልጅ ታምናለህን?” አለው።

36፤ እርሱም መልሶ፦ “ጌታ ሆይ፥ በእርሱ አምን ዘንድ ማን ነው?” አለ።

37፤ ኢየሱስም፦ “አይተኸዋልም፡ ከአንተ ጋርም የሚናገረው እርሱ ነው፡” አለው።

ይህ ሰው እየሱስን በተለያየ ማንነቱ አወቀው::  መጀመርያ በዮሐንስ 9:11፤ “ኢየሱስ የሚባለው ሰው‘ በማለት ሰው ብሎ ነው ያወቀው:: ሲቀጥልም እርሱ ነብይ ነው አለ በቁ 17::  እንደዚሁም በቁ 27፤ እናንተ ደግሞ ደቀ መዛሙርቱ ልትሆኑ ትወዳላችሁን?” አላቸው። አስተማሪና መሪ መሆኑን አውቆ እራሱንም ከተከታዮቹ ወይም ከደቀ መዝሙር  አንዱ አድርጎ የቆጠረ ይመስላል:: በዚህ አላበቃም እርሱ ከእግዚአብሔር ነው አለ ቁ 33::  ከዛም ቀጥሎ ከቁ 35-38 ባለው ክፍል የእግዚአብሔር ልጅ እንደሆነ ከራሱ ከእየሱስ ሰምቶ አወቀ::  አምነው ዘንድ ማነው ብሎ ጠይቆ ጌታውን አውቆ አምናለሁ ብሎ ሰገደ::  እየሱስም ስግደት አይገባኝም አላለም ተቀበለው::  የትኛውም ነብይ ወይም ሐዋርያ ወይም መልአክ ከሰው አምልኮ ሲቀበሉ አናውቅም::  አምልኮ የሚገባው ጌታ ግን ተቀበለ::  

ኢየሱስም ወደ ውጭ እንዳወጡት ሰማ፡ ሲያገኘውም፦ “አንተ በእግዚአብሔር ልጅ ታምናለህን?” አለው።  እራሱ እየሱስ ፈልጎት መጣ እናትና አባቱ እንኳን አብረውት አልቆሙም::  እንደቃሉ ጌታዬ በስሙ በተገፋው ዘንድ ተገኘ በውሃ ውስጥ ባለፍክ ጊዜ እኔ ከአንተጋር እሆናለሁ እንዳለ እንዲሁም እኔ ከእናንተ ጋር ነኝ  የሚለን ቃሉ እውነት እንደሆነ አሳየን:: ሁሉ የተውትን ፈልጎ መጣ! እራሱንም በበለጠ ገለጠለት::  አቤት የጌታ አሰራር ከሰው ይለያል!

ሌሎች እያዩ እውሮች ተባሉ ኃጥያታቸውም ይኖራል ምክንያቱም አዳኝ አልፈለጉምና በጌታ ባለማመናቸው አሁኑኑ ተፈርዶባቸዋል:: ማን በራሱ ንጹ ሊሆን ይችላል በዚህ ቅዱስ በሆን አምላክ ፊት? ከክርስቶስ በቀር ከእግዚአብሔር ቁጣ ማምለጫ መንገድ የታለና::

አባት ሆይ አንተ አብልጠህ የምትጠጋጋ ወዳጅ ነህና አመሰግንሃለሁ::  ማንም ከጎናችን የሚቆም ሳይኖር የምትደርስ ጌታ ተባረክ!  አሁንም በአንተ እንታመናለን ጌታችን ሆይ የምታስመካ ጌታ አንተ ነህ!

አሜን!

ዮሐንስ 10: 1-5

1፤ እውነት እውነት እላችኋለሁ፥ ወደ በጎች በረት በበሩ የማይገባ በሌላ መንገድ ግን የሚወጣ እርሱ ሌባ ወንበዴም ነው፤

2፤ በበሩ የሚገባ ግን የበጎች እረኛ ነው።

3፤ ለእርሱ በረኛው ይከፍትለታል፤ በጎቹም ድምፁን ይሰሙታል፥ የራሱንም በጎች በየስማቸው ጠርቶ ይወስዳቸዋል።

4፤ የራሱንም ሁሉ ካወጣቸው በኋላ በፊታቸው ይሄዳል፥ በጎቹም ድምፁን ያውቃሉና ይከተሉታል፤

5፤ ከሌላው ግን ይሸሻሉ እንጂ አይከተሉትም፥ የሌሎችን ድምፅ አያውቁምና።

ሰዎች ሲናገሩ በእስራኤል በጎች ስም ይወጣላቸዋል ልክ እኛ ለውሻ እንደምናወጣው::  የእረኛቸውንም ድምጽ ለይተው ያውቃሉ::  የእረኛውን ልብስ እንኳን ለብሰው ለማሞኘት ሲሞክሩ በጎቹ አይሰሙም አይታዘዙምም ልብሱን ሳይሆን የሚያውቁት ድምጹን ነውና::  በጎቹ የሚያድሩት ብዙ በጎች በሚያድሩበት በረት ውስጥ ነው::  ጠዋት እረኛው መቶ በረኛውም  አሳልፎት ወደ በሩ ይመጣና ይጠራቸዋል ከያሉበት ከጥጋ ጥግ  ተነስተው ሁሉም ይከተሉታል::  እረኛው ከፊት ይሄዳል እነርሱም ይከተሉታል:: የሌላ የሆኑት ግን ድምጹን ስለማያውቁ አይሰሙም እዛው ቀርተው እረኛቸውን ይጠብቃሉ እንጂ ምን እንዳለም አይሰሙም:: 

ይህንኑ ምሳሌ ነው ጌታ የሚነግረን እረኛችን እየሱስ በስማችን የሚጠራን በዚህ ምድር የምንኖር እንኳን ብንሆን በያለንበት ድምጹን ሰምተን የምንከተል ነን::  ምንም አይነት አዲስ ነገር  ለመስማት ሊገጠምልን አያስፈልግም እርሱን ለመስማት ብቃት ተሰጥቶናል! ሃሌሉያ!  እናውጅ ጠላት አያጭበርብረን ድምጹን እንስማና እንከተል! ከሌላው ግን እንሸሻለን እንጂ አንከተለውም፥ የሌሎችን ድምፅ አናውቅም። እውቅናም አንሰጥም::

በረኛው መንፈስ ቅዱስ እየሱስን ወደእኛ እንዲመጣና እንዲመራን ይሰጠዋል::  በ1 ጴጥሮስ 1:3-5፤ ኢየሱስ ክርስቶስ ከሙታን በመነሣቱ ለሕያው ተስፋና ለማይጠፋ፥ እድፈትም ለሌለበት፥ ለማያልፍም ርስት እንደ ምሕረቱ ብዛት ሁለተኛ የወለደን የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ አምላክና አባት ይባረክ፤ ይህም ርስት በመጨረሻው ዘመን ይገለጥ ዘንድ ለተዘጋጀ መዳን በእምነት በእግዚአብሔር ኃይል ለተጠበቃችሁ ለእናንተ በሰማይ ቀርቶላችኋል። እኛ በእግዚአብሔር ኃይል የምንጠበቅ ነን!!!!

እረኛዬ እየሱስ ተባረክ አምኜ እከተልሃለሁ!  ድምጽህን ለመስማት ብቃት ስለሰጠኸኝ ማንም ስለማይወስድብኝ አከብርሃለሁ!  አመሰግንሃለሁ!  ተባረክ!

ዮሐንስ 10: 7-13

9፤ በሩ እኔ ነኝ፤ በእኔ የሚገባ ቢኖር ይድናል፥ ይገባልም ይወጣልም መሰማሪያም ያገኛል።

10፤ ሌባው ሊሰርቅና ሊያርድ ሊያጠፋም እንጂ ስለ ሌላ አይመጣም፤ እኔ ሕይወት እንዲሆንላቸው እንዲበዛላቸውም መጣሁ።

11፤ መልካም እረኛ እኔ ነኝ። መልካም እረኛ ነፍሱን ስለ በጎቹ ያኖራል።

እውነተኛ እረኛ እየሱስ ነው::  ነፍሱን ስለእኛ የሰጠና ያዳነን:: በሩ እኔ ነኝ ሲል በዘመኑ የነበሩት ሰዎች በደንብ ይገባቸዋል ምክንያቱም በባህላቸው የበጎች ማረፊያ አንድ በር ነው ያለው እበሩም ላይ እረኛው ይተኛል ተኩላ   ከመጣም በመጀመሪያ የሚያገኘው እረኛውን ነው::  እየሱስ በር ሆኖ ተኩላውን እያባረረ አኑሮናል::  እውነተኛ እረኛችን ይባረክ! 

በእኔ የሚገባ ቢኖር 

1. ይድናል፥ መሰማሪያም ያገኛል አለን እየሱስ:: መዳን ከክፉ ከዓለም ከኃጥያት:

2. ይገባልም – ወደቤቱ መግባት 

3. ይወጣልም – ወደ  ውጪው ዓለም ወደ ጨለማው ወተን እናበራለን እንናጠቃለን::

4. መሰማሪያም ያገኛል – የሚያሰማራን የሚመራን እርሱ ነው::  የሚያይልን! እንዲሁም እየሱስ የሚለን እኔ ሕይወት እንዲሆንላችሁ  እንዲበዛላችሁም መጣሁ።  አሜን!

በተቃናኒው ሌባው 

1.  ሊሰርቅና ሊያርድ 

2 . ሊያጠፋም እንጂ ስለ ሌላ አይመጣም፤

ሌላም አላማ የለውም ሰርቆ መግደል ካልሆነለት  ያገኘውን ሁሉ ያጠፋል:- ጤና ቢሆን ህብረትን ቢሆን : መልካም አስተሳሰብን ቢሆን: ንብረታቭችንን ቢሆን ጌታ የሚከብርበትን ሁሉ ያጠቃል ምን ከምን ሳይመርጥ ያሳድዳል::  ጌታ ግን አሸንፎታል እበሩ ላይ ነውና አያስገባውም ስለዚህ ሰርቆማረድ አይሆንለትም የት ያገኘናል::  እኛም እናውቀዋለን እርሱም ያውቀናል::

ኦ! መልካም እረኛ እኔ ነኝ እንዳልከን እየሱስ አንተም መልካሙ እረኛ ነፍሱህን ስለ እኛ አኖርክ ። ክብር ይሁንልህ!! እረኛዬ አንተው አውጣናአግባኝ በወደድክበትም አሰማራኝ! አሜን!

ዮሐንስ 10: 14-21

14-15፤ መልካም እረኛ እኔ ነኝ፥ አብም እንደሚያውቀኝ እኔም አብን እንደማውቀው የራሴን በጎች አውቃለሁ የራሴም በጎች ያውቁኛል፤ ነፍሴንም ስለ በጎች አኖራለሁ።

16፤ ከዚህም በረት ያልሆኑ ሌሎች በጎች አሉኝ፤ እነርሱን ደግሞ ላመጣ ይገባኛል ድምፄንም ይሰማሉ፥ አንድም መንጋ ይሆናሉ እረኛውም አንድ።

መልካም እረኛ እኔ ነኝ፥ ብሎ ሲደመድም ሌላ ስለሌለ ነው::  አብን በሚያውቅበት እውቀቱ ነው የራሱን በጎች የሚያውቀው በጎቹም ያውቁታል::  ምን አይነት መዋሃድ ነው በእረኛችንና በእኛ መካከል ያለው::  ሰው እድሜው ሲገፋ የራሱን ልጅ ሳይቀር ይረሳል ጌታ ግን አልረሳሽም በስምሽ አውቅሻለሁ  አውቅሃለሁ ነው የሚለን:: ነፍሴን ደግሞ አነሣት ዘንድ አኖራለሁና ስለዚህ አብ ይወደኛል አለ::  እራሱ ነው ነፍሱን የሰጠው እንጂ ማንም ነፍሱን ከእርሱ ለመውሰድ ስልጣን የለውም! አብን ታዘዘ አብም የምወደው ልጄ ይህ ነው ብሎ መሰከረለት::  እኛም ዛሬ እንታዘዘዋለን::

ስለምወዳቸው ነፍሴንም ስለ በጎች አኖራለሁ ብሎ ለራሱ ሳይሳሳ ህይወቱን ሰጥቶን ከራሱ ጋር አስታረቀንና በመንፈሱ ሞልቶ የራሱ አደረገን::  ሃሌሉያ!   የራሱ የማድረጉ እቅድ ለእስራኤል ብቻ አልነበረም ነገር ግን ከዚህ በረት ያልሆኑ ሌሎች በጎች አሉኝ ብሎ እኛንም አስቦን ነበረና እነርሱን ደግሞ ላመጣ ይገባኛል ድምፄንም ይሰማሉ፥ አንድም መንጋ ይሆናሉ እረኛውም አንድ ይሆናል::  እረኛችን ባለመለያየት ለሁለቱም እኩል ነገር ነው ያደረገው:: እርሱ አይለያይም እኛም እመንጋው ውስጥ ገባን ድምጹንም የምንሰማ ሆንን::  ደስ የሚለው ይህ ለዘላለም ነው የማያልቅ ህብረት! እየሱስም  ነፍሴን ደግሞ አነሣት ዘንድ አኖራለሁና ስለዚህ አብ ይወደኛል አለ::  እራሱን ሳይሰስት ህይወቱን ሰጠን!

ይህንን ሲሰሙ ከእነርሱም ብዙዎች፦ “ጋኔን አለበት፡ አብዶአልም፤ ስለ ምንስ ትሰሙታላችሁ?” አሉ።ሌሎችም፦ “ይህ ጋኔን ያለበት ሰው ቃል አይደለም፤ ጋኔን የዕውሮችን ዓይኖች ሊከፍት ይችላልን?” አሉ። ይህ ሁሉ ማንነቱ የተገለጠው ከታምራቱ በኃላ ነው ዛሬም ጸጋ ይሰራል እራሱን በተአምራት ይግለጥ::

እረኛችን ሆይ እናመሰግንሃለን! ከፍ በል! እኛም እንታዘዝሃለን::

ዮሐንስ 10: 22-27

24፤ አይሁድም እርሱን ከበው፦ “እስከ መቼ ድረስ በጥርጣሪ ታቆየናለህ? አንተ ክርስቶስ እንደ ሆንህ ገልጠህ ንገረን፡” አሉት።

የዚህን ጥያቄ መልስ ለማወቅ ጏጏሁ::  ጥሩ አጋጣሚ ነው የመጣለት እየሱስ ክርስቶስ ነህን የሚል ጥያቄ መቼም ለማወቅ ፈልገው መሆን አለበት ያሰኛል::

እርሱ ግን ልባቸውን ያውቃልና የመለሰላቸው እንዲህ ሲል፦ “ነገርኋችሁ፡ አታምኑምም፡ እኔ በአባቴ ስም የማደርገው ሥራ ይህ ስለ እኔ ይመሰክራል::  የሚመሰክረው ስራው ነው::  የሚታይ ስራ እያደረገ ነው አስቀድሞ በኢሳይያስ 61:1፤ የጌታ የእግዚአብሔር መንፈስ በእኔ ላይ ነው፥ ለድሆች የምሥራችን እሰብክ ዘንድ እግዚአብሔር ቀብቶኛልና፤ ልባቸው የተሰበረውን እጠግን ዘንድ፥ ለተማረኩትም ነጻነትን ለታሰሩትም መፈታትን እናገር ዘንድ ልኮኛል።የሚያለቅሱትንም ሁሉ አጽናና ዘንድ፤ 3፤ እግዚአብሔር ለክብሩ የተከላቸው የጽድቅ ዛፎች እንዲባሉ ለጽዮን አልቃሾች አደርግላቸው ዘንድ፥ በአመድ ፋንታ አክሊልን፥ በልቅሶም ፋንታ የደስታን ዘይት፥ በኀዘንም መንፈስ ፋንታ የምስጋናን መጐናጸፊያ እሰጣቸው ዘንድ ልኮኛል።  የሚለው እየተፈጸመ ነው በፊታቸው ግን አላስተዋሉም::

ቀጥሎም ቁርጣቸውን ነገራቸው እናንተ ግን እንደ ነገርኋችሁ ከበጎቼ ስላልሆናችሁ አታምኑም አላቸው::  እየጠበቁት ያለው ጌታ በመካከላቸው ቆሞ አላወቁትም:: በእኔ ተገለጥ ብለን ጌታን እንጋብዘው በኃይልም በብርታትም አይደለም በመንፈሱ እንጂ የመንግስቱ ስራ የሚሰራው::

አባት ሆይ አንተን ማወቅ ስለሆነልኝ ተመስገን::  በስራህ ጌትነትህንና አዳኝነትህ ይታያልና አሁንም በመካከላችን በስራህ ተገለጥ: በጨለማ የሄደ ህዝብ ብርሃን ይይ::  አሜን! 

ዮሐንስ 10: 28-42

28፤ እኔም የዘላለም ሕይወትን እሰጣቸዋለሁ፥ ለዘላለምም አይጠፉም፥ ከእጄም ማንም አይነጥቃቸውም።

29፤ የሰጠኝ አባቴ ከሁሉ ይበልጣል፥ ከአባቴም እጅ ሊነጥቃቸው ማንም አይችልም።

30፤ እኔና አብ አንድ ነን።”

እረኛችን የሚያደርግልን ነገር:-

እኔም የዘላለም ሕይወትን እሰጣቸዋለሁ፥ ለዘላለምም አይጠፉም፥ 

ከእጄም ማንም አይነጥቃቸውም!

የሰጠኝ አባቴ ከሁሉ ይበልጣል ስለዚህ:- 

ከአባቴም እጅ ሊነጥቃቸው ማንም አይችልም። የገባንበት ህይወት አስተማማኝ ነው ማንም ከማያወጣን ከልዑል ጉያ ገብተናል! ሃሌሉያ! ሰው ቢሆን ሰይጣን ቢሆን ከፍታ ቢሆን ዝቅታ ምንም ቢመጣ እኛ ግን በአባታችን ፍቅር ተሞልተን እንለመልማለን!  አሜን!

ጌታ እየሱስ እኔና አብ አንድ ነን አለን:: አሜን አንድ አምላክ እናመልካለን!  ብዙዎች ይህ ሚስጢር አይገባቸውም ጌታ ግን በግልጥ ተናግሯል::

ይህ አሳብ እንደገና ሊወግሩት አስነሳቸው ህይወትን መስጠት ብቻ ሳይሆን ያ አምላካችሁ እኔ ነኝ ሲላቸው አልተዋጠላቸውም::  ኢየሱስ፦ “ከአባቴ ብዙ መልካም ሥራ አሳየኋችሁ፤ ከእነርሱ ስለ ማናቸው ሥራ ትወግሩኛላችሁ?” ብሎ መለሰላቸው። አብ ቀድሶ የላከውን አልተቀበሉትም እንዲያውም ትሳደባለህ አሉት::   እርሱ እንዲያዩለት የፈለገውበማደርገው እንኳን እመኑ እኔ  የአባቴን ሥራ እያደረኩኝ ነውና:: እኔን ስንኳ ባታምኑ አብ በእኔ እንደ ሆነ እኔም በአብ እንደ ሆንሁ ታውቁና ታስተውሉ ዘንድ ሥራውን እመኑ።”  አላቸው::  ያደረገ ሁሉ መልካም ነበረ በአንድም ሰው አልፈረደም!

ጌታዬ ሆይ አምናለሁ! መልካሙ እረኛ ዛሬም ድንቅን ትሰራለህና በስራህ ተገለጥ::  ሰዎች አምላክ እንዳለ ይረዱና ያውቁ ዘንድ በምድር እንደተመላለስከው ዛሬም በዋጀኸው ህዝብህ ውስጥ ተመላለስና ሰዎችን ወደ መንግስትህ አፍልስ::  አሜን!

ዮሐንስ 11: 1-16

3፤ ስለዚህ እኅቶቹ፦ “ጌታ ሆይ፥ እነሆ የምትወደው ታሞአል፤” ብለው ወደ እርሱ ላኩ።

4፤ ኢየሱስም ሰምቶ፦ “ይህ ህመም የእግዚአብሔር ልጅ በእርሱ ይከብር ዘንድ ስለ እግዚአብሔር ክብር ነው እንጂ ለሞት አይደለም፡” አለ።

ይህንን ቤተሰብ ጌታ ይወድ ነበረና ምንም እንኳን ሊገድሉት የሚፈልጉት አይሁድ ቢኖሩም ወደ ይሁዳ ለመሄድ ተነሳ::  ይህንንም አሳብ ደቀ መዛሙርቱ ተቃወሙ እንዲያውም  ሄደን እንሙት እስኪሉ ነበረ የገለጡት ያለውን ውጥረት::  እየሱስ ግን ብርሃን ሆኖ ወደ ዓለም መቶ እያበራ እያለ በለሊት እንመላለስ የሚሉትን አይሁድ ሊረዳቸው አይችልም እጃቸውንም ከቀኑ በፊት እንዲጭኑበት አልፈቀደም:: እርሱ የአባቱን ፈቃድ ማድረግ ነውና የሚፈልገው ክብሩ ወደ ሚገለጥበት ዋጋ የሚያስከፍልም ቢሆን ለመሄድ ተነሳ:: 

ይህ ህመም የእግዚአብሔር ልጅ በእርሱ ይከብር ዘንድ ስለ እግዚአብሔር ክብር ነው እንጂ ለሞት አይደለም፡” አለ። የመሞቱ ዜና ለደቀ መዛሙርቱ አልገባቸውም ተኝቷል ሲላቸው ይነሳላ አሉት::  እንደዚህ እየተላለፍን ይሆን?!  ከዚህም በኋላ፦ እንግዲህ ያን ጊዜ ኢየሱስ በግልጥ አላቸው፦ “አልዓዛር ሞተ:: ለመሄድም የሚያስነሳው ይኸው የእርሱ መክበርና በሞትም ላይ ስልጣን እንዳለው የሚያሳይበት ነው::  ከአምላካችን በቀር ማነው በሞት ላይ ስልጣን ያለው?! እየሱስ አምላኬ ሆይ ክበር! አንተ ሞትን ድል አድርገኸዋል::

ቶማስ ግን ሄደን እንሙት በማለት ፋንታ ሄደን ክብርህን እንይ ማለት ነበረበት::  የእግዚአብሔርን አሳብ ከማወቅ የዘገየን እንዳንሆን ጌታ ይርዳን::

አባት ሆይ:- የልብህን አሳብ ስትገልጥልኝ ከአንተ ጋር መስማማት ይሁንልኝ::  ድምጽህን የመስማት ብቃት ሰተኸኛልና ሳልዘገይ ሰምቼህ እንድመላለስ እርዳኝ::  ከአንተ ጋር መተላለፍ አልፈልግም::  ክብርህን በምትገልጥበት መገኘት ይሁንልኝ::  በጨለማ ላሉትም ብርሃን ልሁን::  አሜን! 

ዮሐንስ 11: 17-37

17፤ ኢየሱስም በመጣ ጊዜ በመቃብር እስከ አሁን አራት ቀን ሆኖት አገኘው።

23፤ ኢየሱስም፦ “ወንድምሽ ይነሣል፡” አላት።

እየሱስ ወደ ቢታንያ ሲመጣ አልአዛር አራት ቀን ሆኖት ነበረ ከተቀበረ::  በባህላቸው ነፍስ ለሶስት ቀን እዛው አካባቢ ታንዣብባለች ብለው በአፈ ታሪክ ያምኑነበረና ነው እየሱስ አራት ቀን የቆየው የሚሉም አሉ:: እንደመጣ ያገኘው ማርታን ነበረ ስታገኘው ያለችው ቃል በቃል ማርያምም መታ የምትለውን ነው::  ጸሎታቸው “ጌታ ሆይ፥ አንተ በዚህ ኖረህ ብትሆን ወንድሜ ባልሞተም ነበር” ነው ያሉት::  ሁለቱም በቁጭት ውስጥ ናቸው የሚፈውስ እያለ አንተን የመሰለ ወዳጅ እያለን አለፈ ወንድማችን::  ለእየሱስ የረፈደበትና አሁን ምንም ማድረግ እንደማይችል አድርገው ነው የጸለዮት ወይምእያወሩት ያለው::  ቁጭት!!  

ኢየሱስም አላት፦ “ትንሣኤና ሕይወት እኔ ነኝ፤ የሚያምንብኝ ቢሞት እንኳ ሕያው ይሆናል፤ ሕያው የሆነም የሚያምንብኝም ሁሉ ለዘላለም አይሞትም፤ ይህን ታምኚያለሽን?” አሜን!  እርሱ ትንሣኤና ሕይወት ነው!!!  ሃሌሉያ!  “ወንድምሽ ይነሣል፡”  ሲላት አሜን ማለት ትታ በትንሳኤ ብላ ወደፊት ቀጠረች ግን አንተ መሲህ እንደሆንክ አምናለሁ አለች::  እየስስን በደንብ ገና አላወቀችውም ማርታ:: እምነት ማለት አሁን ነው::

ማርያምም ሊያጽናናቸው የተሰበሰበውን ሰው ሁሉ አስከትላ መጣችና ያንኑ ጸሎት እግሩ ስር ወድቃ እያለቀሰች ነገረችው እርሱም አለቀሰ::  በዙሪያው ያሉት አይሁድ ይህ የእውሩን አይን ያበራ ይህንን እንዳይሞት ማድረግ አይችልም ነበረ ተባባሉ አሁንም ቁጭት::  እየሱስ ወደ ማዶ የተሻገረው ይህ ፈውስ እስኪረሳሳና ነገሩ እስኪረጋጋ ነበረ እነርሱ ግን አልረሱለትም::  የሚያውቁትም የታመመውን እንደሚያድን ብቻ ነው:: የተደገሰላቸውን ተአምር  አላወቁም ገና የሚያውቁት መፈወስ መቻሉን ነው::

እየሱስም “ወዴት አኖራችሁት?” አለም። እነርሱም፦ “ጌታ ሆይ፥ መጥተህ እይ፡” አሉት። ኢየሱስም እንባውን አፈሰሰ። እመቃብሩጋ ሄዶ የሚያለቅስ ነበረ የመሰላቸው:: ስለዚህ አይሁድ፦ “እንዴት ይወደው እንደ ነበረ እዩ፡” አሉ።

ጌታዬ ሆይ አንተ ትንሳኤና ህይወት ነህና በአንተ መታመን ይሁንልኝ! እምነትም አሁን ነውና አምናለሁ!  ያለቀለት ነገር የተውኩት የተቀበረ ሁሉ አሁን ይነሳ::  አሜን!

ዮሐንስ 11: 38-44

39፤ ኢየሱስ፦ “ድንጋዩን አንሡ፡” አለ። የሞተውም እኅት ማርታ፦ “ጌታ ሆይ፥ ከሞተ አራት ቀን ሆኖታልና አሁን ይሸታል፡” አለችው።

ወደ ቢታንያም ይሁን ወደ መቃብሩ ከመምጣቱ በፊት ያመጣው ነገር  ክብሩን ለመግለጥና አባቱን ለማስከበር ነው::“ድንጋዩን አንሡ፡”  ባለ ጊዜ ተቃውሞ የተነሳበት  እኔ ትንሳኤና ህይወት ነኝ ሲላት ከቆየችው ከማርታ ነበረ::  እውነት ወንድምዋ እንዳይነሳ ፈልጋ ነው? አይደለም ግን እንቅፋት ልትሆን የተነሳችው ቃሉ ከእርስዋ ጋር ስላልተዋሃደ ነው::  ቢዋሃድ ኖሮ እንደማርያም ዝም ብላ ትጠብቅ ነበረ::  በራሳችን ነገር ላይ እንቅፋት አንሁን ቃሉ በሙላት ይኑርብን ይህ ቃል ህይወት ነው መንፈስም ነው::  ይሰራል!!!  በእኛ ዙሪያ ባለው ሁኔታ እግዚአብሔርን ልናስረው አንሞክር እርሱ ትልቅ አምላክ ነውና::  ክብር ይሁንለት አሜን!!

ለማርታ የመለሰላት  “ብታምኚስ የእግዚአብሔርን ክብር እንድታዪ አልነገርሁሽምን?” አላት።  እዛው ክፍል ነው የከለሳት ከደቂቃዎች በፊት ወደተናገራት ህይወትነቱና ትንሳኤውን ማለቱ ነው::  ጊዜያችንን እያባከንን አንድ ክላስ ስንከልስ እንዳንገኝ ጌታ ይርዳን:: ዛሬም ብናምን ክብሩን እናያለን!! አሜን!

ሰዎቹ ያለ ምንም ተጨማሪ ጥያቄ ድንጋዩን ለማንሳት ታዘዙ::  እማስበው ግን በዚያ ዙሪያ የነበሩት ሰዎች ምን እያሰቡ ይሆን? ምን ሊያደርግ ነው ብለው እርጭ ብለው እየጠበቁ ነው መቼም::  ድንጋዩንም አነሡት። ኢየሱስም ዓይኖቹን ወደ ላይ አንሥቶ እንዲህ አለ።፦ “አባት ሆይ፥ ስለ ሰማኸኝ አመሰግንሃለሁ። ሁልጊዜም እንድትሰማኝ አወቅሁ፤ ነገር ግን አንተ እንደ ላክኸኝ ያምኑ ዘንድ በዚህ ዙሪያ ስለ ቆሙት ሕዝብ ተናገርሁ።” ብሎ አጭር ጸሎት ጸለየ የጸለየበትም ምክንያት በዙሪያው ያሉት ይሰሙና ጸሎቱም ሲመለስ አይተው እንዲያምኑ ነው::  ዛሬም ይህ ጌታ አልተለወጠም  እንወራረድበት አንዳች እንደፈቃዱ ስንለምን ይሰማናል::  ፈቃዱንም የሚያስታውቀን በህያው ቃሉ ነው::  እየሱስ ጌታና አዳኝ መሆኑን አብ ዛሬም ይመሰክርለታል ብቻችንን አይደለንም ስንመሰክር ሰማይ ሁሉ አብሮ ይሰራል::

ይህንም ብሎ፡ በታላቅ ድምፅ፦ “አልዓዛር ሆይ፥ ወደ ውጭ ና፡” ብሎ ጮኸ። የሞተውም እጆቹና እግሮቹ በመግነዝ እንደ ተገነዙ ወጣ፤ ፊቱም በጨርቅ እንደ ተጠመጠመ ነበር። ኢየሱስም፦ “ፍቱትና ይሂድ ተዉት፡” አላቸው። ሃሌሉያ!  ሰውን ፈቶ የሚለቅ ጌታ!  ነገራችን አሁን ቢሞት ወይም ትላትና ወይም ደግሞ ቆይቶም ቢሆን ትንሳኤ አለ::  ሃሌሉያ!  ዛሬም ይሰራል! 

አባት ሆይ፥ ስለ ሰማኸኝ አመሰግንሃለሁ። ሁልጊዜም እንድትሰማኝ አወቅሁ፤ ብለህ እንዳልክ እኔም በምስጋና ወደፊትህ  እንደምትሰማኝ አውቄ መጣሁ:: አንተ አልተለወጥክም ተራራ የሆነ ነገር ሁሉ አሁን ሜዳ ይሁን የሞተው ነገሬህይወትን ያግኝና  የክብርህ መገለጫ ይሁን::  ትንሳኤና ህይወት እምነትም አሁን ነውና አሁን አድን:: እየሱስ ህያው ነው ብዬ የሰበኳቸው ሁሉ ይዳኑና ክብርህን ይዩ ህይወትም ይሁንላቸው:: በድፍረት ልወራረድብህ! ጸሎቴን እንደምትሰማኝ አምናለሁ::  ተመስገን!!

ዮሐንስ 11: 45-57

51፤ ይህንም የተናገረ ከራሱ አይደለም፥ ነገር ግን በዚያች ዓመት ሊቀ ካህናት ነበረና ኢየሱስ ስለ ሕዝቡ ሊሞት እንዳለው ትንቢት ተናገረ፤

የአላዛርን መነሳት ከማርያም ጋር የመጡት፥ ኢየሱስ ያደረገውን አይተው ብዙዎች በእርሱ አመኑ ይላል:: ከእነርሱ አንዳንዶቹ ግን ወደ ፈሪሳውያን ሄደው ኢየሱስ ያደረገውን ነገሩአቸው። ለምን ይሆን መሲህ ተገኝቷል ይሆን ወይስ ሌላ ምክንያት?  ይህ መረጃ ግን እየሱስን ለመግደል እንዲያሴሩ አደረጋቸው::

እንግዲህ የካህናት አለቆችና ፈሪሳውያን ሸንጎ ሰብስበው፦ “ምን እናድርግ? ይህ ሰው ብዙ ምልክቶች ያደርጋልና። እንዲሁ ብንተወው ሁሉ በእርሱ ያምናሉ፤ የሮሜም ሰዎች መጥተው አገራችንን ወገናችንንም ይወስዳሉ፡” አሉ።  ህዝቡ በእርሱ ማመናቸውና የሮማውያን መጥቶ መውረርን ምን አገናኘው ያሰኛል ምናልባትም እስራኤሎች ብቻ ነበሩ አምላካቸውን እንዲያመልኩ በሮም ህግ የተደነገገላቸውና የተፈቀደላቸው ምክንያቱም ይሞታሉ እንጂ ለቄሳር አይሰግዱም አሁን እየሱስ የሚታይ ንጉስ ማምለክ ቢጀምሩ አመፃችሁ ይባላሉ ይመስላል ፍራቻቸው ያም ሆነ ይህ እየሱስ ተላልፎ መሰጠት ነበረበት::  የፈሩትም ከጥቂት ዓመታት በኃላ ተፈጸመ እየሩሳሌም ጠፋች እየሱስ ግን ቀድሞ አልቅሶላታል:: 

ለምክራቸው መቋጫ ያመጣው በዚያ ጊዜ ሊቀ ካህናቱ ትንቢትን በመናገር ነበረ: ሕዝቡም ሁሉ ከሚጠፋ አንድ ሰው ስለ ሕዝቡ ይሞት ዘንድ እንዲሻለን አታስቡም፡” አላቸው። እንግዲህ ከዚያ ቀን ጀምረው ሊገድሉት ተማከሩ።ከዚያ ወዲያም ኢየሱስ በአይሁድ መካከል ተገልጦ አልተመላለሰም፤ ነገር ግን ከዚያ በምድረ በዳ አጠገብ ወዳለች ምድር፥ ኤፍሬም ወደምትባል ከተማ ሄደ፤ በዚያም ከደቀ መዛሙርቱ ጋር ተቀመጠ።

እየሱስ በዚህ ሁሉ ውድጥ አልፈህ ስለ ሁላችን እራስህን አሳልፈህ ስለሰጠህ ተመስገን! ከጨለማ ወደ ብርሃን አመጣኸን ተባረክ!  አሜን

ዮሐንስ 12: 1-11

3፤ ማርያምም ዋጋው እጅግ የከበረ የጥሩ ናርዶስ ሽቱ ንጥር ወስዳ የኢየሱስን እግር ቀባች፤ በጠጕርዋም እግሩን አበሰች፤ ቤቱም ከናርዶስ ሽቱ ሞላ።

በዚህ የእራት ግብዣ እየሱስ ታድሟል::  ዋው እየሱስን ለእራት መጋበዝ አምላክ የሆነ ጌታ በቤታቸው ተገኘ::  ዛሬም ጌታ ወደ እኛ ይመጣል በዮሐንስ 14:23፤ ኢየሱስም መለሰ፡ አለውም፦ “የሚወደኝ ቢኖር ቃሌን ይጠብቃል፤ አባቴም ይወደዋል፡ ወደ እርሱም እንመጣለን፡ በእርሱም ዘንድ መኖሪያ እናደርጋለን። አሜን! ለዘላለም በእኛ ዘንድ ይኖራል::  አማኑኤል!

ሌላው በእራቱ ላይ የነበረው ከሞት የተነሳው አልአዛር ነው::  በዚህ ደስታ ውስጥ ነው ይህ ቤተሰብ  ያለው ለቅሶ ቀርቶ ደስታ ሆነላቸው::  በዚህ መሃል ለየት ያለ አምልኮ ነው ማርያም ያደረገችው ምናልባትም ከባህሉም ወጣ ያለ::  ሽቶ አፍስሶ በጸጉር ማበስ ሽቶውም ቤቱን ሞላው::  በመነዳት ነው ታደርገው የነበረው እርስዋ ግን ፍቅርዋን ለመግለጽ ነበረ::  ክብርዋን ጥላ ገንዘብዋንም አውጥታ ደስታዋንና አምልኮዋን እየገለጠች ነው::  እያደረገች ያለውንም በቅጡ የተረዳች አትመስልም ነገር ግን ጌታ ገብቶታል:: ይህንን ያደረገችው ለመቃብሬ ነው አለ ምክንያቱም ፋሲካ እየደረሰ ነው:: ተላልፎ ለመሰጠትም የቀረው ጥቂት ቀናት ነው::  ዛሬም በመንፈስ መነዳት ይሁንልንና እርሱን መታዘዝ ፈቃዱንም ማድረግ ይብዛልን::

ማርያም ይህንን አምልኮ ስታደርግ የተቃወመ ነበረ ምክንያቱ ደሃን በማሰብ በሚል የሚኮንን አስተያየት ነገር ግን ጏዳው ሲፈተሽ  ሌብነት ስለነበረበት ነው ይላል ቃሉ::   ተቃውሞ ቢነሳ ጌታን ታዘን አይድነቀን ብቻ እርሱን ደስ እናሰኝ::  ህብረት ውስጥ ብዙ አይነት ሰው አለ ፍረዱ ሳይሆን የተባልነው በፍቅር አቅኑ ነውና ጌታ ይርዳን::  

የሚገርመው አይሁድ እየሱስን ብቻ ሳይሆን አላዛርንም ለማጥፋት ተማከሩ:: እርሱ ህያው ምስክር ሆኖ አስቸግሯልና ነው::  ዛሬም እኔ ከዘላለም ሞት ከጥፋት አምልጬ ወደ መንግስቱ የገባሁ በመንፈስ ቅዱስ የታተምኩኝ ነኝና ጠላት አዋጅን አውጥቷል ሊሰርቅ ሊያጠፋና ሊገድል::  እኔ ግን ብርሃኔን እየሱስን እያብለጨለጭኩኝ እኖራለሁ::  እኔ ምስክር ነኝ ከሞትም ወደ ህይወት የተሻገርኩኝ ነኝና:: 

አባት ሆይ ተመስገን እኔም ዛሬ ከፍ አደርግሃለሁ በዝማሬና በአምልኮ በመገዛትና በመታዘዝ እራሴን ወደ አንተ ህያውና ቅዱስ መስዋእት አድርጌ አቀርባለሁ:: አሜን

ዮሐንስ 12: 13-19

13፤ የዘንባባ ዛፍ ዝንጣፊ ይዘው ሊቀበሉት ወጡና፦ “ሆሣዕና፤ በጌታ ስም የሚመጣ የእስራኤል ንጉሥ የተባረከ ነው፡” እያሉ ጮኹ።

ዮሐንስ 12:14-15፤ “አንቺ የጽዮን ልጅ አትፍሪ፤ እነሆ፥ ንጉሥሽ በአህያ ውርንጫ ላይ ተቀምጦ ይመጣል፤” ተብሎ እንደ ተጻፈ፥ ኢየሱስ የአህያ ውርንጫ አግኝቶ በእርሱ ተቀመጠ።

መጽሃፍት ሁሉ ስለ እኔ ይናገራሉ እንዳለ ጌታ በመዝሙር 118:25፤ አቤቱ፥ እባክህ፥ አሁን አድን፤ አቤቱ፥ እባክህ፥ አሁን አቅና። እንደሚል እርሱን ለመቀበል ህዝቡ ሆሣዕና እያሉ የዘንባባ ዛፍ ዝንጣፊ ይዘው ሊቀበሉት ወጡ::  እርሱም በትንቢት  እንዲህ  እንደተነገረው “አንቺ የጽዮን ልጅ አትፍሪ፤ እነሆ፥ ንጉሥሽ በአህያ ውርንጫ ላይ ተቀምጦ ይመጣል፤” ተብሎ እንደ ተጻፈ፥ ኢየሱስ በአህያ ውርንጫ ተቀመጠ። ቃሉን የሚያከብር ጌታ ይባረክ!

አሁንም አልተለወጠም ቃሉን ይፈጽማልና እምነታችንን እናበርታ አይናችንንም በእርሱ ላይ እናድርግ::  ተላልፎ ወደ መሰጠት ከመሄዱ በፊት ያደረገው ይህ ተአምር ብዙዎችን እንዲያምኑበት በጠላትነት የተነሱበትንም አይሁዶች የሚይዙትን ያሳጣበት ክስተት ነው:: የነገሮችን መክረር እናያለን በእርሱ በኩል ስናየው ሁሉ በእቅድ ወደ ፍፃሜው እየሄደ ነበረ::  ከጌታ ጋር ከተራመድን ነገር ሁሉ እንደፈቃዱ ሲሆን ያስደንቀናል እንመነው ብቻ ይህንን ጌታ::  እርሱ ትህትናውን ለመግለጥ በአህያ እንደመጣ ትህትናንም ከእኔ ተማሩ ስላለን በትህትና ዝቅ ብለን እርሱን እያሳየን መመላለስ ይሁንልን::

አባት ሆይ ማስተዋልን ስጠን! ጸጋህም ይብዛልን!  አሜን

ዮሐንስ 12: 20-26

23፤ ኢየሱስም መለሰላቸው፥ እንዲህ ሲል፦ “የሰው ልጅ ይከብር ዘንድ ሰዓቱ ደርሶአል።

24፤ እውነት እውነት እላችኋለሁ፥ የስንዴ ቅንጣት በምድር ወድቃ ካልሞተች ብቻዋን ትቀራለች፤ ብትሞት ግን ብዙ ፍሬ ታፈራለች።

25፤ ነፍሱን የሚወድ ያጠፋታል፥ ነፍሱንም በዚህ ዓለም የሚጠላ ለዘላለም ሕይወት ይጠብቃታል።

26፤ የሚያገለግለኝ ቢኖር ይከተለኝ፥ እኔም ባለሁበት አገልጋዬ ደግሞ በዚያ ይሆናል፤ የሚያገለግለኝም ቢኖር አብ ያከብረዋል።”

ከግሪክ ለበዕሉ ሊሰግዱ የመጡ ሰዎች እየሱስን ማየት ፈለጉና ጠየቁ::  ደቀመዝሙቱም መተው ሲነግሩት እርሱ የሚመልሰውና የሚጠይቁት የሚገናኝ አይመስልም::  ነገር ግን እነዚህ ሰዎች  እየሱስን ልናይ እንወዳለን ነበረ ጥያቄያቸው እንጂ እንደከዚህ ቀደሙ ወደእርሱ ለፈውስ እንደመጡት አህዛብ አልነበረም ጥያቄያቸው::  የሚፈልጉት መሲሁን ነው!  እየሱስም ያለው፦ “የሰው ልጅ ይከብር ዘንድ ሰዓቱ ደርሶአል::  ምክንያቱም አህዛብም አዳኝ እየፈለጉ ነውና::  አጥብቆ ሲናገር የነበረውና ሁለት ሁለትም አድርጎ ለአገልግሎት ሲልካቸው አገልግሎቱ ለእስራኤል ልጆች እንደሆነ ግልጽ አድርጎ ነበረ::  በተባራሪ መተው ፈውስ ከተቀበሉት በቀር ያተኮረው በእስራኤል ላይ ብቻ ነበር::

ሰዓቱ ደርሶአል ብሎ ሲል “የሰው ልጅ ይከብር ዘንድ” መልካም ነገር አይመስልም?  እንደው ወድያው ንጉስ የሚያደርጉት አይመስልም?  መክበር ሲል ግን ምሳሌ እንደሰጠው እንደስንዴዋ ቅንጣት ነው::  ካልሞተች ብዙውን ፍሬ እንደማትሰጥ እየሱስም ካልከበረ የሰውን ልጅ ማዳንና የጥሉን ግድግዳ ማፍረስ አይችልም ነበረ::  ከዚህ የሚበልጥ ፍቅር ለማንም የለውም::  

እየሱስ እንዳለን ነፍሱን በዚህ ዓለም የሚጠላ ለዘላለም ሕይወት ይጠብቃታል። እርሱ ይህንን አድርጎ ፈለጋውን ትቶልን አለፈ::  ስለዚህ የሚያገለግለኝ ቢኖር ይከተለኝ፥ እኔም ባለሁበት አገልጋዬ ደግሞ በዚያ ይሆናል፤ የሚያገለግለኝም ቢኖር አብ ያከብረዋል።” ብሎ አለን::   ዓለምን ንቀን ለእርሱ በጸጋው እየተገዛን ስንመላለስ እርሱ ከእኛ ጋር ይሆናል:: 

አባት ሆይ ስራዬን ሁሉ ሰርተህ አንተ ባለህበት ህይወቴን ሸሽገኸዋልና አመሰግንሃለሁ::  ፈለጋህን እንድከተልና ፍሬ እንዳፈራ አሁንም እራሴን ለአንተ እሰጣለሁ::  የሰዎች መጥፋት ግድ ይበለኝ! አንተን እንደሚያሳስብህ ያስስበኝ!

ዮሐንስ 12: 27-36

27፤ “አሁን ነፍሴ ታውካለች ምንስ እላለሁ? አባት ሆይ፥ ከዚህ ሰዓት አድነኝ። ነገር ግን ስለዚህ ወደዚህ ሰዓት መጣሁ።

28፤ አባት ሆይ፥ ስምህን አክብረው።” ስለዚህም፦ “አከበርሁት ደግሞም አከብረዋለሁ፡” የሚል ድምፅ ከሰማይ መጣ።

ሰዕቱ ደረሰ ብሎ አውጆ እየተዘጋጀ ነው::  በዚህ ዝግጅት መካከል ያደረገው ጸሎት ነው ምክንያቱም አሁን ነፍሴ ታውካለች ምንስ እላለሁ? አባት ሆይ፥ ከዚህ ሰዓት አድነኝ። ነገር ግን ስለዚህ ወደዚህ ሰዓት መጣሁ እያለ::  ጸሎቱን ሲጨርስ መልስ ከሰማይ መጣ መልሱ ግን ለእርሱ እንዳልሆነ ነገራቸው ምክንያቱም እየሱስ  ማረጋገጫ አያስፈልገውም::  በዙሪያው ያለእ ህዝብ ግን አብ ከእየሱስ ጋር እንዳለና ስሙንም እንደሚያከብር መሰከረ::  ለሰው ልጅ ሲል እየሱስ ነፍሱ ታወከች አድነኝ ብሎም ለመነ መልሶ ደግሞ እራሱን ያጽናናል ወደዚህ የመጣሁት ለዚህ ሰዓት ነው እያለ::  አንዳንዴ ግራ ግብት የሚል ነገር ውስጥ ስንገባ እናስታውስ እየሱስም ገጥሞት እንደነበረና ሊረዳን አብሮን እንደሆነ::

ከሰማይ የመጣውን ድምጽ መልአክ ተናገረው ሲሉ ሌሎች ደግሞ ነገድጏድ ነው አሉ የእግዚአብሔር ነገር ለስጋውያን ሞኝነት ነውና አልተረዱትም ምንም አይነት ሪአክሽን አልነበራቸውም እንግዲህ ምን ይምጣ ድምጹን ከሰማይ ከመላክ በላይ?  ቀጠለ ሊያስረዳ አሁን የዚህ ዓለም ፍርድ ደርሶአል፤ አሁን የዚህ ዓለም ገዥ ወደ ውጭ ይጣላል፤ እኔም ከምድር ከፍ ከፍ ያልሁ እንደ ሆነ ሁሉን ወደ እኔ እስባለሁ።” አላቸው በምን አይነት ሞት እንደሚሞት የሮም ስርዓት ነው ሰውን በመስቀል ላይ መስቀል::  አልገባቸውም!  ክርስቶስ ለዘላለም ይኖራሉ ብለው መለሱለት::  የእግዚአብሔር በግ ሆኖ እንደመጣም አላወቁምና::

አሁንም ተስፋ ሳይቆርጥ ኢየሱስም፦ “ገና ጥቂት ጊዜ ብርሃን ከእናንተ ጋር ነው። ጨለማ እንዳይደርስባችሁ ብርሃን ሳለላችሁ ተመላለሱ፤ በጨለማም የሚመላለስ ወዴት እንዲሄድ አያውቅም።

የብርሃን ልጆች እንድትሆኑ ብርሃን ሳለላችሁ በብርሃኑ እመኑ፡” አላቸው። ኢየሱስም ይህን ተናግሮ ሄደና ተሰወረባቸው። ብርሃኑን እየሱስን አምነው እንዲያመልጡ ነገራቸው እነሱ ግን አልገባቸውም::  ይህ የህይወት ብርሃን በርቶልናልና ሳንሰለች ስለዚህ ስለተንገላታ ጌታ መመስከርን እናብዛ!

ዮሐንስ 12: 37-46

44፤ ኢየሱስም ጮኸ፥ እንዲህም አለ፦ “በእኔ የሚያምን በላከኝ ማመኑ ነው እንጂ በእኔ አይደለም፤

45፤ እኔንም የሚያይ የላከኝን ያያል።

46፤ በእኔ የሚያምን ሁሉ በጨለማ እንዳይኖር እኔ ብርሃን ሆኜ ወደ ዓለም መጥቻለሁ።

ነገር ግን ይህን ያህል ምልክት በፊታቸው ምንም ቢያደርግ፤ ነቢዩ ኢሳይያስ፦ “ጌታ ሆይ፥ ማን ምስክርነታችንን አመነ? የእግዚአብሔርስ ክንድ ለማን ተገለጠ?” ብሎ የተናገረው ቃል ይፈጸም ዘንድ በእርሱ አላመኑም።  ያመኑትም በአደባባይ መመስከርን ፈሩ::  ስለዚህም ኢየሱስ ጮኸ፥ እንዲህም አለ፦ “በእኔ የሚያምን በላከኝ ማመኑ ነው እንጂ በእኔ አይደለም፤ እኔንም የሚያይ የላከኝን ያያል አላቸው መፍራታቸውን ሲያይ:: ዛሬስ የሚያስፈራን ምንድነው? ስለእየሱስ ጌትነት በሙላት እንመስክር:: 

ጌታም እንዳለ በእኔ የሚያምን ሁሉ በጨለማ እንዳይኖር እኔ ብርሃን ሆኜ ወደ ዓለም መጥቻለሁ ብሏል::  ብርሃናችን እየሱስ ለእኛም የህይወት ብርሃን ሆነልን::  ጨለማችን በራ!!  በጨለማ ላሉት የዔለም ብርሃን አደረገን::  ምንም ውስጥ ብንገባ ብርሃናችን ከሩቁ ይታያልና ደምቀን በሙላት እየታየን እንመላለስ እንጂ አንደበቅ!

አባት ሆይ የሰዎች ልብ ተከፍቶ አንተን ያውቁ ዘንድ እርዳን::  እኛም በድፍረት ጌትነትህን እንድንመሰክር በመንፈስ ቅዱስ እርዳን::  አሜን

ዮሐንስ 13:1፤ ኢየሱስም ከፋሲካ በዓል በፊት፥ ከዚህ ዓለም ወደ አብ የሚሄድበት ሰዓት እንደ ደረሰ አውቆ፥ በዚህ ዓለም ያሉትን ወገኖቹን የወደዳቸውን እስከ መጨረሻ ወደዳቸው።

እየሱስ ወደ መስቀል ከዛም ወደመጣበት ክብሩ የሚሄድበት ጊዜ እንደ ደረሰ አውቆ መውደዱን የሚያሳይበት ወቅት ላይ ነው::   በዚህ ዓለም ያሉትን ወገኖቹን የወደዳቸውን እስከ መጨረሻ ወደዳቸው። አቤት ምን አይነት መወደድ ነው? እራሱን እስኪሰጥ ድረስ እኛን መውደዱ?!  ይወዳቸው ነበረ ግን እስከመጨረሻ ሄዶ መውደዱን  ያሳየበት መስቀሉ ነው:: ሰው ምን ያህል እንደተወደደ ከገባው ዘመኑን ሁሉ በእርካታና በእረፍት ይኖራል እንጂ በትልቅ በትንሹ የሚሸበር አይሆንም::  በጌታው ተማምኖ የሚመላለስ ይሆናል::  ይህንን ፍቅር ለማወቅ ጣሩ ይላል ቃሉ::

እግዚአብሔር ሰውን መውደዱ የተገለጠው አንድያ ልጁን ወደ ዓለም ነፍሱን እንዲሰጥ ሲልከው ነው:: የእግዚአብሔር በግ ተብሎ ተሰየመ::  እየሱስ ስለ እኔ በሸላቾቹ ፊት ዝም አለ:: ሃሌሉያ!  እኔን ለማዳን ይህች ጽዋ ከኔ ትለፍ እያለ ግን ቀጠለበት::  እራሱን በፈቃዱ አሳልፎ ሰጠኝ!  

አባት ሆይ ምን አይነት ፍቅር ነው?!  አመሰግንሃለሁ!  ስምህንም እባርካለሁ!  የተወደድኩበት ፍቅር ጥልቅ ነውና ዓለት ዕለት ለማወቅ ልዘርጋ እርዳኝ::

ዮሐንስ 13: 2-5

3፤ ኢየሱስ አብ ሁሉን በእጁ እንደ ሰጠው ከእግዚአብሔርም እንደ ወጣ ወደ እግዚአብሔርም እንዲሄድ አውቆ፥

4፤ ከእራት ተነሣ ልብሱንም አኖረ፥ ማበሻም ጨርቅ ወስዶ ታጠቀ፤

5፤ በኋላም በመታጠቢያው ውኃ ጨመረ፥ የደቀ መዛሙርቱንም እግር ሊያጥብና በታጠቀበትም ማበሻ ጨርቅ ሊያብስ ጀመረ።

እየሱስ ፍጹም ፍቅሩን የሚገልጥበት ጊዜ ደርሷል::  ፍቅሩም የሚገለጠው እራሱን በመስጠት ነው:: 

በጣም የገረመኝ ነገር እራትም ሲበሉ ዲያብሎስ በስምዖን ልጅ በአስቆሮቱ በይሁዳ ልብ አሳልፎ እንዲሰጠው አሳብ ካገባ በኋላ ነው እየሱስ ጊዜው አሁን ነው ብሎ የተነሳው::  ጠላት አሳልፎ ሊሰጠው ሲዶልት አብ አባት ደግሞ ቃሉ  እንደሚለን አብ ሁሉን በእጁ እንደ ሰጠው አውቆ::  የእንግሊዘኛው power እንደሰጠው ነው የሚነግረን:: ሁሉ ስልጣን የተሰጠው ታድያ ትሁት ሆኖ በሸላቾቹ ፊት ዝም ይላል እንዴ?!  እስኪ እናስበው ስልጣን የተሰጠው ሰው ወድያውበስሩ ባሉት ላይ ለመሰልጠን  ነው የሚነሳው ::  እየሱስ ግን   ከእራት ተነሣ ልብሱንም አኖረ፥ ማበሻም ጨርቅ ወስዶ ታጠቀ ይላል!! 

እየሱስ ትህትናን ከእኔ ተማሩ ሲለን ሳይኖረው አይደለም ይኸው ኖሮት ነው::  ትህትና የመንፈስ ፍሬ አይደለም የምናፈራው ነው እንጂ!  ይህ ሁሉ በእጁ የተሰጠው ጌታ ማድረግ የነበረበት ይሁዳን መግለጥና መቆጣ መውቀስ ነበረ ሌላም ሌላም ማለት ይቻላል የአይሁድን መሪዎች እንደፈለገ ማድረግ ይችላል ወይም የሮምን አገዛዝ . . . ግን አላደረገውም::  ለጊዜውለሆኑና  ለሚያልፉ ነገሮች ህይወታችንን አንበጥብጥ አልፈን ፍቅርን እናሳይና በትህትና እናሳልፍ! 

ይህ ታላቅጌታ በመታጠቢያው ውኃ ጨመረ፥ የደቀ መዛሙርቱንም እግር ሊያጥብና በታጠቀበትም ማበሻ ጨርቅ ሊያብስ ጀመረ::  እንማር! ዝቅ ማለት አቅቶን ይሆን?  ጌታን ብቻ በፊታችን እንይ!  እርሱን ምሰሉ ነውና የተባልነው:: ከእግዚአብሔር እጅ በታች እራስን ማዋረድ በፈቃድ የሚደረግ ነው::

አባት ሆይ ትህትናን ከአንተ ልማር አንተንም ወደ መምሰል ልምጣ እርዳኝ! ዛሬ በጎደልኩበት ሁሉ ጸጋህ ሙላት ይሁነኝ::  ቀኔን በፊትህ እቀድሳለሁ እራሴንም በፊትህ ዝቅ አደርጋለሁኝ አንተ ክበር:: ጠላት ለሚያመጣው ሽንገላ እንዳልታለል ማስተዋልን ስጠኝ::

ተባረክ አባ! 

ዮሐንስ 13: 6-10

8፤ ጴጥሮስም፦ “የእኔን እግር ለዘላለም አታጥብም፡” አለው። ኢየሱስም፦ “ካላጠብሁህ፥ ከእኔ ጋር ዕድል የለህም፡” ብሎ መለሰለት።

ጴጥሮስ እግሩን ለመታጠብ ፈቃደኛ አልሆነም::  አስራ አንዱ ይሁዳንም ጨምሮ ሲታጠቡ እርሱ ግን አሻፈረኝ አለ::  ችኩል ይሁን እንጂ ብዙ ነገር እንድንማርረድቶናል በብዙ አጋጣሚ:: ኢየሱስም መልሶ፦ “እኔ የማደርገውን አንተ አሁን አታውቅም፥ በኋላ ግን ታስተውለዋለህ፡” አለው። ይህ ስንቅ ነበረ ለሐዋርያት ወደፊት እንዴት ማገልገል እንዳለባቸው የሚያስተምር::  ማንንም ሳይለዮ ዝቅ ብሎ ይሁዳንም ማጠብ ማለት ነው::

ስንቅም ብቻ ሳይሆን እየተወላቸው ያለው በሌላው እቅጣጫ የየዕለት ኑሮን እንዴት እንደሚኖር  ያሳያል::  አታጥበኝም ለሚለው ለጼጥሮስ አተያየት ሁለተኛው ምላሹ ከባድ ነበረ:- “ካላጠብሁህ፥ ከእኔ ጋር ዕድል የለህም፡”  ለምን ይህንን አለ?  በየዕለቱ የሚገጥመንን አውቀን ነውና  እይሱስን መከተል ያለብን::  ይኸውም እግር መታጠብ:- ለምን አስፈለገ ለምን ሌላውን አካል አይጨምርም::  በዛ ዘመን ባህሉንም ብናይ በሌላም ቃል ስናይ ለምሳሌ መሃልዬ ላይ ያለችው ሴት እግሬን ታጥቤ በአልጋ ነኝ አለች ነጽታ የቅኑን ቁሻሻ ሁሉ አራግፋ ተኛች ከሙሴም ጋር ጫማህን አውልቅ ነበረ::  

በክርስቶስ የሆንን በደሙ ነጽተናል በዝች ቁሻሻ ዓለም ስንመላለስ የምንረጋግጠው ነገር አለና እራስን በንስሃ ካላየን ከእርሱ ጋር እድል ፋንታ የለንም::  የዓለም ነገር በልጦብን ጥለን የምንሄድ እንሆን ይሆናልና ነው::  አገልግዬ የተጣልኩኝ እንዳልሆን እራሴን እየጎሸምኩ አስገዛለሁ እንደሚለው ነው:: ስለዚህም ጌታ፦ “የታጠበ እግሩን ከመታጠብ በቀር ሌላ አያስፈልገውም፥ ሁለንተናው ግን ንጹሕ ነው፤ እናንተም ንጹሐን ናችሁ አለው። አሜን ዛሬ በደሙ ታጥበን ንጹ ሆነናል::

አባት ሆይ እራሴን መመርመር ይሁንልኝ ጎዳናዬን ስጠበጥብ ከአንተ ጋር እድል ፋንታ ያለው በንስሃ የታጀበ ህይወትን እንድኖር እርዳኝ::

ዮሐንስ 13: 11-20

12፤ እግራቸውንም አጥቦ ልብሱንም አንሥቶ ዳግመኛ ተቀመጠ፥ እንዲህም አላቸው፦ “ያደረግሁላችሁን ታስተውላላችሁን?

13፤ እናንተ መምህርና ጌታ ትሉኛላችሁ፤ እንዲሁ ነኝና መልካም ትላላችሁ።

15፤ እኔ ለእናንተ እንዳደረግሁ እናንተ ደግሞ ታደርጉ ዘንድ ምሳሌ ሰጥቻችኋለሁና።

የገረመኝ ክፍል:- “ያደረግሁላችሁን ታስተውላላችሁን? የሚለው ጥያቄ ነው::  ያደረኩትን ሳይሆን ያደረኩላችሁን ነው ያለው::  ያደረገውን እንድናደርግ እርስ በእርሳችን እንድንተጣጠብ ነው እንጂ ቁጭ ብለን እንድናደንቅ አይደለም የተደረገውም በሰው ላይ ውጤት የሚያመጣ ነው:: የሰውን በደል ይቅር ማለትና ማጠብ ማስወገድ ማንፃት በቃሉም ማጽናናት ይጠበቅብናል:: ጌታ እንዳደረገ እኛም ለሰዎች ልናደርግላቸው ይገባናል:: ምሳሌ ነው የተወልን!! ይህንንም ማድረጋችን ብጹእ ያስብለናል:: እናንተ መምህርና ጌታ ትሉኛላችሁ፤ እንዲሁ ነኝና መልካም ትላላችሁ አላቸው አሁንም ማስተዋላችሁ ያደረኩት ላይ ይሁን ምንም ከፍታ ቢኖራችሁ ዝቅ ማለት አይክበዳችሁ።

እርሱ ትልቅ ሆኖ ሳለ እግርን ካጠበ እኔማ እንዴት አልማር ከዚህ?!  ይሁዳንም ሳይለይ ካጠበ ታድያ እኔ ማነኝ ሰውን የምለይ?!  እየሱስ ልፈርድ አልመጣሁም ለማዳን እንጂ እንዳለ ላስተውልና ከፍርድ ወንበር ወርጄ ሰውን ሳለይ ላገልግል ይገባል::  መለየትና መፍረድ በስተመጨረሻ የጌታ ነውና::

“እውነት እውነት እላችኋለሁ፥ ማናቸውን የምልከውን የሚቀበል እኔን ይቀበላል፥ እኔንም የሚቀበል የላከኝን ይቀበላል።” ጌታ ወደ ህይወታችን የላከውን ሰዎች እንቀበል::  በዙሪያችን ስላሉ ቅዱሳን ጌታን እናመስግን እሱ ልኳቸዋልና::

አባት ሆይ ስለ ቃልህ ተመስገን!  አከብርሃለሁ !  በህይወቴ ስለሰጠኸኝ ሰዎች ተመስገን ዝቅ ብዬ ባለመለየት ሁሉንም በትህትናና በፍቅር እንዳገለግል ጸጋህን ስጠኝ! አሜን!

ዮሐንስ 13: 21-30

21፤ ኢየሱስ ይህን ብሎ በመንፈሱ ታወከ መስክሮም፦ “እውነት እውነት እላችኋለሁ፥ ከእናንተ አንዱ አሳልፎ ይሰጠኛል፡” አለ።

27፤ ቍራሽም ከተቀበለ በኋላ ያን ጊዜ ሰይጣን ገባበት። እንግዲህ ኢየሱስ፦ “የምታደርገውን ቶሎ ብለህ አድርግ፡” አለው።

ኢየሱስ ይህን ብሎ በመንፈሱ ታወከ የሚለው ክፍል እንዴት ይነካል?!  ለዚህ ሰዓት ቢመጣም ቅሉ የሚጠብቀው ያውቅ ነበረና ነው::  የሰይጣን ድፍረት ቀን ከለሊት ከእየሱስ ጋር የሚመላለሰውን ደቀ መዝሙር መጥለፍ ቻለ::  ከእየሱስ ስር አባብሎ ወረሰው::  አንድ መዋግያው ሃሳብን ማስገባት ነው::  ለዚህ ነው አእምሯችን ባዶ መሆን የሌለበት ቃሉን በቀንም በለሊትም አሰላስሉት የተባልነው::  የፈጠረን ጌታ ስለሚያውቀን ነው ይህንን ያለን ስለዚህ ቃሉን የምናሰላስል እንሁን::

ያዕቆብ 1:13፤ ማንም ሲፈተን፦ “በእግዚአብሔር እፈተናለሁ፡” አይበል፤ እግዚአብሔር በክፉ አይፈተንምና፤ እርሱ ራሱስ ማንንም አይፈትንም። 14፤ ነገር ግን እያንዳንዱ በራሱ ምኞት ሲሳብና ሲታለል ይፈተናል። 15፤ ከዚህ በኋላ ምኞት ፀንሳ ኃጢአትን ትወልዳለች፤ ኃጢአትም ካደገች በኋላ ሞትን ትወልዳለች።

እግዚአብሔር አይፈትንም ነገር ግን ምኞታችንን ወይም ሃሳባችንን ጠላት እንዳይጠቀምበት ሃሳባችንን በሃሳቡ እንግዛውና ለጠላት እድል ፋንታ አንስጠው::

ይሁዳ አሳልፎ ሳይሰጠው በፊት እየሱስ ያውቅ ነበረ  ደቀ መዝሙሩም እንደማይሆን እያወቀ እግሩን አጠበው አለየውም::  ይህንን የሚያደርግበት ከጌታ የደረሰበት  ነገር የለም::

አባት ሆይ ሃሳቤ ሁሉ ቃልህን በማሰላሰል ይሞላ::  ቃልህ ህይወት ነው መንፈስ ነውና ህይወቴን ይሙላው::  አሜን! 

ዮሐንስ 13: 31-35

34፤ እርስ በርሳችሁ ትዋደዱ ዘንድ፥ እንደ ወደድኋችሁ እናንተ ደግሞ እርስ በርሳችሁ ትዋደዱ ዘንድ አዲስ ትእዛዝ እሰጣችኋለሁ።

35፤ እርስ በርሳችሁ ፍቅር ቢኖራችሁ፥ ደቀ መዛሙርቴ እንደ ሆናችሁ ሰዎች ሁሉ በዚህ ያውቃሉ።”

ይሁዳ የመጨረሻውን ቁራሽ ይዞ ከወጣ በኃላ ጌታ መክበሩን ነገራቸው::  ታሪኩን ወደፊት የሚሆነውን ስናይ ግን ከመክበር በፊት የመስቀል መከራ ይጠብቀው ነበረ:: ሌላው ያደረገው ነገር የጠለቀውን ትምህርት ደቀ መዝሙር ለመሆን የሚያስፈልጋቸውን ያስተምራቸው ጀመረ::

በብሉይ ኪዳን በዘሌዋውያን 19:18፤  . . . ነገር ግን ባልንጀራህን እንደ ራስህ ውደድ፤በሚለው ስርዓት ነው እየኖሩ የነበረው ሌላውን መውደድ አዲስ አይደለም ያውቁታል ከአስሩ ትዕዛዛት አንዱ ነውና::  ይህንን ትዕዛዝ ግን አዲስ የሚያደርገው ነገር ጌታ ዙሩን አከረረውና በስጋ የማይቻል አደረገው::  ትዕዛዙም:- እንደ ወደድኋችሁ እናንተ ደግሞ እርስ በርሳችሁ ተዋደዱ የሚል ነው::  

ለምን አዲስ ሆነ? 

ምክንያቱም በበፊቱ ትዕዛዝ ላይ ሌሎችን መውደድ ያለብኝ እራሴን እንደምወደው ልክ ነበረ ነገር ግን የአሁኑ አዲሱ ትዕዛዝ ክርስቶስ ሰውን በወደደበት ልክ መውደድ አለብኝ:: የክርስቶስ ፍቅር ምን አይነት ነው?  እስከሞት ድረስ ፤ ያለ ስስት ፤ የራሱን ሳይፈልግ ዝቅ ብሎ የባርያን መልክ አስይዞ የሚያስመጣ ፤  በትእግስት የተሞላ ፍቅር፤ ለዘላለም የሆነ ፍቅር::  ታድያ እንደዚህ ሰውን እወዳለሁ?  ከባድ ትዕዛዝ ነው ለካ::   ቃሉ የሚለን ግን በራሴ ይህንን ስለማልችል በመንፈስ ቅዱስ ፍቅሩ በእኛ ውስጥ ፈሷል ይህንን ፍቅር እለማመደዋለሁ::  እየሱስ በእኔ ውስጥ ይወዳል!! አሜን!

በዚህ ፍቅር ስንዋደድ ደቀ መዛሙርቱ እንደ ሆንን ሰዎች ሁሉ በዚህ ያውቃሉ። አሜን!

ዮሐንስ 13:34፤ እርስ በርሳችሁ ትዋደዱ ዘንድ፥ እንደ ወደድኋችሁ እናንተ ደግሞ እርስ በርሳችሁ ትዋደዱ ዘንድ አዲስ ትእዛዝ እሰጣችኋለሁ።

ዙሩ ከሯል እርስ በእርሳችን ብቻ ሳይሆን ጠላታችንንም መውደድ ይጨምራል::  ይህ ለመውደድ ጥረት ማድረግ አይደለም እግዚአብሔር ፍቅር ነውና ከእርሱ ተቀብለን ፍቅርን በመንፈስ ቅዱስ እንወዳለን:: የወደዱኝን መውደድማ ቀላል ነው ይህንን ግን ሽሮት በፍጹም ፍቅር እንድንመላለስ ፈልጏል::  ጌታ ይርዳን!

አባት ሆይ ከመታወቅ ስለሚያልፈው ፍቅርህ ተመስገን::  እኔም በዚህፍቅር መጥለቅለቅ ይሁንልኝ::  ከውስጤ ይህ ምንጭ ይፍለቅ::  ሁሉን ለአንተ ሰጠሁህ መንፈስ ቅዱስ::  አሜን!

ዮሐንስ 13: 36-38

38፤ ኢየሱስም እንዲህ ብሎ መለሰለት፦ “ነፍስህን ስለ እኔ ትሰጣለህን? እውነት እውነት እልሃለሁ፥ ሦስት ጊዜ እስክትክደኝ ድረስ ዶሮ አይጮኽም።”

እየሱስ በዝግ ሐዋርያቱን እያስተማረ ነው::  በዚህ መሃል ልሄድ ነው ማለቱን ሲሰማ ስምዖን ጴጥሮስም፦ “ጌታ ሆይ፥ ወዴት ትሄዳለህ?” አለው። ኢየሱስም፦ “ወደምሄድበት አሁን ልትከተለኝ አትችልም፥ ነገር ግን በኋላ ትከተለኛለህ፡” ብሎ መለሰለት። ያለእኛ ወዴት ይሄዳል ብሎ ነው::  እነርሱ የሚያውቁት ጌታ አብሯቸው ይኖራል ደግሞም ይልካቸዋል ተአምራት ያደርጋሉ::  ሁሉ አልጋ ባልጋ ነው እየሱስ እያለ::  ታድያ የምን እሄዳለሁ ነው የሚለው ይመስላል::

ልትከተለኝ አትችልም ቢባልም ሊዋጥለትያልቻለው ጴጥሮስ ምን ሲሆን ብሎ ፎከረ::  ጴጥሮስም፦ “ጌታ ሆይ፥ አሁን ልከተልህ አለመቻሌ ስለ ምንድር ነው? ነፍሴን ስንኳ ስለ አንተ እሰጣለሁ፡” አለው። በኃይልም በብርታትም አይደለም በመንፈሴ ነው::  በስጋ የእግዚአብሔር ስራ አይሰራም::  እየሱስ ለዝች ሰዓት መጣ ማንም ሳያግዘውና ሳይረዳው የእግዚአብሔር በግ ሆኖ ህይወትን ሊሰጠን ብቻውን መሰጠት ነበረበትና ጌታ እንደተናገረው ሦስት ጊዜ እስክትክደኝ ድረስ ዶሮ አይጮኽምአደረገው::

እርሱ ብቻእን ድንቅ የሚሰራ ነውና በሚለን ልክ እንመላለስ::  በመንፈሱም በውስጥ ሰውነታችን እንበርታ::  አሜን!

አባት ሆይ የኔ ጽድቅ ቤትህን አይሰራም በመንፈስህ ግን አበርታኝ በራስ የሆነ ትምክህትንም ከእኔ አስወግድ::  አሜን

ዮሐንስ 14:1፤ ልባችሁ አይታወክ፤ በእግዚአብሔር እመኑ፥ በእኔም ደግሞ እመኑ።

እየሱስ ይህንን ሲላቸው ደቀ መዛሙርቱ በብዙ ልብ የሚያርድ ነገር ውስጥ እያለፉ ነበረ::  አንደኛው ነገር ከመካከላችሁ አንዱ ይክደኛል አለ  ከዛም ቀጠለና እንደሚለያቸው ነገራቸው ሞት እንደሆነም ገብቷቸዋል ጴጥሮስም እስከሞት እከተልሃለሁ እያለው ነበረና ሌላው ደግሞ ክህደት ዶሮ ሳይጮህ ሶስትጊዜ መካድ::  በዚህ ሁሉ ውስጥ አቅም አተው ተጨንቀዋል ጌታግን ልባችሁ አይታወክ አላቸው::  የህይወት መውጫ ነውና ልብ እንዲታወክ ጌታ አይፈልግም::  የከበባቸው ነገር ግን መፍትሄ የሌለው ነው የሚወዱትን እየሱስን ማስጣል እንደማይችሉ ሲገባቸው ያናውጣል::  አትታወኩ ብሎ ቢያቆም ከባድ ነበረ ግን መታወክ የሌለባቸውንም ምክንያት እንዲሁም ምን ማድረግ እንዳለባቸው ነገራቸው::  

ልባችን አይታወክም አልተባለም ስንታወክ  ግን ምን እናድርግ? መልሱም በእግዚአብሔር  እመኑ፥ በእኔም ደግሞ እመኑ ነው::  እርሱ መታመኛ ነው ማምለጫና መሸሸጊያ!!  ለታወከው ልባችን መፍትሄው ልባችንን ከታወከበት ነገር ላይ አንስተን በእግዚአብሔር ላይ በመታመን መመላለስ ነው::  ቀላል ይመስላል ስንነጋገረው ዋናው በመከራው ውስጥ ስናልፍ ነውና ማስተዋል ይሁንልን:: ዳዊትነፍሱን አታውኪኝ እንዳለ እንዲሁ ልንል ይገባል::

አባት ሆይ  በአንተ ላይ መደገፍ አንተን ማመን ይሁንልኝ::  አይኖቼ አንተ ላይ እንጂ በዙሪያዬ በሚሆነው ነገር ላይ እንዳይሆን እርዳኝ!  አሜን!

ዮሐንስ 14: 2-4

2፤ በአባቴ ቤት ብዙ መኖሪያ አለ፤ እንዲህስ ባይሆን ባልኋችሁ ነበር፤ ስፍራ አዘጋጅላችሁ ዘንድ እሄዳለሁና፤ 3፤ ሄጄም ስፍራ ባዘጋጅላችሁ፥ እኔ ባለሁበት እናንተ ደግሞ እንድትሆኑ ሁለተኛ እመጣለሁ ወደ እኔም እወስዳችኋለሁ።

አትፍሩ እያለ እያበረታቸው ባለበት ጊዜ ጌታ ሃሴት የሚያደርግ ይመስለኛል ይህንን ሲናገር ምክንይቱም ከነገድ ከቋንቋ ሁሉ በቤቱ ስለሚሰበሰቡት አእላፋት እየተመለከተ ነውና::  ምንም እንኳን ሐዋርያት በዛ ሰዓት የሚይዙት የሚጨብጡት የጠፋባቸው ነገሮች ከሚጠበቅ ፍጥነት በላይ እየቸኮሉባቸው ባለበት ሰዓት መረጋጋትና የሚናገረውን ማገናዘብ አልቻሉም::   ስለዚህም ጠለቅ ብሎ ይነግራቸው ጀመረ::  

በአባቴ ቤት ብዙ መኖሪያ አለ ማለትም ይህ ዓለም የእናንተ አይደለም መፃተኞች ናችሁ እያላቸው እኛንም እያለን ነው::  ልክ ልጅ ሊወለድ ሲል ወደዚህ ዓለም መምጫው ደርሷልና ቤተሰብ እየተዘጋጀ ይጠብቃል::  እንደዚሁ እየሱስ ስፍራ አዘጋጅላችሁ ዘንድ እሄዳለሁና አለን::  ስፍራ ተዘጋጅቷል ልጆቹን ለመቀበል አባት ጏጉቷል::  እንዴት ያለ ፍቅር ነው የተወደድንበት?!

ወዳዘጋጀልን ስፍራ ሊወስደንና ለዘላለም  አብረነው እንድንኖር ይመጣል እየሱስ::  በዚህ ደስ ይበለን ሃሴትም እናድርግ:: የእርሱን መምጣት ስንጠባበቅ እራሱ በመንፈሱ በእኛ ውስጥ ሆኖ እየኖረ ነው እርቆ ሄዶ እንደምንም ብላችሁ ጠብቁኝ አላለንምና ስሙ ይባረክ!

አባት ሆይ ስለተዘጋጀልን ስፍራ  እናመሰግንሃለን!  ለዘላለም አብረንህ እንድንኖር ነው ዓላማህ ተመስገን! አሁንም እኛነታችንን ለአንተ አሳልፈን እንሰጣለን! አሜን

ዮሐንስ 14: 5-6

6፤ ኢየሱስም አለው፦ “እኔ መንገድና እውነት ሕይወትም ነኝ፤ በእኔ በቀር ወደ አብ የሚመጣ የለም።

መንገዱንም ታውቃላችሁ ባላቸው ጊዜ ቶማስ፦ “ጌታ ሆይ፥ ወደምትሄድበት አናውቅም፤ እንዴትስ መንገዱን እናውቃለን?” አለው። እርሱ የሚያስበው ከቦታ ወደቦታ የሚወስደውን መንገድ እንጂ እየሱስን እራሱን መንገዴ ነው ብሎ አላወቀውም::  እንኳንም ይህንን ጥያቄ ጠየቀ የእየሱስን ወደ አብ መሄጃ መንገድ እንደሆነና እንዲሁም እውነታችን እየሱስ: ህይወታችን እየሱስ እንደሆነ አሳወቀን::  ያለእየሱስ ወደ አብ መሄድ አይቻልም በፀሎትም ቢሆን በክርስቶስ ነው ወደፊቱ የምንቀርበው::

አባት ሆይ አመሰግንሃለሁ ህይወትን ሰተኸኝ ለዘላለም እውነት ሆነህ ውሸት የሌለብህ  ጌታ ተቀብለህ ወደ አብ መድረሻ መንገድ ሆንከኝ:: ተባረክ!

ዮሐንስ 14: 7-14

9፤ ኢየሱስም አለው፦ “አንተ ፊልጶስ፥ ይህን ያህል ዘመን ከእናንተ ጋር ስኖር አታውቀኝምን? እኔን ያየ አብን አይቶአል፤ እንዴትስ አንተ፦ ‘አብን አሳየን፡’ ትላለህ?

ጌታ እየሱስ እኔንስ ብታውቁኝ አባቴን ደግሞ ባወቃችሁ ነበር። ከአሁንም ጀምራችሁ ታውቁታላችሁ አይታችሁትማል ሲላቸው ግራ የገባው ፊልጶስ፦ “ጌታ ሆይ፥ አብን አሳየንና ይበቃናል፡” አለው። ጌታ ያለው ከአሁን ጀምራችሁ ታውቁታላችሁ ነው እነሱ ግን ልክ እየሱስን እንደሚያዩት አብንም አሳየን ምናልባትም መገለጥ ይሆን የሚጠብቁት እነሙሴን አይተዋል አንዳንዶች ግን በምን መልኩ ነው አብን ማየት የፈለጉት? አብን አሳየንና ይበቃናል የሚለው ጥያቄ መልስ ሲሰጥ 

– ይህን ያህል ዘመን ከእናንተ ጋር ስኖር አታውቀኝምን? እውነት ነው ለአእምሮ አይመችም  የስላሴ ሚስጥር ግን እኔን ያየ አብን አየ: እኔና አብ አንድ ነን ካለን በቂ ነው:: 

– እኔ በአብ እንዳለሁ አብም በእኔ እንዳለ አታምንምን? እኔ የምነግራችሁን ቃል ከራሴ አልናገረውም፤ ነገር ግን በእኔ የሚኖረው አብ እርሱ ሥራውን ይሠራል።

– ስለዚህ ከእኛ የሚጠበቀው ማመን ነው:- እኔ በአብ እንዳለሁ አብም በእኔ እንዳለ እመኑኝ፤ ባይሆንስ ስለ ራሱ ስለ ሥራው እመኑኝ።

በእየሱስ ማመናችን ቃል እንደገባልን፥ በእኔ የሚያምን እኔ የማደርገውን ሥራ እርሱ ደግሞ ያደርጋል፤ ከዚህም የሚበልጥ ያደርጋል፥ አለን::  እርሱ ያደረገው ምንድነው የአባቱን ፈቃድ በመታዘዝ ማገልገል ነው::  አባቱን አከበረ የምናገረው የእኔ አይደለም የማደርገውም አባቴ ሲያደርግ የማየውን ነው ብሎ በአባቱ ላይ ታምኖ ተመላለሰ::  እርሱ እንደተመላለሰ መመላለስ ይሁንልን::

ሌላው እያስተማረ ያለው በስሙ እንድለምን ነግሮን የምንለምነውንም ደግሞ ሁሉ እንደሚያደርገው ቃል ገብቶልናል በስሙም ስንለምን በዚያ አብ ይከብራል::

ዮሐንስ 14:14፤ ማናቸውንም ነገር በስሜ ብትለምኑ እኔ አደርገዋለሁ።” አሜን!

ዮሐንስ 14: 15-18

15-16፤ “ብትወዱኝ ትእዛዜን ጠብቁ። እኔም አብን እለምናለሁ ለዘላለምም ከእናንተ ጋር እንዲኖር ሌላ አጽናኝ* ይሰጣችኋል፤ (* አጽናኝ ማለት በግሪክ ቋንቋ ጰራቅሊጦስ ማለት ነው)

17፤ እርሱም ዓለም የማያየውና የማያውቀው ስለ ሆነ ሊቀበለው የማይቻለው የእውነት መንፈስ ነው፤ ነገር ግን ከእናንተ ዘንድ ስለሚኖር በውሥጣችሁም ስለሚሆን እናንተ ታውቃላችሁ።

ትእዛዜን ጠብቁ ብሎ ሲለን መስፈርቱ ከወደዳችሁኝ ነው ያለን:: ትእዛዝ ብለን ስንል ለምሳሌ በዚሁ ምዕራፍ ያዘዘን ልባችሁ አይታወክ የሚል ሲሆን በቀደመው ምዕራፍ ደግሞ እኔ እንደወድኳችሁ እርስ በእርሳችሁ ተዋወዱ ነው::  

እኔም አብን እለምናለሁ  አለ ምንድነው የሚለምነው? የሚለምነው ለዘላለምም ከእኛ ጋር የሚኖር  ሌላ አጽናኝ እንዲሰጠ:: ልመናው ተሰማ?  በትክክል ተሰምቶ ሐዋ 2 ላይ መንፈስ ቅዱስ ወረደ ቤተክርስትያንንም ተረከበ::  ሃሌሉያ!

ይህ መንፈስ ቅዱድ ሌላ አጽናኝ ተብሎ ነው የተጠራው::  መንፈስ ቅዱስ ስብእና ያለው: ስሜት ያለው: ማንነት ያለው እንጂ ስሜታችን አይደለም:: እርሱም ዓለም የማያየውና የማያውቀው ስለ ሆነ ሊቀበለው የማይቻለው የእውነት መንፈስ ነው፤ ነገር ግን ከእናንተ ዘንድ ስለሚኖር በውሥጣችሁም ስለሚሆን እናንተ ታውቃላችሁ። ዋዉ አምላካችን ሰው በሰራው ህንፃ አይኖርም እራሱ በሰራው ሰው ውስጥ እንጂ::  አሜን!

ጌታእየሱስ ቃል ገብቶልናል ወላጆች እንደ ሌላቸው ልጆች አልተዋችሁም፤ ወደ እናንተ እመጣለሁ ብሎናል::  የምድር ወላጅ በሞት ይለያል የሰማዮ አባት ግን ሁልጊዜ ከእኛ ጋር ነው::  ይህ ደህንነት እንዴት ያለ ነው? ወልድም መንፈስ ቅዱስም ከእኛ ጋር የሆነበት ህይወት::  ብቸኝነት የሌለበት በወላጃችን ጉያ ውስጥ ሆነን የምንኖረው ኑሮ ነው::  ቅዱሳን እንንቃ ጠላት ማስተዋላችንን አይውሰድ ጌታ ከቦናል እርሱ በውስጣችን ሞልቷል የምንፈራውና ደረሰብኝ የምንለው ምንድነው?  

አባት ሆይ ተመስገን ያለስጋት በአንተ ተማምኜና ተደላድዬ እኖራለሁ:: አሜን

ዮሐንስ 14: 19-20

19፤ ገና ጥቂት ዘመን አለ ከዚህም በኋላ ዓለም አያየኝም፤ እናንተ ግን ታዩኛላችሁ፤ እኔ ሕያው ነኝና እናንተ ደግሞ ሕያዋን ትሆናላችሁ።

20፤ እኔ በአባቴ እንዳለሁ እናንተም በእኔ እንዳላችሁ እኔም በእናንተ እንዳለሁ በዚያን ቀን ታውቃላችሁ።

ዓለም አያየኝም እናንተ ግን ታዩኛላችሁ ብሎ ሲላቸው ግራ ይገባል ለስጋዊ ሰው ምክንያቱም እነዚህ ሰዎች በአዲስ ኪዳን በር ላይ ይሁኑ እንጂ ብሉይ ኪዳን ላይ ናቸው::  እንዳለውም ከትንሳኤው በኃላ አብሯቸው አሳልፏል ዓለም አያየውም ነበረ::  አሁንም እየሱስን በዓይን ባናየውም እኛ ውስጥ በመንፈስ ቅዱስ ይኖራል:: 

እኔ ሕያው ነኝና እናንተ ደግሞ ሕያዋን ትሆናላችሁ። እራሱን የህያዋን አምላክ ብሎ ነው የሚጠራው እርሱ ህያው ነውና ለእኛም የዘላለምን ህይወት ሰጠን! ስሙ ይባረክ!

ዛሬ ጌታ እየስስ እንደነገረን በአባቱ እንዳለ እኛም በእርሱ እንዳለን እንወቅ::  ይህ ብቻ አይደለም  እየሱስ በእኛ  እንዳለ  በዚያን ቀን እንደምናውቅ ነግሮናል:: ወላጆች እንደሌላቸው ልጆች የማይተወን ጌታ በእኛ ውስጥ እየኖረ ነው::

አባት ሆይ ስምህን እባርካለሁ  በእኔ ውስጥ ስላለህ እኔም በአንተ ውስጥ ነኝ::  አባቴ ሆይ የማትተወኝ ጌታ ነህና ተባረክ!  ይህ ህይወት የአንተ ነውና ክበርበት::

ዮሐንስ 14: 21-24

21፤ ትእዛዜ በእርሱ ዘንድ ያለችው የሚጠብቃትም የሚወደኝ እርሱ ነው፤ የሚወደኝንም አባቴ ይወደዋል እኔም እወደዋለሁ ራሴንም እገልጥለታለሁ።”

23፤ ኢየሱስም መለሰ፡ አለውም፦ “የሚወደኝ ቢኖር ቃሌን ይጠብቃል፤ አባቴም ይወደዋል፡ ወደ እርሱም እንመጣለን፡ በእርሱም ዘንድ መኖሪያ እናደርጋለን።

24፤ የማይወደኝ ቃሌን አይጠብቅም፤ የምትሰሙትም ቃል የላከኝ የአብ ነው እንጂ የእኔ አይደለም።

ጌታን መውደዳችን የሚታወቀው ትእዛዙ በእኛ ዘንድ ሲሆንና ቃሉንም በመጠበቅ እንደሆነ ጌታ ይናገራል::  እርሱን ስንወድ እኛ ደግሞ በአብ እንወደዳለን ይህም ብቻ አይደለም እራሱንም ይገጥልናል:: ምን ያህል ይወደናል?! በዚህ ጊዜ “ጌታ ሆይ፥ ለዓለም ሳይሆን ራስህን ለእኛ ልትገልጥ ያለህ እንዴት ነው? የሚል ጥያቄ ቀረበለት::

አሁንም መልሱ የሚወደኝ ቢኖር ቃሌን ይጠብቃል፤ አባቴም ይወደዋል፡ ወደ እርሱም እንመጣለን፡ በእርሱም ዘንድ መኖሪያ እናደርጋለን።  እራሱን የሚገልጥልን አንዱ በቃሉ ሌላው ደግሞ በመንፈሱ  ወደእኛ በመምጣት ነው:: ቅደም ተከተሉ ከእኛ የሚጠበቅብን እርሱን መውደድና ቃሉን መጠበቅ ከእርሱ  የምንቀበለው ፍቅሩንና አብሮነቱን:: በኤፌ 3:  16-19 ላይ ጳውሎስ እንደፀለየው እንፀልይ::

በተቃራኒው የማይወደኝ ቃሌን አይጠብቅም፤ የምትሰሙትም ቃል የላከኝ የአብ ነው እንጂ የእኔ አይደለም።

አባት ሆይ እወድሃለሁ በሰጠኸኝም ጸጋ ቃልህን እጠብቃለሁ::  እራስህን ስለምትገልጥልኝና በእኔም ዘንድ ልትኖር ስለምትመጣ ተመስገን::

ዮሐንስ 14: 25-26

25፤ ከእናንተ ዘንድ ስኖር ይህን ነግሬአችኋለሁ፤

26፤ አብ በስሜ የሚልከው ግን መንፈስ ቅዱስ የሆነው አጽናኝ እርሱ ሁሉን ያስተምራችኋል እኔም የነገርኋችሁን ሁሉ ያሳስባችኋል።

ጌታ ነግሬአችኋለሁ የሚለን በስሙ ስለሚላክልን ረዳት ነው::  አሁን በዓለም እየሰራ ያለው ያገልግሎቱን አደራ የተረከበው መንፈስ ቅዱስ ነው::  ያለ እርሱ አንዳች አናደርግም ብለን ስንል ለማለት ያህል አባባል ሳይሆን እውነት ነው::

ከላይም በቁ 16 ላይም እንደጠቀሰው ይህ አጽናኝ ዓለም የማያየው እየሱስ አብን ለምኖ የተላከልን ነው:: ይህ አጽናኝ በእየሱስ ስም ነው የተላከልን ስለዚህ ላክልን ማለት አያስፈልገንም መቀበል እንጂ::  ወደ  ህይወታችን መጋበዝ ብቻ ነው::  ጳውሎስም በ ሐዋ. ሥራ 19:2፤ ባመናችሁ ጊዜ መንፈስ ቅዱስን ተቀበላችሁን? አላቸው። መቀበል ነው አንድ ጊዜ በእየሱስ ተለምኖ የተሰጠን ነው::  አሜን!

መንፈስ ቅዱስ የሚያደርገው ነገር:-

አጽናኝ ነው

ሁሉን የሚያስተምረን ነው 

እየሱስ በቃሉ የነገረንን ሁሉ የሚያሳስበን 

ነው::

አብ አባት ሆይ መንፈስ ቅዱስን ስለላክልን ተመስገን::  ያለ አንተ አንዳች ማድረግ እንደማልችል አውቄያለሁና እርዳኝ:: የምታጽናና የምታስተምር ቅዱሱ መንፈስ ሆይ አስተምረኝ ቃሉንም እኖርበት ዘንድ አሳስበኝ ምራኝ እየሱስንም በህይወቴ አክብረው አንተንም በማወቅ ሙላኝ:.  አሜን!

ዮሐንስ 14: 27-31

27፤ ሰላምን እተውላችኋለሁ፥ ሰላሜን እሰጣችኋለሁ፤ እኔ የምሰጣችሁ ዓለም እንደሚሰጥ አይደለም። ልባችሁ አይታወክ አይፍራም።

ሳይሆን ገና የሚሆነውን ሁሉ እየነገረና እያጽናናቸው ነው ጌታ::  ምዕራፍ 14-17 በሰዓታት ውስጥ የተደረገ የመጨረሻው ወደ መስቀል ከመሄዱ በፊት እንደ ስንቅ የሰጣቸው ምክሩና ትምህርቱ ነው::  ብዙ ነገር የታጨቀበት ነው::  እኔ እሄዳለሁ ወደ እናንተም እመጣለሁ እንዳልኋችሁ ሰማችሁ። የምትወዱኝስ ብትሆኑ ከእኔ አብ ይበልጣልና ወደ አብ በመሄዴ ደስ ባላችሁ ነበር። በመሄዴ ደስ ሊላችሁ ነው የሚገባው አላቸው በእነሱ ቦታ ይህ ምንም ትርጉም አይሰጥም::  እየሱስ ግን የመጣው ተላልፎ ሊሰጥና እንደበግ ሊታረድልን ነው::  በዛ የኃጥያት ስርየት ተገኘ ወደ አብ ሲሄድና ሲከብር ደግሞ መንፈስ ቅዱስን ላከልን::  ለዚህም ነው በመሄዴ ደስ ይበላችሁ የሚላቸው:: ግን አልገባቸውም::

ሲጀምርም ምዕራፉ ልባችሁ አይታወክ  አላቸው ሲጨርሰውም በዚሁ ነው እየጨረሰው ያለው::  እንዴት ግን አይታወኩም ያሉበት ሁኔታ ውጥር ያለ ነው?!  መፍትሄንም ሰጥቶ ነው አትታወኩ የሚለው የሰጠንም ‘ሰላሙን’ ነው::  ሰላምን እተውላችኋለሁ፥ ሰላሜን እሰጣችኋለሁ፤ እኔ የምሰጣችሁ ዓለም እንደሚሰጥ አይደለም። ትቶልን ሄዷል ማንም ከእኛ አይወስድብንም::  ምክንያቱም እኛ ተግተን የምናገኘው ሳይሆን የመንፈስ ፍሬ ነው ይህንን ፍሬ በላያችን የሚያደርገው እራሱ መንፈስ ቅዱስ ነው::  ይህ አእምሮን የሚያልፍ ሰላም ዓለም እንደምትሰጠው አይደለም:: ልባችንን ይጠብቅ ዘንድ ከሰላሙ አለቃ ተሰቶናልና ልባችንን እንጠብቅ የህይወትም መውጫ ከዛ ነውና::  ጌታ ለልባችን መታወክ መፍትሄ ሰቶናል ሰላሙንና አብሮነቱን (በእግዚአብሔር እመኑ በእኔ እመኑ ብሎ)::  ወላጅ እንደሌላቸው አይደለንም እርሱ ከእያንዳንዳችን ጋር ነው::  የክርስትያን ድሉ ሰላሙ ነው ጠላት ሊያውክ ነው የሚመጣው ተረጋግተን እንድንኖር ጌታ ሰጥቶናል:: ሁሉ የተሰጠው ነው እንጂ ለተወሰነ ሰው ብቻ አይደለም::

እየሱስ አባቱን ከመውደዱ የተነሳ  አብን ታዘዘ :: ነገር ግን አብን እንድወድ ዓለም ሊያውቅ፥ አብም እንዳዘዘኝ፥ እንዲሁ አደርጋለሁ። ተነሡ፤ ከዚህ እንሂድ።” ብሎ እራሱን አሳልፎ ሊሰጥ ተነሳ::  ጌታ እየሱስ ምን አይነት ፍቅር ነው::

አባት ሆይ ተመስገን ሰላምህን ትተህልኝ ሄደሃል ይህ ሰላም በማልፍበት ሁሉ ይረዳኛልና ልቤ እንዳይታወክ የአንተን ሰላም በላዬ ላይ አውጃለሁ በእምነት እቀበላለሁም::  አሜን!

ዮሐንስ 14 – ክለሳ

የተሰጠን ትእዛዝ :-

   ልባችሁ አይታወክ

   ብትወዱኝ ትእዛዜን ጠብቁ።

የተሰጠን መፍትሄ ለትእዛዙ

    በእግዚአብሔር እመኑ፥ 

    በእኔም ደግሞ እመኑ።

    ሰላሜን ትቼላችኃለሁ::

የተሰጠን ተስፋ:

  ስፍራ አዘጋጅላችሁ ዘንድ እሄዳለሁና፤

   ሁለተኛ እመጣለሁ ወደ እኔም 

   እወስዳችኋለሁ።

   በእኔ የሚያምን እኔ የማደርገውን ሥራ 

   እርሱ ደግሞ ያደርጋል፤ ከዚህም 

   የሚበልጥ ያደርጋል፥

    ጸሎት የሚመለሰው አብ እንዲከብር 

    ነው:- አብም ስለ ወልድ እንዲከበር 

    በስሜ የምትለምኑትን ሁሉ 

    አደርገዋለሁ።

    ማናቸውንም ነገር በስሜ ብትለምኑ እኔ 

   አደርገዋለሁ።

   ወላጆች እንደ ሌላቸው ልጆች 

   አልተዋችሁም፤ ወደ እናንተ እመጣለሁ።

   እኔ ሕያው ነኝና እናንተ ደግሞ ሕያዋን 

   ትሆናላችሁ።

     እኔ በአባቴ እንዳለሁ እናንተም በእኔ 

     እንዳላችሁ እኔም በእናንተ እንዳለሁ 

     በዚያን ቀን ታውቃላችሁ።

ትዛዙን/ቃሉን ለሚጠብቅ የተሰጠ ተስፋ

የሚወደኝ እርሱ ነው፤ የሚወደኝንም አባቴ ይወደዋል እኔም እወደዋለሁ ራሴንም እገልጥለታለሁ።

አባቴም ይወደዋል፡ ወደ እርሱም እንመጣለን፡ በእርሱም ዘንድ መኖሪያ እናደርጋለን።

የተቀበልነው ተስፋ:-

እኔም አብን እለምናለሁ ለዘላለምም ከእናንተ ጋር እንዲኖር ሌላ አጽናኝ* ይሰጣችኋል፤ 

አብ በስሜ የሚልከው ግን መንፈስ ቅዱስ የሆነው አጽናኝ እርሱ ሁሉን ያስተምራችኋል እኔም የነገርኋችሁን ሁሉ ያሳስባችኋል።

ሰላምን እተውላችኋለሁ፥ ሰላሜን እሰጣችኋለሁ፤ እኔ የምሰጣችሁ ዓለም እንደሚሰጥ አይደለም።

የተሰጠን ድል:-

የዚህ ዓለም ገዥ ይመጣልና፤ በእኔ ላይም አንዳች የለውም::  በእየሱስ ላይ አንዳች እንደሌለው ሁሉ በእኛላይም የለውም እኛ የእየሱስ ነን::  ይህችን ክፉ ዓለም ክደናል::

ከእየሱስ የምንማረው:-

አብም እንዳዘዘኝ፥ እንዲሁ አደርጋለሁ።

አባት ሆይ ይህ ሁሉ ተስፋ አለኝ!  ምን እላለሁ ክበርተመስገን! 

ተመስገን ስለሰጠኸን ተስፋ: መንፈስህንም እንዳንረታ ስለሰጠኸን ተወደስ:: ለዘላለም ከእኔ ጋር  ስለሆንክ  ህያው ስላደረከኝ ተመስገን::

ዮሐንስ 15: 1-2

1፤ “እውነተኛ የወይን ግንድ እኔ ነኝ፤ ገበሬውም አባቴ ነው።

ዮሐንስ 15:2፤ ፍሬ የማያፈራውን በእኔ ያለውን ቅርንጫፍ ሁሉ ያስወግደዋል፤ ፍሬ የሚያፈራውንም ሁሉ አብዝቶ እንዲያፈራ ያጠራዋል።

የወይን ግንድ እኔ ነኝ ብቻ አይደለም ያለው ነገር ግን እውነተኛ ብሎ ጨምሮበታል::  ውሸተኞች አሉ ማለት ነው ልክ እንደወይኑ ግንድ ሰው ተጣብቆባቸው መኖር የሚያስችሉ የሚመስሉ ለምሳሌ:- ሃብት: ዝና: ዘርና የመሳሰሉት::  እነዚህ ግን የተወሰነ መንገድ ድረስ ነው የሚሄዱት አያዋጡም ይሰበራሉ::  የእኛ ጌታ ግን ሁልጊዜ ከእኛ ጋር ነው:: 

ይህ እውነተኛ የወይን ግንድ መደገፍያ መኖርያም ነው::  ግንዱ የሚያስፈልገውን ሁሉ ካላቀረበ ቅርንጫፉ ይሞታል ቅርንጫፉ በራሱ  የሚያደርገው ነገር የለም ተማምኖ መኖር ብቻ ነው::  ደርሶ ያደረግን ቢመስለን እንኳን ውሸት ነው ሁሉ የሆነው በጸጋው ነውና:: የሚገርመው ወይን ከግንዱ ብቻ ሳይሆን ከሌላውም ቅርንጫፍ ጋር ይጠላለፍና ይደጋገፋል አንዱ በአንዱ ይበረታል ቅርንጫፉ እንደዚህ ሲሰናሰን የመውደቁ አጋጣሚ እምንት እየሆነ ይመጣል:: በዚህ ውስጥ የምናየው አጠገባችን ያሉት ቅዱሳን ለመቆምና ለመበርታት እንደሚያስፈልጉን ነው:: ንፋሱም ምኑም ገፍቶ አደጋ ላይ እንዳይጥለን እርስ በእርስ እንጠባበቃለን:: ስለዚህ በወገኖች ውስጥ ያለ ጸጋ ያስፈልገኛል እኔም አስፈልጋቸዋለሁኝ ማለት ነው::  ለብቻዬ እኖራለሁ የሚባል ክርስትና የለም ጸጋ ሁሉ የተለያየ ነውና በአንዱ ላይ ሁሉ ጸጋ የለምና ይህንን አውቀን ህብረት ከቅዱሳን ጋር እናድርግ::

ሌላው ህብረታችን ከወይኑ ግንድ ከእየሱስ ጋር ገበሬውም እየተከታተለ የሚንከባከበን ከአብ እንዲሁም ከእኛ ጋር ከሚኖር መንፈስ ቅዱስ ጋር ነው::   በ1 ዮሐንስ 1:3፤ እናንተ ደግሞ ከእኛ ጋር ኅብረት እንዲኖራችሁ ያየነውንና የሰማነውን ለእናንተ ደግሞ እናወራላችኋለን። ኅብረታችንም ከአባት ጋር ከልጁም ከኢየሱስ ክርስቶስ ጋር ነው። 

ይህ ገበሬ የሚያደርገው መጉዳት ሳይሆን አብዝተን እንድናፈራ ማድረግ ነው::  የትኛው አባት ሰብሮ ያስተምራል እርሱ የሚራራ አባት ነውና መጎዳታችንን አይፈልግም:: እንዴት ይገርዘናል ?  በቃሉና በመንፈሱ ነው የሚያደርገው::  በአእምሯችን መታደስ ተለውጠን እንድንመላለስ ነው የሚፈልገው ስለዚህ ቃሉ ህይወት እንደሆነና መንፈስም እንደሆነ ተነግሮናል ይህ ቃል ይሰራናል ይለውጠናል መንፈሱም ይህንኑ ስራ ቃሉን በማስታወስና በማስተማር በማጽናናት የመንፈስ ፍሬ ሁሉ አፍርተን ለበጎ ስራ የበቃንና ፍሬ እንዲበዛልን ያደርጋል::  ስለዚህ በወይን ግንዱ ላይ እንጣበቅ ሾርት ከት የለም ማደግ ጊዜ ይወስዳልና ጊዜ እንስጠው በፊቱ እንገኝ::

አባት ሆይ ተመስገን እንደዚህ አድርገህ ስለተንከባከብከኝ ተመስገን::  አንተን እታመናለሁ በዙርያዬም ስለሰጠኸኝ ቅዱሳን ተባረክ::  አሜን!

ዮሐንስ 15: 3-4

4፤ በእኔ ኑሩ እኔም በእናንተ። ቅርንጫፍ በወይኑ ግንድ ባይኖር ከራሱ ፍሬ ሊያፈራ እንዳይቻለው፥ እንዲሁ እናንተ ደግሞ በእኔ ባትኖሩ አትችሉም።

እዚህ ስፍራ ላይ እናንተ ስለ ነገርኋችሁ ቃል አሁን ንጹሐን ናችሁ ብሎ ሲል ማንም በክርስቶስ ላይ የሚበቅልና የሚጣበቅ ከኃጥያቱ የታጠበ ወደ እረፍቱ የገባ ነው ይህ እውነት ህይወታችንን ሲገዛው ንጹሃን ነን በስብከት ሞኝነት አምነን ህይወታችንንም የሰጠነው በቃሉ አይደል?

በእኔ ኑሩ እኔም በእናንተ የሚለው በጣም ጥልቀት ያለው የክርስትና ህይወት ነው::  ይህ ማለት ጸሎት ማለት አይደለም ይህ ማለት መዘመር አይደለም ወይም የክርስትና ትእዛዛትንም መፈጸም አይደለም::  በእኔ ኑሩ ማለት ባለማቋረጥ በቀጣይነት ልክ እንደምንተነፍሰው አየር መለያየት እንደማንችለው አየሩ ለደቂቃ ከሌለ እንደማንኖር በእርሱ መኖር ይህ ነው ወይም የህይወት ዘይቤ ነው:: በዕብራ 4:11፤ እንግዲህ እንደዚያ እንደ አለመታዘዝ ምሳሌ ማንም እንዳይወድቅ ወደዚያ ዕረፍት ለመግባት እንትጋ። እንደሚል መትጋት ያለብን በዚህ እረፍት ላይ ለመሆን ነው::  

ፍሬ በህይወታችን አይተን ልባችን እብጥ ብ ት ል   ከግንዱ እንዳገኘነው እንወቅ ጌታን እናክብር እንጂ ቅርንጫፍ ከመቼ ወዲህ ነው  በራሱ ፍሬ የሚያፈራው?!  እርሱ በእኛ እኛም በእርሱ ስንኖር ፍሬ የማይቀር ሃቅ ነው እናፈራለን ወይም እርሱ በእኛ ውስጥ ያፈራል::  ፍሬውም  ለእኛ ይቆጠር እንጂ የእሱ ነው::  ጠላትም ይህንን ስለሚያውቅ የሚያንቀን ብራቮ ይህንን የመሰለ ምሳሌ የሆነ ህይወት ብሎ ይሞላናል ሰልፉ ስውር ነው እውነትም ስንል ነው ጉዱ መልሳችን መሆን ያለበት እኔም ይገርመኛል በእኔ ሆኖ ክርስቶስ ያፈራው ፍሬ ብለን ብንመልስ ጭራውን ቆልፎ ይሮጣል::  እንንቃ!! ውጊያው እውነት ነው እየሱስንም ፈትኗል ሲያቅተውን ጭራሹን ትቶት ሄደ አይልም ለጊዜው ተለየ እንጂ::  እኛንም እንደዚሁ ነው የሚዋጋን ከእየሱስ ውስጥ አውጥቶ በራሳችን ሊያቆመንና ስንደርቅ ሊያይ:: ጎበዝ አይናችንን በመንገዳችን ላይ ህይወታችንን በግንዱ ላይ እናድርግ::

ቅርንጫፍ በወይኑ ግንድ ባይኖር ከራሱ ፍሬ ሊያፈራ እንዳይቻለው፥ እንዲሁ እናንተ ደግሞ በእኔ ባትኖሩ አትችሉም። አለቀ ምንም ማብራሪያ አያስፈልገውም!  በእርሱ ካልሆንን አናፈራም!

አባት ሆይ እዳዬን ከፍለህ ማዳንህ ሳያንስ አንተን እመስል ዘንድ በአንተ ላይ አብቅለኸኝ በእኔ ውስጥ ፍሬን እያፈራህ አለህ:: ከኔ የሆነ ምናለ ጌታ ሁሉ ባንተ ነውና ምስጋናዬ መገዛቴ ይኸው::  በሰንበት እረፍት ውስጥ እርፍ እላለሁ የቀረ የምሰራው የለም!  ተፈጸመ ላልከው ለበጉ ክብር ይሁን!!!  አሜን!

ዮሐንስ 15: 5-8

7፤ በእኔ ብትኖሩ ቃሎቼም በእናንተ ቢኖሩ የምትወዱትን ሁሉ ለምኑ ይሆንላችሁማል።

8፤ ብዙ ፍሬ ብታፈሩና ደቀ መዛሙርቴ ብትሆኑ በዚህ አባቴ ይከበራል።

አሁንም ደግሞ እኔ የወይን ግንድ ነኝ እናንተም ቅርንጫፎች ናችሁ። ያለ እኔ ምንም ልታደርጉ አትችሉምና በእኔ የሚኖር እኔም በእርሱ፥ እርሱ ብዙ ፍሬ ያፈራል እያለ እየደገመ ነገራቸው::  ፍሬ የሚያፈራው እርሱ መሆኑን እንድናውቅ ነው መልክቱ የአድርግና አታድርግ ዘመን አልፎ ሞተናል እርሱ ህያው ሆኖ በእኛ ይኖራል::  ህይወት እንዲበዛልንና እንዲትረፈረፍልን ነው ጌታ የመጣው::

ሌላው ነገር ያስተማረው በእኔ የማይኖር ቢሆን እንደ ቅርንጫፍ ወደ ውጭ ይጣላል ይደርቅማል፤ እነርሱንም ሰብስበው ወደ እሳት ይጥሉአቸዋል፥ ያቃጥሉአቸውማል። ሰው በክርስቶስ ብቻ ነው በህይወት መኖርየሚችለው ምንም ፍሬ የለም በዓለም ምንም እንኳንየሚደንቅ ህይወት የሚኖሩ ቢኖሩም ጌታ ሲያየው ተስፋ ቢስ የደረቀ ቅርንጫፍ እንጂ ፍሬ አያገኝበትም::  የፈለገውን ነገር ያድርግ የፈለገውን ያህል ኃብትና ዝና ትምህርትና እውቅና  ይኑረው ክርስቶስ ከሌለው ሙት ነው እኛ አናሻሽለውም::  እንዲያውም አትኩሮታችንን በመዳኑ ላይ እናድርግ::  ጌታ ይርዳን በምናየው ነገር ተታለን ያልዳነውን ድኗል ብለን የተሰጠንን አጋጣሚ እንዳናባክን::

የምንለምነው ሁሉ የሚሆንልን መቼ ነው? ጌታ እንዳለን:–   

1.  በእኔ ብትኖሩ 

2.  ቃሎቼም በእናንተ ቢኖሩ 

ከዛስ ምን ይሆናል እነዚህ ሲሟሉ? 

የምትወዱትን ሁሉ ለምኑ ይሆንላችሁማል ተባልን::  በእርሱ ስንኖር የምናስበውና የምንለምነው እንደፈቃዱ ይሆናል::  ቃሉ በውስጣችን ሲሞላ ቃሉን ነው የምንፀልየው::  ይህንን እንደባዶ ቼክ የፈለግነውን የምንፅፍበት አድርገው ሰዎች ይወስዳሉ ነገር ግን ከላይ ያለው ሲሟላ ነው የጠየቅነው ሁሉ የሚሰጠን አለዚያ ፀሎታችን  በሉቃስ 9:54፤ ደቀ መዛሙርቱም ያዕቆብና ዮሐንስ አይተው፦ “ጌታ ሆይ፥ ኤልያስ ደግሞ እንዳደረገ እሳት ከሰማይ ወርዶ ያጥፋቸው እንል ዘንድ ትወዳለህን?” የሚል ይሆናል::  ይህንን ፀሎት አይሰማም እንደዚህ የምንፀልይ አንሆንም በእርሱ ስንኖርና ቃሉ ሲሞላን::  እኛ በፍቅር የምንመላለስ ነው የምንሆነው::  ፀሎታችንን መቃኘት ይሁንልን::  እንደቃሉ እንፀልይ::

ፍሬ እንድናፈራ ለምን ተፈለገ? ድነናል አይበቃም?

ልጅ ወልደን ባያድግና ያው የሚታቀፍ ህፃን ቢሆን በሰውነቱም በቁመቱም ባያድግ ምን አለበት እንደማለት ነው:: ደግሞም ከተፈጥሮ ውጪ ነው::  ስለዚህም ፍሬ እያፈራን እየሱስን እየመሰልን እንድንመጣ አንድ ጊዜ ተወስኗል ይህም ብቻ ሳይሆን ብዙ ፍሬ ብታፈሩና ደቀ መዛሙርቴ ብትሆኑ በዚህ አባቴ ይከበራል። አሜን! በፍሬያችን አብ ስለሚከብር ነው::

አባት ሆይ ተመስገን በፍሬዬ አንተትከብራለህና::  በአንተ ውስጥ ነኝና ተመስገን::  አሜን!

ዮሐንስ 15: 9፤ አብ እንደ ወደደኝ እኔ ደግሞ ወደድኋችሁ፤ በፍቅሬ ኑሩ።

አብ ለልጁ ያለውን ፍቅር በአደባባይ ተናገረ “በእርሱ ደስ የሚለኝ የምወደው ልጄ ይህ ነው፤ እርሱን ስሙት፡” በማለት::  እየሱስም ለእኛ ያለውን ፍቅር የገለጠው ከአባቱ ፍቅር ጋር በማወዳደር ነው::  እንዴት ያለ ህብረት ውስጥ ነው የገባነው? ይህ እንደምን ያለ ነገር ነው?! እግዚአብሔር ፍቅር ነው በእርሱ መኖር በፍቅሩ ውስጥ መኖር ነው::  ፍቅር ማለት ማንነቱ ነው::  ይህ ፍቅር መጠን የለውም በቃሉ እንደሚል ከቅዱሳን ሁሉ ጋር ስፋቱና ርዝመቱ ከፍታውም ጥልቅነቱም ምን ያህል መሆኑን ለማስተዋል፥ ከመታወቅም የሚያልፈውን የክርስቶስን ፍቅር ለማወቅ ትበረቱ ዘንድ፥ እስከ እግዚአብሔርም ፍጹም ሙላት ደርሳችሁ ትሞሉ ዘንድ።

ከዚህ ፍቅር ውስጥ ምን ያወጣናል? ምንም!!!!  በሮሜ 8:35፤ ከክርስቶስ ፍቅር ማን ይለየናል? መከራ፥ ወይስ ጭንቀት፥ ወይስ ስደት፥ ወይስ ራብ፥ ወይስ ራቁትነት፥ ወይስ ፍርሃት፥ ወይስ ሰይፍ ነውን? . . .  በክርስቶስ ኢየሱስ በጌታችን ካለ ከእግዚአብሔር ፍቅር ሊለየን እንዳይችል ተረድቼአለሁ። ፍቅሩ ይህንን ሁሉ እንድናልፍ ያደርገናል:: ጠላት ግን በስጋት እንድንኖር ይፈልጋል አረ አንሰጋም ጌታ አስተማማኝ ነው::  ስሙ ይባረክ!!!

ጌታ ብዙ ባህሪያት ቢኖረውም የጋበዘን ግን በፍቅሩ እንድንኖር ነው በኃይሌ ኑሩ ወይም በጥበቤ ወይም በቅድስናዬ ወይም በሌላ  አላለንም – ያለን በፍቅሬ ኑሩ ስርና መሰረታችሁ በፍቅር የጸና ይሁን ነው::

አባት ሆይ ስለወደድከኝ አመሰግንሃለሁ!!  በፍቅርህም እንድኖር ስለምትፈልግ ተመስገን::  ይህንን ፍቅር እንዳውቅ ዕለት ዕለት እርዳኝ:: ከአእምሮ በላይ በሆነ ፍቅር ስለወደድከኝ አመሰግንሃለሁ! ሃሌሉያ

ዮሐንስ 15: 10-13

10፤ እኔ የአባቴን ትእዛዝ እንደ ጠበቅሁ በፍቅሩም እንደምኖር፥ ትእዛዜን ብትጠብቁ በፍቅሬ ትኖራላችሁ።

11፤ ደስታዬም በእናንተ እንዲሆን ደስታችሁም እንዲፈጸም ይህን ነግሬአችኋለሁ።

ጌታ እየሱስ የአባቱን ፈቃድ ፈጽሞ ታዘዘ እናም ምሳሌን ተወልን::  በእርሱ ደስ የሚለኝ ብሎ መስክሮለታል::  በ1 ዮሐንስ 2:5፤ ቃሉን ግን የሚጠብቅ ሁሉ በእርሱ የእግዚአብሔር ፍቅር በእውነት ተፈጽሞአል። በእርሱ እንዳለን በዚህ እናውቃለን ይላል:: 

በመታዘዙ ውስጥ በፍቅር መኖር አለ እንዲሁም  ስንታዘዝ አብረን መኖር እንችላለን:: ትእዛዙን ስንጠብቅ በፍቅሩ እንኖራለን::  ትእዛዙንም የምንጠብቀው በጸጋው ነው::

ደስታዬ በእናንተ እንዲሆን አለን:: ደስታው ምንድነው?  ትእዛዙን እንድንፈጽም: በእርሱ እንድንኖር እንዲሁም እርሱ እንደወደደን እንድንዋደድ ነው::

እየሱስ ፍቅሩን የገለጠበት መንገድ እራሱን በሞት አሳልፎ በመስጠት ነው::  እርሱም እንዳለን ነፍሱን ስለ ወዳጆቹ ከመስጠት ይልቅ ከዚህ የሚበልጥ ፍቅር ለማንም የለውም። እውነት ነው!!  ማንም ነፍሱን እስከሚሰጥ ወዶኝ አያውቅም ከእየሱስ በቀር!!

አባት ሆይ እራስህን እስክትሰጥ ስለወደድከኝ አመሰግንሃለሁ::  እኔም እራሴን እሰጥሃለሁ  አንተ በእኔ ኑር በወይኑ ግንድ ላይ መጣበቅ ይሁንልኝ!

ዮሐንስ 15: 14-15

14፤ እኔ ያዘዝኋችሁን ሁሉ ብታደርጉ እናንተ ወዳጆቼ ናችሁ።

15፤ ከእንግዲህ ወዲህ ባሮች አልላችሁም፤ ባርያ ጌታው የሚያደርገውን አያውቅምና፤ ወዳጆች ግን ብያችኋለሁ፥ ከአባቴ የሰማሁትን ሁሉ ለእናንተ አስታውቄአችኋለሁና።

ወዳጅነት እንዲቀጥል ሰው መስማማትና በአንድ ጎዳና ላይ መሆንንም ይጠይቃል አለበለዚያ ወዳጅ ብዬ ለማለት አልችልም:: እንደዚሁም እየሱስ ወዳጆቼ ናችሁ ሲለን ቅድሚያ ሁኔታን አስቀምጦ ነው::  እርሱም እኔ ያዘዝኋችሁን ሁሉ ብታደርጉ  ያኔ ወዳጅ ነን አብረን መጏዝ እንችላለን ነው ያለን::  ያዘዝኳችሁን ብታደርጉ ሲል መታዘዝን አስተምሮን ነው የሄደው እርሱ አባቱን እስከ መጨረሻ ድረስ ፈቃድህ ይሁን ብሎ እስከመስቀል ሞት ድረስ ታዘዘ::  እኛ ግን የተጠየቅነው ጸጋውንና አብሮነቱንም ሰቶን ነውና ለመታዘዝ እራሳችንን ወደ እርሱ እናቅርብና ወዳጅ መሆናችንን እናስመስክር::

ከእንግዲህ ወዲህ ባሮች አልላችሁም ያለን ምክንያቱ ከአባቱ የሰማውን ሁሉ ስላሳወቀን ነው። ወዳጅ ያስባለን ሚስጥር የሚሆነውን ሁሉ ስለነገረና ስላሳወቀን ነው::  እንደዚሁም ደግሞ የእግዚአብሔር ሚስጥር የሆነውን እየሱስንና መንግስቱን እንድናውቅ የሰማይ አባት ስለገለጠልን ወዳጅ ተባልን::  ወዳጅ ብሎ እንዴት ያለ ክብርን ሰጠን::  የሰው ልጅ እኮ እራሱን ለሰይጣን ባርያ አድርጎ የጣለ ነበረ::  ዛሬ በክርስቶስ ቤዛነት መዋጀት ብቻ ሳይሆን ጠጋ አድርጎ ወዳጅ አለን::  ይህ ምን አይነት ፍቅር ነው?! እጁን ዘርግቶ ተቀበለን::  እንግዲህ እንደወዳጅ እንመላለስ::

አባት ሆይ የፍቅርህ ጥልቀት በቃልህ ውስጥ ሳየው ይገርማል ተመስገን::  ወዳጅ ብለህ ስላቀረብከኝ አመሰግንሃለሁ::  ትእዛዝህንም የምጠብቅበትና የምታዘዝበት ብቃት ሁሉ  በጸጋህ ውስጥ ስለተሰጠኝ ተመስገን:: ባርነት የለም ወዳጅ ነኝና! ክበር ተመስገን!!

አሜን

ዮሐንስ 15: 16-17

16፤ እኔ መረጥኋችሁ እንጂ እናንተ አልመረጣችሁኝም፤ አብም በስሜ የምትለምኑትን ሁሉ እንዲሰጣችሁ፥ ልትሄዱና ፍሬ ልታፈሩ ፍሬአችሁም ሊኖር ሾምኋችሁ።

17፤ እርስ በርሳችሁ እንድትዋደዱ ይህን አዛችኋለሁ።”

ወዳጅ ብያችኃለሁ እያላቸው ቆይቶ ይህንን ጨመረበት እኔ መረጥኋችሁ እንጂ እናንተ አልመረጣችሁኝም::  እኛም አልመረጥነውም ነገር ግን በእርሱ ታስበን ዛሬ በቤቱ እየለመለምን አለን::  ከእኛ የሆነ የምንመካበት አንዳችም የለም ክብር ለንጉሱ ይሁን::  የተመረጥነውም ደግሞ ፍሬ ልናፈራ ነው ፍሬያችንም እንዲኖር እንጂ ጊዜያዊ እንዲሆን አይደለም::

አብም በስሜ የምትለምኑትን ሁሉ እንዲሰጣችሁ፥  እየሱስ በዝች ለሊት ከነሱ ይለያልና ከዚህ በኃላ በስሙ እንዲለምኑ ነው የሚነግራቸው::  በጸሎት ነው የምትለምኑትን ከዚህ በኃላ የምትቀበሉት እንጂ  በአካል አብሯቸው እንዳልሆነ እንዲያውቁ ነው:: 

ልትሄዱና ፍሬ ልታፈሩ ፍሬአችሁም ሊኖር ሾምኋችሁ::  ሾምኳችሁ ሲባል መቼም እንደምናውቀው ባለስልጣን መሆ ን ማለት ነው::  ስለዚህ ፍሬ በማፍራት ላይ ተሹሙናል  ማን ይሽረናል ታድያ?  ፍሬ ማፍራት ግድ ነው ምክንያቱም የተሾምንበት ነውና::  የመንፈስ ፍሬ ግን ፍቅር፥ ደስታ፥ ሰላም፥ ትዕግሥት፥ ቸርነት፥ በጎነት፥ እምነት፣ የውሃት፥ ራስን መግዛት  እነዚህን እናፈራለን:;  ማፍራታችንን ብቻ ሳይሆን የሚፈልገው ፍሬያችንም አብሮን እንዲኖር ነው የሚፈለገው::

በተጨማሪም ደግሞ የሚያዘን እርስ በርሳችን እንድትዋደድ ነው። መቼም ሐዋርያቱ የመዋደድን ትእዛዝ ስንት ግዜ በጥቂት ደቂቃዎች ውስጥ እየደጋገመ ነገራቸው? ሊሄድ ነውና እንደለመዱት እኔ እበልጥ እኔ እበልጥ የሚለውን ልጅነት ትተው የነሱንም የሌላውንም አይን በአንድነት ወደ እየሱስ እንዲያደርጉ ነው:: መዋደድ ትእዛዝ ነው ደቀ መዝሙርም መሆናችን የሚታወቀው በዚህ ነውና::

አባት ሆይ ተመስገን ፍሬ ላፈራ ተሹሜአለሁና::  ይህ ፍሬ በእኔ ውስጥ ይንዠረገጋልና ወደ ህይወቴ መተህ ቅጠል ብቻ ሆኜ አልገኝምና ክበር::  አሁንም እራሴን የጽድቅ የጦር እቃ አድርጌ አቀርባለሁኝ::  አሜን

ዮሐንስ 15: 18-27

18፤ “ዓለም ቢጠላችሁ ከእናንተ በፊት እኔን እንደ ጠላኝ እወቁ።

23፤ እኔን የሚጠላ አባቴን ደግሞ ይጠላል።

26፤ ዳሩ ግን እኔ ከአብ ዘንድ የምልክላችሁ አጽናኝ እርሱም ከአብ የሚወጣ የእውነት መንፈስ በመጣ ጊዜ፥ እርሱ ስለ እኔ ይመሰክራል፤ 

ዓለም ለምን እየሱስን ጠላ ብለን ብንል በጽድቅ እየተመላለሰ ስለኮነናቸው ነው::  ክእርሱ በኃላ እኛን የጠላን ምክንያትም ያው ጌታ በእኛ ውስጥ መጥቶ መኖር ስለጀመረ ነው:: እየሱስን የሚጠላ ሁሉ  አብንም ይጠላል የሚጠሉን ሰዎች ግን ምክንያታቸው ለእግዚአብሔር ቀንተን ነው የሚሉት:: በ2 ጢሞቴዎስ 3:12፤ በእውነትም በክርስቶስ ኢየሱስ እግዚአብሔርን እየመሰሉ ሊኖሩ የሚወዱ ሁሉ ይሰደዳሉ። ቃሉ በብዙ አስረግጦ የሚነግረን መገፋት እንዳለ ነው እርሱን ከመሰልን:: ስለዚህ እንበርታ!

በዚህ መገፋት ውስጥ ግን የሚመሰክረው ማነው? እየሱስ እንዳለን:- ዳሩ ግን እኔ ከአብ ዘንድ የምልክላችሁ አጽናኝ እርሱም ከአብ የሚወጣ የእውነት መንፈስ በመጣ ጊዜ፥ እርሱ ስለ እኔ ይመሰክራል::  ብሎናል::  አሜን ይመስክርለት::  የምንገፋውና የምንጠላው ምንም ስላደረግን ሳይሆን ጌታን ወደ ህይወታችን ስለጋበዝን ነውና ምንም አይምሰለን:: በተጨማሪም ከመንፈስ ቅዱስ ጋር እናንተም ደግሞ ከመጀመሪያ ከእኔ ጋር ኖራችኋልና ትመሰክራላችሁ አላቸው::  እኛም ከመዳናችን ጀምሮ ከእኛ ጋር ለነበረው ጌታ ከመንፈስ ቅዱስ ጋር እየተባበርን እንመሰክርለታለን::

አባት ሆይ እርሱ ስለ እኔ ይመሰክራል ብለሃልና መንፈስ ቅዱስእነሆኝ ህይወቴ ስለእየሱስ መስክር እኔም ደስ እያለኝእተባበራለሁ!  እንዳልክ እንደፈቃድህ ይሁን! አሜን!

ዮሐንስ 16:1-7

1፤ “እንዳትሰናከሉ ይህን ተናግሬአችኋለሁ።

7፤ እኔ ግን እውነት እነግራችኋለሁ፤ እኔ እንድሄድ ይሻላችኋል። እኔ ባልሄድ አጽናኙ ወደ እናንተ አይመጣምና፤ እኔ ብሄድ ግን እርሱን እልክላችኋለሁ።

ይህንን ሁሉ ቀድሞ የሚነግራቸው ሲሆን እንዳይደናገጡ ነው::  ነገር ግን ጊዜው ሲደርስ እኔ እንደ ነገርኋችሁ ታስቡ ዘንድ ይህን ተናግሬአችኋለሁ። ከእንናንተም ጋር ስለ ነበርሁ በመጀመሪያ ይህን አልነገርኋችሁም። ከእነርሱ ጋር እያለ የአይሁድ ክስና ማሳደድ ሁሉ በእርሱ ላይ ነበረ የሚሳደደውም እርሱ ነበረ አሁን ግን እርሱ ሲሄድ ያ ሁሉ ቁጣ ወደ እነርሱ እንደሚዞር ስለሚያውቅ ነው::   ዓለም ጌታችንን ትጠላለች ምክንያቱም መንግስቱ ከዚህ አይደለምና የዚህ ዓለም ገዢ ዲያቢሎስ ነው አንዳችም በእኔ ላይ የለውም አለን ጌታ::  እርሱ ነው ይህንን ሁሉ ማዕበል የሚያስነሳው የሚውጠውን ፈልጎ ይዞረን የለም እድል እስኪያገኝ?!  ነገር ግን ጌታ የሰጠው መፍትሄ ምንድነው? ከምዕራፍ 14 ጀምሮ እያስተዋወቃቸው ያለው የምሽቱን ሸክም ሁሉ የሚወስድ አጽናኝ አለ እርሱም መንፈስ ቅዱስ ነው::  

ሌላ ጥያቄ መጠየቅ እስከማይችሉ በኃዘን ውስጥ ናቸው:: እየሱስ የሚለው የመለየቱና የመሄዱ ነገር ገብቷቸዋል ::  እነሱ ያዘኑት እንዳይለያቸው እሱ ደግሞ የሚላቸው እኔ እንድሄድ ይሻላችኋል ነው:: እርሱ የሚሻል ነው ብሎ ነው የሚለው::  ለነርሱ የተመቻቸው ከእየሱስ ጋር መኖር እርሱ ግን እኔ ባልሄድ አጽናኙ ወደ እናንተ አይመጣምና፤ እኔ ብሄድ ግን እርሱን እልክላችኋለሁ። ወደ እኛ የተላከው ይህ መንፈስ ቅዱስ የሚረዳን ነው በበአድ ምድር በእንግድነት ስንኖር እየሱስን እያከበረ እኛን እያጽናና ያራምደናል::  የዓለም ነገር እየከፋ ነው የሚሄደው አናሻሽለውም ፃድቁም ፅድቁን ኃጥያተኛውም ኃጥያትን ማድረጉን ይቀጥላል::  እኛ ግን መብራታችን በርቶ እንመላለስ የዓለምን ማሳደድ ፈርተን እየሱስን አንሸሽገው::

አባት ሆይ ለዘላለም ከእኔ ጋር እንዲኖር ወደ ህይወቴ የላከው መንፈስ ቅዱስ በሁሉ የሚረዳኝ ነውና ተመስገን::  

ወደ እውነት የምትመራኝ 

ስደክም የምታበረታኝ 

ሳዝን የምታጽናናኝ 

ስሳደን በደስታ የምትሞላኝ

ኃዘንን ከእኔ የምትገፍ

አእምሮን የሚያልፍ ሰላም የምትሞላኝ

እየሱስን በእኔ ውስጥ የምትገልጠው 

ስንቱን ልጥቀስ አባ?!

ጌታ መንፈስ ቅዱስ ተባረክ! 

አንተ እግዚአብሔር ነህ! 

አሁንም እኔነቴ ያንተ ነውና ክበር::  

አሜን!

ዮሐንስ 16: 8-11

8፤ እርሱም መጥቶ ስለ ኃጢአት ስለ ጽድቅም ስለ ፍርድም ዓለምን ይወቅሳል፤

9-10፤ ስለ ኃጢአት፥ በእኔ ስለማያምኑ ነው፤ ስለ ጽድቅም፥ ወደ አብ ስለምሄድ ከዚህም በኋላ ስለማታዩኝ ነው፤

11፤ ስለ ፍርድም፥ የዚህ ዓለም ገዥ ስለ ተፈረደበት ነው።

እየሱስ ፍንትው አድርጎ የመንፈስ ቅዱስን ስራ እየነገረን ነው:: መንፈስ ቅዱስ በብዙ መልክ ተገልጧል በመጽሃፍ ቅዱስ ነገር ግን እነዛን ምሳሌዎቹን ነው ማለት ግን አይደለም:: ንፋስ ወይም እርግብ ወይም ዘይት ወይም ደግሞ እሳት አይደለም::  በእርግጥ በነዚህ መልኩ ተገልጧል እርሱ ግን የፈጠረን እግዚአብሔር አምላካችን ነው:: ሃሌሉያ!!!

እርሱ መጥቶ ነው ስራውን የሚሰራው::  ግን የት ነው የሚመጣው? በእኛ በዳነው ውስጥ ይመጣና ይገለገላል:: ስራውም:-

1.  ስለ ኃጢአት፥ በእኔ ስለማያምኑ ይወቅሳል::  ይህ የእርሱ ስራ እንጂ የእኛ አይደለም::  እኛ የተባልነው ምስክሮቼ ሁኑ  ነው::  ስለኃጥያት መውቀስ  የእርሱ ስራ ነውና ያለስራችን ያልተባልነውን እንዳናደርግ::  በፍቅር እውነትን መግለጥ እንጂ የሰውን ልብ እያሻከሩ ከጌታ ማራቅ አይደለም ስራችን::  የሚያደርገውም በእየሱስ ሰው እንዲያምን ሌላ መውጫ እንደሌለ ማሳየት ነው::  እርሱ ልብን ካልነካ ምን ብንጥር ለውጥ የለም:: መውቀስን ለእርሱ እንተው እኛ ግን እየሱስ አዳነኝ ብለን እንደዛች ሳምራዊት ሴት ወደ እርሱ እናምጣ::

2. ስለ ጽድቅም፥ ወደ አብ ስለምሄድ ከዚህም በኋላ ስለማታዩኝ ነው::  እየሱስ ክርስቶስ በምድር ተመላልሶ የአባቱን ፈቃድ አድርጎ በእርሱ ደስ የሚለኝ የምወደው ልጄ ተብሎ ተመስክሮለት ፥  በመስቀል ስለ እኛ እንጂ ስለራሱ ምንም መስወአት ማቅረብ ሳያስፈልገው ህይወቱን ሰጥቶ ፥  በሶተኛው ቀን በትንሳኤው ኃይል ተነስቶ ፥  በአብ ቀኝ የተቀመጠ ጻድቅ ጌታ ነው::  ጻድቅና እንከን የሌለው እጹብ ድንቅ መሆኑን አስመስክሯል::  ማንም በአንዳች አይከሰውም ኃጥያት አልተገኘበትም ጻድቅ  ጌታ ነው:: አንድ ጊዝ ስለእኛ ደሙን እያንጠባጠበ ወደ አብ ገባ!!!  ደግሞ መቶ ይህንን ማድረግ አላስፈለገውም! ስለዚህም ደግመን በምድር ሲመላለስ ስጋ ለብሶ አናየውም አንድ ጊዜ ተ ፈ ጸ መ!!!! ብሎ ጨረሰው!!!  ለስሙ ክብር ይሁን!!!!

3.  ስለ ፍርድም፥ የዚህ ዓለም ገዥ ስለ ተፈረደበት ነው::  የዚህ ዓለም ገዢ አንዳች የለውም በእኔ ላይአለን:: እየሱስ መጥቶ አዳም ያስረከበውን ሁሉ ከሰይጣን ላይ ተረከበ::  በሰማይና በምድር ሙሉ ስልጣን ተሰጠኝ አለ::  ለአለቅነትና ለሥልጣንም ሁሉ ራስ በሆነ በእርሱ ሆናችሁ ተሞልታችኋል። እርሱ የሁሉ  ራስ ሆነ ይህንንም እያዞረ አሳየ::  የሞትንና የሲኦልን ቁልፍ ተቀበለ::  በዚህ  ዓለም ብቻ ሳይሆን በሚመጣውም ራስ እየሱስ ነው::  

ገዢና አለቃ

አልፋና ኦሜመጀመርያና መጨረሻ

እየሱስ ቻ ነው!!!!

አሜን ሃሌሉያ!

አባት ሆይ አንዳች ሳታስቀር ተፈጸመ ብለህ ሁሉን ጨረስከው! ድል በድል አደረከን ዛሬም በእኛ ውስጥ የምትሰራ አንተ ነህና ክበር የአንተን ስራ እንዳንጋፋ ነገርግን እራሳችንን ለአንተ እንሰጣለን::  ክበር እየሱስ!!!

ዮሐንስ 16: 12-15

12፤ የምነግራችሁ ገና ብዙ አለኝ፥ ነገር ግን አሁን ልትሸከሙት አትችሉም።  13፤ ግን እርሱ የእውነት መንፈስ በመጣ ጊዜ ወደ እውነት ሁሉ ይመራችኋል፤ የሚሰማውን ሁሉ ይናገራል እንጂ ከራሱ አይነግርምና፤ የሚመጣውንም ይነግራችኋል። 14፤ እርሱ ያከብረኛል፥ ለእኔ ካለኝ ወስዶ ይነግራችኋልና።

ሐዋርያት ሊሸከሙ ስላልቻሉ ሊነግራቸው የሚፈልገውን ያህል አልነገራቸውም::  በዚህ ምሽት ተናጋሪው እየሱስ ነው በኃጥያተኞች እጅ ተላልፎ ለመሰጠት ሰዓታት ብቻ ነው የነበረውና ያለውን ሁሉ እንደፈለገው ሊሰጣቸው አልቻለምና ከዚህ ከቆመበት የሚቀጥለውን እያስተዋወቃቸው ነው::  

መንፈስ ቅዱስ ሐዋርያትን ተጠቅሞ የአዲስ ኪዳን ክፍሎችን ባይጽፍልን ኖሮ ብዙ ክፍተት ይኖር ነበረ:: አንዱን ምሳሌ ባነሳ:- አህዛብ አብረን እንደምንወርስ አላወቁም ነበር ለእስራኤል ብቻ ሳይሆን ለአዳም ዘር ሁሉ መምጣቱን አልተረዱም ነበረ::   መንፈስ ቅዱስ ባይረዳቸው ባልደረሱን ነበር::  

ይህንን ሁሉ ትምህርት ሲያስተምር የነበሩት ማትዮስና ማርቆስ (የተቀሩት ወንጌላት) ይህንን ጥልቅ ትምህርት አልፃፉትም::   ዮሐንስም በመንፈስ እየተነዳ  ባይጽፍልን ይህንን ሁሉ አናውቅም ነበረ::  ድንቅ ነው!

የእውነት መንፈስ በመጣ ጊዜ:- 

1.  ወደ እውነት ሁሉ ይመራችኋል፤  እውነት ማነው? እውነትና መንገድ ህይወትም እየሱስ ነውና ወደ እርሱ ነው የሚመራን::

2. የሚሰማውን ሁሉ ይናገራል እንጂ ከራሱ አይነግርምና፤  እየሱስ የአባቱ ፈቃድ መብሉ ነበረ አሁንም መንፈስ ቅዱስ ከወልድ የሰማውን ይነግረናል:: 

3.  የሚመጣውንም ይነግራችኋል:- እርሱ እግዚአብሔር ነውና ከጅማሬ ፍፃሜን ያያል ሳያውቀው የሚሆን ነገር የለም:: ለእርሱ ሰርፕራይዝ የለም::

4.  እርሱ ያከብረኛል፥  መንፈስ ቅዱስ ግቡ ሁሉ እየሱስን ማግነን ነው::  የእኛም ስራ ይኸው ነው ምክንያቱም መንፈስ ቅዱስ በእኛ ውስጥ እየሰራ ነው የሚያገነውና::

5.  ለእኔ ካለኝ ወስዶ ይነግራችኋልና:-  የምናመልከው አንድ አምላክ ነው መንፈስ ቅዱስ በኃላ ስለመጣ ስራው ያነሰ አይምሰለን ለእኛ የተገለጠው ስራውን ከእየሱስ ሲቀበል ስለሆነ ነው:: ለኔ ካለኝ ሲል ሌላ ማንነት አንፈልግ አምላካችን አንድ ነው::

ዮሐንስ 16:15፤ ለአብ ያለው ሁሉ የእኔ ነው፤ ስለዚህ፦ ‘ለእኔ ካለኝ ወስዶ ይነግራችኋል፡’ አልሁ።”

አባት ሆይ እየሱስን ልታገነው መተሃልና በእኔ ውስጥ አግንነው::  

አክብረውም ፤  የሚመጣውንም አሳውቀኝ ፤  ወደ እውነትም ምራኝ ፤  የምትለኝንም መስማት ይሁንልኝ ልትሸከሚ አትችይም አልባል::  አሜን

ዮሐንስ 16: 16-24

19፤ ኢየሱስም ሊጠይቁት እንደ ወደዱ አውቆ፡ እንዲህ አላቸው፦ “ጥቂት ጊዜ አለ፥ አታዩኝምም፤ ደግሞም ጥቂት ጊዜ አለ፥ ታዩኛላችሁ፡ ስላልሁ፥ ስለዚህ እርስ በርሳችሁ ትመራመራላችሁን?

ከላይ ሲነግራቸው የመጣው ስለመንፈስ ቅዱስ ነበረ::  ያለ ምሳሌ በቀጥታ እየነገራቸውና እያስተማራቸው  ቢሆንም አብዛኛው ሃሳብ አልገባቸውም::  ለመታሰርና ወደ መስቀል ለመሄድ ሰዓታት ነው የቀረው እነሱ ግን አልገባቸውም::  

ጥቂት ጊዜ አለ፥ አታዩኝምም፤ ደግሞም ጥቂት ጊዜ አለ፥ ታዩኛላችሁ ሲላቸው ምሳሌያዊ ንግግር መሰላቸውና እንደልማዳቸው እንዲያብራራላቸው ፈልገው እርስ በእርሳቸው ሲጠያየቁ ገብቶት ሊያብራራላቸው ጀመረ::  ነገር ግን እየመጣ ያለው ነገር ምንም ማብራርያ አያስፈልገውም::  አልገባቸውምና ከሴት ምጥ ጋር አመሳስሎ ነገራቸው ዓለም ደስ ይለዋል እነሱ ግን ያዝናሉ::  ምክንያቱም ይህ ሊፈጸም ያለ ነገር እንጂ ምሳሌ አልነበረምና ከዚህ በላይ መብራራት አይችልም:: በሃዘን ውስጥ እንደሚሆኑ ከዛም ደግሞ ሲያዩት በደስታ እንደሚሆኑ ታላቁን ሚስጥር ትንሳኤን ነገራቸው::  ገብቷቸዋል? በፍጹም ለዚህም ነው ከያሉበት የሰበሰባቸው ከትንሳኤው በኃላ::  ይነሳል ብለው አልጠበቁም ሁሉን ትተው ሄዱ::  እነርሱማ የሚጠብቁት በተለያየ የእስራኤል መንግስት ስልጣን ላይ መቀመጥ ነበረ እንጂ ሞቱን አይደለም::

በዚያን ቀንም ከእኔ አንዳች አትለምኑም። እውነት እውነት እላችኋለሁ፥ አብ በስሜ የምትለምኑትን ሁሉ ይሰጣችኋል። ይህ በብሉይ ኪዳን ውስጥ ለሚኖር ሰው ከባድ ነው::  ካህን ጋር ሳይሄዱ መስዋአትን ሳያቀርቡ ያለ መካከለኛ ወደ ቅዱሱ እግዚአብሔር መቅረብ የማይመስል ነገር ነው::  በእየሱስ የመስቀል ስራ የእግዚአብሔር በግ ታርዶ ይህ ተቻለ:: ዛሬ በስሙ አብን እንለምናለን እርሱም ይመልሳል::  ሃሌሉያ!

እስከ አሁን በስሜ ምንም አልለመናችሁም፤ ደስታችሁ ፍጹም እንዲሆን ለምኑ ትቀበሉማላችሁ። እየሱስ እብሯቸው ስለነበረ ጥያቄያቸውን በሌላ አባባል ጸሎታቸውን ወደ እርሱ ነበረ የሚያመጡት እርሱም ጸልዮ የጠየቁትን ይሰጣቸዋል ይህንን ሊቀይረው ነው:: አሁን በስሙ ለምነን እንቀበላለን::  ይህ ስም አብ ያከበረውና ሁሉ የሚገዙለት ነው:: ደስታችሁ ፍጹም እንዲሆን ለምኑ ትቀበሉማላችሁ!  ደስታችን ፍጹም እንዲሆን የሚወድ ጌታ ስሙይባረክ!

አባት ሆይ ተመስገን ይህንን የከበረ ስም ስለሰጠኸኝ::  ስምህን እባርካለሁ! ስምህ ይቀደስ!  ደስታዬን በስምህ ለምኜ በመቀበል አገኛለሁ::  እኔ ወላጅ የሌለኝ አይደለሁኝም አባት አለኸልኝ በሰማይ የምትኖር እኔም ውስጥ ለመኖር የመጣህ  ጌታ ተባረክ!! ላትተውኝ የወደድከኝ የወለድከኝ ጌታ ተወደስልኝ!!!  አሜን

ዮሐንስ 16:25-28

26፤ በዚያን ቀን በስሜ ትለምናላችሁ፤ እኔም ስለ እናንተ አብን እንድለምን የምላችሁ አይደለሁም፤  27፤ እናንተ ስለ ወደዳችሁኝ ከእግዚአብሔርም ዘንድ እኔ እንደ ወጣሁ ስላመናችሁ አብ እርሱ ራሱ ይወዳችኋልና።  28፤ ከአብ ወጥቼ ወደ ዓለም መጥቻለሁ፤ ደግሞ ዓለምን እተወዋለሁ ወደ አብም እሄዳለሁ።

በምሳሌ ሳይሆን በግልጥ እየነገራቸው ነው ግን ጥቂት ጊዜ አለኝ ወይም በዚያን ቀን ያለውን በውል አልተረዱም::  ጥቂት ያለው ሰዓታትን ነበረና ያቺ ቀን መጥታ በራሳቸው የሚለምኑበት ቀን አለና የሚያስፈልጋቸውን  ሁሉ እውቀት እየሰጣቸው ነው::  ከልባችሁ አይታወክ ጀምሮ ብቻቸውን እንደማይሆኑና መንፈስ ቅዱስ እንደሚመጣላቸው እንዲሁም ስለተሰጣቸው ስም ይህም ስም አብ መልስ የሚሰጥበት እንደሆነና ብዙ ነገሮችን እያስተማረ ነው::

በዚያን ቀን በስሜ ትለምናላችሁ፤ እኔም ስለ እናንተ አብን እንድለምን የምላችሁ አይደለሁም::  ሐዋርያቱ  የለመዱት ነገር ጉዳዮችን ሁሉ ወደ እርሱ ያመጣሉ እርሱም አባቱን ይለምናል ይፈጸማል::  እያላቸው ያለው ይህ ግን አሁን ሊቀየር ነው በስሜ አብን ለምናችሁ ትቀበላላችሁ::  እኔ አለምንላችሁም አሁን ወደ አብ ለመግባት ድፍረት አላችሁ ከኃጥያት ነጽታችኃልና በስሜ ለምናችሁ ተቀበሉ እያለ ነው::  ስሜን ተጠቀሙ ሲላቸው ከነሙሉ ማዕረጉ ነው የሰጣቸው ልክ እየሱስ እንደሚለምን ነው አብ የሚያየው በስሙ ስንቀርብ::  ሃሌሉያ!!

አብ ገና ኃጥያተኞች ሳለን ወደደን:: ወላጁን የሚወድ ልጁን ደግሞ ይወዳል::  

ከአብ ወጥቼ ወደ ዓለም መጥቻለሁ፤ ደግሞ ዓለምን እተወዋለሁ ወደ አብም እሄዳለሁ አለን። አሜን!  በአብ ቀኝ በክብር የተቀመጠው ጌታ የተባረከ ይሁን! 

አባት ሆይ ወደፊትህ ቀርቤ በእየሱስ ክርስቶስ ስም ለምኜ እቀበል ዘንድ ፈቃድህ ስለሆነ ተመስገን!!  ስለዚህ ስለከበረው ስምህ አመሰግናለሁ! አሜን!! 

ዮሐንስ 16: 29-33

31፤ ኢየሱስም እንዲህ ብሎ መለሰላቸው፦ “አሁን ታምናላችሁን?  32፤ እነሆ፥ እያንዳንዳችሁ ወደ ቤት የምትበታተኑበት እኔንም ለብቻዬ የምትተዉበት ሰዓት ይመጣል፥ አሁንም ደርሶአል፤ ነገር ግን አብ ከእኔ ጋር ስለ ሆነ ብቻዬን አይደለሁም።  33፤ በእኔ ሳላችሁ ሰላም እንዲሆንላችሁ ይህን ተናግሬአችኋለሁ። በዓለም ሳላችሁ መከራ አለባችሁ፤ ነገር ግን አይዞአችሁ፤ እኔ ዓለምን አሸንፌዋለሁ።”

የሐዋርያቱ ዓይን እየተከፈተ ነበረና ሁሉን እንድታውቅ ማንምም ሊጠይቅህ እንዳትፈልግ አሁን እናውቃለን፤ ስለዚህ ከእግዚአብሔር እንደ ወጣህ እናምናለን፡አሉት።  መልሱ ግን አሁን ታምናላችሁን?  ነበረ ምክንያቱም ከጥቂት ሰዓት በኃላ የሚሆነውን ያውቅ ነበረና በመከራ ውስጥ ጥለውት እንደሚበታተኑ ነገራቸው::  በሰላም ተቀምጠው እያሉ ይህንን ማለቱ ያስከፋል ግን እርሱ በደንብ ያውቃቸዋል ስለዚህም ተፈጽሞ አየነው::

ጥለውት እንደሚሄዱ አውቆ እራሳቸውን እንዳይወቅሱ ካልሆነ በቀር ለምን አብ ከእኔ ጋር ስለ ሆነ ብቻዬን አይደለሁም አላቸው::  ትተውኛላችሁ ይበቃ ነበረ::  በዙሪያችን ሰዎች እስከተወሰነ ደረጃ ነው አብረውን መጏዝ የሚችሉትና ሰውን አንታዘብ እንዘንም ጌታ እራሱ ለብቻ መተው ምን ማለት እንደሆነ ስለሚያውቅ ስለተፈተነበት አብሮን ይሆናል::  እኔና እርሱ ብቻ የምንሆንባቸው ጊዜያትአሉ::  ሁሉ ቢሄድ እርሱ ግን አይሄድም::  እየሱስ የአባቱን ፈቃድ ብቻውን አከናወነ እናንግስህ ያሉት ትተውት አይሁንብህ ያሉትም ያመናቸው ጥቂት ሐዋርያትም ትተውት ብቻውን ሆኖም ወደ ዓላማው ሄደ እንጂ ምክንያት አድርጎ ከመጣበት ዓላማ አልተዛነፈም::  ህይወቱን ለእኛ ሰጠ!

ዓለም ሁሉ ፊቱን እንደሚያዞርበትና ብቻውን እንደሚሆን እያወቀ በእኔ ሳላችሁ ሰላም እንዲሆንላችሁ ይህን ተናግሬአችኋለሁ ይላቸዋል::  በዚህ ውስጥ ሆኖም ሰላምን ይሰጣል:: ይህም ብቻ አይደለም  በዓለም ሳላችሁ መከራ አለባችሁ፤ ነገር ግን አይዞአችሁ፤  በሰውኛ ግን ተላልፎ መሰጠት መታሰር መደብደብ መሰቀልና መሞት ድል አይመስልም መሸነፍ  እንጂ::  እየሱስ ግን የሚመጣውን እያየ አይዟችሁ አላቸው:: ምን አይነት ፍቅር ነው!! በቁጣ መሞላትና እነርሱን ልክ ልካቸውን መንገር ነበረ ለእኛ የሚቀናን እርሱ ግን በስጋ መጋፈጥ እንደማይችሉ መንፈሱ ግን ከላይ ሲወርድባቸው አንበሳ እንደሚያደርጋቸው አውቆ ታገሰ አይዟችሁ አላቸው::  በድካም ላሉት እንፀልይ እንጂ አንፍረድ እርሱ አንስቶ እንደገና ሊጠቀምባቸው ይችላልና::

እኔ ዓለምን አሸንፌዋለሁ ሲላቸው ገና ምንም አልተፈጠረም ነበር::  በህይወቱ ጠላትን ድል ነሳ እርሱ አንዳች ኃጥያት አልተገኘበትም ንፁ የእግዚአብሔር በግ::  በሞቱም ድልነሳ በትንሳኤውም ድል ነሳ! ድል ለነሳው በግ ክብር ይሁን!

አባት ሆይ ይህንን ድል እንዳጣጥም ስለረዳኸኝ ተመስገን በዓለም መከራ ቢኖርም ሁሉን ድል አድርገህልኛልና ድል እየነሳሁ በሰላም ተሞልቼ እመላለሳለሁ:: ሃሉሉያ!

አሜን!

ዮሐንስ 17:1-2

ኢየሱስም ይህን ተናግሮ ወደ ሰማይ ዓይኖቹን አነሣና እንዲህ አለ፦ “አባት ሆይ፥ ሰዓቱ ደርሶአል፤ ልጅህ ያከብርህ ዘንድ፥ በሥጋም ሁሉ ላይ ሥልጣን እንደ ሰጠኸው፥ ለሰጠኸው ሁሉ የዘላለምን ሕይወት ይሰጣቸው ዘንድ ልጅህን አክብረው።

እየሱስ ለራሱ ከቁ 1-5 ድረስ ፀለየ::  ፀሎቱንም አባት ሆይ እያለ እየተጣራ ይፀልይ ነበረ::  በፀሎቱም ልጅህ እያለ እራሱን ይጠራል::  በደህንነታችን ስራ ውስጥ አብንና ወልድን ያሳየናል::  አብ ፀሎቱን በዚህ ስፍራ ባይሰማው ኖሮ ደህንነት በሌለ::  እራሱን በአብ ፊት እየቀደሰና የሌላውን ኃጥያት እየተሸከመ ያለበት ሰዓት ነው::  ልክ በብሉይ ኪዳን ካህናት የሰውየውን ኃጥያት ወደ በሚታረደው እንሰሳ  አናት ላይ ጭነው እንደሚያደርጉት አይነት ማለት ነው::  መስዋትነቱ የጀመረው እዚህ ጋር ነው::

በፀሎቱም ልጅህ ሊያከብርህ ሰዓቱ ደርሷል አለ::  መቼም ይህንን ፀሎት ለሚሰማ ወደ ሞት በመሄድ ነው  አባቱን የሚያከብረው ብሎ መገመት አይቻልም:: ግን እውነቱ እርሱ ነው በሞቱ ሊያከብረው ነው::  ነገር ግን ልጅህ ያከብርህ ዘንድ አክብረው ነው እያለ ያለው:: ይህም ማለት እርዳኝ በዚህ ሞት አከብርህ ዘንድ ምክንያቱም ከዚህ ሞት በኃላ የዘላለምን ሕይወት የሚሰጠን!   የተገዛነው በከበረው በእየሱስ ህይወት መስዋትነት ነው!

በዚህ ሞት ውስጥ አብ እየሱስን ሲያከብረው እየሱስ በሥጋም ሁሉ ላይ ስልጣንን ይቀበላል በዚህም ስልጣን አብ ለሰጠኸው ሁሉ የዘላለምን ሕይወት ይሰጣቸዋል::  አብ ከሳበው በቀር ወደ እኔ የሚመጣ የለም ብሎናል:: 

አባት ሆይ የዘላለምን ህይወት እንድናገኝ እየሱስን ስላከበርከውና መስዋእቱን ስለተቀበልክ ተመስገን::  በከበረው በልጅህ መስዋትነት የራስህ ስላደረከኝ አባ አባት ብዬ እንድጠራህ መንፈስህን ስለሰኸኝ አመሰግንሃለሁ::  ማንም በራሱ አይበረታምና እኔም ዛሬ ፈቃድህን እንድታዘዝና እንዳከብርህ ፀጋህን አብዛልኝ እርዳኝም! አሜን!

እየሱስ ሰዓቱ ደርሷልና ልጅህን አክብር እያለ ወደ አባቱ ቀና ብሎ ሲፀልይ ይህ ሰዓት ምን የሚሆንበት ነው ማለት ያስፈልጋል::  

ሁለቱ መንግስቶች የሚለይላቸው ጊዜ ነው ውድድር የሚገቡ ናቸው ለማለት ሳይሆን ሰይጣን በድለላው ሄዋንንና አስቶ አዳምን ከነዘሩ በስሩ አድርጎ ነበረና ነው::  

የእባቡ ራስ የሚቀጠቀጥበት ጊዜ ነው::  

ሙሴ እንደሰቀለው የናስ እባብ ያዮት ሁሉ ከተነደፉበት መርዝ ነፃ እንደሆኑ እንዲሁም ሰይጣን የነደፈው ሁሉ የሰው ልጅ ነፃ የሚወጣበት ሰዓት ነው::

እየሱስ ከፍ ከፍ ሊልና ምርኮን ሊካፈል ጊዜው ነው::

አለቆች ስልጣናት ጌትነት ሁሉ መበርከክያቸው ሰዓት ነው::

ትንሳሳኤም ሊሆን ነው!!!

የሲኦልና የሞት ቁልፍም ሊነጥቅ ጊዜው ነው::

ሞት ሆይ መውጊያህ የታል ሊባል ጊዜው ነው::

በሰማይና በምድር ስልጣን ተሰጠኝ ሊል ጊዜው ነው! 

እርሱ ሲከብር የእግዚአብሔር መንፈስ በህዝቡ ሊመጣና ሊያትም እንዲሁም ድልን ሊሰጥ ጊዜው ነው::

ይህንን ሁሉ ጦርነት ለመጀመር እየሱስ ሰዓቱ ደርሷል አለ ከዛ በፊት ግን አንዳች ሊያደርጉበት ወይንም ሊይዙት እንዳልቻሉ ቃሉ ይነግረናል አሁን ግን ሰዓቱ ነውና ለኃጥያተኞች ተላልፎ ለመሰጠት ወደ ቀጠሮው ቦታ እየሄደ ነው:: ልጅህን አክብር  ብሎ ለሰይጣን ፈተናና ሽንገላ ያልተረታውን ማንነቱን እያቀረበ::  ሰይጣን ይህንን ማንነቱን በአዳም እንደለመደው ለመደለልና ለመውሰ ድ ሞክሯል የእግዚአብሔር ልጅ ከሆንክ ይህንንና ያንን አድርግ ደግሞም ወድቀህ ብትሰግድልኝ  እያለ ፈትኖት  አልተሳካለትም አልተጠመደም ስለዚህ ይህ የመጨረሻ ጦርነት ሊጀመር ነው::

እራሱን ለመስዋትነት ሲያቀርብ እንደ ካህንም እንደ እግዚአብሔር በግም ነው እየሆነ ያለው::  አብረሃም ከልጁ ጋር ወደ ተራራው ያደረጉትን ጉዞ ያስታውሰኛል ይስሃቅ የሚሰዋው የታለ ብሎ ሲጠይቅ እግዚአብሔር ያዘጋጃል የተባለው በግ እየተዘጋጀ ነው::  በብሉይ ኪዳን እንከን የሌለው እንደሆነ የሚቀርበው መስዋእት ካህኑ ያረጋግጣል እየሱስም እንከን የሌለው በብዙ ተፈትኖ ያለፈ ነውና አክብረኝ እያለ እንከን የለሽ ምመስዋት ሆኖ ለመቅረብ ፀለየ:: 

ዋዉ!!! አባት ሆይ ይህ ሁሉ ለሰው ልጅ?! ምን እንላለን ተመስገን!!!  ፍቅርህ እንዴት ብዙ ነው!!

ዛሬም የቀደስከውንና በመንፈስህ ያተምከውን እኔነቴን በፊትህ  የጽድቅ የጦር እቃ አድርጌ አቀርባለሁ::  ይህ ማንነቴ የአንተ ነው በዋጋ የተገዛ እነሆኝ አባት ሆይ ተጠቀምብኝ ብዙዎችን ከጠላት መንጋጋና ከጨለማው ስልጣን  ለማውጣት የዳነውንም ህዝብህን ለማበርታት ተጠቀምብኝ!!!!   ባከበርከው በልጅህ በእየሱስ ክርስቶስ ስም!  አሜን 

ዮሐንስ 17:3፤ እውነተኛ አምላክ ብቻ የሆንህ አንተን የላክኸውንም ኢየሱስ ክርስቶስን ያውቁ ዘንድ ይህች የዘላለም ሕይወት ናት።

የዘላለም ህይወት ለሁሉም የተሰጠ ነው ሰው ለዘላለም የሚኖር ፍጥረት ነው የሚለየው ዘላለሙን የት ያሳልፋል የሚለው ላይ ነው::  

እየሱስ የሚለን:- የዘላለም ህይወት ማለት ሁለት ነገር ማወቅ ነው:-

1. እውነተኛ አምላክ ብቻ የሆንህ አንተን 

2.  የላክኸውንም ኢየሱስ ክርስቶስን

እግዚአብሔር ልጁን እንዲልክ እየሱስም ህይወቱን እንዲሰጥ ያደረገው  ፍቅር ነው:: በምድር ሲመላለስ አላወቁትም ይህንን ጌታ::  እኛ ግን በስብከት ሞኝነት አምነን በመንፈስ ቅዱስ እራሱን ገልጦን አወቅነው::  ወደ እርሱ ሮጠን ተሸሸግን!

ዮሐንስ 3:16፤ በእርሱ የሚያምን ሁሉ የዘላለም ሕይወት እንዲኖረው እንጂ እንዳይጠፋ እግዚአብሔር አንድያ ልጁን እስኪሰጥ ድረስ ዓለሙን እንዲሁ ወዶአልና።

አባት ሆይ ስለወደድከን እንዳንጠፋ አድነህ እራስህን አሳወከን:: አንተን ማወቅ ስለሰጠኸኝ ተመስገን::  ሃሌሉያ!

ዮሐንስ 17: 4-5

4፤ እኔ ላደርገው የሰጠኸኝን ሥራ ፈጽሜ በምድር አከበርሁህ፤

5፤ አሁንም፥ አባት ሆይ፥ ዓለም ሳይፈጠር በአንተ ዘንድ በነበረኝ ክብር አንተ በራስህ ዘንድ አክብረኝ።

ይህንን ፀሎት መስማት እንዴት የሚገርም አጋጣሚ ነው::  ሙሴ እንደተባለው ጫማ ማውለቅ የሚያስጠይቅ መሆን ነበረበት::  ወልድ ለአብ የሚናገረውን እያደመጡ ነው ያሉት በሌላ አባባል እኛም እየሰማን ነው ይህንን ፀሎት::  እየሱስ ሲፀልይ የመጀመርያው አይደለም ለሊቱን ሁሉ ሲፀልይ ያድር ነበረ ይሄኛው ግን ሊቀ ካህንነቱን በግልጽ እያሳየ ስለራሱም ስለሐዋርያቱም እንዲሁም በሩቅ ስላለነው ስለእኛ ፀለየ::  ዋዉ!!

የመስቀሉን ስራ ገና አልጨርረሰም ግን እኔ ላደርገው የሰጠኸኝን ሥራ ፈጽሜ በምድር አከበርኩህ አለ::  እራሱን አሳልፎ በፈቃዱ ለመስጠት ወደ ቀጠሮ ስፍራው እንደሚሄድ ስለሚያውቅና እንዲሁም ከዚህ በኃላ ስለሚያዋክቡት ተረጋግቶ የሚፀልይበት ጊዜ እንደሌለውም አውቆ::  መስቀል ላይ ገና ሳይወጣ እራሱን ለመስዋእት አቀረበ::  ልክ ካህናት በብሉይ ኪዳን እንደሚያደርጉት  የሚቀርበውን መስዋእት እንከን የሌለው መሆኑን አገላብጠው አይተው እንደሚያረጋግጡት እንዲሁምእየሱስ ህይወቱን በአብ ፊት አቅርቦ እንከን የሌለው በግ መሆኑን አሳየ::  ፈጽሜ አከበርኩህ እያለ ፀለየ እርሱ እፁብ ድንቅ ነው::  ንፁ በግ!  በዕብራውያን 4:14-15፤ እንግዲህ በሰማያት ያለፈ ትልቅ ሊቀ ካህናት የእግዚአብሔር ልጅ ኢየሱስ ስላለን፥ ጸንተን ሃይማኖታችንን እንጠብቅ:: ከኃጢአት በቀር በነገር ሁሉ እንደ እኛ የተፈተነ ነው እንጂ፥ በድካማችን ሊራራልን የማይችል ሊቀ ካህናት የለንም።

ለሐዋርያቱም እምነት እንዲሆናቸው እፊታቸው ስለማንነቱ ፀለየ::  እንዲህም አለ:-  አባት ሆይ፥ ዓለም ሳይፈጠር በአንተ ዘንድ በነበረኝ ክብር አንተ በራስህ ዘንድ አክብረኝ። ይህንን ክብር ጥሎ ሲመጣ ፍቅር ነው ያመጣው ሁሉን ቁጭ አድርጎ ሊታደገን መጣ::  አሁንም ወደዛው ክብሩ ሊመለስ ነው::  እግዚአብሔር ከሆነ ለምን ይህንን ፀሎት ፀለየ የሚሉ ሰውኢች የፀለየውን የሰሙ አይመስሉም::  አንድ አምላክ እንዳለ እርሱንም እንደሚተካከልና አንድ እንደሆነ እያወጀ ያለበት ፀሎት ነው::  አንተው አክብረኝ ብሎ እራሱን ሰጠ!  ስለእኔና ስለሰው ልጅ ሁሉ!! 

አባት ሆይ ተመስገን የተቀደሰውን እራስህን ስለሰው ልጅ መስዋእት ስለሰጠህ እናመሰግናለን::  በከበረው ዙፋንህ ላይ ነህና ክበር::  እኔም የቀደስከውን ማንነቴን እሰጥሃለሁ ክበርበት::  አሜን!

ዮሐንስ 17: 6-13

6፤ ከዓለም ለሰጠኸኝ ሰዎች ስምህን ገለጥሁላቸው። የአንተ ነበሩ ለእኔም ሰጠሃቸው፤

ጌታ እየሱስ ወደ አባቱ የፀለየው ፀሎቱ

ቃሉን ሐዋርያቱ እንደተቀበሉት ነው:: ሲቀበሉትም :- ቃሉን እንደጠበቁ:  ሁሉን ከአባቱ መቀበሉን እንዳወቁ: ቃሉንም እንደሰጣቸውና  ከአብ ወጥቶ መምጣቱን እንዳመኑ ይመሰክርላቸዋል::

በመቀጠልም የካህንነቱን ስራ ሲሰራ እናያለን እኔ ስለ እነዚህ እለምናለሁ፤ ስለ ዓለም አልለምንም ስለ ሰጠኸኝ እንጂ፤ የአንተ ናቸውና፤ የእኔም የሆነ ሁሉ የአንተ ነው የአንተውም የእኔ ነው፤ እኔም ስለ እነርሱ ከብሬአለሁ። እየማለደ ያለው ስለቅዱሳን እንጂ በዓለም ስላሉት አይደለም::  አብ ወደ ክርስቶስ ከሳበው በቀር ማንም እንደማይመጣ ቃሉ ይነግረናል ጌታም ስለሰጠኸኝ ሰዎች ብሎ ነው የፀለየው:: የአንተ የሆነው ሁሉ የእኔ ነው የእኔም የሆነው የአንተ ነው:: ስለዚህ ልመጣ ነውና በዚህ ዓለም አብሬአቸው አልኖርምና በስምህ እንዳይጠፉ ጠበኳቸው ከጥፋት ልጅ በቀር አሁንም አንተ አባት ሆይ እነዚህን እንደኛ አንድ እንዲሆኑ በስምህ ጠብቃቸው! ብሎ ፀለየ::  ዋዉ ዛሬ በስሙ ከእርሱ ጋር አንድ እንድንሆን ከዚህ ፀሎት የተነሳ አብ አባት እየጠበቀን ነው:: ለካስ ብርታቴ ትጋቴ እርሱን መፈለጌ አይደለም በቤቱ የተከለኝ ከፀጋም በላይ እየተደረገልኝ ያለው ጥበቃ ነው::

አብ አባት ሆይ ተመስገን ከዚህ ፀሎት የተነሳ ህብረቴ ከአንተጋር እንዲሆንና እንዲፀና በአንተ ስምና ኃይል እየተጠበኩ ስለሆነ አመሰግንሃለሁ! ሃሌሉያ!  እልልልልልል!!! አሜን

ዮሐንስ 17: 14-18

18፤ ወደ ዓለም እንደ ላክኸኝ እንዲሁ እኔ ወደ ዓለም ላክኋቸው፤ 

ጌታ እየሱስ ሰጥቻቸዋለሁ የሚለው ቃሉን ነው::  ከዛም ይህ ቃል የሚያደርገውን እንይ:- በእውነትህ ቀድሳቸው፤ ቃልህ እውነት ነው። ቃሉ ይቀድሳል::  እንደዚሁም እየሱስ  እራሱን ሰጥቶ ቀደሰን:-  እነርሱም ደግሞ በእውነት የተቀደሱ እንዲሆኑ እኔ ራሴን ስለ እነርሱ እቀድሳለሁ። ብሎ ፀለየና የራሱን ቅድስና ለእኛ ሰጠን::

ሌላው የፀለየው:- እኔም ከዓለም እንዳይደለሁ ከዓለም አይደሉምና ዓለም ጠላቸው። ደግሞም እንደገና እኔ ከዓለም እንዳይደለሁ ከዓለም አይደሉም አለ::

ከዓለም አይደለንም መንገደኞችና መፃተኞች ነን::  ከዚህ ዓለም ጋር ለመዋሃድ አንሞክር አይሰራም!! ስለዚህም ጌታ ከክፉ እንድትጠብቃቸው እንጂ ከዓለም እንድታወጣቸው አልለምንም ብሎ ነው የፀለየው::  እዚህ ዓለም ላይ ስንኖር ከክፉ እንድንጠበቅ ጌታ ፀልዮልናልና ክፉ ይመኛል እንጂ አያገኘኝም!!! ሃሌሉያ! 

እሺ ቀደሰን በቃሉና እራሱን በመስጠት እንዲሁም  ከክፉ ተጠበቅን ከዛስ? 

ከዛማ ወደ ዓለም እንደ ላክኸኝ እንዲሁ እኔ ወደ ዓለም ላክኋቸው ብሎ ላከን::  ከዓለም አይደለንም በዓለም ከሚሰራው መንግስት ተፋተን የእግዚአብሔር ወገን ተብለን ተቆጥረን::   ክፉ በሚቆጣጠረው ዓለም ላይ የመንግስታችንን ስራ ለመስራት አምባሳደር ተደርገን ተሹመናል!!  ስራችንን ስንጨርስ ወደ አገራችን እንሄዳለን ዛሬ ግን ተልከናል ወደዝች ክፉ ወደ ሰለጠነባት ዓለም::  በክፋት ሁሉ ላይ ስልጣን ተሰቶናል ሊጎዳን አይችልምና እናባርረዋለን እናስለቅቀዋለን እንቀማዋለንን እናስተፋዋለን::  ድል ለእግዚአብሔር ህዝብ ነው!!! አሜን

አባት ሆይ ተመስገን በዚህ ቃልህ ስለቀደስከኝ::  ይህ የእየሱስ ፀሎት ዛሬም በፊትህ ነውና ክፉ ስለማይነካኝ አመሰግንሃለሁ::  በአጠገቤ ሺህ በቀኜም አስር ሺህ ይወድቃል እንጂ ወደ እኔ አይቀርብም!!  ሃሌሉያ!  ከበርልኝ!!  ወደዚች ዓለም ተልኬያለሁና ስራህና ፈቃድህ በእኔ ይፈፀም::  መንግስትህ ትምጣ ትግዛ!  አሜን!

ዮሐንስ 17:20-21፤ “ሁሉም አንድ ይሆኑ ዘንድ፥ ከቃላቸው የተነሣ በእኔ ስለሚያምኑ ደግሞ እንጂ ስለ እነዚህ ብቻ አልለምንም፤ አንተ እንደ ላክኸኝ ዓለም ያምን ዘንድ፥ አንተ፥ አባት ሆይ፥ በእኔ እንዳለህ እኔም በአንተ፥ እነርሱ ደግሞ በእኛ አንድ ይሆኑ ዘንድ እለምናለሁ።

ጌታ እየሱስ ስለእኛ የፀለየውን እንይ:-

ሁሉም አንድ ይሆኑ ዘንድ ብሎ ነው ያለው:: ለምን አንድ መሆናችን ተፈለገ?! ወረድ ብሎ እንደሚለው *አንተ እንደ ላክኸኝ ዓለም ያምን ዘንድ*  ይሄ ነው ምክንያቱ::  እየሱስ ወደ ዓለም ተልኮ መምጣቱን ሁሉ እንዲያውቅ ነው:: ወንጌልም ከአንድነታችን የተነሳ እንዲሮጥነው::

ይሄ ፀሎት ተመልሷል::  እኔ የገጠመኝን ልመስክር:-  አንድ የገበያ ስፍራ ላይ ከምትሸጥ እህትጋር መነጋገር ጀመርንና ከየት አገር ነው የመጣሽው ብዬ ስጠይቃት ከኢራን አለችኝ::  እኔም አገርሽ ሰላም ነው እንዴት ናቸው? ብዬ ስጠይቃት አይይ አባረሩን አለችኝና ከአንገትዋ ላይ መስቀልዋን አውጥታ ስታሳየኝ የአገር ጥያቄዬ ምኔ ሁሉ ጠፍቶ የጠፋችብኝን እህቴን ያገኘሁኝ ያህል ደስታ ወረረኝ::  ለካስ ክርስትያን ስትሆን ሊገድልዋትስለሚፈልጉ ነው ከአገርዋ የተሰደደችው:: ቀጥላም እየሱስ መሃላችን ተገለጠ አለችኝ ከዛማ እልል ወደ ማለትና ፀሎት ወሰደኝ::  አላውቃት አታውቀኝ ይህ የፀሎቱ መልስ ነው::  በእርሱ አንድ ነን:: 

ይህንን ሁልጊዜ ጠላት ይዋጋዋል ሊለያይና ሊበትን ነው የሚፈልገውና አንድነትን መጠበቅ ከእኛ ይጠበቃል:: አንድ አካል አለ የዚህም አካል ራስ   እ  የ  ሱ  ስ ነው!  አሜን!  ሁላችን በዚህአካል ውስጥ እየተጋጠምን እናድጋለን:: በኤፌሶን 4:11፤ እርሱም አንዳንዶቹ ሐዋርያት፥ ሌሎቹም ነቢያት፥ ሌሎቹም ወንጌልን ሰባኪዎች፥ ሌሎቹም እረኞችና አስተማሪዎች እንዲሆኑ ሰጠ፤ እርሱ ነው የሰጠው ለአካሉ:: በ1 ቆሮንቶስ 12:12፤ አካልም አንድ እንደ ሆነ ብዙም ብልቶች እንዳሉበት ነገር ግን የአካል ብልቶች ሁሉ ብዙዎች ሳሉ አንድ አካል እንደ ሆኑ፥ ክርስቶስ ደግሞ እንዲሁ ነው፤

አሜን! 

ስለዚህ እየሱስ ሲፀልይ በእኔ እንዳለህ እኔም በአንተ፥ እነርሱ ደግሞ በእኛ አንድ ይሆኑ ዘንድ እለምናለሁ። ከእርሱ ጋር አንድ እንድንሆን ወዶ ፈቅዶ ፀልዮልናል:: ህብረታችን ከአብ ጋር ከልጁም ከእየሱስ ጋር ነው::  አሜን

አባት ሆይ በአንተ ውስጥ መኖርና ከአንተ ጋር አንድ መሆን ከቅዱሳንም ጋር አንድ መሆን ስለተሰጠን ተመስገን::  በዚህ ውስጥ ለዘላለም እንኖራለን! በየትኛውም አገር ውስጥ ስላሉ እህትና ወንድሞቼ እፀልያለሁ አባት ሆይ ባሉበት ይጠበቁ ዘንድና የሚድኑ ነፍሳት በእነርሱ ላይ እንዲጨመሩ እፀልያለሁኝ:: 

አሜን!

ዮሐንስ 17:22-23፤ እኛም አንድ እንደ ሆንን አንድ ይሆኑ ዘንድ፤ እኔም በእነርሱ አንተም በእኔ ስትሆን፥ በአንድ ፍጹማን እንዲሆኑ፥ የሰጠኸኝን ክብር እኔ ሰጥቻቸዋለሁ፤ እንዲሁም ዓለም አንተ እንደ ላክኸኝ በወደድኸኝም መጠን እነርሱን እንደ ወደድሃቸው ያውቃል።

ጌታ ደግሞ ይህንኑ ጸሎት ጸለየ ስለአንድነትና ስላለን ህብረት::  መደጋገሙ የሚያሳየን እንዴት አስፈላጊ መሆኑን ነው::

እኛም አንድ እንደ ሆንን አንድ ይሆኑ ዘንድ፤ –  የአብና የወልድ አንድነት ምን አይነት ነው? የእኔ ሳይሆን የአንተ ፈቃድ ይሁን የሚያሰኝ አንድነት ነው:: 

እኔም በእነርሱ አንተም በእኔ ስትሆን፥ በአንድ ፍጹማን እንዲሆኑ፥ የሰጠኸኝን ክብር እኔ ሰጥቻቸዋለሁ፤ –  እየሱስ በእኛ ውስጥ እንዳለ እራሱ እያወጀ ነው:: እኔና አብ እንመጣለን በእርሱም ዘንድ መኖርያ እናደርጋለን:: ይህ የሚሆነው በአንድ ፍፁማን እንድንሆንና የሰጠኸኝን ክብር እኔ ሰጥቻቸዋለሁ እንዳለ ክብሩን እንድንቀበል ነው::  

የሰጠን ክብር ምንድነው?  በሰማይና በምድር ሙሉ ስልጣን ተሰጠኝ እንግዲህ ሂዱና ብሎ ሙሉ የአምባሳደርነትን ማዕረግ ተቀበልን እንዲሁም ከስም ሁሉ በላይ የሆነውን ስም ተቀብሎ ለእኛ እንድንድንበት ሰጠን:: በፊልጵስዩስ 2:10፤ ይህም በሰማይና በምድር ከምድርም በታች ያሉት ሁሉ በኢየሱስ ስም ይንበረከኩ ዘንድ፥ 11፤ መላስም ሁሉ ለእግዚአብሔር አብ ክብር ኢየሱስ ክርስቶስ ጌታ እንደ ሆነ ይመሰክር ዘንድ ነው። አሜን::  እንደዚሁም ከእርሱ ጋር አንድ የሚያደርገንን  በመንፈስ ቅዱስን ሰጠን!

እንዲሁም ዓለም አንተ እንደ ላክኸኝ በወደድኸኝም መጠን እነርሱን እንደ ወደድሃቸው ያውቃል። ለዓለም የሚቀረው ምስክርነት መወደዳችንን ማወቁ ነው::  የተወደድነውም ልክ እየሱስ  በተወደደበት መጠን ነው:: አብም ይህንን ብሏል:- በማርቆስ 1:11፤ “የምወድህ ልጄ አንተ ነህ፥ በአንተ ደስ ይለኛል፡” የሚል ድምፅ ከሰማያት መጣ። እንግዲህ በዚህ ፍቅር ተወደናል::

አባት ሆይ ክብርህን ስለሰጠኸን ስለወደድከን እናመሰግናለን::  እንደተወደዱ ልጆች መመላለስ ይሁንልን!  አሜን! ይህ ፍቅር ላልገባውና አንተን ለማያውቁ እኛ ነንና መናገሪያ መንገዶችህ እርዳን ለጠፉት ግድ ብሎን እንድንመሰክር! 

ዮሐንስ 17:24፤ አባት ሆይ፥ ዓለም ሳይፈጠር ስለ ወደድኸኝ የሰጠኸኝን ክብሬን እንዲያዩ እኔ ባለሁበት የሰጠኸኝ እነርሱ ደግሞ ከእኔ ጋር ይሆኑ ዘንድ እወዳለሁ።

አባት ሆይ ብሎ አብን እንድንጠራ ያስተማረን ጌታ እርሱም እንደዛው እየፀለየ ነው::  ዓለም ሳይፈጠር ስለ ወደድኸኝ  አለ ጌታ ይህ ማለት በሌላ ክፍል ላይም እንደሚለው እግዚአብሔር ፍቅር ነው::  ይህ ፍቅር ድሮም ያለ ማንነቱ እንጂ አሁን የተፈጠረ አይደለም::  

ሌላው በአባት ፊት የሰጠኸኝን  ብሎ ነው እኛን የሚጠራን ቃሉ እንደሚለን አብ ካልሳበው በቀር ወደ እየሱስ የሚመጣ የለም ይህ ማለት እያንዳንዳችንን አብ እራሱ ለእየሱስ የሰጠን ልጆቹ ነን::  አሜን!

ስለፍቅሩ አነሳ እኛንም ከእጁ ስለመቀበሉ አነሳና በዮሐንስ 14:2፤ በአባቴ ቤት ብዙ መኖሪያ አለ፤ እንዲህስ ባይሆን ባልኋችሁ ነበር፤ ስፍራ አዘጋጅላችሁ ዘንድ እሄዳለሁና፤ ይህንን ቃል ኪዳኑን ይፀልየዋል::  

ይኸውም በተዘጋጀልን ስፍራ ከእርሱ ጋር እንድንኖርና የሚፈልገውም ክብሩን እንድናይ ፀለየልን:: እርሱ ባለበትም እንድንኖር ለዘላለም  እኔ ባለሁበት የሰጠኸኝ እነርሱ ደግሞ ከእኔ ጋር ይሆኑ ዘንድ እወዳለሁ። አሜን ይህ ፀሎት ተመልሷል እኛ በዚህ ምድር ብንመላለስም ወደ ፍቅሩ ልጅ መንግስት ተሸጋግረናል::  እንዲሁም በአብ ቀኝ በእየሱስ ውስጥ ተሰውረናል:;  በትክክል ይህ ፀሎት ተመልሷል!  አሜን

አባት ሆይ እላለሁ እኔም ስምህ ይባረክ አንተ ባለህበት ስለተገኘሁ  በዚህ ሰዓት ስምህ ይባረክ!   በዘላለም ፍቅርህም ስለወደድከኝ ተባረክ!  አሜን!

ዮሐንስ 17: 25-26

25፤ ጻድቅ አባት ሆይ፥ ዓለም አላወቀህም፥ እኔ ግን አወቅሁህ እነዚህም አንተ እንደ ላክኸኝ አወቁ፤

26፤ እኔንም የወደድህባት ፍቅር በእነርሱ እንድትሆን እኔም በእነርሱ፥ ስምህን አስታወቅኋቸው አስታውቃቸውማለሁ።”

በጸሎቱ መዝጊያ የሚያነሳቸው ኃሳቦች/የጸሎት ርዕስ:-

እየሱስ አብን የሚጠራበትን ስናይ:- ጻድቅ አባት ሆይ ይለዋል::  ወደ መስቀልና መከራ እየሄደ ጻድቅ አባት ሆይ ይላል::  ዓለም ዛሬም አላወቀውም አልተረዳውም ለምን እየሱስ እዳ እንደከፈለ ነገር ግን ይሞግታል የተሻለ መንገድ አልነበረም ወይ? ለምን አዳምን  ፈተነው? እዛው ጋር ለምን ህይወት አላበቃምና ሌላም ሌላም አወቅን የእውቀትን ጥግ አየን በሚሉ በየዘመኑ የተነሱ ሁሉ ብዙ ብለዋል::  ነገር ግን ገና አዳም ሲወድቅ ቃል እንደገባው ቃሉን ጠብቆ ተወለደ::  እየሱስ:- እኔ ግን አወቅሁህ ይላል::  ስለ ሐዋርያትም:-እነዚህም አንተ እንደ ላክኸኝ አወቁ ብሎ ይመሰክርላቸዋል:: የእግዚአብሔርን ዓላማ ማወቅ እንደምን መታደል ነው::  ዛሬም እኛ አወቅነው እራሱ ስለገለጠልን:: መስቀል ኃይላችን እንደሆነ ተገነዘብን::

እኔንም የወደድህባት ፍቅር በእነርሱ እንድትሆን ብሎ ከላይም ጸልዮታል::  እየሱስ በተወደደበት በዚህ ፍቅር ነው የተወደድነው:: 

እኔም በእነርሱ:- ቃሉን ተቀብለው አምነዋልና በእነርሱ ዘንድ መኖርን ጸለየ::  እኔና አብ በእርሱ ዘንድ መኖርያን እናደርጋለን እንዲሁም እራሴንም እገልጥለታለሁ እንደሚለው ቃል ማለት ነው:: 

ስምህን አስታወቅኋቸው አስታውቃቸውማለሁ። ይህንን ስም ዛሬም ያስታውቀናል ቀጣይነት ያለው ነው::  ይህ ስም የምንጠበቅበት ነው ከስም ሁሉ በላይ ነው::  ከላይም እንደጸለየው የሰጠኸኝን በስምህ ጠበኳቸው አለ::  አሁንም በስሙ እንጠበቃለን::  ከስም ሁሉ በላይ የሆነ ስም አለልን!  ይህ ስም ከነሙሉ ማዕረጉ እንድንጠቀምበት ተሰጥቶናል::  አሜን!

ጻድቅ አባት ሆይ ስምህ ይቀደስ! ስምህ ይባረክ!  ይህንን ስም ስለሰጠኸኝ እባርክሃለሁ::  ስምህን አስታውቀኝ አሁንም:: ከስም ሁሉ በላይ የሆነው ስምህ በጠላቶቼ ላይ ይገለጥ! 

አንተንም ማወቅ ስለተሰጠኝ አመሰግንሃለሁ::  መውደድህ ለዘላለም ነውና ክበርልኝ!

ዮሐንስ 18: 1-11

8፤ ኢየሱስ መልሶ፦ “እኔ ነኝ፡ አልኋችሁ፤ እንግዲህ እኔን ትፈልጉ እንደ ሆናችሁ እነዚህ ይሂዱ ተዉአቸው፡” አለ፤

9፤ ይህም፦ “ከእነዚህ ከሰጠኸኝ አንዱን ስንኳ አላጠፋሁም፡” ያለው ቃል ይፈጸም ዘንድ ነው።

እየሱስ ሊሸከሙት የሚችሉትን ሁሉ አስተምሮና ጸልዮ ሲያበቃ ተላልፎ ወደሚሰጥበት ስፍራ መጣ::  ይሁዳም አሳልፎ ሊሰጠው ሰራዊት ይዞ መጣ::  ጌታ እየሱስ ማንን ትፈልጋላችሁ ? ብሎ ጠየቃቸው እነርሱም “የናዝሬቱን ኢየሱስን፡” ብለው መለሱለት። ኢየሱስ፦ “እኔ ነኝ፡” አላቸው። እንግዲህ፦ “እኔ ነኝ፡” ባላቸው ጊዜ ወደ ኋላ አፈግፍገው በምድር ወደቁ። ሃሌሉያ!  እኔ እኔ ነኝ ማለት የሚችለው የእኛ ጌታ ብቻ ነው::  እኔ ነኝ በሚለው ማንነቱ ፊት ማን መቆም ይችላል?! እንግዲህ ምን ነካቸውና ወደፊት ሳይሆን እንደተገፉ ያህል ሁሉም ወደኃላ ወደቁ::  የሚያስተውል ቢኖር ይቅርብኝ ብሎ የሚያስተው ነበረ ግን አላስተዋሉም::  አልፋና ኦሜጋ የሆነውን ጌታ በቆመጥና በዱላ ሊይዙ መጡ::  አቤት ትህትና!!! ምን አይነት ጌታ ነው እንዴት ቢወደን ነው እንደዚህ የተዋረደው?!

ይህ ክብር ዛሬም ይሰራል እነ ዳንኤል እራሱም ዮሃንስ በራዕይ ላይ ወድቀዋል በክብሩ ፊት::  እነዚህ ግን ሳይጋበዙ ወደ ክብሩ የቀረቡ ናቸው::  ሊቋቋሙት የሚለው ባይመጥንም ግን በነሱ ቤት ሞክረዋል:: ጴጥሮስን፦ “ሰይፍህን ወደ ሰገባው ክተተው፤ አብ የሰጠኝን ጽዋ አልጠጣትምን?” አለው።

የጌታ”እኔ ነኝ” የሚለው ክብሩ ያልገባው ጴጥሮስ ግን እራሱን መከላከል የሚችለውን እየሱስን ለማስጣል ባለችው ሰይፍ ሊዋጋ ተነሳ::  ጌታ ስንት ሰይፍ አለን ብሎ ጠይቋቸው ሁለት ብለውት ነበረ:: አንዱ አገልግሎት ላይ ባይውልም ቅሉ አንዱን ግን ጴጥሮስ ተጠቀመበት::  ጴጥሮስ የገባውና ሲዘጋጅ የቆየው ለዚህ ነበረ እንጂ ጸልይ ሲባል ቢጸልይ የተሻለ ነገር ይሆን ነበረ:: የጌታ ስራ የሚሰራው በመንፈሱ ነው እንጂ በብርታታችን አይደለም::  እፊቱ ክብሩ እየተገለጠ ጴጥሮስ አላስተዋለም:: የጎዳውን ሰው ጆሮ ፈውሶ ጴጥሮስንም ገስጾ እራሱን ለኃጥያተኞች አሳልፎ ሰጠ ጊዜው ስለሆነ::

ጌታ የተያዘው አድፍጠው ስለጠበቁት ወይንም ብዙ ሆነው ስላልመጡ ሳይሆን በቃሉእንደሚለው የሚመጣውን ሁሉ አውቆ ማንን ትፈልጋላችሁ አላቸውና በፈቃዱ እራሱን ሰጠ::  ለአባቱም ቃል እንደገባው ከአንዱ በቀር ሁሉን ጠበኩ በስምህ እንዳለው እነዚህንተዋቸው ይሁዱ አለ::  እነርሱም ተበታተኑ::  በዚህ ውስጥ ሆኖ ስለእነርሱ ደህንነት ያሰበ ጌታ ዛሬም ስለእኔ ያስባል! የራሴን ጸጉር በቁጥር ያውቃል! ይጠብቀኛል!  ይጋርደኛል! ደግሞም ይዋጋልኛል!!!  አሜን!

አባት ሆይ እራስህን ስለእኔ አዋርደህ ስለሰጠህ ተመስገን::  ዛሬ ኃይልህና ጸጋህ በእኔ ይገለጥ::  በራሴ እንዳልደገፍ እርዳኝ! አንተ በስራ ላይ ነህ!

ዮሐንስ 18: 12-18

14፤ ቀያፋም፦ “አንድ ሰው ስለ ሕዝብ ይሞት ዘንድ ይሻላል፡” ብሎ ለአይሁድ የመከራቸው ነበረ።

በባለ ስልጣናቱ በኩል ስናየው የእየሱስ መያዝ:- እየሱስን መጀመርያ የወሰዱት ወደ ሐና ነበረ ምክንያቱም የሊቀ ካህናቱ አማት ስለነበረ::   ምን ስልጣን ኖሮት ነው ታድያ ወደ እርሱ የሚያመጡት?  እግዚአብሔር እንደደነገገላቸው እየኖሩ ይሆን?! ምናልባትም በአላዛር ከሞት መነሳት የተነሳ ብዙ አይሁድ በእርሱ ስላመኑ በዛም ምክንያት አለቆች እሱን ብቻ ሳይሆን አላዛርንም ለመግደል ተማከሩ ይላል::  ከተማከሩት አለቆች መካከል አንዱ ሳይሆን አይቀርም ፍሬህን እየው ለማለት::

በሐዋርያቱ በኩል ስናየው:- ሁለት ደቀ መዛሙርት ተከትለውታል ዮሃንስና ጴጥሮስ የተቀሩት ተበትነዋል::  ዮሃንስ ስለራሱ ሲጽፍ ሌላኛው እያለ ግን በደንብ የሆነውን ልክ እዛው እንደሆነ ነው የሚናገረው::  በሊቀ ካህናቱ ዘንድ ዮሃንስ ስለሚታወቅ ያለ ችግር ወደ ጊቢው ገባ ጴጥሮስ ግን በውጪ ስለነበረ ተመልሶ ወቶ ጥበቃ ላይ ለነበረችው ነግሮ አስገባው::  እርሷም የእርሱ ደቀ መዝሙር ነህ ስትለው እዛው በዛው ጴጥሮስ ካደ::  እርስዋው አስገብታው እያወቀች ካደ! አይ ጴጥሮስ! 

በጌታ በኩል ስናየው:- ከአንዱ  ወደ አንዱ ተቀባበሉት ዓላማችንን አሳካን እያሉ::ሊቀ ካህናቱ “አንድ ሰው ስለ ሕዝብ ይሞት ዘንድ ይሻላል፡”  ብሎ ትንቢትን መናገሩንም ያወቀ አይመስልም::  በእጃቸው በፈቃዱ የገባው ማን እንደሆነ ባወቁ::  አይ ሊቀ ካህናት ስለህዝቡ በማን ፊት የሚቆም መሰለው?!  ለእርሱም ነበረ የጌታ መምጣት! በፊቱ መጥቶ የሚቆመው የነገስታት ንጉስና የጌቶች ጌታ ዋና ሊቀ ካህን እየሱስ መሆኑን ባወቀ!!! ማን ነው በማን ፊት እየቆመ ያለው?!  ሊቀ ካህንነቱ ሊሻር በተሻለ ኪዳን ሊተካና ይህ ካህን ቅዱስ በሆነ ለራሱ መስዋአት ማቅረብ በማያስፈልገው ሊተካ ጊዜው መሆኑን ባወቀ:: ወይ ሰው አለማስተዋሉ?!!!  አቤት የእግዚአብሔር ፍቅር: ትግስትና ትህትና::  ጌታ አልዛተም አዳሜ በፊቴ ትቆሚያታለሽ አሳይሻለሁ አላለም አፉንም አልከፈተም በሸላቾቹ ፊት ዝም እንደሚል በግ ዝም አለ::  ወይ የኔ ጌታ!! 

በሰማያት ያለኸው ሊቀ ካህኔ እየሱስ እኔ ዛሬ አገንሃለሁ!!  ምስጋናዬንም በፊትህ አኖራለሁ ይህንን ሁሉ ያደረከው ለሰው ልጅ መዳንና  ለእኔም ነው::  ተመስገን ስለፍቅርህ ስለትግስትህ ስለትህትናህ!  ክበር!

ዮሐንስ 18: 19-24

20፤ ኢየሱስም መልሶ አለው፦ “እኔ በግልጥ ለዓለም ተናገርሁ፤ አይሁድ ሁሉ በሚሰበሰቡበት በምኵራብና በመቅደስ እኔ ሁልጊዜ አስተማርሁ፥ በስውርም ምንም አልተናገርሁም።

21፤ ስለምን ትጠይቀኛለህ? ለእነርሱ የተናገርሁትን የሰሙትን ጠይቅ፤ እነሆ፥ እነዚህ እኔ የነገርሁትን ያውቃሉ” አለው::

ሊቀ ካህናቱ ሐና ኢየሱስን ስለ ደቀ መዛሙርቱና ስለ ትምህርቱ ጠየቀው። መልሱም በግልጥ ሁሉም ባለበት አስተምሬአለሁ ወይም በግልጥ አስተምሬአለሁ ምንም በስውር  አልተናገርኩም  ስለምን ትጠይቀኛለህ? ለእነርሱ የተናገርሁትን የሰሙትን ጠይቅ፤ እነሆ፥ እነዚህ እኔ የነገርሁትን ያውቃሉ” አለው::  ምስክር ጥራ እንደ ህጉ እንጂ እንደዚሁ መፍረድ አትችልም እያለው ነው:: ደግሞም እኔ ያስተማርኩትን ከሌሎች ስማ አለው ህዝቡ ግን ስለሚፈርቸው ይህንና ያንን አስተምሯል እውነተኛ ነው ብሎ የሚል የለም::  ብዙዎች አመኑበት ቢልም ቅሉ ማንም ወደ ፊት መጥቶ አልተከራከረለትም::  ሐዋርያቱንም ጨምሮ::  ሰው ፊቱን ከእርሱ ማዞር ጀምሯል:: 

ከሎሌዎች አንዱ፦ “ለሊቀ ካህናቱ እንዲህ ትመልሳለህን?” ብሎ ኢየሱስን በጥፊ መታው።  ማነው ሊቀ ካህኑ እየሱስ ወይንም የሚሻረው ለጊዜው ያለው ሐና? ይህ ታላቅ ጌታ ግን መልሶ፦ “ክፉ ተናግሬ እንደ ሆንሁ ስለ ክፉ መስክር፤ መልካም ተናግሬ እንደ ሆንሁ ግን ሰለ ምን ትመታኛለህ?” አለው። ወደ ፊት በግርማው ፊት ሲቆም ምን ይል ይሆን?! እጁን ሲዘረጋ ወድቆ አለመሞቱ የሚያሳየው የጌታን ፍቅር: ትግስትና ርህሩህነት ነው:: 

አባት ሆይ ተመስገን ልጅህን እየሱስን ስለላክልን::  እየሱስ አንተ ሊቀ ካህን ነህ ለዘላለም! ይህንን ሁሉ መዋረድ ታግሰህ አለፍህ ይህ ሁሉ ስለ እኔ ነውና አመሰግንሃለሁ::  በሄድኩበት ሁሉ ታላቅነትህ ይታይ! ግነን!  አሜን

ዮሐንስ 18:25-32

27፤ ጴጥሮስም እንደ ገና ካደ፥ ወዲያውም ዶሮ ጮኸ።

28፤ ኢየሱስንም ከቀያፋ ወደ ገዡ ግቢ ወሰዱት፤ ማለዳም ነበረ፤ እነርሱም የፋሲካ በግ ይበሉ ዘንድ እንጂ እንዳይረክሱ ወደ ገዡ ግቢ አልገቡም።

ጴጥሮስ ርቆ አይርቅ እየሱስን ይዘው በመጡት ሰዎች መካከል እየተገኘ ከእርሱ ጋር ነበርክ ሲሉት ይክዳቸዋል::  ጌታም አስቀድሞ ነግሮት ነበርና ክህደቱን ቀጠለ ማንም በራሱ አይበረታምና::

በእየሱስ አንፃር ደግሞ ስናይ ከአንዱ ጊቢ ወደ ሌላው እየትወሰደ ነው::  በመጀመርያ ወደ ሐና ከዛም ወደ ቀያፋ አሁን ደግሞ ወደ ገዢው ወደ ጲላጦስ:,  በስተመጨረሻ ግን ወደ አባቱና ወደ አባታችን ደሙን እያንጠባጠበ ይገባና ስለእኛ ይታያል!

አንድ የገረመኝ ነገር በዚህ ክፍል ውስጥ:- እነርሱም የፋሲካ በግ ይበሉ ዘንድ እንጂ እንዳይረክሱ ወደ ገዡ ግቢ አልገቡም ይላል::  የፋሲካውን በግማ ይኸው  ለኃጥያተኞች አሳልፈው ሰጡት እነርሱ የሚያስቡት ምሳሌውን ለመዘከርና ለመብላት ነው ዋናው ግን በእጃቸው ነበረ::  ብዙ ትንቢት በብሉይ ኪዳን መጽሐፍት ሁሉ የተናገረለት እውነተኛው የእግዚአብሔር በግ በፊታቸው ነበረ ግን አላስተዋሉም?!  እርሱን እንደቀላል ነገር አሳልፈው ሰጡት::

ደግሞም ክሳቸው ሲገርም:- ይህስ ክፉ አድራጊ ባይሆን ወደ አንተ አሳልፈን ባልሰጠነውም ነበር፡” አሉት ለጲላጦስ::

ጲላጦስም፦ “እናንተ ወስዳችሁ እንደ ሕጋችሁ ፍረዱበት፡” አላቸው። አይሁድም፦ “ለእኛስ ማንንም ልንገድል አልተፈቀደልንም፡” አሉት፤ ምን?! እንዴ ታድያ እስጢፋኖስን ማን ገደለው?!  ሲፈልጉ ይገላሉ ሲፈልጉ ደግሞ አይገድሉም::  ነገሩ ግን እየሱስ በድንጋይ ተወግሮ መሞት ስለሌለበት ነው ይህ የሆነው::  በቃሉም እንደሚል ኢየሱስ በምን ዓይነት ሞት ሊሞት እንዳለው ሲያመለክት የተናገረው ቃል ይፈጸም ዘንድ ነው ይላል እሱም በመስቀል ላይ መሞት:: ስለእያንዳንዳችን እየሱስ ተላልፎ ተሰጠ::

አባት ሆይ ማንም አብሮት የሚቆም ሳይኖር እየሱስ ስለእኛ ተላልፎ ተሰጠ ምን እንላለን ተመስገን!!  ተመስገን!  ክብር  ምስጋና አምልኮ ለታረደው በግ ይሁን! 

ዮሐንስ 18: 32-40

36፤ ኢየሱስም መልሶ፦ “መንግሥቴ ከዚህ ዓለም አይደለችም፤ መንግሥቴስ ከዚህ ዓለም ብትሆን፥ ወደ አይሁድ እንዳልሰጥ ሎሌዎቼ ይዋጉልኝ ነበር፤ አሁን ግን መንግሥቴ ከዚህ አይደለችም፡” አለው።

ጲላጦስ ግራ ገብቶታል እናም  “የአይሁድ ንጉሥ አንተ ነህን?” ብሎ ጠየቀው ምክንያቱም የሚወጣው ክስ አይደለምና ይሄ ክስ::  ሌላ ንጉስ የሮም መንግስት በሚያስተዳድረው ስር መንገስ አይችልምና አይሁድንም ያስፈራቸው ይኸው ነው::  በእርግጥ ቅናትም ይኖራል ሁሉ እርሱን ተከተሉት እያሉ ነበረና ህዝቡም ሊያነግሱት ፈልገው ነበረ::  ስለዚህ ስለህዝቡ አንድ ሰው ቢጠፋ ይሻላል ብለው አሳልፈው ሰጡት::  ለጥያቄውም ኢየሱስ “አንተ ይህን የምትለው ከራስህ ነውን ወይስ ሌሎች ስለ እኔ ነገሩህን?” አለው። እኔ አይሁድ  አይደለሁ ነበረ መልሱ:: አሳልፈው ሰጡህ ብሎ ስልጣኑን ሊያሳየው ፈለገ::

ጲላጦስ በፊቱ የቆመውን አላወቀውም ለማወቅም የተስፋውን ቃል አያውቅም እሩቅ የሆነ አህዛብ ነው::  ከዚህ በፊት የነበረው ገዢ ግን ንጉስ እንደሚወለድ ከሰባ ሰገል አውቆ ህፃናትን አስፈጅቶ ነበረ ያንን ዘመን ቢያሰላና  ታሪክ ቢያገላብጥ ይደርስበት ይሆናል::  መልሱ ግን እኔ አይሁድ  አይደለሁ  ነበረ::  የሆነ ሆኖ ኢየሱስም መልሶ፦ “መንግሥቴ ከዚህ ዓለም አይደለችም፤ መንግሥቴስ ከዚህ ዓለም ብትሆን፥ ወደ አይሁድ እንዳልሰጥ ሎሌዎቼ ይዋጉልኝ ነበር፤ አሁን ግን መንግሥቴ ከዚህ አይደለችም፡” አለው።  ጴጥሮስ ሞክሮ ነበረ ግን ሎሌዎቼ የሚለው መልአክቱን ነበረ::  ለውጊያ የሚመጣበት ጊዜ አለ ዛሬ ግን በግ የመሆን ጊዜ ነው አንበሳ ሆኖ ሲመጣ ማን ይቆማል በፊቱ?  ይህች መንግስት ምን ልታደርግ እንደምትችል አለማወቁ እንጂ ፍርድን በእጅ በግድግዳ  ጽፎ በትል  ተመቶ  መሞትም አለ:: ሌላውንም በአምላኮቹ ፊት ሞተ ሰራዊቱም አለቀ::  ፈርኦንም ከነሰራዊቱ በባህር ሰጠመ::  ይህ ጌታ የሚለው መንግስት ከሁሉ በላይ ነው:: አሜን!  ለዚህ  መንግስት አምባሳደር አደረገኝ! 

መቼ ንግስና ፈለገ እየሱስ?  ሰይጣንም ስገድልኝና ይህንን ልስጥህ ብሎት ነበረ ነገር ግን እየሱስ ማንነቱንና የመጣበትን አላማ ያውቃል::  ከሙታን ሲያስነሳው በዚህ ዓለም ብቻ ሳይሆን በሚመጣውም ሁሉ ላይ ገዢና ጌታ ነው!! አሜን!

ጲላጦስ ማንን ልፍታ በዚህ ፋሲካ ቢላቸው በርባንን ብለው የመጀመርያው ወንበዴ ከሞት አመለጠ እኔም እርሱን የምመስል ወንበዴና ኃጥያተኛ ከሞት ወደ ህይወት መጣሁና እራሱን አልብሶኝ ጻድቅ ተብዬ ልጁም አድርጎኝ እመላለሳለሁ!  ለታረደው በግ ንግስናና ክብር ይሁን!  አሜን

አባት ሆይ ምን እላለሁ ስለወደድከኝ አመሰግንሃለሁ!

ዮሐንስ 19:1፤ በዚያን ጊዜም ጲላጦስ ኢየሱስን ይዞ ገረፈው።

እየሱስን ይዞ?!?!?! 

ማንም ሊቀርበው በማይችል ብርሃን ውስጥ የሚኖረውን ሰውን ከአፈር  ያበጀውን ጌታ ይዞ! የተያዘለት ግን ስለእኔ ነው!!  ስሜቴ ድብልቅልቅ ብሏል አንድ ልቤ ምናለ ቢያመልጥ ይላል በሌላው በኩል ደግሞ እኔ መያዝና ይህንን ሁሉ ቅጣት ስለኃጥያቴ መቀበል ሲገባኝ እርሱ ለወጠኝ  የሚለው ሃሳብ ይመጣብኛል::  መያዝ ብቻ አይደለም ገረፈው?!  ወይ ጉድ ምንም አላገኘሁበትም እያለ እንደገና በዚህ ክፉ በሆነ መግረፊያቸው ገረፉት ምናልባትም ጲላጦስ በህይወት ሊለቀው ያሰበ ይመስላል::  እየሱስ ግን ለዚህ መጣ!

ይህ ገረፈው የሚለው ሃሳብ ቀላል ይመስላል ነገር ግን በዚህ ግርፋት ጀርባው  ተተልትሏል እያንዳንዱ ግርፋት ሲያርፍበት ጀርባውን እየገሸለጠውና እያረሰው ነው የሚሄደው::  በመስቀል ላይ ወንበዴዎች ብዙ ጣር እንዳይዛቸው ያደርጋል እንዲሁም የሰሩትን ወንጀል ይናዘዛሉ እየሱስ ግን ምን አድርጏልና ይናዘዝ?  በሰውም በእግዚአብሔርም ፊት አንዳች አልተገኘበትም::  በግርፊያው እዚሁ አዳክመው ነው ወደ መስቀል የሚወስዷቸው::  ነገር ግን እየሱስ ስለስጋዬ ፈውስ እንደዚህ ዋጋ ከፈለ::  ከዚህ ቃል እውነት ጋር እስማማለሁ!!  በመገረፉ  ቁስል ተፈውሻለሁ!  እየሱስ እውነቴ እውነትም አርነት እንደሚያወጣ በዚህ እውነት አርነት ለስጋዬ ፈውስን አውጃለሁ!  አሜን!

አባት ሆይ ነፍሴን ብቻ ሳይሆን ይህንንም ስጋዬን ማደርያህን ከበሽታ ስለፈወስከው አመሰግንሃለሁ!!

ዮሐንስ 19:2-5

5፤ ኢየሱስም የእሾህ አክሊል ደፍቶ ቀይ ልብስም ለብሶ ወደ ውጭ ወጣ።

ጲላጦስ እጅ ከገባ ጀምሮ ያደረጉበት:-

1. ወታደሮችም ከእሾህ አክሊል ጐንጕነው በራሱ ላይ አኖሩ:- የእሾክ አክሊል ደፍተው ቢያሾፉም እርሱ የምስጋናን ዘውድ ደፍቷል: በከፍታም ከብሯል!  በራእይ 5:12፤ በታላቅም ድምፅ አሉ፦ “የታረደው በግ ኃይልና ባለ ጠግነት ጥበብም ብርታትም ክብርም ምስጋናም በረከትም ሊቀበል ይገባዋል። አሜን ይገባዋል!

2. ቀይ ልብስም አለበሱት፤ ይህ የዘመኑ የነገስታት አለባበስ ነው::  ለነገስታትም ንጉስ ነው ይህ ጌታ::

3.  አላገጡበት:- የአይሁድ ንጉሥ ሆይ፥ ሰላም ለአንተ ይሁን፡” እያሉ:- በእርግጥም እርሱ የነገስታት ንጉስና የይሁዳ አንበሳ ሁሉን ድል የነሳ ነው::  አልፋና ኦሜጋ!

በጥፊም ይመቱት ነበር:- የመቱትምና የወጉት ያዩታል ያኔ ዋይ ከማለት ውጪ ምን ይሉ ይሆን?! በራእይ 6:16፤ ተራራዎችንና ዓለቶችንም፦ “በላያችን ውደቁ፡ በዙፋንም ከተቀመጠው ፊት ከበጉም ቍጣ ሰውሩን::  ይህንን ነው የሚሉት::

ይህንን ሁሉ የሆነው በምን እዳው ነው? የሰው ልጅ ይህንን ሁሉ ለራሱ መክፈል ሲገባው እርሱ ጣልቃ ገባ:: ፍቅር ጎትቶ ከዙፋኑ አመጣው!!  ይህ ሁሉ ስለእኔ ነው! 

ከዚህ ሁሉ በኃላ ጲላጦስም ደግሞ ወደ ውጭ ወጥቶ፦ “እነሆ፥ አንዲት በደል ስንኳ እንዳላገኘሁበት ታውቁ ዘንድ እርሱን ወደ ውጭ አወጣላችኋለሁ፡” አላቸው። ድሮስ ምን ያገኝበት ኖሯል?!  ንጹህ በግ እራሱን በአባቱ ፊት መርምሮ ያቀረበ ሊቀ ካህን ነው:: ሊለቀው ስለፈለገና ህዝቡ እንዲራሩለት ፈልጎ ነበረ::  ለሮምም ሆነ ለመንግስቴ የሚያሰጋ አይደለም ነው ነጥቡ::  አላወክ ጉድህን ዝም ስላለ ናከው?  የሚያደርገውን የሚያውቅ ጌታ ነው:: ገና በፊቱ ትቆማለህ! 

አባት ሆይ ይህንን ሁሉ መንገላታትና መናቅ ስለ እኔ ተቀበልክ::  ምድርን በቃልህ ደግፈህ የያዝክ ጌታ አሾፉብህ ተዘባበቱብህ ገረፉህ በእሾህ  ራስህን አጠሩት::  አንተ ግን እኛን ነፃ ለማውጣት መጥህ::  ተመስገን ጌታ ሆይ! እገዛልሃለሁ!

ዮሐንስ 19: 6-11

11፤ ኢየሱስም መልሶ፦ “ከላይ ካልተሰጠህ በቀር በእኔ ላይ ምንም ሥልጣን ባልነበረህም፤ ስለዚህ ለአንተ አሳልፎ የሰጠኝ ኃጢአቱ የባሰ ነው፡” አለው።

ጲላጦስ ገርፎ ሲያበቃ እየሱስን ወደ ውጪ አውጥቶ እነሆ ሰውየው አላቸው::  ይራሩለት እንደሆነ ብሎ አስቦ ይመስላል ነገር ግን መልሳቸው ስቀለው ነበረ:: ጲላጦስም፦ “እኔስ አንዲት በደል ስንኳ አላገኘሁበትምና እናንተ ወስዳችሁ ስቀሉት፡” አላቸው።  አንዳች በደል በምድርም ህግ ፊት በአባቱም ፊት ያልተገኘበት ንጹ በግ!  አይሁድም መልሰው፦ “እኛ ሕግ አለን፥ እንደ ሕጋችንም ሊሞት ይገባዋል፥ ራሱን የእግዚአብሔር ልጅ አድርጎአልና፡” አሉት።

አሁን ዋናው ክስ ታወቀ ስለዚህ ጲላጦስ ይህን ነገር በሰማ ጊዜ እጅግ ፈራ፤ የከሰሱት ንጉስ ልሁን ስላለ ሳይሆን ራሱን የእግዚአብሔር ልጅ አድርጎአልና ነው::  ይሄ ታድያ ከሮም ስርአት ጋር ምን አገናኘው?!  የህጋቸውና የኃይማኖታቸው ጉዳይ ነበረ::  ዮሃንስ እዛው ስለነበረ እያንዳንዱን ነገር ዘገበው:: ግራ የተጋባው የሚስቱንም ህልም ያስታወሰው ጲላጦስም “አንተ ከወዴት ነህ?” አለው። ኢየሱስ ግን አንድ እንኳ አልመለሰለትም። ከዚህ በፊት መንግስቴ ከዚህ ምድር አይደለችም እንጂ ሎሌዎቼ ይዋጉልኝ ነበር ብሎ ነግሮት የለም እንዴ ለምን ደግሞ ይጠይቀዋል?!

ስለዚህ ጲላጦስ፦ “አትነግረኝምን? ልሰቅልህ ሥልጣን እንዳለኝ ወይም ልፈታህ ሥልጣን እንዳለኝ አታውቅምን?” አለው። ስልጣን? የምን ስልጣን? እየሱስ ነው እራሱን አሳልፎ በፈቃዱ የሰጠው እና የምን ስልጣን ነው ጲላጦስ የሚያወራው::  እየሱስ እንደሌሎቹ እስረኞች ለነፍሱ አለመነም ስልጣኑንም ፈርቶ አላጎበደደም ያደረገውም ዝምታን መረጠ::  ስልጣንማ ካለህ ፍታዋ ያለ ጥፋቱ እየተፈረደበት ያለውን እያየ ነገር ግን አልቻለም::  ታድያ ምን የሚሉት ስልጣን ነው ይሄ?!  ጌታዬም ስልጣኑን ለማንም የማይሰጥ ጌታ ፦ “ከላይ ካልተሰጠህ በቀር በእኔ ላይ ምንም ሥልጣን ባልነበረህም፤ ስለዚህ ለአንተ አሳልፎ የሰጠኝ ኃጢአቱ የባሰ ነው፡” አለው።

ማንም በእርሱ ላይ ስልጣን የለውም ስልጣን ሁሉ የጌታዬ ነው::  ዛሬም ስልጣን በሚሆነው ሁሉ የጌታ ነው::

አባት ሆይ ተመስገን ስልጣን ሁሉ የአንተ ነው::  ስለተገደድህ መውጫ ስለሌለህ ሳይሆን ወደህ እራስህን አሳልፈህ ሰጠህ ምህረት ይደረግልኝ ንፁ ነኝም አላልክም::  በሸላቾችህ ፊት ዝም አልክ ስለእኔ! ምን እላለሁ ተባረክ!

ዮሐንስ 19: 12-15

15፤ እነርሱ ግን፦ “አስወግደው፥ አስወግደው፥ ስቀለው፡” እያሉ ጮኹ። ጲላጦስም፦ “ንጉሣችሁን ልስቀለውን?” አላቸው። የካህናት አለቆችም፦ “ከቄሣር በቀር ሌላ ንጉሥ የለንም፡” ብለው መለሱለት።

ከዚህ በኋላ ጲላጦስ ሊፈታው ፈለገ፤ ነገር ግን አይሁድ፦ “ይህንስ ብትፈታው የቄሣር ወዳጅ አይደለህም፤ ራሱን ንጉሥ የሚያደርግ ሁሉ የቄሣር ተቃዋሚ ነው፡” አስወግደው፥ አስወግደው፥ ስቀለው፡” እያሉ ጮኹ። አቤት አለማወቅ! 

ጲላጦስም በፍርድ ወንበር ተቀመጠ::  ፈራጅ ሆነ በፈጠረው ላይ:: ምንም እንኳን ሊፈታው ቢፈልግም የካህናት አለቆችም፦ “ከቄሣር በቀር ሌላ ንጉሥ የለንም፡”  ስቀለው አሉት::  

ከዚህ በፊት ንጉስን አንግስልን ብለው ሲጠይቁ እግዚአብሔር እኔን ነው የናቁት አንግስላቸው ብሎ ነበረ:: አሁን ደግሞ የሮም ንጉስ ንጉሳችን ነው ማለታቸው የመጎብኛ ጊዜአቸውን አላወቁምና ከዓመታት በኃላ እየሩሳሌም ፈራረሰች::  የፈሩትም ደረሰ አንድ ሰው ስለህዝቡ ቢሞት ይሻላል ከምንበተን ነበረ ምክሩ ግን አልቀረላቸውም እስከ ዛሬ በየአገሩ ተበትነዋል::  እውነት ያንን ቀን ከትውልዱ መካከል ማን አስተዋለ?! አጋጣሚ ወይም እንደማንኛውም ቀን ነው የሚመስለው:: ይህ ጌታ ለእነርሱ መጥቶ ሳለ አለማወቅና አሳልፈው መስጠት?!  

በመንፈሳዊው ዓለም ዛሬስ ምን እየተካሄደ ነው?  አንተ የምትተኛ ንቃ ነው የሚለውን ቃሉ::  በትራንፕ ዙሪያ የተሰበሰቡት የቴክኖሎጂ ሰዎች ምን ይሆን ግባቸው እግዚአብሔር የሰጠንን መብት ሁሉ መቀማትና ለሃሰተኛው ክርስቶስ ማዘጋጀት? ምን እየተሰራ ይሆን አፍንጫችን ስር?  እኛ ግን የተሰቀለውን ክርስቶስን እንሰብካለን አገራችንም በሰማይ ነው:: አያረጅብንም ንጉሳችን ነው ይመጣልናል:: ማራናታ!

አባት ሆይ ቶሎ ና!  አሜን!

ዮሐንስ 19:16፤ ስለዚህ በዚያን ጊዜ እንዲሰቀል አሳልፎ ሰጣቸው።

በምዕራፉ መጀመርያ በመግረፍ የጀመረውን እንዲሰቅሉት አሳልፎ በመስጠት ፍርዱን አጠናቀቀ::  ጲላጦስ ያላወቀው ነገር ግን ይህ እፁብ ድንቅ ቅዱስና መልካም ጌታ እራሱን ባለመከልከል መስጠቱን ነው:: እንዲህ ባይሆንማ ማን ወንድ ይይዘው ነበረ?  ሊይዙት ሲመጡ እኔ ነኝ ሲላቸው ሁሉም ወደኃላቸው ወደቁ:: መንግስቴ ከዚህ አይደለችም እንጂ ሎሌዎቼ ይዋጉልኝ ነበረ እንዳለው ነው:: አንድ መልአክ ለስንቱ ይበቃ ነበረ ነገር ግን ይህንን ሁሉ ማድረግና ማቆም እየቻለ አላደረገውም ስለዚህም እራሱን በፈቃዱ አሳልፎ ሰጠ! 

የሮም ሰራዊት ወይም ጲላጦስ  ወይንም ደግሞ ቄሳር ይህ እንዲሆን ስልጣን የላቸውም:: ጌታ ኢየሱስም እንዳለው፦ “ከላይ ካልተሰጠህ በቀር በእኔ ላይ ምንም ሥልጣን ባልነበረህም”  ነው ያለው። በፈቃዱ እራሱን ሰጠ በፈቃዱ ነፍሱንም ሰጠ!  ማንም አላስገደደውም ፈልጎና አውቆ ስለእኛ ይህንን አደረገ::  እዳችንን በሙሉ ከፈለ በእኛ ላይየቀረ የሚወራረድ እዳ የለም::  በክርስቶስ ላሉት አሁን ኩነኔ የለባቸውም:.  አሜን!!!

አባት ሆይ እራስህን ስለሰጠኸን እናመሰግንሃለን!!  ተባረክ በመስቀል ምጥ ልጅህ ስላደረከኝ ተመስገን:: ተባረክ!  አሜን

ዮሐንስ 19: 17-27

18፤ በዚያም ሰቀሉት፥ ከእርሱም ጋር ሌሎች ሁለት፥ አንዱን በዚህ አንዱን በዚያ ኢየሱስንም በመካከላቸው ሰቀሉ።

እራሱን በመስቀል ላይ አሳልፎ ሰጠን!

ይህንን ዝማሬ ያስታውሰኛል:-

ጐልጐታ ፡ ትመስክር ፡ ቀራንዮ ፡ ትናገር

የጌታ ፡ ጣሩን ፡ የአኳሃኑን ፡ ነገር

ከዚህስ ፡ የሚበልጥ ፡ ፍቅር ፡ የለም

ከኢየሱስ ፡ የሚበልጥ ፡ ፍቅር ፡ የለም

ከአምላኬ ፡ የሚበልጥ ፡ ፍቅር ፡ የለም

ከጌታ ፡ የሚበልጥ ፡ ፍቅር ፡ የለም

ነፍሱን ፡ ስለእኔ ፡ የሚያሰጥ ፡ መውደድ

መስቀል ፡ አሸክሞ ፡ አስጐንብሶ ፡ የሚያስኬድ

የጌታዬን ፡ ፍቅር ፡ ምን ፡ ይመጥነዋል

ከምንም ፡ ከምንም ፡ ከምንም ፡ ይበልጣል::

አሜን!

በዚህ ክፍል ላይ የተፈጸሙ ትንቢቶች:-

በኢሳይያስ 53:12፤  . . .  ከዓመፀኞችም ጋር ተቈጥሮአልና – ፃድቁ ጌታ እንደዚህ ተቆጠረ ስለእኔ! ወይ ፍቅር!

በ መዝሙር 22:18፤ ልብሶቼን ለራሳቸው ተከፋፈሉ፥ በቀሚሴም ላይ ዕጣ ተጣጣሉ።

እየሱስ ለዮሐንስ እናቱን አደራ ሰጠ::  እስከመጨረሻ ከእርሱ ጋር መዝለቅ የቻለ አንድ ደቀ መዝሙር እርሱ ብቻ ነው::  በዛ ስፍራ የተገኙት ሌሎቹ እናቱና ሴቶች ነበሩ:: ምን አይነት ታማኝነት ነው ያለው ዮሃንስ ሁሉ ጥለው ሲሸሹ እርሱ ግን አብሮት ዘለቀ::  ከዚህ በኋላ ደቀ መዝሙሩን፦ “እናትህ እነኋት፡” አለው። ከዚህም ሰዓት ጀምሮ ደቀ መዝሙሩ ወደ ቤቱ ወሰዳት። ታማኝ መሆን! ጌታ ፀጋውን ያብዛልን በመንፈስ እንጂ በብርታት ታማኝ መሆን አይቻልምና:: 

ጲላጦስም ደግሞ ጽሕፈት ጽፎ በመስቀሉ ላይ አኖረው፤ ጽሕፈቱም፦ “የአይሁድ ንጉሥ የናዝሬቱ ኢየሱስ፡” የሚል ነበረ። አይሁድም ይህንን ሲቃወሙ ጲላጦስም፦ “የጻፍሁትን ጽፌአለሁ፡” ብሎ መለሰ። እርሱ የአይሁድ ንጉስ ብቻ ሳይሆን የጲላጦስም የአይሁድ አለቆችም ሊሰቅሉት የተሰበሰቡትም ሁሉ እንዲሁም የዓለም ሁሉ ንጉስ ነው::  

ጻድቅ አባት ሆይ ተመስገን በምን አይነት ፍቅር ወደድከን? እራስህን ስለኃጥያታችን ስለሰጠህና ለመስቀል ሞት ስለታዘዝክ እናመሰግናለን:: እኛም እንደዮሃንስ ታማኝ እንድንሆን  ጸጋህን ስጠን በመንፈስ ቅዱስም አበርታን!  አሜን

ዮሐንስ 19: 28-30

28፤ ከዚህ በኋላ ኢየሱስ አሁን ሁሉ እንደተፈጸመ አውቆ፡ የመጽሐፉ ቃል ይፈጸም ዘንድ፦ “ተጠማሁ፡” አለ።

30፤ ኢየሱስም ሆምጣጤውን ከተቀበለ በኋላ፦ “ተፈጸመ፡” አለ፥ ራሱንም አዘንብሎ ነፍሱን አሳልፎ ሰጠ።

የጌታ የእየሱስ የመጨረሻው ሰዓታት ስቃይ የበዛበት ዮሃንስ ባይዘግበውም አባት ሆይ ለምን ተውከኝ እያለ የለመነበት ነበር::  ከዚህም በኃላ ተጠማሁ አለ አንዳንዶች ተወው ኤልያስ መቶ ይርዳው እያሉ አፌዙበት አንድ ሰው ግን ቆምጣጤን ሰጠው::  ኢየሱስም ሆምጣጤውን ከተቀበለ በኋላ፦ “ተፈጸመ፡” አለ፥ ራሱንም አዘንብሎ ነፍሱን አሳልፎ ሰጠ::  

ተፈጸመ ሲል ህመምን በኃጥያት መከሰስን ከእግዚአብሔር ጋር የነበረው ጠብ መነሳቱን የብሉይ ኪዳን የህግ ዘመን ማለፉንና አዲስ ኪዳን የፀጋ ዘመን መሆኑን ሁሉ ያወጀ ነው:: በትንቢት የተፃፈውን ሁሉፈጸመው:: በምድርም አባቱን አከበረና ታዘዘ ለእኛም ማምለጫ መንገድ ሆነልን!  አቤትእንዴት ያለ ፍቅር ነው ይሄ!!!  እራሱን በፈቃዱ ሰጠ!  ሌሎች እንደዘገቡት ፀሃይ ብርሃንዋን ከለከለች የቤተክርስቲያን መጋረጃም ከላይ ወደታች ተቀደደ ቅድስተ ቅዱሳን በምድር የለም በሰማይ እንጂ ወደ እዛም እየሱስ አንድ ጊዜ ደሙን እያንጠባጠበ ገባ::  በእየሱስ ማለትም በስጋው በኩል እኛም ገብተናል ወደ አብ!  ሃሌሉያ!!

አባት ሆይ በክርስቶስ ያለነው ኩነኔ የለብንም እየሱስ ስለእኛ እራሱን ሰቷልና!  ተመስገን አባት ሆይ ወደ አንተ መቅረብ ችለናልና በፊትህም ካህንነት ለማጠን ተሰቶናልና ተባረክ! ምስጋንና አምልኮን ወደፊትህ አመጣለሁ!

ዮሐንስ 19: 31-42

33፤ ወደ ኢየሱስ በመጡ ጊዜ ግን እርሱ ፈጽሞ እንደ ሞተ አይተው ጭኑን አልሰበሩም፤

ዮሐንስ 19:34፤ ነገር ግን ከጭፍሮች አንዱ ጎኑን በጦር ወጋው፤ ወዲያውም ደምና ውኃ ወጣ።

አይሁድም የማዘጋጀት ቀን ስለ ሆነ ያ ሰንበት ትልቅ ነበረና ሥጋቸው በሰንበት በመስቀል ላይ እንዳይኖር፥ ጭናቸውን ሰብረው እንዲያወርዱአቸው ጲላጦስን ለመኑት። ለምን ይሆን ይህ ሰንበት ትልቅ የሆነው?  ከግብጽ የጥፋት ልጅ እንዳያገኛቸው ያመለጡበት ስለነበረም አይደል? የበጉን ደም በበራቸው ስላደረጉ የግብፅ በኩር ሁሉ ሲሞት በእስራኤሎች ዘንድ ግን ሞት ተከለከለ::  ይህ በብሉይ ጥላ የነበረው አሁን በፊታቸው ፋሲካቸው እየሱስ እየፈፀመው መሆኑን  አላስተዋሉም::  ሞታቸውን የሚሞተው የእግዚአብሔር በግ አላወቁትም!  ከጌታ ጋር የተሰቀሉትን ጭን ሲሰብሩ በትንቢት እንደተነገረው የእርሱን ግን አልሰበሩም ምክንያቱም እርሱ በፈቃዱ ነፍሱን ሰቶ ስለነበረ ሞቶ ነው ያገኙት::  እነሱ ቢገድሉትማ በፈቃዱ አልሰጠም ነበረ ነገር ግን ያለ ማንም ተጽዕኖ እርሱ ነፍሱን ሰጠ!

የወጉት ሁሉ ያዩታል የሚለው ወደፊት የሚፈፅም ሲሆን እስከአሁን ከቃሉ አንዳች ስላልጎደለ በእርግጥ ይህ ከጭፍሮች አንዱ ጎኑን በጦር የወጋው ጌታን ያያል:: ሲወጋው የወጣው  ደምና ውኃ ነበረ ከተለመደው ደንብ እግርን ከመስበር መሞቱን ለማረጋገጥ አድርጎትም ይሆናል::  

ሌላው በስተመጨረሻ የተገኙትና ስጋውን ያሳረፉት በድብቅ ደቀመዝሙር  የነበረው የአርማትያሱ ዮሴፍና በለሊት የመጣው ኒቆዲሞስ ነበሩ::  ዮሴፍ የእየሱስን ስጋ አስፈቀደ ኒቆዲሞስ ደግሞ ከርቤና የእሬት ቅልቅል ይዞ መጣና በወጋቸው ገነዙትና ማንም ባልተቀበረበት አዲስ መቃብር ውስጥ አኖሩት::  መቃብሩ ከባለፀጎች ጋር መቃብሩ ሆነ እንደሚለው ትንቢት መሰረት ሆነ::

አባት ሆይ አመሰግንሃለሁ! ይህንን እውነት እንድገነዘብና በእየሱስ ሞት መዳኔን እንዳውቅ ስለረዳኸኝ ተመስገን!  የእግዚአብሔር በግ እየሱስ ስለእኔና ስለሰውልጅ ሁሉ እንደዚህ ዋጋ ከፍለሃልና ተመስገን!  ሃሌሉያ!

ዮሐንስ 20:1፤ ከሳምንቱም በፊተኛው ቀን መግደላዊት ማርያም ገና ጨለማ ሳለ ማለዳ ወደ መቃብር መጣች ድንጋዩም ከመቃብሩ ተፈንቅሎ አየች።

ገና ጨለማ ሳለ በማለዳ መቅደላዊት ማርያም ፍለጋ መጣች ቢለንም ዮሃንስ በሌሎቹ ወንጌሎች ግን ሌሎች እህቶችም ነበሩ::  ምናልባት እዛ እንገናኝ በማለዳ ተባብለው እርስዋ ቀድማ መጥታ ይሆን?  የእነዚህ ሴቶች ትጋትና ፍቅር ምን አይነት ነው?  ከተያዘ ጀምሮ በኃዘን ነበረ የከረሙት በእውነትም የሚፈልጉት ያለ ህግ በግፍ መገደሉን የሚያውቁ እህቶች::  ፍቅራቸውን ሊገልጹ መጡ የከበረ ነገር ለማብሰር ፊተኞች ሆኑ::  ዮሴፍና ኒቆዲሞስ ካቆሙበት አገልግሎታቸውን ቀጠሉ:: እርሱም ማብሰር!  

በደረሰችበት ሰዓት ብዙ ነገር ተፈጽሟል ያ ሁሉ ጣርና ጭንቅ የከሳሾቹም ማሽሟጠጥና ማሰቃየት አልፎ እየሱስ መቃብሩን ፈነቃቅሎ ተነስቷል!!!  እነርሱም መተው ድንጋዮን እንዲያንከባልሉለት አልጠበቀምም አላስፈለገውምም!!!  ድንጋዮን ፈነቃቅሎ ተነሳ ሞት እንደለመደው ሁሉን ገቢ አድርጎ እንደሚይዘው ሊይዘው አልቻለም::   የእግዚአብሔርም የብርታቱ ጉልበት የታየበት ትንሳኤ ሆነ!  ሞትና ሲኦል መውጊያቸውን ተነጠቁ:: እርሱ ሲነሳ እኛም አብረን ተነሳን::  ሃሌሉያ! 

አባት ሆይ ተመስገን ስለ ትንሳኤው ኃይል የሞትን ጣር አጥፍተህ ኢየሱስን አስነሳኸው!  ይህ የትንሳኤው ኃይል በእኔ ላይ ይምጣና እየሱስን ያሳይ! አሜን! በእኔም ውስጥ ትጋትን ጨምርልኝ!  አሜን

ዮሐንስ 20:2፤ እየሮጠችም ወደ ስምዖን ጴጥሮስና ኢየሱስ ይወደው ወደ ነበረው ወደ ሌላው ደቀ መዝሙር መጥታ፦ “ጌታን ከመቃብር ወስደውታል ወዴትም እንዳኖሩት አናውቅም፡” አለቻቸው።

ኢየሱስ ሞትን አሸንፎ ትንሳኤ ሆንዋል ተከታዮቹ ግን አላወቁም የተናገራቸውንም ቃል አላስተዋሉም::  ስንት ጊዜ ነበር እንደሚነሳ የነገራቸው? ማርያም ከእግሩ ስር የማትነሳ የተሻለውን መረጠች የተባለች ሆና ሳለ ስለትንሳኤው ረሰታ ፦ “ጌታን ከመቃብር ወስደውታል ወዴትም እንዳኖሩት አናውቅም፡” ብላ ለጴጥሮስና ዮሃንስ ነገረቻቸው::  እነሱም እዛው ጋር አለቀንዋትም:- እነሳለሁ ብሏል አታስታውሺም ማለት ነበረባቸው::  እነሱም ለዜናው እንግዳ ሆነው ወደ መቃብር ስፍራ ሮጡ::  ህያውን ከሙታን መካከል ሊፈልጉ::

የማርያም ነገር አይግረመን ብዙዎቻችን በዚህ ውስጥ እየዳከርን እንገኛለን::  ዛሬም ማስተዋል ይሁንልን ጌታ የሚናገረውን እናስተውል እንጂ ሰምተን የምንረሳ አንሁን::  ምን ተስፋ ሰቶናል? ከተናገረ ይፈጽማል እርሱ በጊዜ አይወሰንም ዘገየ ብለንም መስጋት የለብንም መታመን ብቻ ነው ያለብን::  እርሱን ለሚወዱት እንደ አሳቡም  ለተጠሩት ነገርሁሉ ለበጎ ይደረጋልና::

ጻድቅ አባት ሆይ ክብር ለአንተ ይሁን ዛሬም በስራ ላይ ነህ::  በመንፈስ ቅዱስ ማስተዋልን ስጠኝ::  አንተ ስትናገር የሚሰማና የሚያደምጥ ጆሮ የሚያስተውል ልብን ስጠኝ! ቃልህ ከእኔ ጋር በእምነት ይዋሃድና ይጥቀመኝ::  አሜን! 

ዮሐንስ 20: 3-10

3፤ ስለዚህ ጴጥሮስና ሌላው ደቀ መዝሙር ወጥተው ወደ መቃብሩ ሄዱ።

9፤ ከሙታን ይነሣ ዘንድ እንዲገባው የሚለውን የመጽሐፉን ቃል ገና አላወቁም ነበርና።

ጴጥሮስና ዮሃንስ “ጌታን ከመቃብር ወስደውታል ወዴትም እንዳኖሩት አናውቅም፡”  የሚለውን ዜና ከማርያም ሲሰሙ ወደ መቃብሩ ሮጡ::  በዓይናችን ሳናይ ያልሽውን አናምንም የሚሉ ይመስላል::  ደርሰውም በመቃብር አለመኖሩን አረጋገጡ ::  የተከፈነበትም ጨርቅና በጭንቅላቱም ተጠምጥሞ የነበረው ጨርቅ ተቀምጠው አገኙ::  ግን ሰው ቢወስደው መገነዙን ለምን ይፈታል ብለው እንኳን አላሰቡም:: የማርያምን ዜና  ካረጋገጡና ካመኑ በኃላ ግን ወደ ቤታቸው ነው የሄዱት::  እየፈረድኩኝ አይደለም እራሴን በነሱ ውስጥ እያየሁኝ ነው:: የመንፈስ ነገር በመንፈስ ነው የሚገባው::

ከሙታን ይነሣ ዘንድ እንዲገባው የሚለውን የመጽሐፉን ቃል ገና አላወቁም ነበርና ይላል ቃሉ:: እነርሱ ከሙታን መካከል እየፈለጉት ነው እርሱ ግን የኤማኦስን መንገደኞች እየመለሰ ሁሉንም እያገደ ያለ ከሞት የተነሳ እረኛ ነበረ::  ሁሉንም ወደ ቀጠሮ ቦታ እየጠራ ያለ ታጋሽ ጌታ::  ይህንን ሁሉ ጊዜ አስተምሬያቸው የታሉ? በአንድ ቦታ ተሰብስበው እንኳን መጠበቅ አቃታቸው እኔ ይህንን ሁሉ አድርጌ?! አላለም::  መጽሐፍትን ገለጠላቸው እንጂ!  ታግሶ ሰበሰባቸው! ዋዉ! ሲያገኛቸውም ሰላም ለእናንተ! ነበረ ያላቸው እንጂ ወደ መወቃቀስም አልሄደም::

እራሱ እየሱስ እየተገለጠ መነሳቱን ያበስራቸው ጀመረ::  መንፈስ ቅዱስ ስላልወረደ የጠለቀውን የእግዚአብሔርን መንግስት መረዳት አልቻሉም ምንም እንኳን ሶስት ዓመት ተኩል ከእርሱ ጋር ሲመላለሱ የቆዮና የተማሩ ቢሆንም አላስተዋሉም ይላል::  ዛሬም መንፈስ ቅዱስ ወደ እውነት ሁሉ ይመራናል ቃሉንም ይተረትርና ማስተዋልን ይሰጠናል::  

አባት ሆይ ተመስገን!  ስምህ ይባረክ! አንተ ታጋሽና ርሁሩህ ጌታ ነህ::  የምትለውን የምንረዳበትን ጸጋ ስጠን::  መንፈስ ቅዱስ የምትናገረውን ማስተዋል ይሁንልን በራሳችን እንዳንመካና የአንተን ነገር ችላ እንዳንል እርዳን! 

ዮሐንስ 20: 11-16

11፤ ማርያም ግን እያለቀሰች ከመቃብሩ በስተ ውጭ ቆማ ነበር። ስታለቅስም ወደ መቃብር ዝቅ ብላ ተመለከተች፤

ደቀ መዛሙርቱ ወደ ቤታቸው ሲሄዱ ማርያም ግን እዛው እያለቀሰች ቆየች:: ያስተማራቸውን ቃሉን ባይዘነጉ እዚህ ሁሉ ውስጥ ባልገቡ ነገር ግን የእውነት መንፈስ ሲመጣ ሁሉን ማስተዋል ቻሉ::  ሐዋርያቱን የጠራቻቸው መጀመርያውንም እንዲረድዋት ነበር እነርሱ ግን ወደቤታቸው ሲሄዱ መልስ ሳላገኝ አልሄድም ብላ እዛው ቆይታ መልስን አገኘች::  ምን አይነት ፍቅር ነው?!  በዚህም  መሃል ወደ መቃብር ዝቅ ብላ ተመለከተች፤ ሁለት መላእክትም ነጭ ልብስ ለብሰው የኢየሱስ ሥጋ ተኝቶበት በነበረው አንዱ በራስጌ ሌላውም በእግርጌ ተቀምጠው አየች። እነዚህ መልአክት መቼም መቃብሩን እየጠበቁ አይደለም ባዶ ነው ምኑን ይጠብቁታል?  ለእርስዋ መልክት ይዘው ነበረና “አንቺ ሴት፥ ስለ ምን ታለቅሻለሽ?” አሉአት። እርስዋም፦ “ጌታዬን ወስደውታል ወዴትም እንዳኖሩት አላውቅም፡” አለቻቸው።  መልአክት መሆናቸውን እንኳን አልደነቃትም ወይም አላስተዋለችም የምትፈልገው ጌታዋን ብቻ ነው::  እርስዋ በኃዘንዋ ውስጥ ናት በራስዋ ነገር ተይዛለች::  በተለያየ ነገር ተይዘን ጌታን ሳንሰማው እንዳንቀር ጌታ ይርዳን::

ነገር ግን ይህንም ብላ ወደ ኋላ ዘወር ስትል ኢየሱስን ቆሞ አየችው፤ ኢየሱስም እንደ ሆነ አላወቀችም። እስዋ ብቻ ሳትሆን የኤማኦስም መንገደኞች አብሯቸው ተጉዞም አላወቁትም::  የኃዘንዋን ጥልቀት ያየው ጌታ መልአክቱ የጠየቁትን መልሶ ጠየቃት “አንቺ ሴት፥ ስለ ምን ታለቅሻለሽ? ማንንስ ትፈልጊያለሽ?” አላት። እርስዋም የአትክልት ጠባቂ መስሎአት፦ “ጌታ ሆይ፥ አንተ ወስደኸው እንደ ሆንህ ወዴት እንዳኖርኸው ንገረኝ እኔም እወስደዋለሁ፡” አለችው። አቤት?!የምትገርም ሴት ናት ስጋውን ስጡኝ ለኔ የከበረ ነው የት ወሰዳችሁት?  እያለች የፍቅርዋን ትወተውታለች የጥያቄዋ መልስ ስጋውን የምትጠይቀው እራሱ እየሱስ በፊትዋ ቆሟል:: መልሳችን በፊታችን እንዳይሆን ብቻ የእኛ ሃሳብ በብዙ ተይዞ እንዳንሸዋወድ::

ወድያውም ኢየሱስ፦ “ማርያም፡” አላት። እርስዋ ዘወር ብላ በዕብራይስጥ፦ “ረቡኒ፡” አለችው፤ ትርጓሜውም፦ “መምህር ሆይ፡” ማለት ነው። ያን ጊዜ አወቀችው!  ጌታ ማስተዋል ይስጠን::  የእግዚአብሔር ነገር በመንፈስ ነው:: ይህ መልካም ጌታ ካለችበት ሊያወጣት እርስዋን ጠበቀ::  ይገርማል!  በስማችን የሚያውቀን እረኛ አይፈርድብንም ባለንበት ይገናኘናል::

አባት ሆይ አንተ መልካም ነህ መንፈሳዊዉን ነገር በስጋ ለመረዳት እንዳንሞክር  እርዳን::  ማስተዋልንም ስጠን:: መንፈስ ቅዱስ በአንተ ላይ መደገፍ ይብዛልን::  አሜን

ዮሐንስ 20: 17-18

17፤ ኢየሱስም፦ “ገና ወደ አባቴ አላረግሁምና አትንኪኝ፤ ነገር ግን ወደ ወንድሞቼ ሄደሽ፦ እኔ ወደ አባቴና ወደ አባታችሁ ወደ አምላኬና ወደ አምላካችሁ ዓርጋለሁ፡ ብለሽ ንገሪአቸው፡” አላት።

ሐዋርያቱ ቢሄዱም ማርያም እዛው ቆይታ መልስዋን አገኘች::  በዮሐንስ 11:25፤ ኢየሱስም አላት፦ “ትንሣኤና ሕይወት እኔ ነኝ፤ የሚያምንብኝ ቢሞት እንኳ ሕያው ይሆናል ብሏት አምና የሞተው ወንድሟ ተነስቷል::  ይሄንና እነሳለሁ ያለውን  ቃል ብታስተውል ኖሮ እንደዚህ በኃዘን ውስጥ አትሆንም ደግሞም እርሱ በሌለበት ስፍራ ከሙታን መካከል ትንሳኤና ህይወት የሆነውን አትፈልግም ነበር::  የሚለንን ዛሬም በመንፈስ ቅዱስ ኃይል ማስተዋል ይሁንልን ቃሉም በእምነት ከእኛ ጋር ተዋህዶ ይጥቀመን::

የአትክልት ጠባቂ የመሰላት እየሱስ ግን ስምዋን ሲጠራ ነቃችና ረቡኒ አለችው::  እርሱም ገና ወደ አባቴ አላረግሁምና አትንኪኝ አላት::  ምናልባትም ገና እንደተነሳ ነው የደረሰችው ስለዚህም አትንኪኝ አላት::  በአብ ፊት ደሙን እያንጠባጠበ የታረደው በግ ሊገባና ስለ እኛ ሊታይ ይገባዋል::  ወድያውም ተመልሶ ሐዋርያቱን መሰብሰብ ይጀምራል ገና አብሯቸው  አርባ ቀን ይቆይ የለ::  

ለማርያምም:- “ወደ ወንድሞቼ ሄደሽ” ተብላ የትንሳኤው አብሳሪ ሆነች::  በዘመኑ ፍርድ ስርአት ውስጥ ሴት ለምስክርነት አትበቃም ጌታ ግን ላካት ወንድ የለም ሴት የለም ደሃ የለም ሃብታም የለም ሁሉ በክርስቶስ አንድ ነው:: ምናልባትም እርስዋ ልትናገር ስትሄድ ሌሎቹ  እህቶች መተዋል ምክንያቱም በማቴዎስ 28:9፤ እነሆም፥ ኢየሱስ አገኛቸውና፦ “ደስ ይበላችሁ፡” አላቸው። እነርሱም ቀርበው እግሩን ይዘው ሰገዱለት። እርስዋን ከልክሎ ለሌሎች መፍቀዱ አይመስልም ተመልሶ መቶ ይሆናል ብዬ እላለሁ:: 

የላከው መልእክት:- ” እኔ ወደ አባቴና ወደ አባታችሁ ወደ አምላኬና ወደ አምላካችሁ ዓርጋለሁ፡ ብለሽ ንገሪአቸው፡” አላት።” ከዚህ መልክት የምንረዳው አብ የእየሱስ አባት ብቻ ሳይሆን የእኛም መሆኑንና ልጅ መሆናችንን ይገልፃል::  በግልፅ ጌታ አወጀ ወደ አባታችሁ ብሎ:: እንዲሁም ወደ አምላካችሁ! አሜን!   እርሱ አባትና አምላካችን ነው::  መግደላዊት ማርያም መጥታ ጌታን እንዳየች ይህንም እንዳላት ለደቀ መዛሙርቱ ነገረች። እየሱስ ተነስቷል! የሞትንና  የሲኦልን ቁልፍ ይዟል የሚጎዳንም የለም::

አባቴና አምላኬ ሆይ ተመስገን!  ጌታዬ እየሱስ ሆይ በአብ ፊት ስለታየህልኝ አመሰግናለሁ::  መንፈስ ቅዱስ  የምትለኝን ሁሉ እንድሰማና ቃሉም ከእኔ ጋር እንዲዋሃድ እንድታዘዝም እርዳኝ! አሜን!

ዮሐንስ 20: 19-20

19፤ ያም ቀን እርሱም ከሳምንቱ ፊተኛው በመሸ ጊዜ፥ ደቀ መዛሙርቱ ተሰብስበው በነበሩበት፥ አይሁድን ስለ ፈሩ ደጆቹ ተዘግተው ሳሉ፥ ኢየሱስ መጣ፤ በመካከላቸውም ቆሞ፦ “ሰላም ለእናንተ ይሁን፡” አላቸው።

ያም ቀን እርሱም ከሳምንቱ ፊተኛው እየሱስ ከሙታን የተነሳበት ቀን ምን አይነት ቀን ነው?  የሰው ልጆች ታሪክ የተለወጠበት! 

ደቀ መዛሙርቱ ተሰብስበው በነበሩበት፥ አይሁድን ስለ ፈሩ ደጆቹ ተዘግተው ሳሉ፥ ኢየሱስ መጣ!  አቤት ሲያዩት ደስታ በህይወት ስላለ እፍረት ጥለውት ስለጠፉ::  ድብልቅልቅ ያለ ስሜት ያለበት ክፍል ነው::  በሮቹ ተዘግተው ተቆልፈው ሳሉ በር ማንኳኳት የማይጠበቅበት ጌታ በመካከላቸው ቆመ::  ቀኑን ከማርያም ከሌሎችም እህቶችና ከኤማኦስ መንገደኞችጋር አሳልፎ ማምሻውን ደግሞ እዚህ በመካከላቸው መጣ::  ጌታ በስራ ላይ ነው ጊዜ አያባክንም:: ጌታ በመካከላቸው ሲቆም አስሩንም እያስነሳ የሚወቅሳቸው መስሏቸው ነበረ እርሱ ግን አልወቀሳቸውም ምንም እንዳልተፈጠረ በዛው በፍቅሩ ቀረባቸው::  ስለእነሱ ማልዶም ነበረ ይህም እንደሚሆን ያውቅ ነበረ ምንም አዲስ ነገር አልተፈጠረም::

በመካከላቸውም ቆሞ፦ “ሰላም ለእናንተ ይሁን፡” አላቸው እንጂ ሌላ አላለም እንዴት ልብን ይፈውሳል?  የጠበቁት ሌላ የሆነው ሌላ::  ጌታቸውን በህይወት አግኝተው  ሰላማቸውም ተመልሰ::  እነዚህ በር ዘግተው ፈርተው የተቀመጡ ወገኖች አንበሳ ሲሆኑ እናያለን ከመንፈስ ቅዱስ የተነሳ::

ይህንም ብሎ እጆቹንም ጎኑንም አሳያቸው። ደቀ መዛሙርቱም ጌታን ባዩ ጊዜ ደስ አላቸው። እንዴት ደስ አይላቸው ይህንን ጌታ በመካከላቸው ሲያገኙ?! ስለ እኔ ነው የተወጋኸው ተመሰገን ከዚህም የተነሳ ታሪክ ተለወጠ ሞትና ሲኦል ተሻሩ ፤  የኃጥያት ባርያ መሆን ተሻረ ፤  የዘለላ ም ህይወት ተሰጠን! ሀሌሉያ!

ጌታ ሆይ ተመስገን የኃጥያቴን እዳ ስለከፈልክልኝ::  ስለወደድከኝ ተመስገን ሰላምህን ስለ ሰጠኸኝ ተባረክ! አሜን!

ዮሐንስ 20: 21-23

ኢየሱስም ዳግመኛ፦ “ሰላም ለእናንተ ይሁን፤ አብ እንደ ላከኝ እኔ ደግሞ እልካችኋለሁ፡” አላቸው። ሰላሙን አስታጥቆ እርሱ እንደተላከው ልኮናል::  እኛ የሰማይ መንግስት አምባሳደሮች ነን::  ተልእኮውንም የተቀበልነው ከራሱ ከጌታ ነው:: እርዳን አባት ሆይ የላከንን ፈጽመን እንድናከብርህ በሰውም ፊት እንዳናፍር ነገር ግን እንድንገልጥህ እርዳን:: 

ስንላክም “መንፈስ ቅዱስን ተቀበሉ እንዳለው በመንፈስ  ቅዱስ ተሞልተን መውጣት አለብን ምክንያቱም በኃይልም በብርታትም አይደለም በመንፈሴ ብሎናልና::  መንፈሱንም ሳይሰስት በልግስና ይሰጠናል::  ዕለት ዕለትም በመንፈስ ተሞሉ ተብለናልና መፈለግና መጠማት ካለ እርሱ ይሞላናል::

ኃጢአታቸውን ይቅር ያላችኋቸው ሁሉ ይቀርላቸዋል፤ የያዛችሁባቸው ተይዞባቸዋል፡” አላቸው። ይህንን በሁለት አቅጣጫ እረዳለሁ አንዱም የበደሉንን ይቅር ማለትና የሰዎችን ኃጥያት አለመያዝ ሲሆን ሌላው ወንጌልን እየሰበክን የእግዚአብሔር መንግስት ቀርባለችና ንስሃ ግቡ እያልን ሰዎች ከነኃጥያታቸው እንዳይኖሩ መርዳት::  ከላይም ሂዱ ብሎ ሲልከን ከእግዚአብሔር ጋር ታረቁ የምንል አምባሳደሮች ነን::  ይቅር የሚልና ከመንግስቱ የሚወልዳቸው እራሱ ጌታ ነው::

አባት ሆይ ተመስገን መንፈስህን ስላስታጠከን::  እየሱስ በምድር የሰጠኽኝን ፈጽሜ አከበርኩህ እንዳለና ምሳሌውን እንደተወልን እኛም በምድር እናክብርህ ሂዱ እንደተባልን የምንሄድና ምስራቹን  የምናበስር አድርገን::  አባት ሆይ ዛሬ ም ብፊትህ ነንና በመንፈስህ ሙላን::

ዮሐንስ 20: 24-31

27፤ ከዚያም በኋላ ቶማስን፦ “ጣትህን ወደዚህ አምጣና እጆቼን እይ፤ እጅህንም አምጣና በጎኔ አግባው፤ ያመንህ እንጂ ያላመንህ አትሁን፡” አለው።

29፤ ኢየሱስም፦ “ስለ አየኸኝ አምነሃል፤ ሳያዩ የሚያምኑ ብፁዓን ናቸው፡” አለው።

ከሐዋይያት አንዱ ቶማስ ጌታ ለሌሎቹ ሲገለጥና እፍ ብሎ “መንፈስ ቅዱስን ተቀበሉ” ብሎ ሲባርካቸው አልነበረምና ተነስቷል ብሎ ለማመን ቸገረው::  እንዲያውም ከማመን ይልቅ “የችንካሩን ምልክት በእጆቹ ካላየሁ ጣቴንም በችንካሩ ምልክት ካላገባሁ እጄንም በጎኑ ካላገባሁ አላምንም፡” አላቸው። የተቀሩት ተነስቷል አልተነሳም ላይ አይደሉም::  ቶማስ ግን አልተቀበለም::  በስጋ ነው እያሰበ ያለው አእምሮአችን ካልታደሰና በመንፈስ ቅዱስ ካልታገዝን የእግዚአብሔርን ነገር ማወቅ አይቻልም::  ማየት ማመን ቢሆንም ከማየታቸው ባሻገር ትእዛዝን ተቀበሉ ወንጌል ለመስበክ እርሱ ግን ይህንን ጉብኝት አላገኘም ገና::  ያለ እምነት እግዚአብሔርን ደስ ማሰኘት አይቻልም:: እምነትም ከእግዚአብሔር  አይጨመርም የሚመጣው ህያው ቃሉን ከመስማት ነው::

እንደተለመደው ደጆች ተዘግተው ሳሉ ኢየሱስ መጣ፤ በመካከላቸውም ቆሞ፦ “ሰላም ለእናንተ ይሁን፡” አላቸው። ምንም እንኳን አየሩ ደፍርሶ ቢመጣም አላምን ብሎ ያስቸገረ ቢኖርም እርሱ አሁንም ሰላም ለእናንተ ብሎ በመካከላቸው ቆመ::  ምን አይነት እረኛ ነው?! የሚረዳን የማይፈርድብን ታጋሽና ርህሩህ! ከዚያም በኋላ ቶማስን፦ “ጣትህን ወደዚህ አምጣና እጆቼን እይ፤ እጅህንም አምጣና በጎኔ አግባው፤ ያመንህ እንጂ ያላመንህ አትሁን፡” አለው። አምነን እንድንከተለው ነው ጌታ የሚፈልገው::  አለ ማመንም ማመን ነው::  እንደቃሉ ማሰብ ይሁንልን:: በዕብራውያን 11:1፤ እምነትም ተስፋ ስለምናደርገው ነገር የሚያስረግጥ፥ የማናየውንም ነገር የሚያስረዳ ነው። እንመን!

ቶማስም፦ “ጌታዬ አምላኬም፡” ብሎ መለሰለት። ኢየሱስም፦ “ስለ አየኸኝ አምነሃል፤ ሳያዩ የሚያምኑ ብፁዓን ናቸው፡” አለው። ቶማስን ግድ የለም ባታምን አላለውም ማመንና መከተል አስፈላጊ ነው::  በሚያምኑ ሰዎች እየሱስ እንዴት እንደተደነቀ እናስብ ሌላው የሰው ልጅ ሲመጣ እምነትን ያገኝ ይሆንን የሚለውንም አንርሳ:: እኛ ግን ባናየውም አምነነዋል!

ኢየሱስም በዚህ መጽሐፍ ያልተጻፈ ሌላ ብዙ ምልክት በደቀ መዛሙርቱ ፊት አደረገ፤ ነገር ግን ኢየሱስ እርሱ ክርስቶስ የእግዚአብሔር ልጅ እንደ ሆነ ታምኑ ዘንድ፥ አምናችሁም በስሙ ሕይወት ይሆንላችሁ ዘንድ ይህ ተጽፎአል። በቂ ቃል ተሰቶናል አላማውም አንድና አንድ ነው በእየሱስ አምነን እንድንድን!!

አባት ሆይ ክበር ተመስገን::  ሰላም ለእናንተ የምትል ጌታ ተባረክ! ስለተሰጠን ቃል ተባረክ! አሁንም ድንቅና ተአምራት ታደርጋለህ አላረጀህም አልተቀየርክም!  አሜን!

ዮሐንስ 21: 1-14

5፤ ኢየሱስም፦ “ልጆች ሆይ፥ አንዳች የሚበላ አላችሁን?” አላቸው። “የለንም፤” ብለው መለሱለት።

ጌታ እየሱስ አብሯቸው በነበረበት ጊዜ በገንዘብ የሚደግፉ ሰዎች ነበሩ አሁን ግን ደጋፊ የሌላቸው ሐዋርያት ለመስራት ወጡ::  እየሱስ ነው ገሊላ እንገናኝ ብሎ የላካቸው ስለዚህ እየጠበቁ እያለ ለኑሮአቸውም መስራትን ጀመሩ::  ወደ ሰባት ደቀ መዛሙርት በተገኙበት እዛው እየሰሩ ባለበት ስፍራ ጌታ ለሶስተኛ ጊዜ ተገለጠ::  እነርሱ ለሊቱን ሙሉ ለፍተው ምንም አሳ አልያዙምና እንደቀደመው “መረቡን በታንኳይቱ በስተ ቀኝ ጣሉት ታገኙማላችሁ፡” አላቸው።  

በጣሉትም ጊዜ እጅግ ብዙ አሳ ያዙ መረቡም አልተቀደደም ይላል::  ይህ ሁሉ ሲሆን አላወቁትም ምክንያቱም በደንብ አልነጋ ይሆናል ደግሞም ባህሩ ላይ ነበሩ እርሱ ግን ዳሩ ላይ ነበረና እርቀቱምተጽእኖ ይኖረዋል::  ወደ ምድርም በወጡ ጊዜ ፍምና ዓሣ በላዩ ተቀምጦ እንጀራም አዩ።  የመረቡ አለመቀደድ እንዲሁ አልተጠቀሰም ለማለት የተፈለገው መያዝ ከሚገባው በላይ ይዟል ይህ ተአምር ነው::  ሙሉ ለሊት የተፈለገው አሳ መረብ እስኪቀደድ መገኘቱ ጌታ የሰራው ድንቅ ነው::  ዛሬም ለከበበን ለፍተን ምንም ባላገኘንበት ላይ ይህ እጁ ይገለጥና ተአምራት በህይወታችን ይሁን::

ይህ ተአምራት የጀመረው ልጆች ሆይ፥ አንዳች የሚበላ አላችሁን?” ከሚለው ጥያቄ ነው እነርሱም “የለንም፤” ብለው መለሱለት። የለም ብለው ባሉት ላይ ጌታ አለ ብሎ መሸከም ከሚቻለው በላይ አንበሸበሻቸው::  ሌላው ጌታ ሐዋርያቱን በምንም አልወቀሳቸውምና ከአገልግሎት እየኮበለሉ ነው ለማለት ይከብዳል::  ለእለት ኑሮ ለመስራት ነበረ የወጡት::  ጌታም እራሱ ምግብ አዘጋጅቶ ጠበቃቸው! ኢየሱስም፦ “ኑ፥ ምሳ ብሉ፡” አላቸው። ከደቀ መዛሙርቱ አንድ ስንኳ፦ “አንተ ማን ነህ?” ብሎ ሊመረምረው የደፈረ አልነበረም፤ ጌታ መሆኑን አውቀው ነበርና። ዮሃንስም ለጴጥሮስ ጌታ እኮ ነው እያለው ነበር:: ኢየሱስም መጣና እንጀራ አንሥቶ ሰጣቸው፥ እንዲሁም ዓሣውን።

አባት ሆይ ክብር ለአንተ ይሁን ዛሬም ድንቅና ተአምራትን ታደርጋለህ ሁሉን በፊትህ አናኖራለን::  ሩጫችንን ባርክ እንደቃልህ መውጣትና መውረስ ይሁንልን::  ድካም የበዛበት ሩጫ ከማድረግ ጠብቀን::  አሜን!

ዮሐንስ 21: 15-19

15፤ ምሳ ከበሉ በኋላም ኢየሱስ ስምዖን ጴጥሮስን፦ “የዮና ልጅ ስምዖን ሆይ፥ ከእነዚህ ይልቅ ትወደኛለህን?” አለው።  “አዎን ጌታ ሆይ፥ እንድወድህ አንተ ታውቃለህ” አለው።  “ግልገሎቼን አሰማራ፡” አለው።

የስጋቸውን ፍላጎት ምሳ አዘጋጅቶና አብልቶ ከጨረሰ በኃላ ወደ ጥያቄ ገባ::  “የዮና ልጅ ስምዖን ሆይ፥ ከእነዚህ ይልቅ ትወደኛለህን?”  ብሎ ሶስት ጊዜ ጠየቀው::  ጥያቄው ትወደኛለህን ብቻ አይደለም ከእነዚህ ይልቅ ትወደኛለህን? የሚል ነው::  ጌታ ፉክክር አይወድም ለምን ይህን አለ?  ከዚህ ቀደም ጌታ መሄጃው መድረሱን በነገራቸው ጊዜ ጴጥሮስ እነዚህ ሁሉ ቢከዱህ እኔ ከአንተ ጋር ነኝ እስከሞት ብሎ ሲያበቃ አላውቀውም ብሎ ሶስት ጊዜ ካደው::  ስለዚህም ነው እዚህ ጋርየካደውን ሁሉ እወድሃለሁ እያለ እራሱን ከመኮነንና በወንድሞቹም ፊት ከማፈር ሊያወጣው ነው::  እኛም እራሳችንን ከሌሎች ሳናስተያይ ምሳሌያችን እየሱስ ብቻ ይሁንልን:: 

ይህንን ጥያቄ ሲጠይቅ ጌታ ሃሳቡንም እንዳልቀየረ ለሌሎቹም ለማሳየት ነው:: ጴጥሮስ መሪ ነው ምንም እንኳን በቃሉ ተፈትኖ ወድቆ ቢገኝም::  ይህንን በሁሉ ፊት ሊያሳይና አገልግሎቱንም ሊያፀናለት ነው:: ኢየሱስም አለው፦  “ግልገሎቼንና በጎቼን አሰማራ፡” : “ጠቦቶቼን ጠብቅ፡” አለው::  ጌታ እየሱስ የተጠቀመው  ቃል ግልገሎቼን በጎቼን ጠቦቶቼን- የእኔ ናቸው እያለ ነው:: ግልገሎች አይደለም ያለው የእኔን ግልገሎች ወይም ግልገሎቼን::  መንጋው የእየሱስ ነው እንጂ የማንም አይደለም:: የእግዚአብሔር ህዝብ የሞተለት እውነተኛ እረኛ አለው:: አሜን

አገልግሎት በፍቅር ነው የሚሰራው ይህም ማለት ከወደድነው የተሰጠንን ስራ እንሰራለን በቤቱ:: እዚህም ጋር የምናየው ከወደድከኝ በጎቼንና ግልገሎቹን አሰማራ ጠቦቶቹን ግን ጠብቅ::  ጠቦት ጎረምሳ ነው ትግስትን የራስን መተውንና ክትትልን ይፈልጋል መጠበቅ  ሁልጊዜ አብሮ መሆንን ይጠይቃል ገና ቀንዱ በቀል በቀል ያለ ስለሆነ ከዚህም ከዛም ይጋጫል የራሱን ይፈልጋል ታድያ ያለፍቅር ይሄ እንዴት ይጠበቃል?! ጌታ የሰጠንን ፀጋ በፍቅር እንጠቀምበት ::  ደቀ መዛሙርቱ መሆናችንንም በፍቅር እናሳይ::  እንደጌታ ይቅር የምንል እንሁን::  ክህደት ሊኖር ይችላል ይቅርታ ግን ሁሉንም ይፈውሳል!

አባት ሆይ በሰጠኸኝ ስፍራና ስራ ላይ እንደልብህ አሳብ በፍቅርና በመንፈስ ቅዱስ ኃይል እንዳገለግልህ እርዳኝ:: የይቅርታንም ልብ ስጠኝ ከፍቅር በቀር አንዳች እዳ አይኑርብኝ::  አሜን!

ዮሐንስ 21: 20-25

22፤ ኢየሱስም አለው፦ “እስክመጣ ድረስ ይኖር ዘንድ ብወድስ፥ ምን አግዶህ? አንተ ተከተለኝ።”

ጌታ እየሱስ ጴጥሮስን ትወደኛለህ ወይ ብሎ ሶስት ጊዜ ጠይቆ መልስን ካገኘ በኃላ ተከተለኝ አለው::  ለዚህ ትዕዛዝ መልስ ሳይሰጥ ዞር ብሎ ሲያይ ዮሃንስን አይቶ ኢየሱስን፦ “ጌታ ሆይ፥ ይህስ እንዴት ይሆናል?” አለው። እርሱ የተጠየቀው ተከተለኝ ነው ምናለ ለእርሱ ብቻ መልስ ቢሰጥ::  ደርሶ ኮሚቴ ማን አደረገው ጌታ የወደደውን ያደርጋል አንዱን ጠርቶ ይህንን ፀጋ ይሰጣል ለሌላው ደግሞ ሌላ:: እያንዳንዱ የራሱን መንገድ ይጠብጥብ! 

ጌታም ለጴጥሮስ ሲመልስ  “እስክመጣ ድረስ ይኖር ዘንድ ብወድስ፥ ምን አግዶህ? አንተ ተከተለኝ።” የራስህን እወቅ ስለሌላው ተው እያለውነው::  እያንዳንዳችን በእኔ ስራ ብለን ከእርሱ ጋር እንስማማ እንጂ ስለሌሎች ልጆቹ ጌታን ልንሞግት አንነሳ::  አንድ አገልጋይ የመሰከረው ትዝ ይለኛል ለአገልግሎት የሄደበት ቤተክርስቲያን አንዲት ሴት ያለችውን ሲመሰክር እኔና ባለቤቴ ከቸርች ቀርተን አናውቅም: ሰንበት ትምህርት ቤት እናስተምራለን: አስራት እንከፍላለን  እርስዋ ግን ጌታ ድንቅ ያደረገላትን እያነሳች ቸርች እንኳን አንዳንዴ ነው የምትመጣውና እንዴት ለእኛ ቀርቶ ለእርስዋ ይደረጋል ብላ ጠየቀችው::  የእህትዋ መጎብኘት አስቀናት! ከዚህ መንፍስ  ይጠብቀን በቤት ውስጥ እንዳንጠፋ አንድ ፊቱን ሸፍቶ የሄደው ልጅ ይሻል ነበር ተምሮ ወደ አባቱ በትህትና ተመለሰ::  በቤት ያለው ግን በመጣው ወንድሙ ተናደደና ቀና የአባቱ የሆነው ሁሉ የእርሱ መሆኑን ዘነጋና ጎሽ ጎሽ  መባልን ፈለገ:: አደራውን ብቻ ከእርሱ ባገኘነው ፀጋ አገልግለን ጎሽታን እንዳንፈልግ::  የማንጠቅም አገልጋዮች ነን ማለትን ጌታ ይስጠን በቅዱሳንም መጎብኘት ደስ ይበለን::

ስለዚህ፦ “ያ ደቀ መዝሙር አይሞትም” የሚለው ይህ ነገር ወደ ወንድሞች ወጣ፤ ነገር ግን ኢየሱስ፦ “እስክመጣ ድረስ ይኖር ዘንድ ብወድስ ምን አግዶህ?” አለው እንጂ አይሞትም አላለውም። ስለ እነዚህም የመሰከረ ይህንንም ጽፎ ያለ ይህ ደቀ መዝሙር ነው፥ ምስክሩም እውነት እንደ ሆነ እናውቃለን። ዮሃንስ ነው ይህንን ሁሉ የጎደለውን ከብዙ መካከል በመንፈስ ተነድቶ የፃፈልን ::  ደግሞም እውነት ለመናገር ጌታ ተላልፎ ከተጠበት ከመጀርያው ጀምሮ እስቀመስቀሉ ግርጌ ተገኝቶ የእናቱንም ኃላፊነት የተሰጠው ይኸው ሐዋርያ ነበረ:: ኢየሱስም ያደረገው ብዙ ሌላ ነገር ደግሞ አለ፤ ሁሉ በእያንዳንዱ ቢጻፍ ለተጻፉት መጻሕፍት ዓለም ራሱ ባልበቃቸውም ይመስለኛል ብሎ ወንጌሉን አጠናቀቀ!

በዚህ የዮሐንን ጥናት አጠናቀናል የረዳንን ጌታን አመሰግናለሁ! 

ቅዱስ አባት ሆይ ክበር ተመስገን አንተ ወድደህና ፈቅደህ በምታደርገው የቤትህ ስራ ተባባሪ እንድሆን እርዳኝ! በቅዱሳን ውስጥ እንድትገለጥ ዛሬ በፊትህ እማልዳለሁ!  በፀጋ ላይ ፀጋን ስጠኝ! አሜን

በክርስቶስ ማን ነኝ?

በክርስቶስ በሰሚያዊው በረከት ሁሉ የባረከኝ በአብም ቀኝ በክርስቶስ ውስጥ የሰወርከኝ ጌታዬ ተባረክ እኔ ከዚህ ዓለም አይደለሁም መጻተኛና እንግዳ ነኝ ቤቴ በሰማይ ነው:: አሜን!

ማንነታችንን እንወቅ፤ እኛ ጌታ እንደሚለን ነን::  እራሳችን ነን ካልነው ሰዎችም ከነገሩን ይልቅ ቃሉ የሚለን ነንና ቃሉ በልባችን ይተከል::

በክርስቶስ ማነኝ? በቀን አንድ የእግዚአብሔር ቃልን ይዘን ስለማንነታችን እናስብ::

ይህንን እውነት እናጥና በልባችንም በቀንም በለሊትም እናሰላስለው::

1.   ልጅ ነኝ!!  

ዮሐንስ 1:12፤ ለተቀበሉት ሁሉ ግን፥ በስሙ ለሚያምኑት ለእነርሱ የእግዚአብሔር ልጆች ይሆኑ ዘንድ ሥልጣንን ሰጣቸው፤

ሮሜ 8:14፤ በእግዚአብሔር መንፈስ የሚመሩ ሁሉ እነዚህ የእግዚአብሔር ልጆች ናቸውና:: 15፤ አባ አባት ብለን የምንጮኽበትን የልጅነት መንፈስ ተቀበላችሁ እንጂ እንደገና ለፍርሃት የባርነትን መንፈስ አልተቀበላችሁምና።

ገላትያ 3:26፤ በእምነት በኩል ሁላችሁ በክርስቶስ ኢየሱስ የእግዚአብሔር ልጆች ናችሁና፤

ልጅነት በመቀበል የሚገኝ እንጂ ለሰው ሁሉ የሚታደል አይደለም:: ኢየሱስ የእግዚአብሔር ልጅ እንደሆነ ማወቅ ከዛም ‘ጌታዬ ነህ’ ብለን በጌትነቱ ስንቀበለው ልጅነትን እናገኛለን::ማወቅ

ልጅነት የተሰጠን በእንስሳት ደም ሳይሆን ኃጥያት የማያውቀው የእግዚአብሔር በግ ኢየሱስ ዋጋ ከፍሎ ነው!! 

ጸሎት

አባት ሆይ እንዳውቅህ ስለረዳኸኝ አመሰግንሃለሁ:: ከአንተ ተወልጃለሁኝ ይህንን ልጅነት ማንም አይነጥቀኝም:: ተመስገን!

2. ወዳጅ ነኝ!!  

ዮሐንስ 15:15፤ ከእንግዲህ ወዲህ ባሮች አልላችሁም፤ ባርያ ጌታው የሚያደርገውን አያውቅምና፤ ወዳጆች ግን ብያችኋለሁ፥ ከአባቴ የሰማሁትን ሁሉ ለእናንተ አስታውቄአችኋለሁና።

ወዳጅ አድርጎናል!  ስለዚህም ‘እኔ የእየሱስ ወዳጅ ነኝ’ ብለን አፋችንን ሞልተን ልንናገር እንችላለን::  እራሳችንን አናርቀው::  የሆነ ነገር ስንሆን ደስታም ይሁን ክፉ ቶሎ ብለን ወደ ወዳጃችን እንደሮጣለን:: ታድያ ከእርሱ የሚበልጥ ወዳጅ ማነው?  ይህንን ማንም አይቀይረውም አንድ ጊዜ ተቀብሎናል::

ጸሎት

ሃሌሉያ  ጌታ ኢየሱስ ሆይ ወዳጄ ነህ!

3.  ጨው ነኝ!!  

ማቴዎስ 5:13፤ “እናንተ የምድር ጨው ናችሁ፤ ጨው አልጫ ቢሆን ግን በምን ይጣፍጣል? ወደ ውጭ ተጥሎ በሰው ከመረገጥ በቀር ወደ ፊት ለምንም አይጠቅምም።

ይህች ምድር ጠዕሟን አታለች:: የተሰጠን ስራ ጨው መሆንና ለዚች ዓለም ጣዕም መስጠት ነው::  

አለበለዚያ ሰይጣን ሲኦል ነው ሊያደርገው የሚፈልገው ግቡ እግዚአብሔርን መፍራትን ፈጽሞ ሊያጠፋ ነው::  እኛ ግን እያለን ይህ አይሁን!   

ስለዚህ ሳይበላሽ ምግብን ማቆየት የሚችለው የጨው ስራ ይገለጥና እርሱን መፍራት ይመጣል:: ልክ ያልሆነው በእኛ ህይወት ሊወቀስና ሊቆጠቁጥ ይገባል ልክ ጨው ቁስል ላይ እንደማድረግ::  

ግን ማንነታችንን ችላ ብለን ዓለምን ብንመስል አብረን እንበሰብሳለን የሚቀጥለውም መረገጥ ነው ለምንም አንጠቅምምና::

ዮሐንስ 15:6፤ በእኔ የማይኖር ቢሆን እንደ ቅርንጫፍ ወደ ውጭ ይጣላል ይደርቅማል፤ እነርሱንም ሰብስበው ወደ እሳት ይጥሉአቸዋል፥ ያቃጥሉአቸውማል። 

ስራችንን እንስራ እኛ ጨው ነን!  ለዝች ዓለም አስፈልጋለሁኝ ብለን እርግጠኛ እንሁን!!

ጸሎት

አሜን ጌታ ሆይ በእኔ እየተገለጥህ ታይ ጨውነቴን ልቀጥል  ፍሬንም ላፍራ!

4.  ብርሃን ነኝ!!  

ማቴዎስ 5:14፤ “እናንተ የዓለም ብርሃን ናችሁ። በተራራ ላይ ያለች ከተማ ልትሰወር አይቻላትም።

ይህች ዓለም ጨለማ ናት ወንጌል ደግሞ ብርሃን ነው::  በጨለማችንን ላይ ብርሃን ይብራ ያለው እርሱ ነው እንደሚል እኛም ጨለማ ነበርን የወንጌል ብርሃን እስኪበራልን::

ለዝች ዓለም በክርስቶስ በማመኔ ብርሃን ተደርጌአለሁ::  ብርሃንን ጨለማ አያሸንፈውም::  ብርሃን ካለ ጨለማ የለም የአንዱ መገኘት ሌላውን እንዳይገኝ ያደርገዋል:: ስለዚህ እኛ ባለንበት ጨለማ ይባራል ወይም በዙሪያችን ያሉት በጨለማ የሚመላለሱ ከብርሃኑ የተነሳ ዙሪያቸውን እንዲያዩ የሚያደርግ ማንነት አለን::  

ለዝች ዓለም አስፈልጋለሁ ምክንያቱም እየሱስ በእኔ ውስጥ ተብለጭልጮ እየታየ ከጨለማ ሌሎችን ይስባል እንጂ እኔ ወደ ጨለማ የምሳብ አይደለሁም::  

ብርሃናችሁ በሰው ሁሉ ፊት ይብራ ተብለናልና የእኛ ማንነት ነው ብርሃን መሆን በጨለማ የሚደናበሩትን ማሳየት::

ጌታ ይርዳን!

5.  አዲስ ፍጥረት ነኝ

2 ቆሮንቶስ 5:17፤ ስለዚህ ማንም በክርስቶስ ቢሆን አዲስ ፍጥረት ነው፤ አሮጌው ነገር አልፎአል፤ እነሆ፥ ሁሉም አዲስ ሆኖአል።

አዲስ ፍጥረት ስንሆን አሮጌው ማንነት ሞቶ ቅዱስ እና ህያው ፈጣሪን የሚያኖር ማንነት ተፈጠረ:: ቤተመቅደሱ አደረገኝ!! ይህም አዲስ ማንነት እኛ ጌታን ደስ አስኝተን የምንኖርበት ሳይሆን እርሱ  መቶ የሚኖርበት ነው::  የእግዚአብሔር መንፈስ ማደሪያ አደረገን ይህ በብሉይ አልነበረም በእነርሱም የእግዚአብሔር መንፈስ ይሰራ ነበር ልዮነቱ በአዲስ ኪዳን ሰርቶ የሚመለስ ሳይሆን በእኛ የሚኖር ነው!! ሃሌሉያ!!  የብሉይ አገልጋዮች በአህዛብ  ላይ መንፈሱ መፍሰሱን ቢያዩ ምን ይሉ ይሆን?!

በጣም የጠለቀ እውነት ነው!  ማንም ከእኛ የማይወስድብን ማንነት የእርሱ ማደርያ መሆን ማንስ ያስወጣዋል እርሱ የእኛ እኛም የእርሱ አንድ ጊዜ ከእርሱ ተወለድን ከስጋና ከደም ፈቃድ አይደለም:: ተቀባይነትን አግኝተናል!! ስሙ ይባረክ!

ጸሎት

አሜን እኔ አዲስ ፍጥረት ነኝ ጠላት አሮጌ ነገር እያመጣ አይከሰኝም::  ከወይኑ ግንድ ጋር ተጣብቄያለሁ!!!ክበር ጌታዬ ይህ የከበረ እውነት በውስጤ ይታተም!!  በእኔ ውስጥ ኑሮህን ኑረው  አባ! አሜን

6.  ቅዱስ ነኝ

ሮሜ 1:7፤ በእግዚአብሔር ለተወደዳችሁና ቅዱሳን ልትሆኑ ለተጠራችሁ በሮሜ ላላችሁት ሁሉ፥ ከእግዚአብሔር ከአባታችን ከጌታም ከኢየሱስ ክርስቶስ ጸጋና ሰላም ለእናንተ ይሁን።

1 ቆሮንቶስ 1:2፤ በቆሮንቶስ ላለች ለእግዚአብሔር ቤተ ክርስቲያን፥ በክርስቶስ ኢየሱስ ለተቀደሱት፥ የእነርሱና የእኛ ጌታ የሆነውን የጌታችንን የኢየሱስ ክርስቶስን ስም በየስፍራው ከሚጠሩት ሁሉ ጋር ቅዱሳን ለመሆን ለተጠሩት፤

ጳውሎስ ለሁለቱም ቤተክርስትያናት ሲጽፍ ቅዱሳን ልትሆኑ ለተጠራችሁ ይላል::  እኛ በእግዚአብሔር የተወደድንና ኑሯችንም በቅድስና መመላለስ የሞላበት ነው::  የጠራን ቅዱስ ነውና ቅዱሳን ሁኑ ተብለናል:: 

በክርስቶስ ኢየሱስ ለተቀደሱት እንዴት ደስ ይላል የተቀደስነው በእርሱ ስራ ነው::  ስለዚህ ቅዱስ ነኝ ብለን ለማለት የምንደፍረው በእርሱ ነው::  ቅዱስ ነኝ ስል አልፈራም እርሱ ቀድሶ በውስጤ እየኖረ ነውና::

ጸሎት

ቅዱስ ላደረገኝ ስሙ ይባረክ!!!

7.  ለሐጥያት የሞትኩኝ ነኝ!!

ሮሜ 6:2:  ለኃጢአት የሞትን እኛ ወደ ፊት እንዴት አድርገን በእርሱ እንኖራለን?

ሮሜ 6:11፤ እንዲሁም እናንተ ደግሞ ለኃጢአት እንደ ሞታችሁ፥ ግን በክርስቶስ ኢየሱስ በጌታችን ሆናችሁ ለእግዚአብሔር ሕያዋን እንደ ሆናችሁ ራሳችሁን ቈጠሩ።

1 ጴጥሮስ 2:24፤ ለኃጢአት ሞተን ለጽድቅ እንድንኖር፥ እርሱ ራሱ በሥጋው ኃጢአታችንን በእንጨት ላይ ተሸከመ፤ በመገረፉ ቁስል ተፈወሳችሁ። 

ብዙ ነገር አሳባችንን ለመቆጣጠር ይፈልጋል እኛ ግን ለዓለም ነገር ሞተናል ለክርስቶስ ግን ለእግዚአብሔር ሕያዋን ነን የመንግስቱን ስራ ለመስራት ለዝችም ዓለም ብርሃንና ጨው ለመሆን::  ለብዙ ነገሮች መልሳችን እኔ ለኃጥያት ሞቻለሁ ነው::  ስድብ ቢሆን ባርከን ማለፍን እንማር ለሚደረግብን ክፋት ሁሉ መልካምን መመለስ እናስቀድም:: 

የጌታን ፊት እያየን እናገልግል እርሱን ደስ ይበለው::

እስኪ እንለማመድ አኔ ሞቻለሁ ክርስቶስ በእኔ ይኖራል እያልን:: እውነታው እርሱ ነው::

ጌታ ጸጋ ያብዛልን!

8.  አሸናፊ ነኝ

ሮሜ 8:37፤ በዚህ ሁሉ ግን በወደደን በእርሱ ከአሸናፊዎች እንበልጣለን።

በዚህ ሁሉ ብሎ የጀመረበትን  ምክንያት ከላይ ስናየው ከፍታና ዝቅታ ማንም ከእርሱ አይለየኝም:: ከክርስቶስ ፍቅር ማን ይለየናል? መከራ፥ ወይስ ጭንቀት፥ ወይስ ስደት፥ ወይስ ራብ፥ ወይስ ራቁትነት፥ ወይስ ፍርሃት፥ ወይስ ሰይፍ ነውን?  ከዚህ ውጪ  ምን  ይመጣል? ጠላትና ስጋ  በዚህ ነው የሚፈትኑን መሸነፍ አይታሰብም::  እንዲያውም ታሸንፋላችሁ ብቻ ሳይሆን የተባልነው ጭራሽ ከአሸናፊዎች ሁሉ ትበልጣላችሁ ነው

ህይወቱን በሰጠኝ ጌታ ተወድጃለሁ ይህ ጌታ ደግሞ  ማሸነፍን በእርሱ በኩል ተሰጠኝ::  መሸነፍ የለም ማሸነፍ ግን ተሰቶኛል by default. 

በክርስቶስ የማይሸነፍ ምን አለ?! ሁሉ ተሸናፊ ነው::  የከበረው የጥበብ ሁሉ መዝገብ እየሱስ በዚህ ሸክላ ውስጥ እየኖረ ነው::  ሸክላ ተሰባሪ ነው ጌታ ግን እየጠበቀኝ ከውስጤ ሆኖ ድል እየነሳ በድል ጎዳና ያራምደኛል::

ጸሎት

ሰባሪው እግዚአብሔር ከፊቴ ሲወጣ ሊገዳደር የሚቆም ማን ነው? ማንም! ጌታ ሆይ ድልን ስለሰጠኸኝ አመሰግናለሁኝ!  አቤት የኔ ጌታ እንዴት ይደንቃል ስራህ እራስህ ጠርተህ በደምህ አጽድቀህ የምቆምበትን ጸጋ ሰተህ ደግሞም በእኔ ውስጥ እየኖርክ ጉልበትና ብቃት ሆነኸኝ ከአሸናፊዎች እንድበልጥ አደረከኝ::  ተ መ ስ ገ ን!!!!አሁንም በቃልህ ላይ እንድቆም እርዳኝ::

9.  በጌታ ተመርጫለሁ ፍሬንም ለማፍራት ተሾምኩ ነኝ!!  

ዮሐንስ 15:16፤ እኔ መረጥኋችሁ እንጂ እናንተ አልመረጣችሁኝም፤ አብም በስሜ የምትለምኑትን ሁሉ እንዲሰጣችሁ፥ ልትሄዱና ፍሬ ልታፈሩ ፍሬአችሁም ሊኖር ሾምኋችሁ።

እራሱ ጌታ መረጠን እርሱ በጸጋ አዳነን እርሱ በጸጋ ያኖረናል::  የእኛ ነገር የቱ ጋር ነው ያለው ታድያ?!  እርሱ ሁሉን አደረገልን በእኛ የሚኖር ዛሬም እርሱ ነው::  

ፍሬ ለማፍራት የሚያስፈልገንን ሁሉ እንድንጠይቅ አብም በእየሱስ ስም የምንጠይቀውን እንደሚሰጠን ተነግሮናል:: ፍሬ  ልናፈራ ተሹመናል ይህም ፍሬ ለአንድ ጊዜ አፍርተን አስቆጠርን ለማለት ሳይሆን ፍሬያችንም ከእኛ ጋር እንዲኖር ይፈልጋል::  ክርስትና በወቅት መሆን የለበትም አመቱን ሙሉ ማፍራት አለብን::  ፍሬ ፍለጋ ጌታ ይመጣልና ፍሬያችን ሁልጊዜ ይገኝ::  ፍሬ  ብለን ስንል የመንፈስ ፍሬ ነው እርሱም በገላትያ 5:22፤ የመንፈስ ፍሬ ግን ፍቅር፥ ደስታ፥ ሰላም፥ ትዕግሥት፥ ቸርነት፥ በጎነት፥ እምነት፣ 23፤ የውሃት፥ ራስን መግዛት ነው። እንደዚህ ያሉትን የሚከለክል ሕግ የለም።

ይህንን በህይወታችን ማየት ይፈልጋል ፍሬውም የሚፈራው በመንፈስ ነው:: እራሱ መንፈስ ቅዱስ ያፈራዋል መቅደሱ ስለሆንን በእኛ እየኖረ ነው::

የጌታ ጸጋ ይብዛልን::

10. በእርሱ ሙሉ ነኝ!

ቆላስይስ 2: 9 -10፤ በእርሱ የመለኮት ሙላት ሁሉ በሰውነት ተገልጦ ይኖራልና።  ለአለቅነትና ለሥልጣንም ሁሉ ራስ በሆነ በእርሱ ሆናችሁ ተሞልታችኋል።

አምላክና ፈጣሪ በሆነው በክርስቶስ እየሱስ ከመሞላት በላይ ምን ያስፈልጋል?!  ለአለቅነትና ለስልጣንም ሁሉ ራስ በሆነው በእርሱ ከመሞላት በላይ ምን ይስጠን? በእርሱ ላይ የሚጨመር ነገር የለም – ሙሉ ነን!!  

ጠላት ሁልጊዜ ጎዶሎ አለ ነው የሚለን ሊያታልለን በዚህ ላይ የሆነ ነገር መጨመር አለበት እያለ::  ጸሎት ቢሆን ማገልገል ቢሆን ምንም ነገር ቢሆን እኛን ለመሙላት አይደለም ስለምንወደው የምናደርገው ነው  ጠላት የሆነ ነገር አድርገን ክፍተትን ለመሙላት እንድነሳ ነው የሚያሳስበን ነገር ግን ሁሉ በክርስቶስ ተሟልቷል እኛም በእርሱ ተሞልተናልና :: ጌታን እናመስግን ለጠላት ሽንገላ መልሳችን ሙሉ ነኝ የምጨምረው የለም ነው::

ጌታ ይባረክ በራሱ ማንነት የሞላን!

ጸሎት

አባት ሆይ ተመስገን ማንነቴ ሙሉ ነው:: በአንተ ተሞልቻለሁ ይህንን ማንም አይሽረውም! አይለውጠውምም!

11. የጸደኩኝ ነኝ!

ሮሜ 5:1፤ እንግዲህ በእምነት ከጸደቅን በእግዚአብሔር ዘንድ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ሰላምን እንያዝ፤

መጽደቃችን እርግጥ ነው::  ቃሉ እንደሚለን የጸደቅነውም በእምነት ነው እንጂ በስራ አይደለም::  ደርሶ በራሳችን የጸደቅን ይመስል ጠላት ይመጣና ውጊያውን በስራችን ላይ አድርጎ ይዋጋናል::  በስራ ወደ ጌታ እንዳልመጣን ሁሉ በስራችን ታምነን አንመላለስም ዛሬም ጽድቃችን ጌታ ነው::  አብርሃም በእምነት እንደጸደቀ እንዲሁ እኛም በእምነት ጸድቀናል::  

መጽደቃችን በእምነት እንደሆነ ከተገነዘብን በክርስቶስ ሰላምን እንያዝ::  ሰላም ይሁንልን! እንረጋጋ::  አእምሮን የሚያልፍ ሰላም የሚሰጥ የሰላም አለቃ ከእኛ ጋር ነውና:: ማንነታችንን አውቀን የሚመጣብንን ፍላጻ ሁሉ በቃሉ ውስጥ እንየው ያኔ ነገሩ ሁሉ ቀላል ይሆናል::  ጌታ እየሱስ የጠላትን ፈተና ያሸነፈው እንደዚህ ተብሎ  ተጽፏል ብሎ ነውና ከእርሱ እንማር::

ጸሎት

ጌታ ሆይ አመሰግንሃለሁ ለመጽደቄ ያደረኩት አስተዋጽኦ ስለሌለ::  አንተው ነህ በመስቀል ላይ ስራዬን  አጠናቀህ ተፈጸመ ብለህ የሰራህልኝ::  ይህንንም እንዳውቅ ልቦናዬን ከፈትክልኝና ያመንኩት::  በዚህም የአንተ ጽድቅ ይኸው ለእኔ ተቆጥሮ ጻድቅ ተባልኩኝ::  አመሰግንሃለሁ!!!!

12. የክርስቶስ አካል ነኝ

1 ቆሮንቶስ 12:27፤ እናንተም የክርስቶስ አካል ናችሁ እያንዳንዳችሁም ብልቶች ናችሁ።

በክርስቶስ ውስጥ ብልት ነኝ:: ይህንንም ያገኘሁት በእርሱ በማመን ነው::  ስራዬን የሰራና የራሱ ያደረገኝ ጌታ የተባረከ ይሁን!  

በአካል ውስጥ ደግሞ የማያስፈልግ  ብልት የለም ሁሉ ብልት ይሰራል::  እኔ አስፈላጊ ነኝ ጠላት አታስፈልጊም ይላል ወይም አንቺ ብትመጪ ብትቀሪ ምንም አታመጪ ብሎ ሊዋጋ ይችላል ነገር ግን አስፈልጋለሁ::  እኔም በአካሉ ውስጥ ስራ አለኝ  እርሱ አውቆኛል በስሜ ጠርቶኛል ጌታዬን እንጂ ጠላትን አልሰማም::  ስራዬን መስራትና በተሰጠኝ መክሊት ማትረፍ አለብኝ:: 

ጸሎት

ጌታ ሆይ በአካልህ ውስጥ ስፍራ ስላለኝ ስለተቀበልከኝ ይህንንም ማንም ስለማይቀይረው  አመሰግንሃለሁ:: እንደሰጠኸኝም ጸጋ አገለግልሃለሁ::

13.  ኩነኔ የሌለብኝ ነኝ! 

ሮሜ 8:1፤ እንግዲህ በክርስቶስ ኢየሱስ ላሉት አሁን ኵነኔ የለባቸውም። 2፤ በክርስቶስ ኢየሱስ ያለው የሕይወት መንፈስ ሕግ ከኃጢአትና ከሞት ሕግ አርነት አውጥቶኛልና።

ከመኮነን ነፃ መሆን ምንኛ ደስ የሚል ነገር ነው? ግን እንደዚሁ አይደለም ነፃ የወጣነው እየሱስ ዋጋ ከፍሎ የሕይወትን መንፈስ ሕግ በእኛ ውስጥ አድርጎ ነው::  ይህ የህይወት መንፈስ ህግ ደግሞ ከኃጢአትና ከሞት ሕግ ጋር እጅ ለእጅ አይሰራም የአንዱ መገኘት የሌላው አለመገኘት ነው::  ኃጢአትና ሞት በእኔ ላይ ስልጣን የላቸውም ተሽረዋል::  ኩነኔ ቢኖርብኝ መብት በነበራቸው  አሁን ግን የእየሱስ ህይወት በእምነት ከእኔ ጋር ስለተዋሃደ  መሰልጠንና እኔን በስራቸው ማድረግ አልቻሉም:: ኃጢአትና ሞት ከእኔ ተሽሯል ክብር ለአዳኜ!!!

በጸጋ ድኛለሁ ከህግ ጋር ተፋትቻለሁ::  በህግ እንደማልድን አውቆ ጌታዬ እንደበግ ስለእኔ ታረደ::  ስለዚህ ጌታ እኔን  አርነት አውጥቶኛል::  ክብርና ምስጋና ይብዛለት!

ጸሎት

አባት ሆይ ኩነኔ ስለሌለብኝ የሕይወት መንፈስ ሕግ  በእኔ ላይ ስላደረክ- ተመስገን::  ህይወት እንዲበዛልኝ እንዲትረፈረፍልኝ ስለመጣህ ተመስገንልኝ!!! አሜን!

14.  የመንፈስ ቅዱስ ቤተ መቅደስ ነኝ

1 ቆሮንቶስ 6:19-20፤ ወይስ ሥጋችሁ ከእግዚአብሔር የተቀበላችሁት በእናንተ የሚኖረው የመንፈስ ቅዱስ ቤተ መቅደስ እንደ ሆነ አታውቁምን? በዋጋ ተገዝታችኋልና ለራሳችሁ አይደላችሁም፤ ስለዚህ በሥጋችሁ እግዚአብሔርን አክብሩ።

ይህ የኔ የምለው ስጋ በዋጋ የተገዛ የኔ ያልሆነ በደሙ የዋጀው ጌታ ያለው ነው:: የኔ ብዬ እለዋለሁ እንጂ የተቀበልኩትም ከእግዚአብሔር ነው:: እሱው ሰቶኝ እሱው እንደገና ዋጅቶት እንዴት የኔ እለዋለሁ?  ኩነኔ የሌለኝ አድርጎ ጻድቅና ቅዱስ አድርጎኝ ይኖርብኛል::  እንዴት ይደንቃል!  ይህ ስጋ የመንፈስ ቅዱስ ቤተ መቅደስ ነው ቢባል አይደንቅም ይህ በልቤ ሊታተም ይገባል::

እራሳችሁን የጽድቅ የጦር ዕቃ አድርጋችሁ አቅርቡ እንደሚል ቃሉ እራሳችንን ዕለት ዕለት ለእርሱ እናቅርብለት::

በሥጋችሁ እግዚአብሔርን አክብሩ። እንደሚል ነፍስን ከሚዋጋ የስጋ ምኞት እራሳችንን እየጠበቅን እራሳችንን ህያዋን ቤተመቅደስ ሆኖ ለመሰራት በፊቱ እናቅርብ::  በዝች ዓለም መጻተኞች ነንና  በሰማይ አገር አለን::  በሰማይ ስለእኛ የሚያስብ አለ:: 

ይህንን ቃል ለአንድ ሰው አካፍይው እንደዛ ሲሆን ይበዛልሻል በውስጥሽም ይታወጃል::

ፀሎት: – 

አባት ሆይ ሰው በሰራው አላድርም ብለህ እራስህ በሰራኸው ማንነቴ ልታድር ስለወደድክ አመሰግንሃለሁ:: እኔነቴን በፊትህ የጽድቅ የጦር ዕቃ አድርጌ አቀርባለሁኝ::  በአእምሮዬም መታደስ ለውጠኝ ቃልህም ከኔ ጋር በእምነት ይዋሃድ:: አሜን

15.  ከጨለማው ስልጣን የዳንኩ ፤  ይቅር  የተባልኩና ወደ መንግስቱ  የገባሁ ነኝ!

ቆላስይስ 1:13-14፤ እርሱ ከጨለማ ሥልጣን አዳነን፥ ቤዛነቱንም እርሱንም የኃጢአትን ስርየት ወዳገኘንበት ወደ ፍቅሩ ልጅ መንግሥት አፈለሰን።

እኔም ጨለማ ሆኜ በጨለማው  አገዛዝ ስር ሆኜ እንደወደደ ያሽከረክረኝ ነበር::  ጌታዬ ግን ብርሃን ይብራ ብሎ በህይወቴ ጨለማውን ገፎ ሐጥያቴን ሁሉ ይቅር ብሎ ወደ መንግስቱ አፈለሰኝ!! አነፃኝና ቀደሰኝ!! 

አቤት ቀላል ነገር ይመስላል መዳን ነገር ግን የከበረ ነው::  ወንጌል ለሰው  ነግራችሁ አልገባው ሲል ሲያሾፍ  አቤት እኔ እንዴት አመለጥኩ ያስብላል ምክንያቱም የጨለማው አለቃ አእምሯቸውን አሳውሮት ይህንን የመዳን ወንጌል ቸል ይላሉና ወደው አይደለም እንዘንላቸው::

በክርስቶስ በሰማያዊዉ በረከት ሁሉ የበረከኝ በአብም ቀኝ በክርስቶስ  ውስጥ የሰወርከኝ ጌታዬ ተባረክ እኔ ከዚህ ዓለም አይደለሁም መጻተኛና እንግዳ ነኝ ቤቴ በሰማይ ነው::  አሜን!

ጸሎት

አባት ሆይ ወደ መንግስትህ ስላፈለስከኝ የጠላትን ቀንበር ስለሰበርክልኝ ሐጥያቴንም ሁሉ ይቅር ስላልከኝ አመሰግንሃለሁ:: 

16.  ከጌታ ጋር አንድ መንፈስ ነኝ

1 ቆሮንቶስ 6:17፤ ከጌታ ጋር የሚተባበር ግን አንድ መንፈስ ነው።

ይህንን ማሰብ ድፍረት ይመስል ይሆናል ነገር ግን ይህ እውነት ነውና ከእኛ ጋር መዋሃድ አለበት::  ቤተመቅደስ አድርጎኝ እኔ እኖራለሁ በውስጥሽ ካለኝ በዚህ በመንፈሱ ከእርሱ ጋር አንድ ሆኛለሁ::

ይህንን ህብረት ማቋረጥ የሚችል ኃይል የለምና ጌታዬ የተመሰገነ ይሁን::  ከእርሱ ጋር አንድ ነኝ በመንፈስ::

17.  ወደ ጸጋ ዙፋኑ ለመቅረብ መብት ያለኝ ነኝ!

ዕብራውያን 4:14፤ እንግዲህ በሰማያት ያለፈ ትልቅ ሊቀ ካህናት የእግዚአብሔር ልጅ ኢየሱስ ስላለን፥ ጸንተን ሃይማኖታችንን እንጠብቅ። 15፤ ከኃጢአት በቀር በነገር ሁሉ እንደ እኛ የተፈተነ ነው እንጂ፥ በድካማችን ሊራራልን የማይችል ሊቀ ካህናት የለንም። 16፤ እንግዲህ ምሕረትን እንድንቀበል በሚያስፈልገንም ጊዜ የሚረዳንን ጸጋ እንድናገኝ ወደ ጸጋው ዙፋን በእምነት እንቅረብ።

ይህ ግብዣ ሁሌ ይገርመኛል::  በሰማያት ሊቀ ካህናት ስላለን እርሱ ስለሚማልድልን ኑ ወደ ጸጋ ዙፋኑ እርሱ እንዳዳናችሁ እርሱው ይረዳችኃል ያለ እርሱ አንዳች ማድረግ አትችሉምና::  እርሱ እንደሆነ ይራራልናል እንጂ አይፈርድብንም!  ምንኛ መታደል ነው?!  

ድካም እንዳለብን የታወቀ ነው ነገር ግን ወደ ጸጋ ዙፋኑ በእምነት ማለትም  በሙሉ ልብና በእርግጠኝነት እንደምንቀበል አውቀን ቀርበን ድካማችንን መርታትና ብርታትን መቀበል እንችላለን:: 

ጸሎት

አባ እያልኩኝ  አባት ሆይ ስምህ ይባረክ ስለረዳኸኝ ከፍ በል::  

ካህኔ ሆይ!   ይኸው አሁን ወደ ጸጋ ዙፋንህ  በእምነት ቀርቤ ጸጋ ስጠኝ እላለሁ::  በጎደልኩበት ሁሉ ሙላት ይሁንልኝ::  አሜን!

18.  በስጋው ተቀድሻለሁ

ዕብራውያን 10:10፤ በዚህም ፈቃድ የኢየሱስ ክርስቶስን ሥጋ አንድ ጊዜ ፈጽሞ በማቅረብ ተቀድሰናል።

የተቀደስኩት በኮርማ ወይም በእንስሳ ደም አይደለም:: በፈጠረኝ ክብሩን ትቶ የባርያን መልክ ይዞ በመጣው በልጁ ነው:: እኔን ለመታደግ የማይገባውን ኑሮ ኖሯል ይህ ጌታ ይገርመኛል ፍቅሩና ትህትናው:: ዛሬም ዓይኑን በእኔ ላይ ማጽናቱ:: በራሴ መቆም አሁንም አልችልም የሚያስችለኝ መንፈስ ቅዱስ ነው:: ሮሜ 8:11፤ ነገር ግን ኢየሱስን ከሙታን ያስነሣው የእርሱ መንፈስ በእናንተ ዘንድ ቢኖር፥ ክርስቶስ ኢየሱስን ከሙታን ያስነሣው እርሱ በእናንተ በሚኖረው በመንፈሱ፥ ለሚሞተው ሰውነታችሁ ደግሞ ሕይወትን ይሰጠዋል:: አሜን

ጸሎት

አባት ሆይ አመሰግንሃለሁ ምንም ማድረግ እለመቻሌን አይተህ ሙሉ በሙሉእዳዬን ከፈልክልኝ:: ተ መ ስ ገ ን!

አሜን

19.  ወራሽ ነኝ!

ሮሜ 8:17፤ ልጆች ከሆንን ወራሾች ደግሞ ነን፤ ማለት የእግዚአብሔር ወራሾች ነን፥ አብረንም ደግሞ እንድንከበር አብረን መከራ ብንቀበል ከክርስቶስ ጋር አብረን ወራሾች ነን።

ልጅ ከሆንን አብሮ ከልጅነት ጋር መውረስ ይመጣል የማይነጣጠል ጉዳይ ነው::  ምን ያህል ቤተሰብ እንዳደረገን እንመልከትና እናስተውል::  ልጅ አድርጎ ተቀብሎኛል!!! ዛሬ የምንቀበለው ማንኛውም ነገር ጊዜያዊ ነው ሁሉም ነገር ያልፋልና ቃሉን በልባችን እንሸሽግ!!

ጸሎት

አባት ሆይ ልጅ ነኝና ወራሽ ነኝ::  ልጅነትን ስለሰጠኸኝ ተመስገን ንፁ አድርገህ የራስህ አድርገኸኛልና ተባረክ!!  አባት ሆይ እንደአባት እፈራሃለሁ አከብርህማለሁ::  በህይወቴ ክበር!  አሜን!

20.  ከክርስቶስ ጋር የተሰቀልኩ ነኝ!

ገላትያ 2:20፤ ከክርስቶስ ጋር ተሰቅዬአለሁ፤ እኔም አሁን ሕያው ሆኜ አልኖርም ክርስቶስ ግን በእኔ ይኖራል፤ አሁንም በሥጋ የምኖርበት ኑሮ በወደደኝና ስለ እኔ ራሱን በሰጠው በእግዚአብሔር ልጅ ላይ ባለ እምነት የምኖረው ነው።

ከክርስቶስ ጋር ተሰቅዬአለሁ የሚለው ሃሳብ በራሱ የቆመ አይደለም ሞቻለሁ በቂ አይደለም ምክንያቱም ህጋዊ ያደርገናል::  ሞተናል የተባለበት ምክንያት:-  እኔም አሁን ሕያው ሆኜ አልኖርም ክርስቶስ ግን በእኔ ይኖራል፤ በአንድ ህይወት ውስጥ ሁለት ሰው መሆን አይቻልም ወይ እኔ ወይም ደግሞ እርሱ መኖር አለበት::  ከሞትን እርሱ ይኑር!!!

እምነት ከመስማት ነው መስማትም የእግዚአብሔርን ቃል እንደሚለን ቃሉ ስለ እኔ ራሱን በሰጠው በእግዚአብሔር ልጅ ላይ ባለ እምነት የምኖረው ነው የዛሬው ኑሮዬ። 

ጸሎት

አባት ሆይ ቤተመቅደስህ አድርገኸኛልና ሞቻለሁምና በእኔ የምትኖረው እየሱስ ኑሮህን ኑረው::  አሜን!!

21.   ከክርስቶስ ጋር ሕይወት የተሰጠኝ ነኝ!

ኤፌሶን 2:5፤ ከወደደን ከትልቅ ፍቅሩ የተነሣ በበደላችን ሙታን እንኳ በሆንን ጊዜ ከክርስቶስ ጋር ሕይወት ሰጠን፥ በጸጋ ድናችኋልና፥

በህይወት መኖር የተሰጠኝ ከትልቅ ፍቅሩ የተነሣ ነው በእርሱ ተወድጃለሁ::  በበደላችን ሙታን እንኳ በሆንን ጊዜ እግዚአብሔር አሰበን ምንም የሚያስመካንና ለመዳን የሚያበቃን ነገር ሳይኖር  ከክርስቶስ ጋር ሕይወት ሰጠን::  ይህንን ህይወት ያገኘነው ጎበዝ ስለሆንም አይደለም የዓለምን ምናምንቴ መርጦ ደህንነትን ገለጠልንና  በጸጋ ዳንን::  ሃሌሉያ!!

የሰው እጅ በሰራው ውስጥ አልኖርም ሲል ሁሉንም አጠናቆ ሰርቶ አንዳችም የምንመካበት የሌለን መሆናችን እያየን ያለ እርሱም አንዳች ማድረግ እንደማንችል አውቀን በእርሱ እንመካ! እንደገፍበት: እንጣልበት በዚህ ድንቅ ጌታ ላይ::  

ጸሎት

አባት ሆይ ክርስቶስን ከሙታን ስታስነሳው እኔንም ከእርሱ ጋር አስነስተህ ህይወትን ስለሰጠኸኝ ተባረክ::  ይህ የተሰጠኝ ህይወት ዘላለማዊ ነው ሞትም አይወስደውም የህይወት ህግ እንጂ የሞት ወይም የሐጥያት ህግ በእኔ አይሰራም!  ህይወት እንዲበዛልንና እንዲትረፈረፍልን አንተ መተሃል::  ጌታዬ ሆይ ተባረክ! አሜን!

22.  ከእግዚአብሔር ጋር የታረኩኝ ነኝ!

2 ቆሮንቶስ 5:18፤ ነገር ግን የሆነው ሁሉ፥ በክርስቶስ ከራሱ ጋር ካስታረቀን የማስታረቅም አገልግሎት ከሰጠን፥ ከእግዚአብሔር ነው፤

እግዚአብሔር  እራሱ ታረቀኝ እውነታው ግን የሰው ልጅ ነበር ትዕዛዙን አፍርሶ የተባረረው::  መሆን የነበረበት ሰው እራሱ ነበር እግዚአብሔርን ፈልጎ መምጣትና ይቅርታ መጠየቅ  የነበረበት::  ይህ አለመሆኑ  ሳያንስ እራሱ እዳችንን ከፍሎ ወደቤቱ መለሰን ልያውም በተሻለ ክብር እርሱም ልጅ መሆን::  እንዴት ያለ ፍቅር ነው?! 

ወደቤቱ መመለሱና ከእኛ ጋር መታረቅ ሳያንስ ደግሞ ይህንን የማስታረቅ አገልግሎት ሰጠን::  በእኛ ውስጥ በሚኖረው በመንፈሱ ይህንን ያደርገዋል::  ሰውን ሁሉ ከእግዚአብሔር ጋር ታረቁ እንላለን::

ጸሎት

አባት ሆይ የጠፋሁትን ፈልገህ ስለታረከኝና  በቤትህ ስለተከልከኝ  አመሰግንሃለሁ::  ከኔ የሆነ አንዳንችም የለምና ክበርልኝ::  እኔ ከእግዚአብሔር ጋር የታረኩ ነኝ!  ክበር! ክበር ተመስገን!ሃሌሉያ!

23.  የተመረጠ ትውልድ፥ የንጉሥ ካህናት፥ ቅዱስ ሕዝብ፥ ለርስቱ   የተለየ ወገን ነኝ!

1 ጴጥሮስ 2:9፤ እናንተ ግን ከጨለማ ወደሚደነቅ ብርሃኑ የጠራችሁን የእርሱን በጎነት እንድትናገሩ የተመረጠ ትውልድ፥ የንጉሥ ካህናት፥ ቅዱስ ሕዝብ፥ ለርስቱ የተለየ ወገን ናችሁ፤

ጨለማችንን አብርቶ ወደ እራሱ የጠራን ጌታ ስሙ ይባረክ!  የጠራንም  የእርሱን በጎነት እንድንናገር ነው የመረጠን::  ተመርጠናል  ወደሚደነቅ ብርሃኑ ተጠርተናል:: የሆነልንን በራሳችን ማድረግ አንችልም!  ሆነልን እራሱ መርጦ ጠርቶ የራሱ አደረገን::

ጸሎት

አባት ሆይ ለዚህ ክብር ያበቃኸኝ አንተ ነህና ክብር ምስጋና ይገባሃል::  ከጨለማ አውጥተህ የተመረጠ ትውልድ፥ የንጉሥ ካህን፥ ቅዱስ ሕዝብ፥ ለርስትህ  የተለየ ወገን ስላደረከኝ ተመስገን:: ዘመኔን ሁሉ እገዛልሃለሁ::

24.  አገር አለኝ በሰማይያለኝ ነኝ!

ፊልጵስዩስ 3:20፤ እኛ አገራችን በሰማይ ነውና፥ ከዚያም ደግሞ የሚመጣ መድኃኒትን እርሱንም ጌታን ኢየሱስ ክርስቶስን እንጠባበቃለን፤

አገር  እንዲኖረኝ ያደረገው እራሱ ጌታ ነው::  እኔ የፈለገውን ባደርግ መግባት የማልችልበት ስፍራ በስራ ሳይሆን በእግዚአብሔር ልጅ ላይ ባለ እምነት የገባሁበት ነው:: በዚህ ምድር መጻተኛና ስደተኛ ነኝ ተመቻችቼ በዓለም ውጥንቅጥ ሳልጠላለፍ የሚመጣውን ተስፋዬን እየሱስን እጠባበቃለሁ::  እርሱን ስጠባበቅ አንዳችም ጸጋ አይጎድልብኝም ብቃቱን ሰቶኛል::  አሜን ዜግነቴንም በደሙ ታጥቤ በመንፈስ ቅዱስ  ታትሜ አረጋግጫለሁ::

ጸሎት

አባት ሆይ በዚች ምድር ስደተኛ ነኝ ስፍራ ባዘጋጀህበት በዛ ከአንተ ጋር እኖራለሁ:  ተመስገን አገሬ በሰማይ ነው:: ተመስገን እላለሁ እየተደነኩ!

25.  ከህያው ድንጋይ የተሰራሁ  መንፈሳዊ ቤት ነኝ!

1 ጴጥሮስ 2:5፤ እናንተ ደግሞ እንደ ሕያዋን ድንጋዮች ሆናችሁ፥ በኢየሱስ ክርስቶስ ለእግዚአብሔር ደስ የሚያሰኝ መንፈሳዊ መሥዋዕትን ታቀርቡ ዘንድ ቅዱሳን ካህናት እንድትሆኑ መንፈሳዊ ቤት ለመሆን ተሠሩ።

ለሁለት ምክንያት ነው መንፈሳዊ ቤት ለመሆን የምሰራው::  እርሱም 

1. በኢየሱስ ክርስቶስ ለእግዚአብሔር 

    ደስ የሚያሰኝ መንፈሳዊ መሥዋዕትን 

    ታቀርቡ ዘንድ 

2. ቅዱሳን ካህናት እንድትሆኑ 

መስዋእት ካለ የሚያቀርበው ካህን እንደሚያስፈልግ ግልፅ ነው::  ስለዚህም በብሉይ መስዋትን ወደ መቅደስ ይወስዱና  ለካህኑ ይሰጡታል እንዲያቀርብላቸው::  በአዲስ ኪዳን ወዴትኛውም መቅደስ አንሄድም አምልኮ በመንፈስና በእውነት እንጂ በስፍራ አይወሰንም:: እኛው ነን መቅደሱ::  መስዋቱም የእኛው አምልኮና ምስጋና ነው::  ካህንም ፍለጋ አንሄድም እኛኑ ካህን አደረገን:: 

ስለዚህ በእየሱስ መንፈሳዊ ቤት ሆነናል ደስ የሚያሰኘውን መስዋት እንሰዋለን መስዋእቱንም እንደካህን እናቀርባለን:: 

ጸሎት

አባት ሆይ አመሰግንሃለሁ  መንፈሳዊ ቤት  አደረከኝ ዕለት ዕለትም እየገነባኸኝ ስለሆነ ተመስገን::  የተወደደና የተቀደሰ አንተንም ደስ የሚያሰኝ መስዋትን በፊትህ የማቀርብ ካህን ስላደረከኝም አመሰግንሃለሁ!! ሃሌሉያ!

26.  መልካሙን ሥራ ለማድረግ የተፈጠርኩኝ ነኝ!

ኤፌሶን 2:10፤ እኛ ፍጥረቱ ነንና፤ እንመላለስበት ዘንድ እግዚአብሔር አስቀድሞ ያዘጋጀውን መልካሙን ሥራ ለማድረግ በክርስቶስ ኢየሱስ ተፈጠርን።

እኔ በክርስቶስ አዲስ ፍጥረት ነኝ አሮጌው አልፏል ሁሉ አዲስ ነው::  የቀደመው ማንነቴ ከጨለማው ነበርና ክፋት የሞላበት ነበረ::  በጌታ እየሱስ  የተፈጠረው ማንነቴ መልካም ማድረግ እንጂ ክፋት የለበትም:: አዲስ ማንነት!

አስቀድሞ ያዘጋጀውን መልካሙን ሥራ ለማድረግ ነው በክርስቶስ ኢየሱስ እኔ የተፈጠርኩት::  ዛሬ አይደለም ጌታ የሚያስበው ምን ታድርግልኝ ብሎ እርሱ ያቀደው  አስቀድሞ የምመላለስበትን ጎዳና አዘጋጅቷል::  ሃሌሉያ!   እርሱ አስቦ ወለደኝ አስቦበትም አባት ሆነኝ:: 

ጸሎት

አባት ሆይ አንተ ፍቅር ነህ!  አደራረግህ ሁሉ ይገርማል አሰራርህም ግሩም ነው::  በእኔ ውስጥ ስለፈጠርከው ማንነት ተመስገን ከእኔ አይደለምና መልካም ማድረግ ከአንተ ነው ተመስገን!  ይህንን ማንነት ማንም መለወጥ አይችልምና ስለታተመው አዲስ ማንነት አከብርሃለሁ::  እኔም እራሴ ብሆን መለወጥ አልችልም::  መልካምነትን ያገኘሁት ከአንተ ነውና ክበር::  አሁንም መልካሙን በእኔ የጀመርከውን ስራ እስከፍፃሜው ስለምትቀጥለው ተመስገን::  ጠላቴ እፈር!  አሜን!

27.  ከኃጢአት አርነት የወጣሁ ነኝ!

ሮሜ 6:17-18፤ ነገር ግን አስቀድማችሁ የኃጢአት ባሪያዎች ከሆናችሁ፥ ለተሰጣችሁለት ለትምህርት ዓይነት ከልባችሁ ስለ ታዘዛችሁ፥ ከኃጢአትም አርነት ወጥታችሁ ለጽድቅ ስለ ተገዛችሁ ለእግዚአብሔር ምስጋና ይሁን።

ቀላል ነገር ይመስላል ከኃጢአት አርነት መውጣት ነገር ግን ሁሉን ከስሩ አድርጎ ማን አለብኝ የሚል ነበር::  እየሱስ ግን የእግዚአብሔር በግ ሆኖ መቶ እንደ በግ ታረደና የኃጢአታችንን ዋጋ  ሁሉ ስለከፈለው ነው ዛሬ በነፃነት ከኃጢአት አርነት ወጥቻለሁ ማለት የቻልኩት::

በራሴ  እንዳላደረኩት ማስተዋልና በጌታ ላይ ተደግፌ መራመድ አለብኝ::  ጠላት ይህን አደረግሽ ያንን አደረግሽ እያለ የሚከሰኝ ስራ ሊያሰራኝና ከጌታ ጸጋ  ሊያወጣኝ ነው::  ስራው ተሰርቶ አልቋል ጌታዬ ከፍሎልኛል እኔ የምጨምርበት ምንም የለም ይህ ህይወት በእኔ ያብባል::  በሁኔታዎች የሚለዋወጥ  ማንነት  አይደለም የተቀበልኩት::  ጠላት የማታለሉን ስራ እየሰራ ዘመኔን እንዳይፈጀው መጠንቀቅ አለብኝ::  በአእምሮዬ መታደስ መለወጥ አለብኝ::  ይህ ማንነቴ በውስጤ እየደመቀ መምጣትና ከኔ አሳብ ጋር መዋሃድ አለበት:: 

ጸሎት

አባት ሆይ ከኃጢአት አርነት ስላወጣኸኝ አመሰግንሃለሁ::  ይህ ማንነቴ ነው!! የሚከሰኝና የሚኮንነኝም የለም አዲስ ፍጥረት አድርገኸኛል::  ተመስገን! በዚህ እውነት ውስጥ ስር ልስደድ በአእምሮዬም መታደስ ልለወጥ:: ጠላቴን ኩምሽሽ  ስላደረከው ተመስገን በእኔ ዘንድ አንዳችም የለውም!!  ጸጋህን ስጠኝ::  አሜን!

28.  የሞትኩኝ ነኝ!

ቆላስይስ 3:3፤ ሞታችኋልና፥ ሕይወታችሁም በእግዚአብሔር ከክርስቶስ ጋር ተሰውሮአልና።

ሞትን ከእግዚአብሔር አንፃር ስናስብ መለየት ነው::  አዳምና ሄዋን ሞቱ ሲባል በስጋ አልነበረም ነገር ግን በመንፈስ የሞቱ ሆኑና ከእግዚአብሔር ተለዩ::  አሁንም መሞት ሲባል ከዓለም መለየትና ለጌታ መኖር ነው::

ይህ አባባል ቀልድ ቢመስልም እንኳን መልክቱ ይገርመኛል “የዘንድሮ ክርስትያን ሙት ሲባል ፌንት ያደርጋል” የሚለው::  መሞት ማለት ከአንድ ቦታ መለየትና በሌላ ቦታ መገኘት ነው ስለዚህ ለዓለም ሞተን ከክርስቶስጋር መሰወር ሆኖልናል::

ይህንን እውነት እናስተውል ክርስትና የምንኖረው ነው እንጂ የምንለውጠው ወይም ማሻሻያ ማድረግ የምንችለው አይደለም የእግዚአብሔር ቃል እንዲህ ናችሁ ሲለን እሺ ብለን መኖር እንጂ እስኪ ልየው ብለን በማየት አንመላለስም በእምነት ነው::  ደህንነትን ስንቀበል ወደ እግዚአብሔር መንግስት ፈልሰናል ግን የተፈራረምነው ነገር የምናሳየው መረጃ ምንድነው?  የለንም በእምነት ግን እርግጠኞች ነን::  እንደዚሁ መሞቴንና በጌታ ውስጥ የሰወረኝ  ስስት የሚያደርገኝ ልጁ ነኝ ብለን እንመን:: በላይ ያለውን እናስብ እንጂ በምድር ያለውን አይደለም::

ጸሎት

አባት ሆይ ተመስገን ለዓለም ሞቼ ለአንተ የተለየሁ ስላደረከኝ ተመስገን::  ህይወቴን በክርስቶስ ውስጥ ስለሰወርከው ተመስገን አሁንም አንተው ክበርበት::አሜን!

29.  ፍርሃት የሌለኝ ነኝ

2 ጢሞቴዎስ 1:7፤ እግዚአብሔር የኃይልና የፍቅር ራስንም የመግዛት መንፈስ እንጂ የፍርሃት መንፈስ አልሰጠንምና።

ፍርሃት ሰውን የሚያስር የመንፈስ አሰራር ነው::  ጠላትም የሚጠቀምበት ነው::  ለዚህ ነው እግዚአብሔር እንዳንጠቃበት 

–  የኃይል

–  የፍቅር 

–  ራስንም የመግዛት መንፈስ 

የሰጠን::  የፍርሃት መንፈስ በእርሱ ዘንድ የለም ማንን ይፈራል?  እኛም እንድንፈራ አይፈልም::  የመጨረሻውን ውሳኔ የሚወስን የእኛ አባት ነው::  እንመነው ይህንን ጌታ በሰጠን በመንፈሱ እንጏደድና እርፍ እንበል ወደእኛ የሚመጣውን ጠላት የሚያስፈራራበትን ነገሩን ሁሉ ወደ ጌታ እግር ስር እያመጣን እንጣለው እንጂ እንዳንሸከም::

ጌታ በሰጠን ኃይል እንደገፍ

በሰጠን ፍቅር ሁሉን እንውደድ::  

ፍጹም ፍቅር ፍርሃትን አውጥቶ ይጥለዋል::  አብረው አይሄዱም እንደብርሃንና ጨለማ የአንዱ መገኘት የሌላውን አለመኖር ያረጋግጣል::

እንዲሁም ምንም አይመጣምና እራሳችንን እንግዛ::  ተናደን አቅላችንን መሳት የለብንም::  አንድ ቁጫጭ ዛሬ ሳልገልሽ አልመለስም ብላ ብትሳደብ ምን ያህል ያስፈራና ያናድደኛል? በምንም አይነት አያስቆጣኝም ወይም ያስቀኛል::  

ጠላትም የተረታ ከእግራችን በታች የወደቀ መንፈስ ነው የቀረለት ሽንገላ ብቻ::  ዙሪያችንን እንዳበሳ ይዞራል አንበሳው ግን በእኔ ውስጥ ይኖራል::  ሃሌሉያ! 

ጸሎት

አባት ሆይ ተመስገን እንዳልረታብህ መንፈስህን ስለሰጠኸኝ ተባረክ! አሜን!

30.  በግንዱ ላይ የምኖር ብዙ ፍሬ  የማፈራ ቅርንጫፍ ነኝ!

ዮሐንስ 15:5፤ እኔ የወይን ግንድ ነኝ እናንተም ቅርንጫፎች ናችሁ። ያለ እኔ ምንም ልታደርጉ አትችሉምና በእኔ የሚኖር እኔም በእርሱ፥ እርሱ ብዙ ፍሬ ያፈራል።

እየሱስ የወይን ግንድ ለቅርንጫፎች ሁሉ ምግብን የሚሰጥ ነው::  በዚህ ግንድ ላይ ያለ አሳብ ነው ቅርንጫፎች የሚኖሩት አይዘሩም አያጭዱም አይቆፍሩብ ብቻ ይኖራሉ ግንዱን ተማምነው::  ግን ጎደለብኝ ብለን ለመዝራትና ለመቆፈር ብንነሳ ደርቀን በዛው መቅረት ነው::  ይህንን እንድናደርግ ነው ጠላት የሚያዋክበን ተረጋግተን በጌታ እርፍእንበል::  

ስለዚህ በግንዱ ላይ መጣበቅና  ያለእርሱ አንዳች እንደማናደርግ አውቀን መደገፍ አለብን::  ጥረት ግረት የሌለበት እድገትን በእርሱ ላይ በመደገፍ ብቻ እናገኛለን:: እድገት ካለ ፍሬ ማፍራት አለ በእርሱ ደግሞ ብዙ ፍሬ ነው የሚፈራው::

ጸሎት

አባት ሆይ በእየሱስ ላይ እንደቅርንጫፍ ስለተከልከኝ ብዙ እንዳፈራም ስለሰጠኸኝ ተመስገን!  ዛሬም ውሳኔዬ በአንተ ላይ መጣበቅ ነው::  አሜን!

31.  የማስታረቅ አገልግሎት የተሰጠኝ ነኝ!

2 ቆሮንቶስ 5:18፤ ነገር ግን የሆነው ሁሉ፥ በክርስቶስ ከራሱ ጋር ካስታረቀን የማስታረቅም አገልግሎት ከሰጠን፥ ከእግዚአብሔር ነው፤  19፤ እግዚአብሔር በክርስቶስ ሆኖ ዓለሙን ከራሱ ጋር ያስታርቅ ነበርና፥ በደላቸውን አይቆጥርባቸውም ነበር፤ በእኛም የማስታረቅ ቃል አኖረ።

ክርስትናን ከሌላው እምነት የሚለየው ትልቁ ነገር የመኖር ዘይቤ አይደለም አምላካችን የሰጠን::  ዋጋውን ከፍሎ እዳችንን አስወግዶ ከእራሱ ጋር አስታርቆ ተቀበለን ልክ ምንም እርም እንደሌለን ጻድቅ አድርጎ::  

መቀበል ብቻ አይደለም ዋጋው ተከፍሏልና ለሰው ልጅ በሙሉ ተናገሩ::  ምን ብለን እንናገር?  እግዚአብሔር እንታረቅ ይላል እርሱ ሁሉን ይቅር ብሎ እየጠበቀ ነው ብለን ማወጅ::  ዛሬም በእኛ ውስጥ እየሱስ የማስታረቁን ስራ ቀጥሏል::

ጸሎት

አባት ሆይ ተመስገን እኔ ከአንት ጋር ታርቄ ታረቁ የሚልን አገልግሎት ስለሰጠኸኝ::  አሁንም አባቴ ሆይ በምደርስበት ስፍራ ሁሉ ከእግዚአብሔር ታረቁ እያልክ እራስህ እንድታውጅና የሰዎችንም ልብ እንደ ሊድያ ልብ እንድትከፍት  መንግስትህ እንዲሰፋ እፀልያለሁ:: አሜን!

32.  ክርስቶስ በሚሰጠኝ ኃይል ሁሉን የምችል ነኝ።

ፊልጵስዩስ 4:13፤ ኃይልን በሚሰጠኝ በክርስቶስ ሁሉን እችላለሁ።

እኔ በራሴ አንዳች ማድረግ የማልችል ነኝ::  ለዚህም ነው በወይኑ ግንድ ላይ የተተከልኩኝ ቅርንጫፍ የሆንኩት::  ቅርንጫፍ በራሱ ምንም አያደርግም መድረቅ ነው የሚቀርለት  ከግንዱ ሲለይ::  

እኔም እንደዚሁ ከጌታ በሚሰጠኝ  ኃይል ነው ኑሮዬን የምኖረውና ሁሉንም የምችለው::  ኃይል የሚሰጠኝ  በራሴ ቆሜ (ኢንዲፐንደንት) እንድሆን አይደለም ሁልጊዜም በእርሱ ውስጥ እንድኖር ነው እንጂ::  ኃይል ተሰቶኛል በቃ ልሂድና ኑሮዬን ልኑር  እንድልም አይደለም ነገር ግን ሁልጊዜ በእርሱ ላይ ተደግፌ ዕለት ዕለት ኃይልን እየተቀበልኩ የምቀጥለው ኑሮ ነው::  እስራኤላውያን መናን በየዕለቱ ይለቅሙ እንደነበረው ብዙ ቢለቅሙም ለነገ አይሆንም ነበር::  በእርሱ ላይ መታመንን ሊያስተምራቸውና መሪ ሊሆናቸው ነበር እነርሱ ግን ሰለቸን አሉት::  ለኔ ግን ምን አይነት እድል ተሰጠኝ ወደፊቱ ቀርቤ ድካምን የማሸንፍበት ኃይል መቀበል መቻል?! ክርስትና ዕለት በዕለት የሚኖር ነው::  

ስለዚህ በማልፍበት ጎዳና ሁሉ ኃይልን በሚሰጠኝ በክርስቶስ ሁሉን እችላለሁ። 

ጸሎት

አባት ሆይ ተመስገን ኃይልን ስለሰጠኸኝ::  ምንም ቢመጣ በህይወቴ አያስፈራኝም የሚረታኝም የለም:: ዛሬም ኃይልን ስጠኝ::  ጸጋህንም ሙላኝ!  አሜን!

33.  ድምጹን የምለይና የምሰማ ነኝ!

ዮሐንስ 10:3፤ ለእርሱ በረኛው ይከፍትለታል፤ በጎቹም ድምፁን ይሰሙታል፥ የራሱንም በጎች በየስማቸው ጠርቶ ይወስዳቸዋል።

ይህ ማንነቴ ነው!  እርሱን ለይቼ መስማት!!  ይህንን ነገር ለማምጣት ምንም የማደርገው ነገር የለም በፊቱ በፀሎት መገኘት ብቻ ነው::  

በእግዚአብሔር መንፈስ የሚመሩ እነዚህ የእግዚአብሔር ልጆች ናቸው እንደሚል ቃሉ እኔ እረኛና አባት አለኝ:: ይህ እረኛ በስሜ ይጠራኛል – የሚገርም አይደል?!  ከዚህ ሁሉ ሰራዊት ለይቶ ያውቀኛል::   

ጸሎት

አባት ሆይ ተመስገን አንተን የምሰማበትን ብቃት ስለሰጠኸኝ አመሰግንሃለሁ!  አባት ሆይ እከተልሃለሁ! አንተ የእኔ እረኛ ተባረክ ወደ ለመለመ መስክ ሁሉ ስለምታሰማራኝ አንዳችም ስለማይጎድልብኝ ክበር ተመስገን! አሜን!

34.  ጌታን ብቻ እየሰማሁ የምከተል ነኝ!

ዮሐንስ 10:4፤ የራሱንም ሁሉ ካወጣቸው በኋላ በፊታቸው ይሄዳል፥ በጎቹም ድምፁን ያውቃሉና ይከተሉታል፤

5፤ ከሌላው ግን ይሸሻሉ እንጂ አይከተሉትም፥ የሌሎችን ድምፅ አያውቁምና።

ከእየሱስ በቀር አሳቹን አልሰማም ደግሞም አልከተልም::  የእየሱስን ድምጽ የመስማት ብቃት አለኝ ይህንንም ብቃት ከእርሱ በመወለድ አገኘሁኝ::  ጠላት እንዴት እለያለሁ የእግዚአብሔርን ድምፅ እያልኩኝ እንድጨነቅና እንድጠራጠር ይፈልጋል::  ጌታዬ ግን የሚናገረኝ በቃሉ ነው::  አዲስ ነገር አይናገርም አይኮንነኝም ንስሃ እንድገባ ስህተቴን አሳይቶ ወደ ንስህ ያመጣኛል::  ዝም ብሎ የሚተገትግና የሚያዋርድ ግን የጠላት ድምፅ ነው::  ለዚህ ነው በአእምሯችን መታደስ መለወጥ ያለብን::  ቃሉን ባወቅን መጠን የጠላት ሽንገላ እርቃኑን ይቀራል::  ቃሉ ውስጣችንን ይለውጣል ያቀናል በሰላምና ደስታ ይሞላናል::

ጸሎት

ጌታዬ ሆይ አንተን ብቻ የምሰማ ነኝና ተምስገን!  እረኛዬ ክበርልኝ ጠብቀኝ ብዬ ዛሬ አላስታውስህም ልክ እንደአይንህ ብሌን ትጠብቀኛለህ::  ክብር ይብዛልህ!  አሜን!

35.  ለአዲስ ኪዳን አገልጋይ ነኝ!

2 ቆሮንቶስ 3:6፤ እርሱም ደግሞ በመንፈስ እንጂ በፊደል ለማይሆን ለአዲስ ኪዳን አገልጋዮች እንሆን ዘንድ አበቃን፤ ፊደል ይገድላልና መንፈስ ግን ሕይወትን ይሰጣል።

ህይወትን በሚሰጠው በእግዚአብሔር መንፈስ ለዚህ አዲስ ኪዳን ብቁ ሆንኩኝ ከኔ የሚጨመር ምንም የለም::  በቃሉ እንደሚል እናንተም በሕያው እግዚአብሔር መንፈስ እንጂ በቀለም አይደለም፥ ሥጋ በሆነ በልብ ጽላት እንጂ በድንጋይ ጽላት ያልተጻፈ፥ በእኛም የተገለገለ የክርስቶስ መልእክት እንደ ሆናችሁ የተገለጠ ነው። በክርስቶስም በኩል ወደ እግዚአብሔር እንዲህ ያለ እምነት አለን። ብቃታችን ከእግዚአብሔር ነው እንጂ፥ በገዛ እጃችን እንደሚሆን አንዳችን እንኳ ልናስብ ራሳችን የበቃን አይደለንም::  በእውነትም አይደለንም!

ጸሎት

አባት ሆይ በራስህ አሰራር ልቤን ቀይረህ የአዲስ ኪዳን አገልጋይ ስላደረከኝ አመሰግንሃለሁ::  አሜን!

36.  ለበጉ ሰርግ የተዘጋጀሁ ነኝ!

ራእይ 19:7፤ የበጉ ሰርግ ስለ ደረሰ ሚስቱም ራስዋን ስላዘጋጀች ደስ ይበለን ሐሤትም እናድርግ ክብርንም ለእርሱ እናቅርብ።

እየሱስ ስፍራ አዘጋጅቶ እርሱ ባለበት እንድንኖር ሊወስደን ይመጣል::  ይህ የሰርግ ግብዣ በጣም በትልቁ ነው አምላካችን እየተዘጋጀበት ያለው የሚፈፀምና የሚሆን ነው::  

እንደነዛ ልባም ቆነጃጅት የተዘጋጀንና በር በሩን የምናይ እንሁን እንጂ ይህንን ዓለም አንምሰል::  ጌታ ሊመጣልን በደጅ ነው::  መምጣቱንም ወንጌልን እየሰበክን እናቻኩል::   በሰማይ አገር አለን ከዛም የሚመጣ ሙሽራና ንጉስ እንጠብቃለን::  እርሱ ሲመጣ ነገር ሁሉ ይለወጣል ትንሽ ጠብቅ ብሎ ዮናይት ኔሽን አያቆመውም ወይም ምንም ኃይል የሚያቆመው የለም::  አባት በፈቀዳት በዛች ጊዜና ሰዓት ላይ ይመጣል መሲሁ::  አሜን!

ጸሎት

ማራናታ!!

የይሁዳ መልእክት

መግቢያ:-

ይህ በአለአንድ ምዕራፍ ደብዳቤ የተፃፈው በይሁዳ ነው::  ይህ ሰው የጌታ የእየሱስ ወንድም ነው እራሱን ግን የሚጠራው የያዕቆብ ወንድም ብሎ ነው::  ከወንድምነቱ ይልቅ እራሱን የኢየሱስ ክርስቶስ ባሪያ ብሎ ነው የሚጠራው::  የፃፈበትንም ምክንያት ሲናገር እማኞች ሳይሆኑ አማኝ መስለው የሐሰት ትምህርት ከሚያስተምሩ እንዲጠበቁ ለማስጠንቀቅ የተፃፈ ነው:: እግዚአብሔር ለመዳን አንድ ጊዜ በተሰጠው እምነት እንዲፀኑ ይመክራል::

ይሁዳ 1: 1-2

1፤ የኢየሱስ ክርስቶስ ባሪያ የያዕቆብም ወንድም የሆነ ይሁዳ፥ በእግዚአብሔር አብ ተወደው ለኢየሱስ ክርስቶስም ተጠብቀው ለተጠሩ፤

2፤ ምሕረትና ሰላም ፍቅርም ይብዛላችሁ።

ምንም እንኳን የጌታ ወንድም ቢሆንም እራሱን ባሪያ ብሎ በትህትና መጥራቱ ደስ ይላል:: በማቴዎስ 13:55፤ ይህ የጸራቢ ልጅ አይደለምን? እናቱስ ማርያም ትባል የለምን? ወንድሞቹስ ያዕቆብና ዮሳ ስምዖንም ይሁዳም አይደሉምን?

ጌታ እየሱስም ስለቤተሰብ ሲናገር በማርቆስ 3:34፤ በዙሪያው ተቀምጠው ወደ ነበሩትም ተመለከተና፦ “እነሆ እናቴ ወንድሞቼም። 35፤ የእግዚአብሔርን ፈቃድ የሚያደርግ ሁሉ፥ እርሱ ወንድሜ ነው እኅቴም እናቴም፡” አለ። የእግዚአብሔርን ፈቃድ ከማድረግ ጋር ነው ያገናኘው:: ይሁዳም ይህንኑ ነው ያደረገው::

የፃፈውም በእግዚአብሔር አብ ተወደው ለኢየሱስ ክርስቶስም ተጠብቀው ለተጠሩ፤ እያንዳንዳችን በእግዚአብሔር አብ ተወደናል:: እንዲሁም መወደድ ብቻ ሳይሆን ለኢየሱስ ክርስቶስም ተጠብቀናል::

ምሕረትና ሰላም ፍቅርም ይብዛላችሁ።

ይሁዳ 1: 3-4

3፤ ወዳጆች ሆይ፥ ስለምንካፈለው ስለ መዳናችን ልጽፍላችሁ እጅግ ተግቼ ሳለሁ፥ ለቅዱሳን አንድ ጊዜ ፈጽሞ ስለ ተሰጠ ሃይማኖት እንድትጋደሉ እየመከርኋችሁ እጽፍላችሁ ዘንድ ግድ ሆነብኝ።

4፤ ከብዙ ጊዜ በፊት ለዚህ ፍርድ የተጻፉ አንዳንዶች ሰዎች ሾልከው ገብተዋልና፤ ኃጢአተኞች ሆነው የአምላካችንን ጸጋ በሴሰኝነት ይለውጣሉ ንጉሣችንንና ጌታችንንም ብቻውን ያለውን ኢየሱስ ክርስቶስን ይክዳሉ።

የይሁዳን መልእክት ያስቀየረው መንፈስ ቅዱስ ነው እርሱ መፃፍ የፈለገው ስለተቀበልነው ደህንነት ሆኖ ሳለ ጌታ ደግሞ የፈለገው በሃይማኖት ስለመጋደል ነው እንዲፅፍ ግድ ያለው::  

ለምንድነው ስለ ተሰጠን ሃይማኖት መጋደል ያለብን?  ይህ እምነት ወይም ሃይማኖት አንድ ጊዜ ተሰቶናል መጋደልን ምን አመጣው? ጌታ የሚያውቀውና የሚያየው ነገር ስላለ ነው እንዲፃፍልን ያደረገው::

በመፅሃፉ መግቢያ እንደነገረን በጌታም ተወደንና ለክርስቶስ እንደሚገባ ሆነን ተጠብቀናል ::  የሚጠበቅ ነገር ዋጋ አለው::  አንድ ዳይመንድ የሚሸጥበት ሱቅ ብንሄድ በካሜራ እንዲሁም ሴኩሪቲ ሲስተሙ ከተነካ ከፖሊስ ጋር የተገናኘ ነው ግን ምስኪን ሱቅ ስንሄድ እንደዛ  አይደለም:: የሚጠበቀው ውስጡ ካለው ሃብት የተነሳ ነውና እኛም ውስጥ ክርስቶስ ስላለ አብ ልጁን በእኛ ውስጥ እያየ ወዶን ያስጠብቀናል ለመምጣቱ የተዘጋጀን እንድንሆንና በጠላት እንዳንዘረፍ  ያስጠብቀናል::  ዋጋችን ከፍ ያለ ነው!!

እርሱ እንደዚህ እያስጠበቀን ነውና እኛም እንተባበር::  የህይወታችን ዋጋ ከፍ ያለ ነውና እንጋደል::  መጋደል የአንድ ጊዜ ትዕይንት አይደለም ቀጣይነት ያለው ነው::  ባላጋራችን ዲያቢሎስ  በዙሪያችንን ይዞራል ያለ እረፍት ስለዚህ የነቃን ስር የሰደድን እንሁን:: በቆላስይስ 2:7፤ ሥር ሰዳችሁ በእርሱ ታነጹ፥ እንደ ተማራችሁም በሃይማኖት ጽኑ፥ ምስጋናም ይብዛላችሁ።

እንደሚገባ በቃሉ የማይኖሩ ቃሉንም እንደወደዱ የሚያጣምሙ ከብዙ ጊዜ በፊት ለዚህ ፍርድ የተጻፉ አንዳንዶች ሰዎች ሾልከው ገብተው እንዳያታልሉን እንጠንቀቅ::  በስተመጨረሻ አላውቃችሁም የሚባሉ ናቸውና ደህንነታችንን ዕለት ዕለት እንጠብቅ:: 

ኃጢአተኞች ሆነው የአምላካችንን ጸጋ በሴሰኝነት ይለውጣሉ::  ይህንን በብዙ መልኩ እያየን ነው በስጋ የማደርገው ኃጥያት ምንም አይደለም የጸጋ ዘመን ነው እያሉ የከበረውን የሚያስጥሉ አሉና ቅድስና ለእግዚአብሔር ልንል ይገባል ይህ ስጋችን የመንፈስ ቅዱስ ማደርያ ነውና በቅድስና መጠበቅ አለበት:: ይህነው መጋደል ፋራ አመነፈስሽው ሊያስብል ቢችልም ጸጋውን እንዳናጣጥል እንጠንቀቅ::  በማይመች አካሄድ እንዳንጠላለፍ እንጠንቀቅ::

ደግሞም እኛም አምላክ ነን የሚሉ እያደረጉ ያሉት ነገር ንጉሣችንንና ጌታችንንም ብቻውን ያለውን ኢየሱስ ክርስቶስን መካድ ነው። እርሱ ብቻ አምላክ ነውና ከምንሰማው እየተጠነቀቅን መጋደላችንን እንቀጥል::  

የጌታ ጸጋ ይብዛልን!

ይሁዳ 1:5፤ ዳሩ ግን ሁሉን አንድ ጊዜ ፈጽሞ ምንም የተማራችሁ ብትሆኑ ጌታ ከግብፅ አገር ሕዝቡን አድኖ የማያምኑትን በኋላ እንዳጠፋቸው ላሳስባችሁ እወዳለሁ።

በእምነት ተጋደሉ የሚለውን ለማጉላት እግዚአብሔር የማያምኑትን እንዴት እንዳጠፋ እንድናስተውል ይነግረናል:: ከግብፅ ህዝቡን ለምንና እንዴት አዳነ? በዘጸአት 3:9፤ አሁንም እነሆ የእስራኤል ልጆች ጩኸት ወደ እኔ ወጣ፤ ግብፃውያንም የሚያደርጉባቸውን ግፍ ደግሞ አየሁ። 10፤ አሁንም ና፥ ሕዝቤን የእስራኤልን ልጆች ከግብፅ ታወጣ ዘንድ ወደ ፈርዖን እልክሃለሁ።” ብሎ ሙሴን ላከ:: ሲያወጣቸውም በኃይልና በተዘረጋች ክንድ ነበረ::  ሊያወጣቸውም የመጣበት ምክንያት ቃሉን ለመጠበቅ ነው ለአብርሃም ቃል ገብቶ ነበረና::  ምን የሚል ቃል?  ትውልድህ ባሪያ ይሆናል ግን አወጣቸዋለሁ ሌላኛው ተስፋ ደግሞ በአንተ የምድርን ህዝብ ሁሉ እባርካለሁ የሚል መሲሁን የሚያመጣበት መንገድ ነበረና ነው::  

እግዚአብሔርም እንደተናገረው ሲያደርግ ህዝቡ ግን አመጹበት በእርሱ ላይ መደገፍና መታመን  አልቻሉም::  አንዴ ወደ ግብጽ እንመለስ ብለው አለቃ ሲሾሙ አንዴ መቀበርያ ስለሌለ በእዚህ እንድንሞት ነው ያመጣኸን ሲሉ ሌላ ጊዜ መና ሰለቸኝ እያሉ ቅዱሱን መንፈስ አስመረሩት:: በዚህም የተነሳ የተስፋይቱን ምድር አያዮም ብሎ አለ::  በዘኍልቍ 14:22፤ በግብፅ ምድርና በምድረ በዳ ያደረግሁትን ተአምራቴንና ክብሬን ያዩ እነዚህ ሰዎች ሁሉ አሥር ጊዜ ስለ ተፈታተኑኝ፥  23፤ ነገሬንም ስላልሰሙ፥ በእውነት ለአባቶቻቸው የማልሁላቸውን ምድር አያዩም፤ ከእነርሱም የናቀኝ ሰው ሁሉ አያያትም፤ እንዳለው እንዲሁ ዛሬ የምናምን እንሁን::  

እነዚህ ሰዎች ወደ ተስፋይቱ ምድር ያልገቡት በራሳቸው ችግር ነው እንጂ እግዚአብሔር ስላልፈለጋቸው ወይም አሳቡን ለውጦ አይደለም::  እዚህም ስፍራ ላይ ሀሰተኞች ሾልከው ገብተው የአምላካችንን ጸጋ በሴሰኝነት ይለውጣሉ እንዲሁም ብቻውን ጌታ የሆነውን እየሱስን ይክዳሉ::  እንግዲህ የተሰጠንን ይህንን መዳን ችላ ብንልና ባንጋደል እኛው ነን ከህይወት የምንጎድለው::  እግዚአብሔር እጁን ከፍቶ ከኃጥያታችን በልጁ ደም አንጽቶ አድኖን ልጆቹ አድርጎናልና የጊዜውን ነገር እየናቅን በጌታ ስር ሰደን ቃሉን በልባችን እየሸሸግንና እየታዘዝን እንመላለስ:: ሌሎችንም እናንቃ!

የጌታ ጸጋ ይብዛልን!

ይሁዳ 1: 6-7

6፤ መኖሪያቸውንም የተዉትን እንጂ የራሳቸውን አለቅነት ያልጠበቁትን መላእክት በዘላለም እስራት ከጨለማ በታች እስከ ታላቁ ቀን ፍርድ ድረስ ጠብቆአቸዋል። 7፤ እንዲሁም እንደ እነርሱ ዝሙትን ያደረጉና ሌላን ሥጋ የተከተሉ ሰዶምና ገሞራ በዙሪያቸውም የነበሩ ከተማዎች በዘላለም እሳት እየተቀጡ ምሳሌ ሆነዋል።

ይሁዳ የሚሰጠን ሌላኛው ምሳሌ ደግሞ መኖሪያቸውንም ስለተዉት መላእክት ነው::   እነዚህ መልአክት መሆን የሌለባቸውን ሆነዋል ወይም ማድረግ የሌለባቸውን አድርገዋል ስለዚህም ምክንያት ከጨለማ በታች እስከ ታላቁ ቀን ፍርድ ድረስ ጠብቆአቸዋል።

በዘፍጥረት 6:2፤ የእግዚአብሔር ልጆችም የሰውን ሴቶች ልጆች መልካሞች እንደ ሆኑ አዩ፤ ከመረጡአቸውም ሁሉ ሚስቶችን ለራሳቸው ወሰዱ።  ስለነዚህ ይሆን ክፍሉ የሚያወራው?  ምክንያቱም  የሚቀጥለው ቁጥር ከዝሙትጋር ግንኙነት እንዳለው ያስረዳ “እንዲሁም እንደ እነርሱ ዝሙትን ያደረጉና” ብሎ ስለሰዶምና ጎሞራ ያወራል::   በዚህ ምክንያት ይሆን የውሃ ጥፋት የመጣውና ኖህንና ቤተሰቡን ብቻ ያስቀረው፤ እግዚአብሔርም ሰውን በመፍጠሩ የተፀፀተው እዚህ ጋር ነው::  

የሚቀጥለው ምሳሌ ወይም ሌላው በእግዚአብሔር የተቀጡት ይሁዳ እንደሚለን ሌላን ሥጋ የተከተሉ ሰዶምና ገሞራ በዙሪያቸውም የነበሩ ከተማዎች በዘላለም እሳት እየተቀጡ ምሳሌ ሆነዋል ይላል::  ሰው በብዛት ስለተቀበለው ወይንም ደግሞ እየበዛ ስለመጣ ይህ የተመሳሳይ ጾታ ግንኙነት እንዳንለዝብና እንዳናመቻምቸው ሐጥያት ነው እግዚአብሔርም የፈረደው በእሳት በማጥፋት ነው ዛሬም ውሳኔው አይለወጥም::

ይህ የሚያሳየው እግዚአብሔር መለየታችንን መቀደሳችንን ቃሉን መጠበቃችንን ይፈልጋልና ጠላትና ዓለም በፊታችን የሚያመጡትን እየናቅን በጸጋው እንቁም መጋደላችንንም እናብዛ:: እርሱ ክርስቶስ ብቻውን ጌታ እንደሆነ ሁሉ ይወቅ እንጂ አሁን በዘመኑም እንደሚባለው እኛ አምላክ አይደለንም ፍጥረት ነን እርሱ ብቻውን ከፍ ያለ ሁሉን የፈጠረ የሁሉ መገኛ ጌታና ንጉስ ነው::  አሜን!

ይሁዳ 1: 8-10

8፤ እንዲሁም እነዚህ ሰዎች ደግሞ እያለሙ ሥጋቸውን ያረክሳሉ ጌትነትንም ይጥላሉ ሥልጣን ያላቸውንም ይሳደባሉ። 9፤ የመላእክት አለቃ ሚካኤል ግን ከዲያብሎስ ጋር በተከራከረ ጊዜ ስለ ሙሴ ሥጋ ሲነጋገር፦ “ጌታ ይገሥጽህ፥” አለው እንጂ የስድብን ፍርድ ሊናገረው አልደፈረም። 10፤ እነዚህ ግን የማያውቁትን ሁሉ ይሳደባሉ፥ አእምሮም እንደሌላቸው እንስሶች በፍጥረታቸው በሚያውቁት ሁሉ በእርሱ ይጠፋሉ።

እነዚህ ሰዎች ህልም ውስጥ ናቸው የራሳቸውን የምናብ ዓለም ፈጥረው ከእውነታ ርቀዋል::  ስለዚህም ስጋቸውን እያረከሱ በቤተክርስቲያንም የተሾሙትን ይሳደባሉ::  ለእርምት እንኳን ስፍራ የላቸውም ሁሉን ይንቃሉ እነርሱ ብቻ ያሉት ነው ትክክል የሚመስላቸው::  አሁን ያለው የቤተክርስቲያን ችግር ይህ ነው ሀይ ባይ ማጣት እና ድፍረት የተሞላበት ሆንዋል::  ስልጣንንም አያከብሩም ብሎ የመላእክት አለቃ ሚካኤል ጋር እያወዳደረ ይናገራል::  ሚካኤል ግን ሰይጣንን  እንኳን አልተሳደበም::  የወደቀውን የተጣለውን ከስልጣኑ የተነሳውን እግዚአብሔርን የተቃወመውን::  ያለው አንድ ነገር ነው  “ጌታ ይገሥጽህ፥” ::  

ዛሬም እኛ ሰይጣንን በራሳችን አይደለም የምንዋጋው በእየሱስ ስም ነው::  ለእግዚአብሔር ተገዙ ሰይጣንን ተቃወሙት ከእናንተ ይሸሻል ነው የተባልነው::  ራሳችንን ማስገዛት እንለማመድ:: ስድብንም በስድብ አንመልስ እንመርቅ ፤ ባለስልጣንንም እናክብር::

ከባድ አባባል ነው አእምሮም እንደሌላቸው እንስሶች መባል::  እንሰሳ ነው አእምሮ የሌለው ሰው ግን በእግዚአብሔር አምሳል የተፈጠረ ሆኖ ሳለ እራሱን ያዋርዳል::  መንፈሳዊ መስለው ለመታየት ይሞክራሉ ነገር ግን  ፍጥረታዊ ናቸው::  ስለዚህም በፍጥረታቸው በሚያውቁት ሁሉ በእርሱ ይጠፋ ይላል::  ማስተዋል ይሁንልን::  ዝቅ ብለን ሌላው ከእኔ ይሻላል እያልን በትህትናና በፍቅር እንመላለስ::  መታወቅም ያለብን በፍቅራችን ነው::  እግዚአብሔርን ስንፈራና ስንወድ ከዚህ እንጠበቃለን::

አባት ሆይ ሀይ ባይ ያጡትንና ማንንም አንሰማም ያሉትን ወገኖች ዛሬ ታስብ ዘንድ ከእንቅልፍ እንደሚነቁ ይነቁና ለአንተ ይገዙ ዘንድ እጸልያለሁኝ::  በእየሱስ ስም አሜን!

ጸጋው በእውነት ይብዛልን!

ይሁዳ 1: 11፤ ወዮላቸው፥ በቃየል መንገድ ሄደዋልና ስለ ደመወዝም ለበለዓም ስሕተት ራሳቸውን አሳልፈው ሰጥተዋል በቆሬም መቃወም ጠፍተዋል።

ይህንን ክፍል ይሁዳ ሲጀምረው ለቅዱሳን አንድ ጊዜ ፈጽሞ ስለ ተሰጠ ሃይማኖት እንድትጋደሉ እየመከርኋችሁ እጽፍላችሁ ዘንድ ግድ ሆነብኝ ነው የሚለው እንዴት እንጋደል ስንል እነዚህን የሚጠቅሳቸውን ሰዎች ባለመምሰል ነው:: እነዚህም ሶስት ሰዎች:- ቃየል፤  በለዓምና ቆሬ ናቸው::

  1. ከቃየል ብንጀምር መስዋትን በእግዚአብሔር ፊት አቅርቦ ተቀባይነትን አላገኘም ምክንያቱ ግን እንደወንድሙ እንደ አቤል የደም መስዋአት ስላልሆነ ብቻ አይደለም በዕብራውያን 11:4፤ አቤል ከቃየል ይልቅ የሚበልጥን መሥዋዕት ለእግዚአብሔር በእምነት አቀረበ፥ በዚህም፥ እግዚአብሔር ስለ ስጦታው ሲመሰክር፥ እርሱ ጻድቅ እንደሆነ ተመሰከረለት፤ ሞቶም ሳለ በመሥዋዕቱ እስከ አሁን ይናገራል።  በእምነት ስላቀረበ ነው:: እንዲሁም በ1 ዮሐንስ 3:12፤ ከክፉው እንደ ነበረ ወንድሙንም እንደ ገደለ እንደ ቃየል አይደለም፤ ስለ ምንስ ገደለው? የገዛ ሥራው ክፉ፥ የወንድሙም ሥራ ጽድቅ ስለ ነበረ ነው።  ስለዚህ ወዮላቸው እግዚአብሔር አልተቀበላቸውምና በቁጣና በቅምያ ተሞልተዋል በእጃቸው ማንንም ባይገድሉም እንኳን ቃሉ እንደሚል ወንድሙን የማይወድ ነፍሰ ገዳይ ነው::  በቃየል መንገድ እራሳችንን እንዳናገኘው እኛ የክርስቶስ እንጂ የራሳችን አይደለንም::  በፍቅርና በእምነት እህቶችንና ወንድሞችንም በማክበርና እርስ በእርስም በክርስቶስ ፍርሃት የተገዛን ሆነን እንመላለስ።  ከንቱ ከሆነው ነገር ፈቀቅ እንበልና የራሳችንን መንገድ እንጠብጥብ::  የኃይማኖት መልክ ያለን ኃይሉን ግን የካድን እንዳንሆን ዕለት ዕለት በመንፈስ ቅዱስ መሞላትን እንፈልግ እርሱ ይመራናል ይረዳንማል::
  2. ሁለተኛው እንዳንከተለው የተተወልን ምሳሌ በለዓም ነው::  በለዓም ማነው?  ነብይ ነው::  ነገር ግን ገንዘብ አጏጉቶት እስራኤልን ሊረግም ወጣ::  ሶስት ጊዜ ሞከረ ከአፉ የሚወጣውና የሚያየው ራዕይ እስራኤልን መባረክ ብቻ ሆነ::  እግዚአብሔር ያልረገመውን መርገም አይቻልም::  ከውጪ ለሚሆነው ጌታ እንደዚህ ይጠብቃል::  እስራኤን ተዘልሎ ተቀምጧል በለዓም እንደዚህ ሊረግማቸው መከራውን እየበላ እንዳለ የሚያውቁት ነገር የለም::  ጠባቂያችን አይተኛም አያንቀላፋም! በዘኍልቍ 22:18፤ በለዓምም መልሶ የባላቅን ባሪያዎች፦ ባላቅ በቤቱ የሞላውን ወርቅና ብር ቢሰጠኝ፥ በትንሹ ወይም በትልቁ ቢሆን የአምላኬን የእግዚአብሔርን ቃል እተላለፍ ዘንድ አይቻለኝም፤ እንደሚል ቃሉን አልተላለፍም እያለ ግን ለመርገም ይነሳል::  ይህ ሁሉ ለገንዘብ:: በአህያ እንኳን ተናግሮት እያለ ይህ ሰው ብዙ ጥረት ከማድረግ ወደ ኃላ አላለም::  በመጨረሻም ክፉ ምክርን መከረ ይህንን ህዝብ መርገም አልቻልኩም ግን በዝሙት ቢወድቅ እግዚአብሔር እራሱ ይዋጋዋል የሚል:: ደግሞም በለዓም እንደመከረው እግዚአብሔርን አስቆጡት በዚህ ሐጥያት ምክንያት ሃያ አራት ሺ ሰው አለቀ::በዘኍልቍ 25:2፤ ሕዝቡንም ወደ አምላኮቻቸው መሥዋዕት ጠሩ፤ ሕዝቡም በሉ፥ ወደ አምላኮቻቸውም ሰገዱ።  3፤ እስራኤልም ብዔልፌጎርን ተከተለ፤ የእግዚአብሔርም ቍጣ በእስራኤል ላይ ነደደ።በዘኍልቍ 31:16፤ እነሆ፥ እነዚህ በፌጎር ምክንያት በበለዓም ምክር እግዚአብሔርን ይበድሉ ዘንድ ለእስራኤል ልጆች ዕንቅፋት ሆኑ፤ ስለዚህም በእግዚአብሔር ማኅበር ላይ መቅሠፍት ሆነ። አለ ሙሴ::
  3. ሶስተኛው ምሳሌ እንዳትመስሉት የተባልነው ቆሬ ነው::  ቆሬ በሙሴ ላይ ተነሳና ጉባኤን ሰበሰበ ሙሴ የሚሉትን በሰማ ጊዜ በግንባሩ ወደቀ ምክንያቱም የሚመጣውን የእግዚአብሔርን ቁጣ አውቆ ነበረና:: በዘኍልቍ 16:3፤ በሙሴና በአሮን ላይ ተሰብስበው፦ ማኅበሩ ሁሉ እያንዳንዳቸው ቅዱሳን ናቸውና፥ እግዚአብሔርም በመካከላቸው ነውና እናንተ እጅግ አብዝታችኋል፤ በእግዚአብሔርም ጉባኤ ላይ ለምን ትታበያላችሁ? አሉ።  4፤ ሙሴም በሰማ ጊዜ በግምባሩ ወደቀ፤ ሙሴ የፈራው አልቀረም መሬት ተከፍታ ዋጠቻቸው::  የመቃወም ህይወት በእግዚአብሔር ቤት መኖር የለበትም:: ሁሉም እያገለገለ ያለው አንድን ጌታ ነውና መፎካከር የለብንም::  በቤተክርስቲያንም የተሾሙትን እንፀልይላቸው::  ባልተሰጠንም ጸጋ ገብተን የሌሎችን ስራ ለመስራት አንሞክር የስራው ባለቤት ጌታ ነውና እርሱን ደስ ለማሰኘት እንድንችል እርሱን እንስማው እርሱ እራሱ ያሰማራል::  የእግዚአብሔር መንግስት ስራ ባለቤት አለው::

ከምን እንሽሽ ታድያ?  

1.  ገንዘብን ከመውደድ:-    ገንዘብን መውደድ የክፋት ሁሉ ስር ነው::  ጌታም ያለን ለሁለት ጌቶች መገዛት አትችሉም ነው::  ጌታን በሙሉ ኃይላችን እንውደድ::

2.  ከዝሙት መሸሽ –  ቆማችሁ ተቃወሙት አይደለም የተባልነው ሽሹት ነው::  እግዚአብሔር ዝሙትን ይጠላል ምክንያቱም በስጋችን ላይ የምንፈፅመውና ከውስጥ የሚወጣ ደግሞም ሁለንተናን የሚበክል ነው::  ይህ ስጋችን የጌታ መቅደስ ነው::  እርሱ ራሱ ይቀድሰን!

3. የመቃወም ህይወት በእግዚአብሔር ቤት መኖር የለበትም

በቃሉና በጸሎት እንትጋ እራሳችንንም እንመርምር ሌሎችንም እያነቃን አንድ ጊዜ ፈጽሞ ስለተሰጠን መዳን እንጋደል::  ጌታ ጸጋውን ያብዛልን በማስተዋል እንድንመላለስ::

ይሁዳ 1: 12 – 13

12፤ እነዚህ ከእናንተ ጋር ሲጋበዙ በፍቅር ግብዣችሁ እንደ እድፍ ናቸው፤ እንደ እረኞች ያለ ፍርሃት ራሳቸውን ይጠብቃሉ፤ በነፋስ የተወሰዱ ውኃ የሌለባቸው ደመናዎች፥ ፍሬ የማያፈሩ ሁለት ጊዜ የሞቱ ከነሥራቸው የተነቀሉ በበጋ የደረቁ ዛፎች፥ 13፤ የገዛ ነውራቸውን አረፋ እየደፈቁ ጨካኝ የባሕር ማዕበል፥ ድቅድቅ ጨለማ ለዘላለም የተጠበቀላቸው የሚንከራተቱ ከዋክብት ናቸው።

አሁንም ማሰብ ያለብን ይሁዳ የተነሳበትን አሳብ ነው::  እርሱም ስለቅዱሳን አንድ ጊዜ ፈጽሞ ስለ ተሰጠ ሃይማኖት እንድትጋደሉ እየመከርኋችሁ እጽፍላችሁ ዘንድ ግድ ሆነብኝ ያለውን::  ስንጋደል ይህንን ለመጠበቅ በመካከላችን እነዚህን ሰዎች የሚመስሉ ካሉ እንድንጠበቅ ነው::   

እነዚህ ሰዎች እራሳቸውን የሚወዱ ናቸውና በድሮ የቅዱሳን ልምድ ውስጥ የሆነውን በህብረት እንጀራን የመቁረስ ጊዜ ላይ ሲገኙ የራሳቸውን ምግብ ይዘው የማያካፍሉ እራሳቸውን የሚወዱ ሌላው ምግብ ቢኖረው ባይኖረው ግድ የማይላቸው እኔ ብቻ የሚሉ በሁሉ መታየትን የሚሹ ለታይታ የሚመላለሱ ውሃ የሌለው ደመና ናቸው::  ደመና ከመጣ ዝናብ መዝነብና ምድርን ማጠጣት ነበረበት እነርሱ ግን ምንም አይነት ፍሬ የሌላቸው ናቸው::  ጳውሎስም በ1 ቆሮንቶስ 11:21፤ በመብላት ጊዜ እያንዳንዱ የራሱን እራት ይበላልና፥ አንዱም ይራባል አንዱ ግን ይሰክራል። 22፤ የምትበሉባቸውና የምትጠጡባቸው ቤቶች የላችሁምን? ወይስ የእግዚአብሔርን ማኅበር ትንቃላችሁን አንዳችም የሌላቸውን ታሳፍራላችሁን? ምን ልበላችሁ? በዚህ ነገር ላመስግናችሁን? አላመሰግናችሁም።  ይላቸዋል ተመሳሳይ ችግር ነው የምናየው::

እነዚህ ሰዎች ፍሬ የማያፈሩ ሁለት ጊዜ የሞቱ ከነሥራቸው የተነቀሉ በበጋ የደረቁ ዛፎች፥ ፍሬ በሚፈራበት ወቅት እንኳን ፍሬ የሌላቸው ለማንም ምንም የማይሰጡና የደረቁ ናቸው::  እግዚአብሔር ከዚህስ ይጠብቅ!  ውሃ ዳር እንደሚታይ አረፋ ደርሶ ስራ የሰራ ይመስላል ግን ምንም ያላደረገ  በማእበል ብቻ ተገፍቶ የተፈጠረ አረፋ ማለት ናቸው::  እነዚህም ሰዎች ዝም ብለው ግርግር  ይፈጥራሉ እንጂ ፍሬ ያለው ነገር የሌላቸው ናቸው::  መጨረሻቸውም ንስሃ ካልገቡ ጥፋት ነው::  የሚጠብቃቸውም ጨለማ ነው::  

ስለዚህ እራሳችንን እየመረመርን ለራሳችን እንደምናስበውና እንደምንወደው  ሌሎችንም  እንድንወድና ስለሌሎችም እንድናስብ ግድ ይለናል::  ባልንጀራህን እንደራስህ ውደድ!  ጌታ ፍሬ ልናፈራ ሾሞናል!

ይሁዳ 1:16-18

16፤ እነዚህ እንደ ምኞታቸው እየሄዱ የሚያንጎራጉሩና ስለ ዕድላቸው የሚያጕረመርሙ ናቸው፥ እንዲረባቸውም ለሰው ፊት እያደሉ አፋቸው ከመጠን ይልቅ ታላቅ ቃል ይናገራል። 17፤ እናንተ ግን፥ ወዳጆች ሆይ፥ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ሐዋርያት ቀድሞ የተነገረውን ቃል አስቡ፤ 18፤ እነርሱ፦ “በመጨረሻው ዘመን በኃጢአተኝነት እንደ ገዛ ምኞታቸው እየሄዱ ዘባቾች ይሆናሉ፥” ብለዋችኋልና።

እነዚህ ሰዎች የእግዚአብሔርን ነገር የጣሉ እንደ ምኞታቸው እየሄዱ የሚያንጎራጉሩና ስለ ዕድላቸው የሚያጕረመርሙ  በኃጢአተኝነት እንደ ገዛ ምኞታቸው የሚሄዱ ዘባቾች ናቸው::  እግዚአብሔር  ማጉረምረምን ይጠላል ይህ የሚመጣው ደግሞ ከእርሱ ጋር ህብረት ማድረግ ሲቀርና መንፈስ ቅዱስን መተው ሲመጣ ነው::  እርሱ አእምሮን በሚያልፍ  ሰላም ይጠብቀናል ተላልፈንም አንሰጥም አለበለዚያ የራሳችን መሪ እንሆንና በእርሱ ላይ መደገፉን እንተዋለን::  ቃሉ እንደሚል እነዚህ ሰዎች ማታለልና ሰውን መደለል እንዲሁም ሰውን አይተው አድልዎ ያደርጋሉ እንደነዚህ ያሉ እንደሚመጡ ቀድሞ ተነግሮናል::  ዛሬ ብዙ ዘባቾችን እያየን ነው::  ጌታ ይጠብቅ ለወጥመዳቸው እንዳንወድቅ::

የእግዚአብሔር ቃል ችግርን ብቻ ነግሮን አይተወንም መፍትሄም ይሰጠናል::  እናንተ ግን ይለናል ይሁዳ እንዴት መመላለስ እንዳለብን ሊነግረን:- ቃሉ አስቀድሞ ነግሮናልና እንደቃሉ እንኑር:: ከእርሱ ጋር ህብረትን እናድርግ በጌታ ላይ እንደገፍ!  እንደምኞታችን ሳይሆን እንደእርሱ ፈቃድ እንመላለስ::  እኛ የራሳችን አይደለንምና::

ይሁዳ 1:19-23

19፤ እነዚህ የሚያለያዩ ሥጋውያንም የሆኑ መንፈስም የሌላቸው ሰዎች ናቸው። 20፤ እናንተ ግን፥ ወዳጆች ሆይ፥ ከሁሉ ይልቅ በተቀደሰ ሃይማኖታችሁ ራሳችሁን ለማነጽ እየተጋችሁ በመንፈስ ቅዱስም እየጸለያችሁ፥ 21፤ ወደ ዘላለም ሕይወት የሚወስደውን የጌታችንን የኢየሱስ ክርስቶስን ምሕረት ስትጠባበቁ በእግዚአብሔር ፍቅር ራሳችሁን ጠብቁ።

አንድ ጊዜ ስለተሰጠን መዳን እንድንጋደል እየመከረን ነው ቃሉ::  እነዚህ ለማሳሳት ወደ እግዚአብሔር ቤት ሾልከው የሚገቡትን ጥሉ አዋርዱ አይደለም እያለን ያለው::  ነገር ግን የራሳችሁን መዳን ፈጽሙ ምክንያቱም እነዚህ ሰዎች ስጋውያን ናቸው::  

እናንተ ግን 

  – በመንፈስ ተመላለሱ፥  ስጋውያን  አንሁን

  – ራሳችሁን ለማነጽ ትጉ፥  በቃልም  በፀሎትም ከቅዱሳን ጋር ፀጋን  በመከፋፈል

  – በመንፈስ ቅዱስም ጸልዮ፥ እራስን ማነፅ ነውና

  – ምሕረት እየተጠባበቃችሁ በእግዚአብሔር ፍቅር ራሳችሁን ጠብቁ። 

  – ተከራካሪዎችንም ውቀሱ፥ 

  – አንዳንዶችንም ከእሳት ነጥቃችሁ አድኑ፥

  – በኃጥያት የወደቁትን በፍርሃት ማሩ

ነው የተባልነው::

በራሳችን ፍቅር ሌላውን ብንወድ ያልቅብንና እንሰለቻለን የተባልነው ግን በእግዚአብሔር ፍቅር ራሳችሁን ጠብቁ ወይም በፍቅሩ ውስጥ ሁኑ ሌላውን ጌታ እንደሚወድ ውደዱ ነው የተባልነው::  ይህ ፍቅር ለማንም አያዳላም ሁሉን ይወዳልና አብረን እንፍሰስ  ጌታ በእኛ ውስጥ ሌላውን ወዶ መንገዳቸውን ያቅና! 

በመንፈስ ቅዱስም መፀለይን ችላ እንዳንለው::  አብዝተን በመንፈስ እንፀልይ!

የእግዚአብሔር ጸጋ ይብዛልን!

ይሁዳ 1: 24-25

24፤ ሳትሰናከሉም እንዲጠብቃችሁ፥ በክብሩም ፊት በደስታ ነውር የሌላችሁ አድርጎ እንዲያቆማችሁ ለሚችለው፥ 25፤ ብቻውን ለሆነ አምላክና መድኃኒታችን ከዘመን ሁሉ በፊት አሁንም እስከ ዘላለምም ድረስ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ክብርና ግርማ ኃይልም ሥልጣንም ይሁን፤ አሜን።

የእግዚአብሔር ቸርነቱ እንዴት ይደንቃል? እንዳንሰናከል ይጠብቀናልና በሌላ ስፍራ በእግዚአብሔር ኃይል ለተጠበቃችሁ እንደሚለው እንጠበቃለን ስሙ ይባረክ:: እግዚአብሔር ማንንም በክፉ አይፈትንም ሲጀምርም ተወዳድረን አሪፍ ስለሆንን አይደለም ወደ ጉያው የመጣነው ነገር ግን እርሱ የዓለምን ምናምንቴ መረጦ ታድያ ምናችን ይፈተናል ይጠብቀን እንጂ በራሳችንም አልዳንን በጸጋው ነው እውቀታችን እንዳንል ደህንነት መገለጥ ነው ጴጥሮስን እንዳለው አንተ የእግዚአብሔር ልጅ ነህ ሲለው ስጋና ደም ሳይሆን የአባቴ መንፈስ ነው የገለጠልህ እንዳለው ነው::  ምንም የምንመካበት የሌለን ነን:: እንጠበቅ እንጂ በእርሱ!

በክብሩም ፊት በደስታ ነውር የሌላችሁ አድርጎ እንዲያቆማችሁ ለሚችለው፥

እናስተውል በክብሩ ፊት!!!! ሃ ሌ ሉ ያ!  በክብሩ ፊት ሳንሸማቀቅ እየሱስን ጽድቃችን ለብሰን በደስታ ነውር የሌለን አድርጎ ሊያቆመን ለሚችለው ክብር ይሁን!! ምን አይነት መታደል ነው?!  ሰው በራሱ አይበረታም የሚያበረታና የሚረዳ እራሱ ጌታ ነውና ክብር ይሁንለት::  ምን እንላለን ምን አይነት ፍቅር ነው ለእኛ ያለው ከማለት በቀር!!  የጌታ ስም ይባረክ!!

በዚህ የይሁዳ መጽሐፍ ጥናት በዚህ ተጠናቀቀ የሚገርመው አንድ ምዕራፍ ቢሆንም ግን ብዙ አሳብ የታጨቀበት ነው  መዳናችንን በጌታ ላይ በመታመን እንፈጽም ፤  ፍሬንም እናፍራ፤  ወደ ጥፋት የሚሮጡትንም ቅዱሳን እንታደግ፤  በእግዚአብሔር ፍቅር ውስጥ እንኑር:: 

ብቻውን ለሆነ አምላክና መድኃኒታችን ከዘመን ሁሉ በፊት አሁንም እስከ ዘላለምም ድረስ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ክብርና ግርማ ኃይልም ሥልጣንም ይሁን፤ አሜን።

አሜን!!!

የጌታ ጸጋ ይብዛልን! 

የዮሐንስ ራእይ

መግቢያ

በዚህ መጽሐፍ ብዙ አሳብ አለ ከዚህ መካከልም እንደገባን የምናየው:-

1.  ስለ እየሱስ መገለጥ

2.  የእግዚአብሔርን ፍርድ

3.  ለባርያዎቹ የክርስቶስን ክብር ለማሳየት

4. ወደፊት ሊሆን ያለውን

5.  ስለሐሰተኛው ክርስቶስ እና ሌላም

ጥልቅ መጽሐፍ ነው ምክንያቱም ትንቢት ስለሆነ በዚህ ውስጥ ግን እግዚአብሔር ቃሉን ይግለጥና መረዳትን ይስጠን ይህንን እየሱስን የበለጠ በክብሩ እንወቀው: የማይገባንም ክፍል ቢኖር ስንሄድ ሙሉ እውቀት ይኖረናልና:: በመልእክቶችና በወንጌል መጽሐፍት ውስጥ እየሱስን የምናውቀው ዝቅ ብሎ በትህትና እንደመጣ ስናይ በዚህ ክፍል ደግሞ ያለውን ክብርና ግርማ እንዲሁም ወደ ምድር ሲመጣ ጥሎት የመጣውን ክብሩን ያሳያል::

ይህ ጌታ ታላቅ ነው ደግሞም መንፈስ ነው!  ጌታ ያስተምረን!

የዮሐንስ ራእይ 1: 1-3

1፤ ቶሎ ይሆን ዘንድ የሚገባውን ነገር ለባሪያዎቹ ያሳይ ዘንድ እግዚአብሔር ለኢየሱስ ክርስቶስ የሰጠው በእርሱም የተገለጠው ይህ ነው፥ ኢየሱስም በመልአኩ ልኮ ለባሪያው ለዮሐንስ አመለከተ፥ 2፤ እርሱም ለእግዚአብሔር ቃልና ለኢየሱስ ክርስቶስ ምስክር ላየውም ሁሉ መሰከረ። 3፤ ዘመኑ ቀርቦአልና የሚያነበው፥ የትንቢቱን ቃል የሚሰሙትና በውስጡ የተጻፈውን የሚጠብቁት ብፁዓን ናቸው።

በሰማይ ያለውን ክብሩን እናይ ዘንድ እግዚአብሔር አብ  ነው ይህንን ራዕይ እንዲገለጥ ያደረገው ስለ ለእየሱስ ፤ እየሱስም መልአኩን ልኮ ለዮሐንስ ፤ ዮሐንስም ለእኛ አደረሰን:: የሐዋርያት ሥራ 1: 9፤ ይህንም ከተናገረ በኋላ እነርሱ እያዩት ከፍ ከፍ አለ፤ ደመናም ከዓይናቸው ሰውራ ተቀበለችው ይለናል ቃሉ::  ከዛስ ምን ተፈጠረ? እየሱስን የምናውቀው ዝቅ ብሎ የመጣ ትሁት፤    ስለእኛ ዝም ብሎ የተንገላታ ፤  የተመታ፤  የተሰቀለ ጌታ ነው::  ምንም እንኳን ጌታ ክብሩን ቢነግረንም ብዙም አልገባንም ለዚህ ነው ከደመናው ባሻገር ያለውን እንድናይና እንዴት እንደከበረ ደግሞም እንደሚመጣ ሙሉ መረጃ ሊሰጠን ወደደ::  ስፍራን ላዘጋጅላችሁ እሄዳለሁ ብሎን ነበረ የት ነው ይህ ስፍራ የተዘጋጀው ካልን መልሱን እዚህ ክፍል ላይ ይሰጠናል:: እንዴት ድንቅ ነው ይሄ ጌታ?!

ዮሐንስም  ለእግዚአብሔር ቃልና ለኢየሱስ ክርስቶስ ምስክር ላየውም ሁሉ መሰከረ።  ዛሬም ቃሉን ልናውቅና ምስክሮቹ እንድንሆንና የእርሱን በጎነት እንድንናገር ተጠርተናል እንናገር እንመስክር!

ዘመኑ ቀርቦአልና የሚያነበው፥ የትንቢቱን ቃል የሚሰሙትና በውስጡ የተጻፈውን የሚጠብቁት ብፁዓን ናቸው።  ዘመኑ ያኔ ደርሷል ከተባለ ዛሬማ በደጅ ነው ጌታ እናክብረው በህይወታችን! እንበርታ!

የዮሐንስ ራእይ 1: 4-5፤ 

ዮሐንስ በእስያ ላሉት ለሰባቱ አብያተ ክርስቲያናት፤ ካለውና ከነበረው ከሚመጣውም፥ በዙፋኑም ፊት ካሉት ከሰባቱ መናፍስት፥ ከታመነውም ምስክር ከሙታንም በኵር የምድርም ነገሥታት ገዥ ከሆነ ከኢየሱስ ክርስቶስ ጸጋና ሰላም ለእናንተ ይሁን።

እዝች ክፍል ላይ ስላሴን ቁልጭ አድርጎ  ያሳየናል በዚህ ሰላምታ ውስጥ::  ራዕይ በብዛት የተጠቀሰው ከብሉይ ኪዳን ነው አንዳንዶች እንደሚሉት 70%  የሚሆነው::  እግዚአብሔር አዲስ ኪዳን ላይ አይደለም የራዕይን መጽሐፍ ያሰበው ገና ድሮ በቃሉ ውስጥ በነብያቱ ተናግሯል::  

ሰላምታውም :- 

1. ከአብ : ካለውና ከነበረው ከሚመጣውም፥  ኦሪት ዘጸአት 3

14፤ እግዚአብሔርም ሙሴን፦ «ያለና የሚኖር» እኔ ነኝ አለው፤ እንዲህ ለእስራኤል ልጆች፦ «ያለና የሚኖር» ወደ እናንተ ላከኝ ትላለህ፡ አለው።

2. ከመንፈስ ቅዱስ:   በዙፋኑም ፊት ካሉት ከሰባቱ መናፍስት፥ 

ትንቢተ ኢሳይያስ 11

2፤ የእግዚአብሔር መንፈስ፥ የጥበብና የማስተዋል መንፈስ፥ የምክርና የኃይል መንፈስ፥ የእውቀትና እግዚአብሔርን የመፍራት መንፈስ ያርፍበታል።

ይህንን ቃል ስንተነትነው ሰባቱ የመንፈስ ቅዱስ መገለጫዎች ናቸው:- 

2.1 የእግዚአብሔር መንፈስ

2.2 የጥበብ መንፈስ

2.3 የማስተዋል መንፈስ፥ 

2.4 የምክር መንፈስ

2.5 የኃይል መንፈስ፥ 

2.6 የእውቀት መንፈስ

2.7  እግዚአብሔርን የመፍራት መንፈስ

ይህ መንፈስ በእኛ ላይ ይምጣ ዘይታችንም የሞላ የሚሆነው እንደዛ ነው ዕለት ዕለት በእርሱ ስንሞላ:: ይሙላን በማንነቱ::

3. ከወልድ: ከታመነውም ምስክር ከሙታንም በኵር የምድርም ነገሥታት ገዥ 

አባቱን እስከሞት እንደታዘዘና እንደታመነው እናውቃለን:: 

እኔን ባታምኑ አብን በስራው እመኑት እያለ መስክሯል::

ከሙታን በኩር ሆኖ ደሙን እያንጠባጠበ ወደ አብ ገብቷል ከሁሉ በፊት ነው:: እርሱ ነገሥታት ገዥ ነው ሁሉን ከእግሩ ስር ያስገዛለታል::

አሜን እንዴት ያለ መልእክት ነው አምላካችን የላከልን::  ልናገነውና ልናመልከው ይገባል::  እርሱ ትልቅ ሆኖ ሳለ አስቦን  ይህንን  መልእክት ላከልን:: እኔንም ታሳቢ አድርጎ የተፃፈ ነው ብዬ እላለሁ::  እያንዳንዳችን እንደዚህ እናስብ:: ለሚናገረን መልእክት ጆሯችን የተከፈተ ይሁን::

የዮሐንስ ራእይ 1:6

ለወደደን ከኃጢአታችንም በደሙ ላጠበን፥  6፤ መንግሥትም ለአምላኩና ለአባቱም ካህናት እንድንሆን ላደረገ፥ ለእርሱ ከዘላለም እስከ ዘላለም ድረስ ክብርና ኃይል ይሁን፤ አሜን።

ቃሉን እናስተውል ለወደደን ነው እንጂ ለሚወደን አይልም::  በኃላፊ ነው የተገለጠው የቱጋ ነው ታድያ የወደደን?!  በመስቀል ላይ በመሞት ነው አንድ ጊዜ የወደደን በሮሜ 5:8 እንደሚለን:- ነገር ግን ገና ኃጢአተኞች ሳለን ክርስቶስ ስለ እኛ ሞቶአልና እግዚአብሔር ለእኛ ያለውን የራሱን ፍቅር ያስረዳል። አይገርምም ገና ኃጥያተኞች ሳለን የሚወደድነገርም ሳይኖረን ነው የወደደን ስለዚህ ነው ዮሃንስም ልጆች ሆይ ሐጥያትን ብታደርጉ ጠበቃ አላችሁ የሚለን::  ጠበቃ አለን ብለን ደግሞ በኃጥያት እንዳንመላለስ በእርሱ የሚኖር ሁሉ ኃጢአትን አያደርግም፤ ኃጢአትን የሚያደርግ ሁሉ አላየውም አላወቀውምም። ይለናል::  እራሳችንን ማየት ያለብን በመስቀሉ ውስጥ ነው ተወደናል!!

የሚገርመው ሐጥያታችንን ያጠበው ከወደደን በኃላ ነው::  መውደዱ ነው ወደ መስቀል የወሰደውና ደሙን እንዲያፈስ ያስገደደው::  በዛም ደም እኛ ታጠብን የሰማይ ሰራዊትም ሲጠይቁ  እናያለን እነዚህ እነማን ናቸው ብለው መልሱ ልብሳቸውን በበጉ ደም ያነፁ ነው!!  ሃሌሉያ!!! ታጥበናል ከሐጥያታችን::

አጥቦ አንጽቶ ብቻ አይደለም የተወን መንግስትን ሊያወርሰን እንጂ:: የመሰረተው መንግስት የካህናት መንግስት ነው:: 1ኛ ጴጥሮስ 2: 9፤ እናንተ ግን ከጨለማ ወደሚደነቅ ብርሃኑ የጠራችሁን የእርሱን በጎነት እንድትናገሩ የተመረጠ ትውልድ፥ የንጉሥ ካህናት፥ ቅዱስ ሕዝብ፥ ለርስቱ የተለየ ወገን ናችሁ፤

የንጉስ ካህናት ሆነናል!!! አሜን ታድያ ለዚህ ጌታ ክብርና ኃይል ይሁን፤ አሜን።

ቀናችንን ስንውል ምስጋናን እየሰዋን እናመስግነው እናወድሰው ስለመወደዳችንና የካህንነትን ማዕረግ በእርሱ ስራ ስለተቀበልን:: ካህን ስራው መቀደስ ነውና ስሙን እየቀደስ  በቤቱ እናገልግለው ይህንን እድል አግኝተናል ማንም ከእኛ አይወስደውም ድሮውንም ስራችንን አይቶ ሳይሆን መጥፋታችንን አውቆ ነውና የሞተልን::  የዓለምን ሁሉ ኃጥያት የሚያስወግደው የእግዚአብሔር በግ ታድጎናል!!!  ሃሌሉያ!

የዮሐንስ ራእይ 1: 7-8

7፤ እነሆ፥ ከደመና ጋር ይመጣል፤ ዓይንም ሁሉ የወጉትም ያዩታል፥ የምድርም ወገኖች ሁሉ ስለ እርሱ ዋይ ዋይ ይላሉ። አዎን፥ አሜን። የዮሐንስ 8፤ ያለውና የነበረው የሚመጣውም ሁሉንም የሚገዛ ጌታ አምላክ፦ አልፋና ዖሜጋ እኔ ነኝ፡ ይላል።

እነሆ ስንባል ምን ብለን ቀና ማለታችን አይቀርም አንዳች ለማየት እንዲሁ ባለ ጉጉት ነው ጌታን መጠበቅ ያለብን እርሱ ይመጣል:: በዳንኤል 7: 13-14 እንዳለው እንዲሁም በማቲዎስ 24: 42 ላይ መቼ እንደሚመጣ አናውቅምና የተዘጋጀን እንሁን:: ደመና እንደተቀበለው ደመና በእርግጥ ደመና ሲሆን ሌላው ፍቺው ደግሞ የእግዚአብሔር ህዝብ ማለት ነው በዕብ 11:1 እንደሚናገረው በምዕራፍ 10 ያሉትን የእምነት አርበኞች ደመና ብሎ ይጠራቸዋል:: ከደመና ጋር ይመጣል ቅዱሱ በሐውዋርያት ስራ 1:9::

 በፊት የመጣው ዝቅ ብሎ ተዋርዶ የባርያን መልክ ይዞ ሲሆን ሲመለስ ግን በኃይል ነው የሚመጣው::  እራሱም ጌታ በማርቆስ ወንጌል 14: 62፤ ኢየሱስም አለ፦ እኔ ነኝ፤ የሰው ልጅም በኃይል ቀኝ ሲቀመጥ በሰማይም ደመና ሲመጣ ታያላችሁ። በብሉይ ኪዳንም ለሙሴም ሲገለ በሲና ተራራ እንዲሁም ወደ መገናኛው ድንኳን ሲጣ ደመናው ነበረ::  እርሱ በደመና ላይ ይራመዳል ደመና የሚታዘዝ አይደለም በውስጡ ይታለፋል እንጂ የማይጨበጥ ነገር ነው:: ለእርሱ ግን ግዑዙ ሁሉ ይታዘዛል::

ዓይንም ሁሉ ያዩታል ይላል ሲመጣ ጌታ መጣ ብሎ አዋጅ ነጋሪ የለም በዜናም አይደለም የሚሰማው ሁላችን በህይወት ካለን በዛው ቅጽበት እናየዋለን::  በማቴዎስ 24:26፤ እንግዲህ፦ ‘እነሆ፥ በበረሀ ነው’ ቢሉአችሁ፥ አትውጡ፤ ‘እነሆ፥ በእልፍኝ ነው’ ቢሉአችሁ፥ አትመኑ፤27፤ መብረቅ ከምሥራቅ ወጥቶ እስከ ምዕራብ እንደሚታይ፥ የሰው ልጅ መምጣት እንዲሁ ይሆናልና፤

እኛ ብቻ ሳንሆን የወጉትም ያዩታል::  የወጉት ሲባል በስጋ  የወጉትን ብቻ ሳይሆን እርሱን አውቀው የዓለም ነገር በልጦባቸው ትተውት የሄዱት ልቡን የወጉት ሁሉ  ያዩታል::  ምን ይሉ ይሆን? ለምናውቃቸው ወደኃላ ለተመለሱት እንፀልይ ልብን ያሳዝናል ከእርሱ መለየታቸው:: 

ለምን ይሆን የምድርም ወገኖች ሁሉ ስለ እርሱ ዋይ ዋይ ይላሉ የሚለው? ስላላወቁትና ስላልተቀበሉት ነው ::  ከዚህ ዋይታ ያወጣን ጌታ ይመስገን::  ማራናታ!

ያለውና የነበረው የሚመጣውም ሁሉንም የሚገዛ ጌታ አምላክ፦ አልፋና ዖሜጋ እኔ ነኝ፡ ይላል። ሁሉ በእርሱ ሆነ ከሆነውም አንዳች ያለ እርሱ አልሆነም::  እርሱ አልፋ የሁሉ መጀመሪያ መነሻ እንዲሁም ዖሜጋ የሁሉ መደምደምያ ነው::  ክብር ይሁንለት!!

የዮሐንስ ራእይ 1: 9-11

9፤ እኔ ወንድማችሁ የሆንሁ ከእናንተም ጋር አብሬ መከራውንና መንግሥቱን የኢየሱስ ክርስቶስንም ትዕግሥት የምካፈል ዮሐንስ ስለ እግዚአብሔር ቃልና ስለ ኢየሱስ ምስክር ፍጥሞ በምትባል ደሴት ነበርሁ። 10፤ በጌታ ቀን በመንፈስ ነበርሁ፥ በኋላዬም የመለከትን ድምፅ የሚመስል ትላቅ ድምፅ ሰማሁ፥

በፍጥሞ ደሴት በእስር ላይ ነበረ ዮሃንስ የታሰረውም ስለ እግዚአብሔር ቃልና ስለ ኢየሱስ ምስክር  በመሆኑ ምክንያት ነበር::   እኔ ወንድማችሁ የሆንሁ ከእናንተም ጋር አብሬ መከራውንና መንግሥቱን የኢየሱስ ክርስቶስንም ትዕግሥት የምካፈል ይላል::  መከራ የለም አላለንም በተለይ ዮሃንስ በሚጽፍበት ዘመን የሮም አገዛዝ ሁሉንም አካባቢ ተቆጣጥሮ የነበረበትና ተገዳዳሪ ወይም ሌላ መንግስት የማይታሰብበት ጊዜ ነው::  ይህ መንግስት ጊዜያዊ ነው የእግዚአብሔር መንፍስት ግን ዘላለማዊ ነው::  እርሱ እራሱ መከራ እየተቀበለ ያለ ሰው ነው በዝች ደሴት ማምለጥ ስለማይችሉ ነው እስረኞቹን እዚህ አምጥተው የሚጥሏቸው::  የመልእክቱ ተቀባዮችም ቢሆኑ ይኽው የመንግስት ጡጫ የሚያገኛቸው ስለሆኑ እኔ ወንድማችሁ ከእናንተ ጋር አብሬ መከራውን የምካፈል ብሎ ብቻ አልዘጋም ነገር ግን የእግዚአብሔርን መንግስት የምካፈል ብሎ ይጨምራል::  ጊዜያዊዉ መንግስት ያልፋል የማያልፍን መንግስት እኛም ተካፋይ የሆንበትን እንወርሳለን:: የሮም መንግስት ቢያስረውን እግዚአብሔርን ወደ ዮሃንስ ከመምጣት አላገደውም::  እግዚአብሔር አይከለከልም የምናመልከው ጌታ ትልቅ ነው:: በምንም ነገር ውስጥ እንለፍ እርሱ ከእኛ ጋር ነውና በድል እንወጣለን::

በጌታ ቀን በመንፈስ ነበርሁ፥ ይላል ሰዎቹ ያሰሩት ከዛ እንዳይወጣ እርሱ ግን በመንፈስ ሆኖ በንጉሱ ፊት ከሁሉ በላይ በሆነውም መንግስት ፊት ነበረ::  የዓለም ነገር በእግዚአብሔር ተሸናፊ ነው ምን ቢከበን ጊዜያዊ ነው እንበርታ::  በመንፈስ ሆኖ በኋላዬም የመለከትን ድምፅ የሚመስል ትላቅ ድምፅ ሰማሁ፥ ይላል::  ይህንን ድምጽ በሲና ተራራ ሲሰሙት እስራኤሎች ያሉት አንድ ነገር ነው እግዚአብሔር አይናገረን ሙሴ አንተ ተናገረን የሚለውን ሁሉ ንገረን እናደርጋለን ነበር::  እንደ ታላቅ የመለከት ድምፅ የሆነበት የጌታ የእየሱስ ክርስቶስ ንግግር ነበረ::  ሃሌሉያ!!  በመንፈስ ተሆኖ የሚሰማ ድምጽ:: በመንፈስ እንመላለስ ፤ በመንፈስ እንጸልይ::

ይህም ድምጽ የምታየውን በመጽሐፍ ጽፈህ ወደ ሰባቱ አብያተ ክርስቲያናት ላክ፡ አለኝ። የታሰረው እንዳያገለግል ነበረ ግን እያገለገለ ነው ዮሃንስ::  እግዚአብሔር ይጠበባል መንግስቱ በምንም አይቆምም!!! ሃሌሉያ! ዛሬም እናገለግለዋለን! 

የዮሐንስ ራእይ 1: 12-16

13፤ በመቅረዞቹም መካከል የሰው ልጅ የሚመስለውን አየሁ፥ እርሱም እስከ እግሩ ድረስ ልብስ የለበሰው ደረቱንም በወርቅ መታጠቂያ የታጠቀ ነበር። 

14፤ ራሱና የራሱ ጠጕርም እንደ ነጭ የበግ ጠጕር እንደ በረዶም ነጭ ነበሩ፥ ዓይኖቹም እንደ እሳት ነበልባል ነበሩ፤

15፤ እግሮቹም በእቶን የነጠረ የጋለ ናስ ይመስሉ ነበር፥ ድምፁም እንደ ብዙ ውኃዎች ድምፅ ነበረ።

16፤ በቀኝ እጁም ሰባት ከዋክብት ነበሩት፥ ከአፉም በሁለት ወገን የተሳለ ስለታም ሰይፍ ወጣ፤ ፊቱም በኃይል እንደሚበራ እንደ ፀሐይ ነበረ።

ዮሃንስ እየሱስን በደንብ ያውቀዋል ግን በዚህ መልኩ አልነበረምና ወደቀ::  ልክ ዳንኤል እንዳለው እርሱም እየሱስን የሰው ልጅ የሚመስል ብሎ ይጠራዋል::  አልፋና ኦሜጋ እኔ ነኝ ብሎ ስለራሱ ያወጀ ጌታ! ስሙ ይባረክ::  

በመቅረዞቹም መካከል ነበረ ጌታ የነበረው ይህ መቅረዝ የሚያስታውሰን የቀደመውን ሙሴ የሰራውን የመገናኛ ድንኳን ነው ምንም ሳትሳሳት እንዳየኸው ስራ የተባለው በሰማይ ስላየው ነው መቅረዙን::    መቅረዙ በራሱ ብርሃን አይሰጥም ከዘይቱ እንጂ ዘይት ካልተጨመረ አይበርም የእኛም ህይወት ያለ መንፈስ ቅዱድ መብራት አይችልም ዕለት ዕለት ተሞሉ ተብለናል እየሱስን እየመሰልን እያብለጨለጭን እንድንመላለስ:: 

እየሱስ በብዙ መከራ አልፎ ከብሮ እያየ ነው በመከራና ስደት ውስጥ ያለው ዮሃንስ::  ያንን ሁሉ ያለበትን የሚያስረሳ ነው በራዕይ እያየ ያለው እርሱም የጌታን ክብር::  ሁሉ ይታለፋል እንዲህ የከበረ ጌታ በሰማይ በክብሩ ሆኖ አይኑን በእኛ ላይ አድርጏል:: ዓለም አታሸንፍም ድሉ የተረጋገጠ ነው ጌታን እናገለግላለን!!

ዮሃንስ በተቻለው መጠን ካለው እውቀቱ ጋር በማዛመድ ግልፅ የሆነ መረጃ ሊሰጠን ጥሯል::  እየሱስ በወርቅ መታጠቂያ የታጠቀ ነበር ይላል እንደዚሁም  በዳንኤልም መጽሃፍ እንደሚልው ራሱና የራሱ ጠጕርም እንደ ነጭ የበግ ጠጕር እንደ በረዶም ነጭ ነበሩ ይላል ይህ ቅድስናውንና በዳንኤልም ላይ እንደምናየው ዳንኤል 7: 22፤ በዘመናት የሸመገለው እስኪመጣ ድረስ፥ ይላል እርሱ በዙፋኑ ላይ የጸና ጌታ ነው::

ዓይኖቹም እንደ እሳት ነበልባል ነበሩ፤ ይህ የሚያሳየው ፍርድን ነው እግሩም የጋለ ናስ በምንም ውስጥ የሚራመድ ጌታ የከበረ ጌታ ነው:: ድምጹም የሚያስፈራ እንደብዙውሃ ድምጽ::

በቀኝ እጁም ሰባት ከዋክብት ነበሩት፥ በፊቱ ያየናል በመካከላችንም ይመላለሳል:: ከአፉም በሁለት ወገን የተሳለ ስለታም ሰይፍ ወጣ፤ እርሱ ሲናገር ይቆራርጣል እኛንም በቃሉ ይሰራናል ጠላትንም በቃሉ ያጠፋል:: የእግዚአብሔር ቃል ለእኛም መዋጊያችን ነው በኤፌ 6 ላይ እንደምናየው:: ፊቱም በኃይል እንደሚበራ እንደ ፀሐይ ነበረ። ማን ያየዋል?

ጌታ ሆይ አንተ ትልቅ ነህ ተባረክ::

የዮሐንስ ራእይ 1: 17

17፤ ባየሁትም ጊዜ እንደ ሞተ ሰው ሆኜ ከእግሩ በታች ወደቅሁ። ቀኝ እጁንም ጫነብኝ፥ እንዲህም አለኝ፦ አትፍራ፤ ፊተኛውና መጨረሻው ሕያውም እኔ ነኝ፥   18፤ ሞቼም ነበርሁ እነሆም፥ ከዘላለም እስከ ዘላለም ድረስ ሕያው ነኝ፥ የሞትና የሲኦልም መክፈቻ አለኝ።

ዮሃንስ እየሱስን ባየ ጊዜ መቆምም አልቻለም ወደ ደረቱ ተጠግቶ የሚጠይቀው ዮሃንስ እንደሞተ ሰው ሆኖ ወደቀ ልክ እንደእርሱ ዳንኤልም መቆም አልቻለም ነበረ::

ሕዝቅኤል 1:28፤ በዝናብ ቀን በደመና ውስጥ እንደ ቀስተ ደመና አምሳያ፥ እንዲሁ በዙሪያው ያለ ፀዳል አምሳያ ነበረ። የእግዚአብሔር ክብር ምሳሌ መልክ ይህ ነበረ። ባየሁም ጊዜ በግምባሬ ተደፋሁ፥ የሚናገርንም ድምፅ ሰማሁ።

ዳንኤል 8:17፤ እኔም ወደ ቆምሁበት ቀረበ፤ በመጣም ጊዜ ፈርቼ በግምባሬ ተደፋሁ፤ እርሱም፦ “የሰው ልጅ ሆይ፥ ራእዩ ለፍጻሜ ዘመን እንደ ሆነ አስተውል፡” አለኝ።

 ጳውሎስ እንዳለው ነው ክርስቶስን በስጋ ታውቁት ከነበረ አሁን እንደዛ አትወቁት  ክቡር  ንጉስ ነው::  ዮሃንስ በወደቀበት ቀኝ እጁንም ጫነበት፥ እንዲህም አለው፦ አትፍራ፤ ብሎ አበረታው::  መፍራትም የሌለበትን  ምክንያት እየሱስ ሲያብራራ:

1.  ፊተኛውና መጨረሻው ሕያውም እኔ ነኝ፥   በኢሳያስ 44:6  ላይ ይህንኑ ቃል ጌታ ስለራሱ ተናግሯል::  እርሱ ከሁሉ በፊት የነበረና የሚኖር እኔ እኔ ነኝ የሚል የህይወት ሁሉ መገኛ ጌታ ነው! 

2.  ሞቼም ነበርሁ፥ ከዘላለም እስከ ዘላለም ድረስ ሕያው ነኝ፥  ጌታ አንድ ጊዜ የሞትን ጽዋ ጠጥቶ እዳችንን ሁሉ ከፍሎ በትንሳኤ ተነስቷል ደግሞ  መሞት አያስፈልገውም  ስለዚህ ለዘላለም ህያው ነው::

3. የሞትና የሲኦልም መክፈቻ አለኝ።  የመጨረሻ ሰውን የሚያስፈራራው ነገር ቢኖር ሞት ነው እሱም ተሸንፏል::  ሰይጣን እንደፈለገየሚያደርገው ነገር የለም ገደብ አለው::  ለእኛ ለምናምነው የታመነ ጌታ ነው ታድያ ምን ያስፈራል ጌታ ለእኛ ነው እንታመነው::  ይህንን ትልቅ ጌታ እንወድሰው!  ሃሌሉያ ይገባዋል!!

ዋው ጌታዬ ሆይ ክብርና ምስጋና ኃይልም ልትቀበል ይገባሃል:: አሜን

የዮሐንስ ራእይ 1: 19-20

19፤ እንግዲህ ያየኸውን አሁንም ያለውን ከዚህም በኋላ ይሆን ዘንድ ያለውን ጻፍ።  

20፤ በቀኝ እጄ ያየሃቸው የሰባቱ ከዋክብትና የሰባቱ የወርቅ መቅረዞች ምሥጢር ይህ ነው፤ ሰባቱ ከዋክብት የሰባቱ አብያተ ክርስቲያናት መላእክት ናቸው፥ ሰባቱም መቅረዞች ሰባቱ አብያተ ክርስቲያናት ናቸው።

ዮሃንስ ጌታን እንደዚህ በክብሩ አይቶ ከወደቀበት አይዞህ ተብሎ ተበረታቶ ተነስቶ ሳለ ጌታ ጻፍ ይለዋል:: ጻፍ ትእዛዝ ነው እኛም የህይወታችንን ታሪክ ብንጽፍ ለምስጋና ይሆናል አቤነዘር ለማለትም ይጠቅማል የምናልፍበትን ሁሉ ለበጎ አድርጎ እየለወጠ እዚህ ያደረሰን ጌታ ብዙ የሚነገርለት ነገር አለ በህይወታችን::  ስሙ ይባረክ:: የሚጽፈውም ያየኸውን አሁንም ያለውን:- በቤተክርስቲያናቱ (ከምዕራፍ 2-5) ውስጥ በዛ ሰዓት እየሆነ ስላለው እንዲሁም ደግሞ  ከዚህም በኋላ ይሆን ዘንድ ያለውን ነው።   

እነዚህ በቀኝ እጄ ያየሃቸው የሰባቱ ከዋክብት የሰባቱ አብያተ ክርስቲያናት መላእክት ናቸው፥ አለው መላእክት ሲባል አንዳንዶች መላእክ ማለት ክንፍ ያለው መላእክት ማለቱ ላይሆን ይችላል እረኛን ወይም የቤተክርስቲያን ሽማግሌን ማለቱ ይሆናል ይላሉ ምክንያቱም በምዕራፍ 2 ሲጀምር የደብዳቤው ተቀባይ  በኤፌሶን ወዳለው መልአክ ነው የሚለው::  አብራርቶ ነግሮንም ሚስጥር አለው ይገርማል::  እነዚህን ከዋክብት በቀኝ እጁ ይዟል ከእጁ ማንም አያወጣውም ዋስትና ያለው ቦታ ናቸው:: 

የወርቅ መቅረዞቹ ደግሞ ሰባቱም መቅረዞች ሰባቱ አብያተ ክርስቲያናት ናቸው።  የሚገርመው 1:13 ላይ ጌታ በመቅረዞችር መካከል ነበረ::  እነዚህ መቅረዞች ቤተክርስቲያንን የሚወክሉ ናቸው ስለዚህ ጌታ በመካከላቸው ነው ያለው::  ዛሬም በመካከላችን የሚመላለስ ጌታ አለ::  እሩቅ አይደለም መንግስትህ ትምጣ ብላችሁ ጸልዮ ብሎ ያስተማረን ጌታ መንግስቱ በመካከላችን ናት::  እንዴት ያለ መታደል ነው በእርሱ ፊት መሆን?!  ተባረክ ጌታ ሆይ!!  ክብር ምስጋና ለአንተ ይሁን::

የዮሐንስ ራእይ 2: 1-7

1፤ በኤፌሶን ወዳለው ወደ ቤተ ክርስቲያን መልአክ እንዲህ ብለህ ጻፍ፦ በቀኝ እጁ ሰባቱን ከዋክብት የያዘው በሰባቱም የወርቅ መቅረዞች መካከል የሚሄደው እንዲህ ይላል፦

2፤ ሥራህንና ድካምህን ትዕግሥትህንም አውቃለሁ፤ ክፉዎችንም ልትታገሥ እንዳትችል፥ እንዲሁም ሳይሆኑ፦ ሐዋርያት ነን፡ የሚሉቱን መርምረህ ሐሰተኞች ሆነው እንዳገኘሃቸው አውቃለሁ፤

3፤ ታግሠህማል፥ ስለ ስሜም ብለህ ጸንተህ አልደከምህም። 

4፤ ዳሩ ግን የምነቅፍብህ ነገር አለኝ፡ የቀደመውን ፍቅርህን ትተሃልና።

ይህ መልእክት የተላከው ቀጥታ ከእየሱስ ወደ ኤፌሶን ቤተክርስቲያን ነው:: ኤፌሶን ማለት ትልቅ የመገበያያ ከተማ ነበረች የዳያናም ቤተመቅደስ ያለባት ልክ የሆነ የግብረ ስጋ ግንኙነት የሚበረታታበትና የጠላት አምልኮ የሰለጠነበት ከተማ ነው::  በዚህ መካከል ነው እንግዲህ ይህች ቤተክርስቲያን ያለችው::  ጳውሎስ ለሶስት ዓመት ቁጭ ብሎ አገልግሏቸዋል ከእርሱም ጋር አጵሎስ ና ጢሞቲዎስ እንዲሁም ዮሃንስም አቂላና ጵርስቅላም አገልግለዋል::   ብዙዎች የደከሙበት ነው::  

ጌታ የሚወደው ነገር አለ

1.  ስራህን አውቃለሁ:- ምክንያቱም በመቅረዞቹ መካከል እየተመላለሰ ነውና እርሱ እሩቅ አይደለም ዛሬም ስራችንን ያውቃል ማንም ሊነግረው አያስፈልግም::  እርሱን በመፍራትና በማክበር እንመላለስ መንጋውምየጌታ እኛም የጌታ::

2. ድካምህን ትዕግሥትህንም አውቃለሁ፤  በመከራ ውስጥ ከውጪ ውጊያ ቢኖርም ታግሰው በትጋት ለጌት ስራ እየደከሙ እንዳለም ያውቃል::  እንዴት ነው ዛሬ የጌታን ስራ እየደከምን/እየሰራን ያለነው ? እርሱ ያያል::

3. ክፉዎችንም ልትታገሥ እንዳትችል፥ እንዲሁም ሳይሆኑ፦ ሐዋርያት ነን፡ የሚሉቱን መርምረህ ሐሰተኞች ሆነው እንዳገኘሃቸው አውቃለሁ፤ በሐዋ 20:29 ላይ ጳውሎስ  ሽማግሌዎችን ከቤተክርስቲያንዋ ጠርቶ ሲመክር ነግሯቸው ነበር ምን አይነት ሰዎች እንደሚነሱ ጌታም ከዛው ነው የቀጠለው::  እነዚህን ስህተተኞች አስወግደዋል:: ዛሬም አለማዊ ምኞትን አስወግደን የተባረከውን የጌታችንን መምጣት በጸጋው እንጠባበቅ::

የወቀሰባቸው ነገር

1.  ዳሩ ግን የምነቅፍብህ ነገር አለኝ፡ የቀደመውን ፍቅርህን ትተሃልና።

ብዙ  የምነቅፍብህ ነገር አለኝ ብሎ ፍቅርህን ትተሀል ነው::  ብዙ እንደተባለ እናስተውል ፍቅር በብዙ ተወክሏል ምክንያቱም የጌታ አገልግሎት ሁሉ መሆን ያለበት በፍቅር ስለሆነ::  ፍቅር ከሌለ እንደሚንሿሿ ጸናጽል ነን:,  ጌታን ወደን ከዛም ሰውን ሁሉ እንድንወድ ተጠርተናልና::  ፍቅራችን ይብዛ!!

የዮሐንስ ራእይ 2: 5-7

5፤ እንግዲህ ከወዴት እንደ ወደቅህ አስብ ንስሐም ግባ የቀደመውንም ሥራህን አድርግ፤ አለዚያ እመጣብሃለሁ ንስሐም ባትገባ መቅረዝህን ከስፍራው እወስዳለሁ። 

6፤ ነገር ግን ይህ አለህ፤ እኔ ደግሞ የምጠላውን የኒቆላውያንን ሥራ ጠልተሃልና።

7፤ መንፈስ ለአብያተ ክርስቲያናት የሚለውን ጆሮ ያለው ይስማ። ድል ለነሣው በእግዚአብሔር ገነት ካለው ከሕይወት ዛፍ እንዲበላ እሰጠዋለሁ።

ቃሉን እንደመስታወት ነውና በቃሉ ውስጥ ተነክቼ በፊቱ መምጣት ሲገባኝ እንደገና ሌላ መልእክትን ላከልኝ ሊምረኝ የወደደ ጌታ::  የተለየ ፍቺ ካለ እታረማለሁ::  

ያ የድሮው ፍቅር የት ሄደ እኔን ብቻም አይመስለኝም ሁላችንንም ነው ጌታ የሚጠይቀው ዛሬ ለማንበብ ያህል ማንበብ የለብንም ንስሀ እንግባ ፍቅሩን በልባችን የሚያድስ እርሱ ነው::  መፈለግንም ማድረግንም በእኛ የሚሰራ እርሱ ነውና::  አይለፈን ይህ አጋጣሚ እንጠቀምበት::  ሁሉ ሰላም ቢመስል ብንዘምር ብናገለግል ነፍሳችንን እንኳን ለመቃጠል አሳልፈን ብንሰጥ ምንም ጥቅም የለውም ፍቅር ከሌለ::  ይህ በአንድ ጊዜ የሚሆን አይደለም ቀስ በቀስ ስፍራችንን ለቀን ይሆናልና እንመለስ:: የሚዘረዝረው መልካም ነገር ስለ ኤፌሶን ቤተክርስቲያን የሚገርም ነው ግን ምን ያደርጋል?  ፍቅር ቀዝቅዟልና ዋጋ የለውም::  እርሱ የሚጠላውን ጠልተዋል ግን ፍቅር ጎደለ::

እንግዲህ ከወዴት እንደ ወደቅህ አስብ ንስሐም ግባ የቀደመውንም ሥራህን አድርግ፤ አለዚያ እመጣብሃለሁ ንስሐም ባትገባ መቅረዝህን ከስፍራው እወስዳለሁ።  ንስሀ መግባት ያስፈልጋል በወደቅንበት ነገር ደግሞ ደጋግሞ መናገር የለበትም ሊረዳን የሚፈልግ ጌታ እያሰበን ነው::  ፍቅር ብዙ ወይም ዋናው የተጠራንበት የታዘዝነውም ነገር ነውና::  የማቴዎስ 22: 37፤ ኢየሱስም እንዲህ አለው፦ ጌታ አምላክህን በፍጹም ልብህ በፍጹም ነፍስህም በፍጹም አሳብህም ውደድ። 38፤ ታላቂቱና ፊተኛይቱ ትእዛዝ ይህች ናት።39፤ ሁለተኛይቱም ይህችን ትመስላለች፥ እርስዋም፦ ባልንጀራህን እንደ ነፍስህ ውደድ፡ የምትለው ናት። ጌታ አዲስ ነገር አይደለም እየጠየቀ ያለው የቀደመውንም ሥራህን አድርግ፤ ነው እያለ ያለው አመድ  የለበሰ የተዳፈነውን እናራግፍ ዛሬ::

እንግዲህ ምን ያህል እንደራቅን እንይና በፊቱ ወድቀን እርዳን እንበለው ሁሉ በፍቅር ማሰሪያ መታሰር አለበት::  በፍጹም ፍቅር ከተመላለስን በፊቱ መሆንን አንጠግብም ሁሌ እርሱን የምንራብና የምንጠማ እንሆናለን አለበለዚያ ያለህን እወስደዋለሁ እያለን ነው:: ይህ ምን ማለት ነው ህልውናው የሌለበት ወይም ከሚመላለስበት ከመቅረዙ መካከል  መነሳት ማለት ነው በጣም ያስፈራል:: ምን ይጠቅመናል እሱ የሌለበት ህይወት ማባከን ነው::

በቃሉና በጸሎት በመትጋት ከቅዱሳን ጋር ህብረትን ለማድረግ በመጏጏት እንዲሁም ስለ እየሱስ በመመስከር የመጀመርያ ፍቅራችን መመለሱን ማወቅ እንችላለን:: 

መንፈስ ለአብያተ ክርስቲያናት የሚለውን ጆሮ ያለው ይስማ። ድል ለነሣው በእግዚአብሔር ገነት ካለው ከሕይወት ዛፍ እንዲበላ እሰጠዋለሁ።

ጆሮአችን ሰምቶ ልባችን ተለውጦ እንገኝ::  ሽልማቱም ከህይወት ዛፍ መብላትና ለዘላለም ከእርሱ ጋር መኖር::  አዳምና ሔዋን እንዳይደርሱበት ያስጠበቀውን የህወት ዛፍ የሚናገር ይመስለኛል::  ፍቅራችንን እናድስ!!

የዮሐንስ ራእይ 28-11

9፤ መከራህንና ድህነትህን አውቃለሁ፥ ነገር ግን ባለ ጠጋ ነህ፤ የሰይጣንም ማኅበር ናቸው እንጂ አይሁድ ሳይሆኑ፦ አይሁድ ነን፡ የሚሉት የሚሳደቡትን ስድብ አውቃለሁ።

10፤ ልትቀበለው ያለህን መከራ አትፍራ። እነሆ፥ እንድትፈተኑ ዲያብሎስ ከእናንተ አንዳንዶቻችሁን በወኅኒ ሊያገባችሁ አለው፥ አሥር ቀንም መከራን ትቀበላላችሁ። እስከሞት ድረስ የታመንህ ሁን የሕይወትንም አክሊል እሰጥሃለሁ።

ይህ መልክት የተፃፈው ለሰምርኔስም ቤተ ክርስቲያን ነው::  መልክቱን የላከው  

ሞቶ ከነበረው ሕያውም ከሆነው ፊተኛውና መጨረሻው ከሆነው ከእየሱስ ነው::  ሞትን ሞቼ ነበር አሁን ግን ህያው ነኝ ያለበት ምክንያት ሞት ነው እያሳደዳቸው ያለው ለዚህ ነው በመዝጊያውም ላይ ድል የነሣው በሁለተኛው ሞት አይጐዳም። እያለ የሚያመለክታቸው::  ግን በዚህ ሁሉ ውስጥ ሲያልፉ መቼም ጌታ ለምን ተወን አይመልስም አያተርፈንም እያሉ ጥያቄ ውስጥ መግባታቸው አይቀርም ነገር ግን እዚህ መልክት ላይ መከራህንና ድህነትህን አውቃለሁ፥ ያላየሁት አይምሰልህ ሞትን ድል የነሳሁኝ ነኝ ምንም ቢመጣ ጸንተህ ቁም ነው መልእክቱ::  ድህነት ውስጥ ቢሆኑም ጌታ የሚላቸው ግን ባለ ጠጋ ነህ፤ ነው የእኛና የጌታ አስተያየት ይገርማል::  እንዲሁም 

የሚደርስባቸውን ስድብ አውቃለሁ እያላቸው ነው። ስድቡ አይሁድ ካልሆኑ ነገር ግን ነን ከሚሉ ነው::  

የመልክቱ ዋና ጭብጥ በርቱ ነው !ሊመጣ ያለ ልትቀበለው ያለህን መከራ አለና አትፍራ። እነሆ፥ እንድትፈተኑ ዲያብሎስ ከእናንተ አንዳንዶቻችሁን በወኅኒ ሊያገባችሁ አለው፥ አሥር ቀንም መከራን ትቀበላላችሁ። እስከሞት ድረስ የታመንህ ሁን የሕይወትንም አክሊል እሰጥሃለሁ። ማለትም በወህኒ መጣል ብቻ ሳይሆን ሞትም እንዳለ ሊያሳያቸውና እንዲጸኑ ነው የጻፈው:: ቃሉ እንደሚል  2ኛ ጢሞቴዎስ 3: 12፤ በእውነትም በክርስቶስ ኢየሱስ እግዚአብሔርን እየመሰሉ ሊኖሩ የሚወዱ ሁሉ ይሰደዳሉ። ይህ ሞት በዘመናችን ብዙም የለም ግን ዓለም ልታሸፍተን ትፈልጋለች ከጌታ ስር እኛ የተጠራነው እሱን ልንመስል ነውና እንምሰለው:: በምንም ነገር ውስጥ ብናልፍ ጌታ ያያል ችላ አይለንም ድል የነሳ ጌታ አለን!  በምናልፍበት ነገር ሁሉ እንጽና::  እርሱ ድል ነስቷል!!  ሃሌሉያ!

የዮሐንስ ራእይ 2: 12-17

13፤ የሰይጣን ዙፋን ባለበት የምትኖርበትን አውቃለሁ፤ ስሜንም ትጠብቃለህ፥ ሰይጣንም በሚኖርበት፥ በእናንተ ዘንድ የተገደለው የታመነው ምስክሬ አንቲጳስ በነበረበት ዘመን እንኳ ሃይማኖቴን አልካድህም። 14፤ ዳሩ ግን ለጣዖት የታረደውን እንዲበሉና እንዲሴስኑ በእስራኤል ልጆች ፊት ማሰናከያን ሊያኖርባቸው ባላቅን ያስተማረ የበልዓምን ትምህርት የሚጠብቁ በዚያ ከአንተ ጋር ስላሉ፥ የምነቅፍብህ ጥቂት ነገር አለኝ።

15፤ እንዲሁ የኒቆላውያንን ትምህርት እንደ እነዚህ የሚጠብቁ ሰዎች ከአንተ ጋር ደግሞ አሉ።

ጰርጋሞን ቤተክርስትያን የምትገኘው በግሪክና በቱርክ መካከል ነው::  ይች ከተማ ጌታ እንደገለጸው የሰይጣን ዙፋን ባለበት የምትኖርበትን አውቃለሁ፤ ነው ያለው::  በጣኦት አምልኮ የተበከለ ወይም ባህላቸውየሆነ ነው::  እነዚህ ክርስትያኖች በለአም እስራኤልን እንዳሳተና 24ሺው እንዳለቀበት ዘመን ያለ ቁጣን የሚያመጣ ነው:: እንዲሁም ደግሞ የኒቆላውያንን ትምህርት የሚከተሉም ነበሩባት ቤተክርስቲያንዋ::   ጌታ እንደመልእክቱ ፀኃፊ እራሱን የጠራው በሁለት ወገን የተሳለ ስለታም ሰይፍ ያለው እንዲህ ይላል፦ ነው ያለው ይህ ውጊያና ቁጣም እንዳለበት ያሳያል:: አንዳንዱ ስለክርቶስ ህይወቱን ያጣል ሌላው ደግሞ ተመሳስሎ ለመኖር ያመቻምቻል::  ጌታ ሁሉንም ያያል!

ከዓለም ጋር ወዳጅነትን እንድመሰርት ጌታ አይፈልግም እራሳችንን ከዓለም እንለይ እንደሱ እንደሚሆኑት አንሆንም እኛ የምንወደውና የምንኖርለት ጌታ አለን:: ስለዚህ ንስሀ ግቡና ተመለሱ ነው የተባሉት::  ዛሬም መልክቱ ይኼው ነው::  ህይወታችንን እንይና እናስተካክል::

ይህንን ላደረገው ከህይወት መና ይበላል ያለው የህይወት መና እራሱ ጌታ ነው:;  ነጭም ድንጋይ በላዮ የተፃፈበት ይቀበላል ይላል ይህ የሮማውያን የዘመኑ ሽልማት ነው በጊዜው ያለውን የሚገባቸውን ምሳሌ ነው የሚነግራቸው::  ሽልማት በሰማይ አለ ለእያንዳንዳችን  ተዘጋጅቷል እንበርታ!  

ጆሮ ያለውይስማ!

የዮሐንስ ራእይ 2: 18-19

18፤ በትያጥሮንም ወዳለው ወደ ቤተ ክርስቲያን መልአክ እንዲህ ብለህ ጻስናካፍል

19፤ ሥራህንና ፍቅርህን እምነትህንም አገልግሎትህንም ትዕግሥትህንም ከፊተኛውም ሥራህ ይልቅ የኋለኛው እንዲበዛ አውቃለሁ።

ትያጥሮን ቤተክርስቲያን ሊድያ ሐዋ 16:14 የመጣችበት ከተማ ነው:: ይህች ከተማ በንግድ የታወቀች ናት::  የተለያዩ ነገሮችን ያመርታሉ ወደ ፊልጲስዮስና ሌሎችም ስፍራ ይነግዳሉ::  ሊድያ ሀር ሻጭ ነበረች::  

ስለ መልእክቱ ላኪ መግለጫ ስናይ:-

– እንደ እሳት ነበልባል የሆኑ ዓይኖች ያሉት – ይህ የእግዚአብሔርን ፍርድ የሚያሳይ ነው::

– በእቶንም የነጠረ የጋለ ናስ የሚመስሉ እግሮች ያሉት – ምንም የሚያቆመው የለም::

– የእግዚአብሔር ልጅ እንዲህ ይላል፦ እስከአሁን እራሱን የሰው ልጅ እያለ ይጠራ ነበር እዚህ ጋር ግን የእግዚአብሔር ልጅ ብሎ ነው እራሱን የጠራው::  ክብሩን ያሳያል! ይህንን ሁሉ ለምን መግለጽ አስፈለገው ብለን ስንል በመልክቱ  ውስጥ ማንነቱን ማሳየት ያለበት መልክት ስላለ ነው::  በመካከላቸው እርሱን እንዳይከተሉ የሚያደርግ ሰው ስላለ::

ይህች ቤተክርስትያን የተመሰገነችበት ብዙ ነገር አለ

ሥራህንና 

ፍቅርህን 

እምነትህንም 

አገልግሎትህንም 

ትዕግሥትህንም 

ከፊተኛውም ሥራህ ይልቅ የኋለኛው እንዲበዛ አውቃለሁ።

ይህ ሁሉ መልካም ነገር ያላትን ቤተክርስቲያን እንትወቀስ ያደረጋት ምን ይሆን?

ስለበዛልን ነገር ሁሉ ጌታን እናመስግን::  ህብረት ቢሆን ፍቅር ቢሆን ይኸው ቃሉን ማንበብ ቢሆን::  የኤፌሶን ቤተክርስቲያን የተወቀሰችው በፍቅርዋ መቀነስ ብቻ ነው እነዚህ ደግሞ ብዙ የበዛላቸው ናቸው::  ጌታ ይመጣልና እንዘጋጅ::

የዮሐንስ ራእይ 2: 20-29

20፤ ዳሩ ግን፦ ነቢይ ነኝ፡ የምትለውን ባሪያዎቼንም እንዲሴስኑና ለጣዖት የታረደውን እንዲበሉ የምታስተምረውንና የምታስተውን ያችን ሴት ኤልዛቤልን ስለምትተዋት የምነቅፍብህ ነገር አለኝ፤

የትያጥሮን  ቤተክርስቲያን ቅዱሳን በብዙ የተጉ ከፊት ይልቅ ስራው የበዛላቸው ነበሩና ጌታም ያላቸው 

ራእይ 2: 24፤ ዳሩ ግን ይህን ትምህርት ለማትይዙ ሁሉ የሰይጣንንም ጥልቅ ነገር እነርሱ እንደሚሉት ለማታውቁ ለእናንተ በትያጥሮን ለቀራችሁት እላለሁ፤ ሌላ ሸክም አልጭንባችሁም፥

25፤ ነገር ግን እስክመጣ ድረስ ያላችሁን ጠብቁ።

ዳሩ ግን ይህች ነብይ ግን በዚሁ ቤተክርስቲያን ውስጥ ብዙዎችን እያሳተች በእግዚአብሔር ላይ አመጽን ታለማምዳለች::   ልክ ኤልዛቤል በእስራኤል ላይ አመጽን እንዳመጣችውና ኤልያስ ዝናብ እንዳይዘንብ ለ3 ዓመት ሰማይ ተዘጋ::  አገሩ ሁሉ ከእርስዋ የተነሳ ተቀጣ:: በአካብ ዘመን የእግዚአብሔር አገልጋዮች ለእስዋ አማልክት አገልጋዮች ሆኑ እስራኤል አመነዘረች::

ይህችም ሴት ይህንኑ ነው ያደረገችው የጠለቀ የአጋንንት ስራ ውስጥ ገብታ የምትተነብየውም በዚሁ በክፉ መንፈስ ነበረ::  የሐዋርያት ሥራ 15

28-29፤ ለጣዖት ከተሠዋ፥ ከደምም፥ ከታነቀም፥ ከዝሙትም ትርቁ ዘንድ ከዚህ ከሚያስፈልገው በቀር ሌላ ሸክም እንዳንጭንባችሁ እኛና መንፈስ ቅዱስ ፈቅደናልና፤ ከዚህም ሁሉ ራሳችሁን ብትጠብቁ በመልካም ትኖራላችሁ። ጤና ይስጣችሁ።

ቃሉ እንደሚለው እኛና መንፈስ ቅዱስ ይህንን ወስነናል ብሏል ይህ ትእዛዝ ነው ለእኛ::  ከቃሉ ውጪ የሆነ ትንቢት ይቅርብን በዙሪያችንም ያሉትን እንመርምር  ትንቢት ሁሉ ከእግዚአብሔር አይደለምና::  የጌታ ፍርድ በዝች ሴት ላይ በአልጋ እጥላታለሁ የሚከተሏትንም ንስሀ ካልገቡ በታላቅ መከራ ውስጥ ይገባሉ::  ማየት ያለብን ነገር ጌታ ታግሷታል ንስሀ እንድትገባ እርስዋ ግን አሻፈረኝ አለች ስለዚህ እራሱን የእግዚአብሔር ልጅብሎ የጠራው ለዚች ቤተክርስቲያን ሲጽፍ ምክንያቱ ስልጣኔን የሚጋፋ አለ ማለቱ ነው::  ክብር ሁሉ የሚገባው ጌታ ነው::  

ያላችሁን ጠብቁ ሲል ይህ ለዛሬ ለእኛም ነው::  ሰው ይሰለችና  መጸለዮንም በቃል መሞላቱንም ችላ ይልና ህይወቱ ለብ ወደማለት እየሄደ መሆኑን አይገነዘብም ለብ ካልን ልተፋህ ነው እንደሚከተል እንወቅ መቅረዛችን ከሚወሰድ እንትጋ:: 

ሁልጊዜ እንትጋ የጌታ ነገር አያርጅብን::  ህብረትን ከቅዱሳን ጋር እናድርግ እርስ በእርሳችንም እንበረታታ::

ድል ለሚነሳው ሽልማት አለ ይላል ጌታ!

ጆሮ ያለው ይስማ!

ማራናታ

የዮሐንስ ራእይ 3: 1

1፤ በሰርዴስም ወዳለው ወደ ቤተ ክርስቲያን መልአክ እንዲህ ብለህ ጻፍ፦ ሰባቱ የእግዚአብሔር መናፍስትና ሰባቱ ከዋክብት ያሉት እንዲህ ይላል፦ ሥራህን አውቃለሁ ሕያው እንደ መሆንህ ስም አለህ ሞተህማል።

ለሰርዴስ  ቤተክርስቲያን መልክቱን ሲልክ ጌታ እራሱን የጠራበት ስም:- ሰባቱ የእግዚአብሔር መናፍስትና ሰባቱ ከዋክብት ያሉት ብሎ ነው::  አጠራሩ መልእክቱን ይወስነዋል ለምን ስለ መንፈስ ቅዱስና ስለ ቤተክርስቲያኑ አነሳ? በሌሎቹም ቤተክርስቲያኖች እራሱን በተለያየ ማዕረግ ነው የሚጠራው ሽልማቱም ይለያያል::  

ይህን ያለበት ምክንያት ስንመለከት ሥራህን አውቃለሁ ሕያው እንደ መሆንህ ስም አለህ ሞተህማል። ህያው ሆኖ መሞት ስም ብቻ?!  ምን አይነት አገላለጽ ነው?  ስራህን አውቃለሁ ከኔ የተሰወረ አይደለም እያላቸው ያለው ለእነሱ ብቻ ሳይሆን ለእኛም ነው::  እያየን ነው ጌታ::

እዚህ ቤተክርስቲያን ያሉት ቅዱሳን ያሉ ይመስላሉ እንጂ የያዙት ስም ብቻ ነው ድሮ ብርቱ ሆነው ሊሆን ይችላል ዛሬ ግን ሙት ሆነዋል:: ፕሮግራሞች ይደረጉ ይሆናል ግን ጌታ ሲያይ ሞተሀል እያለ ስለሆነ የሚያስፈልጋቸው የመንፈስ ቅዱስ ጉብኝት ነው::  

ትላንትና የኖርነው ኑሮ ለዛሬ ዋስትና አይደለም ዛሬ ተግተን መገኘት አለብን አለዛ የሞተ ተብሎ ነው የሚጠራው በጌታ ፊት:: ይህች ቤተክርስቲያን የስህተት ትምህርት ወይም መከራ የለባትም በርቱ አይዟችሁ ሲባሉ አናይም ጠላትም አይዋጋቸውም ስላልተዋጉት:: ከሞቱ የሚፈለገው እርሱ ነው ለምን ይዋጋቸዋል ያሉ መስለው መጥፋታቸውን ስላወቀ ትቷቸዋል ጠላትም::  ማንም የቆመ ቢመስለው እንዳይወድቅ ይጠንቀቅ!!!

መንፈስ ለአብያተ ክርስቲያናት የሚለውን ጆሮ ያለው ይስማ።

አቤቱ እርዳን መዳናችንን ዕለት ዕለት እንድንፈጽም!  አሜን

የዮሐንስ ራእይ 3

2፤ ሥራህን በአምላኬ ፊት ፍጹም ሆኖ አላገኘሁትምና የነቃህ ሁን፥ ሊሞቱም ያላቸውን የቀሩትን ነገሮች አጽና።

3፤ እንግዲህ እንዴት እንደ ተቀበልህና እንደ ሰማህ አስብ፥ ጠብቀውም ንስሐም ግባ። እንግዲያስ ባትነቃ እንደ ሌባ እመጣብሃለሁ በማናቸውም ሰዓት እንድመጣብህ ከቶ አታውቅም።

ጌታ ያለንበትን ሁኔታ ያውቃልና ለሚናገረን ነገር ልብ እንስጥ::  ይህንን ራዕይ ጌታ እንድንማርበት በቃሉ ሲሰጠን ከዚህ አይነት ስህተት እንድንጠበቅና እንድንነቃ ነው::  የትኛውም ቤተክርስቲያን ወይም አማኝ በነዚህ መልክቶች እራሱን መመርመር ይችላል::  ሆስፒታል ስንድ ሃኪም ኤክስሬ ወይም ደም እንድንሰጥና ያለውን ችግር  ለማወቅ እንደሚጥር ጌታም ይህንን ቃል እራሳችንን እንድንመረምርበት ሰቶናልና በቃሉ እውነት ተረድተን ህይወታችንን እናስተካክል::

ሥራህን በአምላኬ ፊት ፍጹም ሆኖ አላገኘሁትምና የነቃህ ሁን፥ 

እንዴት ያስደነግጣል?! እንዴት ነው ፍጹም የሚኮነው?! ወደቀደመው ነገር በመመለስ እዚህ ጋር ጌታ የሚያስታውሳቸው እንዴት ወደጌታ እንደመጡ ነው::  ወደነው እሺ ብለን ፈልገነው መተን ታድያ ዛሬ ምን ነካን ነው መልክቱ:: የነቃህ ሁን ይላልና ቃሉ እንንቃ እኛ ህያዋን ነን::  ከዚህ ዓለምም አይደለንምና ለጌታ እንገዛ:: 

ሊሞቱም ያላቸውን የቀሩትን ነገሮች አጽና።  ፈጽሞ ከህይወት መንገድ አትውጣ እንደ ሌባ እመጣለሁና ጊዜ አለኝ ብለህ አትዘናጋ አሁኑኑ እርምጃ ውሰድ!  ተመለስ ነው መልእክቱ መመለስ ያለብን ነገር ይኖር ይሆን?

ማንም ቢደክም  ጌታ ወድያው ለመፍረድ አይደለም የሚነሳው የሚለን ንስሀ ግቡና ተመለሱ ነው::  ዛሬ ቀን ሳለ እራሳችንን እንመርምር::

እንግዲህ እንዴት እንደ ተቀበልህና እንደ ሰማህ አስብ፥ ጠብቀውም ንስሐም ግባ ነው መልእክቱ ሊረዳን ይፈልጋል:: 

የማቴዎስ ወንጌል 25

13፤ ቀኒቱንና ሰዓቲቱን አታውቁምና እንግዲህ ንቁ።

እንንቃ!!  

የዮሐንስ ራእይ 3

2፤ ሥራህን በአምላኬ ፊት ፍጹም ሆኖ አላገኘሁትምና የነቃህ ሁን፥ ሊሞቱም ያላቸውን የቀሩትን ነገሮች አጽና።

3፤ እንግዲህ እንዴት እንደ ተቀበልህና እንደ ሰማህ አስብ፥ ጠብቀውም ንስሐም ግባ። እንግዲያስ ባትነቃ እንደ ሌባ እመጣብሃለሁ በማናቸውም ሰዓት እንድመጣብህ ከቶ አታውቅም።

ጌታ ያለንበትን ሁኔታ ያውቃልና ለሚናገረን ነገር ልብ እንስጥ::  ይህንን ራዕይ ጌታ እንድንማርበት በቃሉ ሲሰጠን ከዚህ አይነት ስህተት እንድንጠበቅና እንድንነቃ ነው::  የትኛውም ቤተክርስቲያን ወይም አማኝ በነዚህ መልክቶች እራሱን መመርመር ይችላል::  ሆስፒታል ስንድ ሃኪም ኤክስሬ ወይም ደም እንድንሰጥና ያለውን ችግር  ለማወቅ እንደሚጥር ጌታም ይህንን ቃል እራሳችንን እንድንመረምርበት ሰቶናልና በቃሉ እውነት ተረድተን ህይወታችንን እናስተካክል::

ሥራህን በአምላኬ ፊት ፍጹም ሆኖ አላገኘሁትምና የነቃህ ሁን፥ 

እንዴት ያስደነግጣል?! እንዴት ነው ፍጹም የሚኮነው?! ወደቀደመው ነገር በመመለስ እዚህ ጋር ጌታ የሚያስታውሳቸው እንዴት ወደጌታ እንደመጡ ነው::  ወደነው እሺ ብለን ፈልገነው መተን ታድያ ዛሬ ምን ነካን ነው መልክቱ:: የነቃህ ሁን ይላልና ቃሉ እንንቃ እኛ ህያዋን ነን::  ከዚህ ዓለምም አይደለንምና ለጌታ እንገዛ:: 

ሊሞቱም ያላቸውን የቀሩትን ነገሮች አጽና።  ፈጽሞ ከህይወት መንገድ አትውጣ እንደ ሌባ እመጣለሁና ጊዜ አለኝ ብለህ አትዘናጋ አሁኑኑ እርምጃ ውሰድ!  ተመለስ ነው መልእክቱ መመለስ ያለብን ነገር ይኖር ይሆን?

ማንም ቢደክም  ጌታ ወድያው ለመፍረድ አይደለም የሚነሳው የሚለን ንስሀ ግቡና ተመለሱ ነው::  ዛሬ ቀን ሳለ እራሳችንን እንመርምር::

እንግዲህ እንዴት እንደ ተቀበልህና እንደ ሰማህ አስብ፥ ጠብቀውም ንስሐም ግባ ነው መልእክቱ ሊረዳን ይፈልጋል:: 

የማቴዎስ ወንጌል 25

13፤ ቀኒቱንና ሰዓቲቱን አታውቁምና እንግዲህ ንቁ።

እንንቃ!!  

የዮሐንስ ራእይ 3: 4-6

4፤ ነገር ግን ልብሳቸውን ያላረከሱ በሰርዴስ ጥቂት ሰዎች ከአንተ ጋር አሉ፥ የተገባቸውም ስለ ሆኑ ነጭ ልብስ ለብሰው ከእኔ ጋር ይሄዳሉ።

5፤ ድል የነሣው እንዲሁ በነጭ ልብስ ይጐናጸፋል፥ ስሙንም ከሕይወት መጽሐፍ አልደመስስም፥ በአባቴና በመላእክቱም ፊት ለስሙ እመሰክርለታለሁ።

በሰርዴስ ቤተክርስቲያን ያልረከሱና ስም ብቻ ያልሆኑ በቅድስና የሚመላለሱ ጥቂት ቅዱሳን  አሉ::  ለእነርሱ ልብሳቸውን ላላረከሱት የሚላቸው የተገባቸውም ስለ ሆኑ!  ዋዉ የተገባቸው!  ምንድነው የሚገባቸው? 

ነጭ ልብስ መልበስና  ከእርሱ  ጋር መሄድ።  ይህ ነጭ ልብስ እራሱ እየሱስ ነው አዲሱን ሰው ልበሱ ተብለን የለም?  እንዲሁም ደግሞ በራዕይ መጽሐፍ ላይ እነዚህ ነጫጭ የለበሱ እነማን ናቸው ከተባሉት ውስጥ ናቸው ::  እኛም ነጩን ልብስ ለብሰን እንገኝ እርሱ በእኛ ይክበር ይንገስ::  

ሌላው ደግሞ የሚላቸው ስሙንም ከሕይወት መጽሐፍ አልደመስስም፥ በስማችን የሚያውቀን እረኛ ስማችንን በህይወት መጽሐፍ  ጽፎታል አቤት እንዴት ያለ መወደድ ነው?! እኔ በስም ታውቄ ስሜ በበጉ መጽሐፍ ላይ ተጽፏል!  ምን እላለሁ አሁንም እገዛልሀለሁኝ አባት ሆይ::

በዚህም ብቻ አያበቃል የሚገባላቸው ቃል በመጨረሻ  በነጩ ዙፋን ፍርድ ጊዜ እየሱስን አውቃለሁ  እርሱ ነው ጽድቄ ብለን ስንመልስ አብ ወደ እየሱስ ነው የሚያየው እየሱስም እንዳላቸው በአባቴና በመላእክቱም ፊት ለስሙ እመሰክርለታለሁ አለ::  የእርሱ ምስክርነት አውቃታለሁ የሚለው እዚህ ምድር ላይ በእርሱ ሳናፍር ከመሰከርን እርሱም በሰማይ ይመሰክርልናል:: የተቀሩት ሞታችኃል የተባሉት የህይወትን መንገድ ትተው በምናለበት ብዙ ነገር እየቀላቀሉ ስለመጡ ነው:: ዛሬም ጸንተን ቆመን ለስሙ እንመሰክራለን::

ዛሬ ቀን ሳለ ህይወታችን እየሱስን ያሳይ ምስክርነት ወንጌልን መመስከር (ዋና ስራችን ነው) ብቻ ሳይሆን የህይወትም ምስክርነት ሊኖረን ይገባል::  እርሱን በመፍራትና በቅድስና ስንኖር እንዳንተ/እንዳንቺ መኖር እፈልጋለሁ ይላሉ ሰዎች ፍሬ ያለውህይወት እንኑርእርሱንም እናስከብረው::

ጌታ ከሞተ ህይወት ይታደገን ህያው የሆነ የሚታይ ህይወትን በመንፈስ ቅደስ ያድርግልን::

የዮሐንስ ራእይ 3: 7-9

7፤ በፊልድልፍያም ወዳለው ወደ ቤተ ክርስቲያን መልአክ እንዲህ ብለህ ጻፍ፦ የዳዊት መክፈቻ ያለው፤ የሚከፍት፥ የሚዘጋም የሌለ፤ የሚዘጋ፥ የሚከፍትም የሌለ፤ ቅዱስና እውነተኛ የሆነው እርሱ እንዲህ ይላል፦

8፤ ሥራህን አውቃለሁ፤ እነሆ፥ በአንተ ፊት የተከፈተ በር ሰጥቼአለሁ ማንምም ሊዘጋው አይችልም፤ ኃይልህ ምንም ትንሽ ቢሆን ቃሌን ጠብቀሃልና፥ ስሜንም አልካድህምና።

እራሱን የጠራበትን ማዕረግ ስናይ የዳዊት መክፈቻ ያለው፤  ከዳዊት ዘር ንጉስ አይጠፋም የተባለውን ትንቢት የፈጸመ

የሚከፍት፥  ይህ ንጉስ ከከፈተ ከፈተ ነው

የሚዘጋም የሌለ፤  እርሱ ከፍቷልና ማን ይችላል መዝጋት

የሚዘጋ፥   ከዘጋም ዘጋ ነው

የሚከፍትም የሌለ፤  ይህ ንጉስ ከዘጋ ዘጋ ነው

ቅዱስና እውነተኛ የሆነው:- እርሱ ቅዱስና እውነተኛ መሲህ ነው

ለምን ጌታ ስለ ቁልፍ እንዲሁም ቅዱስና እውነተኛ የሚለውን ማዕረግ እዚህ ስፍራ ላይ ተጠቀመ?  እስከ አሁን ያሉትን ማዕረጎች ስናይ በመጀመርያ ዮሃንስ ካየው ማንነቱ ነው የተጠቀሰው ይህ ግን በምዕራፍ አንድ ላይ አልተጠቀሰም:: የተከፈተ በር ስለሰጣቸው ነው ስለ ቁልፍ የሚናገረው ደግሞም አይሁድ ሳይሆኑ ነን የሚሉ ውሸታሞች ብዙ ነገር ሊልኑባቸው ስለጣሩ ነው::  ማለትም ስታችኃል እኛ ነን የመጀመሪያዎቹ የእግዚአብሔር ህዝብ::  ነገር ግን ጌታ መሲህ እንደሆነ እራሱን እውነተኛና ቅዱስ ብሎ ይጠራል::  በተጨማሪም የሞትና የሲኦልን ቁልፍ የያዘ እርሱ እንጂ እነዚህ ሰዎች የሚሉት አይደለም የሚሆነው::  እንዴት ደስ ይላል ማንም በእኛ ህይወት ላይ አይወስንም የሚወደን ጌታ እንጂ!!!  ስሙ ይባረክ!  ስራህን አውቃለሁ የምትለው በሁሉ ቤተክርስቲያን የተጠቀሰ ነው ዛሬም ስራችንን ያውቃል:  ይመረምራል ለእርሱ ታማኝ እንሁን!

የዮሐንስ ራእይ 3: 12

12፤ ድል የነሣው በአምላኬ መቅደስ ዓምድ እንዲሆን አደርገዋለሁ፥ ወደ ፊትም ከዚያ ከቶ አይወጣም፤ የአምላኬን ስምና የአምላኬን ከተማ ስም፥ ማለት ከሰማይ ከአምላኬ ዘንድ የምትወርደውን አዲሲቱን ኢየሩሳሌምን፥ አዲሱንም ስሜን በእርሱ ላይ እጽፋለሁ።

የፊላደልፍያ ቅዱሳን በመከራ ውስጥ እያለፉ በመሆናቸው ጌታ ምንም ሲወቅሳቸው አናይም ነገር ግን ያላችሁን እስክመጣ ጠብቁ ነው የተባሉት::  ሰው ይሰላችና ካለበት ነገር ሳያስበው እየተንሸራተተ ስለሚሄድ ነው ያለህን ጠብቅ የሚለን ጌታ::  

ይህንን ሁሉ አልፎ ድል ለነሳ ሽልማቱ ጌታ የሚገባላቸው ቃል :-

1.  በአምላኬ መቅደስ ዓምድ እንዲሆን አደርገዋለሁ፥ ወደ ፊትም ከዚያ ከቶ አይወጣም፤  ዓምድ የሌለው ቤት የለም ያለ ዓምድም ቤት አይቆምም ቃል እየገባላቸው ያለው እርግጠኛ ሁኑ የዓምዱን ያህል በቤቴ መሆናችሁ አይቀርምና::  ከዚያም ከቶ ማንም አያወጣም::  ፈተናቸው ከአይሁድ ነበረና እኛ የምንላችሁን ካላደረጋችሁ አትድኑም ወይም የእግዚአብሔር መሆን  አትችሉም የሚሉ ስለነበሩ የዳዊት መክፈቻ ያለው፤ የሚከፍት፥ የሚዘጋም የሌለ፤ የሚዘጋ፥ የሚከፍትም የሌለ፤ ቅዱስና እውነተኛ ከሆነው ነው የስራው ባለቤት:: ዛሬም ጌታ እንድንጸና እንዲሁም የምንወርሰውን እንወቅ::

2.  የአምላኬን ስምና የአምላኬን ከተማ ስም፥ ማለት ከሰማይ ከአምላኬ ዘንድ የምትወርደውን አዲሲቱን ኢየሩሳሌምን፥ አዲሱንም ስሜን በእርሱ ላይ እጽፋለሁ።  ይህንን ስም ማንም አያውቀውም ግን ይህንን ስም በእኛ ላይ ይጽፈዋል:: 

ተስፋችን ህያው ነውና እንጽና ያለንንም ተግተን እንጠብቅ::  ጌታ ይመጣል::

የዮሐንስ ራእይ 3: 14-16

14፤ በሎዶቅያም ወዳለው ወደ ቤተ ክርስቲያን መልአክ እንዲህ ብለህ ጻፍ፦ አሜን የሆነው፥ የታመነውና እውነተኛው ምስክር፥ በእግዚአብሔርም ፍጥረት መጀመሪያ የነበረው እንዲህ ይላል፦

15፤ በራድ ወይም ትኩስ እንዳይደለህ ሥራህን አውቃለሁ። በራድ ወይም ትኩስ ብትሆንስ መልካም በሆነ ነበር።

16፤ እንዲሁ ለብ ስላልህ በራድም ወይም ትኩስ ስላልሆንህ ከአፌ ልተፋህ ነው።

ለሎዶቅያ ላይ የተገለጠበት ማዕረግ:- 

1. አሜን የሆነው፥ የእግዚአብሔር የተስፋ ቃል ሁሉ የተገለጠበት ጌታ በእርሱ ዘንድ አሜን ነው::

2. የታመነውና እውነተኛው ምስክር፥  እየሱስ ነው እውነተኛና የታመነ ምስክር ስለ አባቱም የተረከልን አባቱንም በእርሱ ውስጥ አሳየን::  የአብንም ስራ በእርሱ ውስጥ አየን:: የእየሱስ ምስክርነግ እውነተኛ ነው:: 

3. በእግዚአብሔርም ፍጥረት መጀመሪያ የነበረው:: የዮሐንስ 1: 1፤ በመጀመሪያው ቃል ነበረ፥ ቃልም በእግዚአብሔር ዘንድ ነበረ፥ ቃልም እግዚአብሔር ነበረ።  ጌታ እየሱስ ፍጥረት አይደለም ሁሉ ሲፈጠር ቭን ያለእርሱ የተፈጠረ የለም:: እርሱ አልፋና ኦሜጋ ነው::

እንግዲህ እንዲህ ባለው እውነተኛና የታመነ ምስክር ፊት የሎዶቅያ ቤተክርስቲያን ምን ትመስላለች? በራድ ወይም ትኩስ እንዳይደለህ ሥራህን አውቃለሁ። በራድ ወይም ትኩስ ብትሆንስ መልካም በሆነ ነበር።

እንዲሁ ለብ ስላልህ በራድም ወይም ትኩስ ስላልሆንህ ከአፌ ልተፋህ ነው።

እንዴት ከባድ ነገር ውስጥ ነው ያሉት?! ለብ ያለ ውሃ ማን ይፈልጋል? ለጌታ የሚያቀርቡለት ህይወትና አምልኮ ምንም የሚጋብዝ አይደለም::  ለብ ያለ ነው:: ለመዋጥ አይቻልም መትፋት እንጂ!  የሚገርመው ልተፋህ ነው ብሎ ያስጠነቅቃል ምን አይነት ፍቅር ነው? ማንም እንዲጠፋበት የማይፈልግ ጌታ::  ይህች ቤተክርስቲያን ከመንፈስ ቅዱስ እሳት ወጥተዋል ግን አላስተዋሉም ያለ መንፈስ ቅዱስ መመላለስ ወደ ለብታ ነው የሚያመጣው::

ለእኛም ዛሬ የሚቀርልን ነገር ይህ ርሁሩህ ጌታ ህይወታችንን እንድናይ ይፈልጋል::  እንደው እንደነገሩ ነው ጸሎታችን? አምልኳችን?  ለነፍሳትን ግድ ይለናል? ወይስ የሌሎች ስራ ነው?  ቸልታ ማለት ለብታ ነው::  በመንፈስ ቅዱስ እየተቀጣጠልን ነው ወይስ የራሳችንን እስት እያቀጣጠልን?  እርሱ አንዳች ጎሎት በሰው አይደገፍም:: በአካሉ ውስጥ ምን እያደረግን ነው?  ጌታ ስራህን አውቃለሁ እንዳለ ስራችንን ያውቃል::  በመንፈስ እንቀጣጠል::

የዮሐንስ ራእይ 3: 17-18

17፤ ሀብታም ነኝና ባለጠጋ ሆኜአለሁ አንድም ስንኳ አያስፈልገኝም፡ የምትል ስለ ሆንህ፥ ጐስቋላና ምስኪንም ድሀም ዕውርም የተራቆትህም መሆንህን ስለማታውቅ፥

18፤ ባለ ጠጋ እንድትሆን በእሳት የነጠረውን ወርቅ፥ ተጐናጽፈህም የራቁትነትህ ኃፍረት እንዳይገለጥ ነጭ ልብስን፥ እንድታይም ዓይኖችህን የምትኳለውን ኵል ከእኔ ትገዛ ዘንድ እመክርሃለሁ።

የጌታ እይታና የሰው እይታ ልዩነቱን እናያለን::  

ይህች ቤተክርስቲያን የምትለው:- 

ሀብታም ነኝ

ባለጠጋ ሆኜአለሁ 

አንድም ስንኳ አያስፈልገኝም፡ ነው

በጌታ እይታ ደግሞ

ጐስቋላ

ምስኪንም 

ድሀም 

ዕውርም 

የተራቆትህም መሆንህን ስለማታውቅ፥

የሆነችውን ያላወቀች ቤተክርስቲያን ናት ዛሬ ጣታችንን ወደዝች ቤተክርስቲያን እንጠቁም እንጂ መልክቱ ለአንባቢው ሁሉ ነው::  ምንድነው ያላወቅነው ነገር?! ድሀ ሆነን ሳለ ሀብታም ነን የምንልበት ጉዳይ በምድራዊው ነው እራሳችንን የምንለካው?  ወይስ በማያልፈው በጌታ ቃልና በመንፈሱ ነው እራሳችንን የምንመረምረው?  ጸጋውን ይስጠንና እራሳችንን እንይ ምክሩንም እንስማ::

ይህወታችንን እንደቀልድ የምንይዘው ጉዳይ አይደለም::  እነሱን የመከረው ለኛም ይጠቅማል::  መፍትሄ ሳይሰጥ ችግር ብቻ ገልጦ አይሄድም የእኛ ጌታ አላማው መርዳት ስለሆነ:: ማነው ከእኛ መካከል እርቃኑን ወቶ የሚሄድ?  አሳቡ እንኳን ይዘገንናል እንኳን ተፈጽሞ ማየት ታድያ እንዲሁ ቶሎ እርምጃ መውሰድ አለብን እራቁትነታችንን ካሳየን በመንፈስ::

ምክሩም:- ባለ ጠጋ እንድትሆን (የምድሩን እንርሳውና):- 

በእሳት የነጠረውን ወርቅ፥ ተጐናጽፈህም የራቁትነትህ ኃፍረት እንዳይገለጥ ነጭ ልብስን፥ 

እንድታይም ዓይኖችህን የምትኳለውን ኵል ከእኔ ትገዛ ዘንድ እመክርሃለሁ።

ልብሱንም እንድንለብስ ነጩ ልብስ ተሰቶናል እንደወርቅ የሚፈተነውን እምነታችንን እንድናንነሳ ይፈልጋል አይናችንንም እንድንኳል::  ይህ ሁሉ ግዛ የሚለንን ኑና በነጻ ግዙ ብሎ ያወጀውን የመንፈስ ቅዱስን ስጦታ በልግስና ሳይሰስት የሚሰጠውን እንቀበል::  በራሳችን አንዳች ማድረግ አንችልምና ዕለት ዕለት መንፈስ ይሙላብን:,  

አሜን!

የዮሐንስ ራእይ 3: 19-22

19፤ እኔ የምወዳቸውን ሁሉ እገሥጻቸዋለሁ እቀጣቸውማለሁ፤ እንግዲህ ቅና ንስሐም ግባ።

20፤ እነሆ በደጅ ቆሜ አንኳኳለሁ፤ ማንም ድምፄን ቢሰማ ደጁንም ቢከፍትልኝ፥ ወደ እርሱ እገባለሁ ከእርሱም ጋር እራት እበላለሁ እርሱም ከእኔ ጋር ይበላል።

እኔ የምወዳቸውን ሁሉ እገሥጻቸዋለሁ እቀጣቸውማለሁ፤ እንግዲህ ቅና ንስሐም ግባ። ለብ ላለችው ቤተክርስቲያን የሰጣት ተግሳጽ ምክሬን ስሚ ደሀ ነሽ ተራቁተሻል ነው ከዛም ሲበዛ በደጅ መሆን ነው::  ለሰው ከእርሱ መለየት የባሰ ቅጣት ይኖር ይሆን?!  እኔ የለም ባይ ነኝ!  ጌታ ወቷል እኮ ከመካከላቸው ግን አላስተዋሉም::  ፕሮግራም እየቀጠለ ነውግን ተመላኪውየለም:: ማስተዋል ይሁንልን::

አንድ እንኳን አያስፈልገኝም የምትለው ሎዶቅያ ጌታዋን ውጪ አድርጋ ነው::  ምን አላት ታድያ?!   በደጅ ቆሜ አንኳኳለሁ የሚጠቀሰው ለአዲስ ሰው ሆንዋል ጌታ ግን ለቤተክርስቲያን በስሙ ለተጠሩት ነው የተጠቀመው::  የሚፈልገው ህብረት ነው::  እራት መብላት ከእኛ ጋር ጊዜን ማሳለፍ ነው የሚፈልገው::  ቁርስ እበላለሁ ቢሆን ወደ ጉዳያችን ወደ ስራ ለመሄድ ልባችን የተነሳ ይሆንና ብዙ ጊዜ ላንሰጥ እንችላለን እራት ግን የምንቸኩልበት ጊዜ አይደለም ቁጭ ብለን ከእርሱ ጋር ጊዜ እንድናሳልፍ የተመቸውን ጊዜ ነው የመረጠው::

የጌታ ፍቅርይገርማል በደጅ ቢሆንም ለመግባት ያንኳኳል እንጂ መብታችንን ጥሶ ልግባ አይልም::  መገዛት በውድ እንጂ በግድ አይደለም::  እንደዚህም ሆኖ መልእክት ከመላክ አልቦዘነም::  አረ አስተውሉ እያለነው::  እራሳችንን ብንመረምር ባልተፈረደብንም ነበር ይላል ቃሉ::  ክርስትና ከክርስቶስ ጋር ህብረት ነው::  ከእርሱ ጋር ህብረትን ስናደርግ ከቅዱሳንም ጋር ህብረትን እያደረግን ጸጋን እንከፋፈላለን::  

የምናገኘው ሽልማት:-

21፤ እኔ ደግሞ ድል እንደ ነሣሁ ከአባቴም ጋር በዙፋኑ ላይ እንደተቀመጥሁ፥ ድል ለነሣው ከእኔ ጋር በዙፋኔ ላይ ይቀመጥ ዘንድ እሰጠዋለሁ።  አሜን

ጆሮ ያለው ይስማ!!

የዮሐንስ ራእይ 4: 1-7

2፤ ወዲያው በመንፈስ ነበርሁ፤ እነሆም፥ ዙፋን በሰማይ ቆሞአል በዙፋኑም ላይ ተቀማጭ ነበረ፤

4፤ በዙፋኑ ዙሪያም ሀያ አራት ዙፋኖች ነበሩ፥ በዙፋኖቹም ላይ ነጭ ልብስ ለብሰው በራሳቸውም የወርቅ አክሊል ደፍተው ሀያ አራት ሽማግሌዎች ተቀምጠው ነበር።

በዝች አጭር ባለ11 ቁጥር ምዕራፍ ውስጥ ስለዚህ ታላቅ ዙፋን 12 ጊዜ ተጠቅሷል::  እንድናውቅ የተፈለገው በሰማይ ስላለው የዙፋኑ ክፍል ንው::  የተከፈተ በር ውስጥ ነው የገባው ዙፋኑ  ወዳለበት::  ስለዙፋኑና እንስሳቱ ጥልቅ የሆነ ነገር በአእምሮ ለመሳልና ለመረዳት የሚከብድ ነው ደስ የሚለው ስንሄድ እናየዋለን ዛሬ ግን ምን እንወቅ? 

በዙፋኑ  ላይ አምላካችን አለ የሰማይና የምድር ፈጣሪ ምን አይነት ቤት ሰርቶ እየጠበቀን ይሆን? ዓይን ያላየው  ጆሮም ያልሰማው አይደልየተባልነስ ስፍራ ላዘጋጅላችሁ እሄዳለሁ እኔ ባለሁበት እናንተ ትሆናላችሁ ብሎናል::  እንዴት አስውቦ እንደሚሰራው ማሰብ ነው::  ሁን ሲለው ሁሉ ይፈጠራልና::

ሌላው 24 ዙፋኖችና የተቀመጡባቸውም አሉ ነጭ የለበሱና የወርቅ ዘውድ የጫኑ ማንነታቸው ካልተገለጸ ልገምት አልነሳም ስሄድ አያቸዋለሁ::  እንግዲህ ይህንን ጌታ እንዴት እናምልከው?  ምን አይነት መስዋትስ ይቀበላል?  እራሱ በሰራው ስፍራ ከብሮ ያለው ጌታ ከእኛ የሚፈልገው የተሰበረ መንፈስና የልብ ትህትናን እንዲሁም ቃሉን ማክበርን ነው::

ትንቢተ ኢሳይያስ 66

1፤ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፦ ሰማይ ዙፋኔ ነው፥ ምድርም የእግሬ መረገጫ ናት፤ የምትሠሩልኝ ቤት ምን ዓይነት ነው? የማርፍበትስ ስፍራ ምንድር ነው?

2፤ እነዚህን ሁሉ እጄ ሠርታለችና እነዚህ ሁሉ የእኔ ናቸው ይላል እግዚአብሔር፤ ነገር ግን ወደዚህ ወደ ትሑት፥ መንፈሱም ወደ ተሰበረ፥ በቃሌም ወደሚንቀጠቀጥ ሰው እመለከታለሁ።

ይህንን ጌታ ልናመልክ ተጠርተናል!  እናመልክሃለን አምላካችን ሆይ አንተ ትልቅ ነህ ተባረክ!!  በዙፋንህ ከብረህ ላለኸው ለአንተ ክብር ይሁን! አሜን!

የዮሐንስ ራእይ 4: 8-11

8፤ አራቱም እንስሶች እያንዳንዳቸው ስድስት ክንፎች አሉአቸው፥ በዙሪያቸውና በውስጣቸውም ዓይኖች ሞልተውባቸዋል፤ ቅዱስ፥ ቅዱስ፥ ቅዱስ፥ የነበረውና ያለ የሚመጣውም፥ ሁሉንም የሚገዛ ጌታ አምላክ፤ እያሉ ቀንና ሌሊት አያርፉም። 

9፤ እንስሶቹም በዙፋን ላይ ለተቀመጠው ከዘላለምም እስከ ዘላለም በሕይወት ለሚኖረው ለእርሱ ክብርና ውዳሴ ምስጋናም በሰጡት ጊዜ፥

10-11፤ ሀያ አራቱ ሽማግሌዎች በዙፋን ላይ በተቀመጠው ፊት ወድቀው፦ ከዘላለም እስከ ዘላለም በሕይወት ለሚኖረው እየሰገዱ፦ ጌታችንና አምላካችን ሆይ፥ አንተ ሁሉን ፈጥረሃልና ስለ ፈቃድህም ሆነዋልና ተፈጥረውማልና ክብር ውዳሴ ኃይልም ልትቀበል ይገባሃል፡ እያሉ በዙፋኑ ፊት አክሊላቸውን ያኖራሉ። 

በቀንና በለሊት ሳያቋርጡ  ቅዱስ፥ ቅዱስ፥ ቅዱስ፥ የነበረውና ያለ የሚመጣውም፥ ሁሉንም የሚገዛ ጌታ አምላክ፤ እያሉ ያመልኩታል።  አምላካችን አምልኮ አይጎድልበትም!  ሁሌም ይመለካል::  

አምላካችን:-

 – የነበረው

–  ያለ 

– የሚመጣ፥ 

–  ሁሉንም የሚገዛ ጌታ አምላክ፤ እንደሆነ እንወቅ::  

እንስሶቹ እንዲህ ብለው ሲያመልኩት 24ቱ ሽማግሌዎችም ተቀላቀሉና አክሊላቸውን በዙፋኑ ፊት አድርገውና በዙፋኑም ፊት ወድቀው እየሰገዱ ከዘላለም እስከ ዘላለም በሕይወት ለሚኖረው፦ 

– ጌታችንና አምላካችን ሆይ፥ 

– አንተ ሁሉን ፈጥረሃልና 

– ስለ ፈቃድህም ሆነዋልና 

– ተፈጥረውማልና 

ስለዚህ:- 

ክብር ውዳሴ ኃይልም ልትቀበል ይገባሃል፡ እያሉ ሰገዱ። 

አሜን ይህ የዘላለም ጌታ ድሮም ዛሬም ወደፊትምያለ ጌታ አምልኮ ስግደት ሊቀበልይገባዋል::  እርሱ ሁሉን ፈጥሯል ሁሉ ደግሞ ያልፋል ዘላለማዊዉ ኑሮ በላይ በሰማይ ነው የዚህ ምድር ነገር ግን ቀሪ ነው::  ልባችንንም አይናችንንም በዚህ ጌታ ላይ አድርገን በፊቱ በመገዛት እንመላለስ እናምልከው እናወድሰው ስለሚገባው:: እውቅና ለሚገባው እውቅናን እንስጠው::

ሃሌሉያ!

የዮሐንስ ራእይ 4: 8-11

ቅዱስ፥ ቅዱስ፥ ቅዱስ፥ የነበረውና ያለ የሚመጣውም፥ ሁሉንም የሚገዛ ጌታ አምላክ፤ እያሉ ቀንና ሌሊት አያርፉም። 

ከዘላለም እስከ ዘላለም በሕይወት ለሚኖረው እየሰገዱ፦ ጌታችንና አምላካችን ሆይ፥ አንተ ሁሉን ፈጥረሃልና ስለ ፈቃድህም ሆነዋልና ተፈጥረውማልና ክብር ውዳሴ ኃይልም ልትቀበል ይገባሃል፡

ይህንን አምልኮ ስናይ እዛ መካከል አሁን መገፕት ያሰኛል::  ይህ ጌታ ቅዱስ ነው ብቻ ብለው አይደለም እያመለኩት ያሉት ቅድስና ከኃይል ጋር  ያለውና ሁሉን የሚገዛ እያሉ ነው የሚሉት::  መቼ መቼ ነው የሚያመልኩት? ያልን እንደሆነ በቀንና በለሊት አይቋረጥም ::  ኢሳያስም ይህንኑ ነው የሚነግረን አንዱ ለአንዱ ቅዱስ ነው እያለ ይነግራል::  አይገርምም!!  ዛሬውኑ ማምለክን ካልተለማመድን እንዴት ልንሆን ነው ሰማይ ስንሄድ?!  ይህንን ሁሉን የሚገዛ አምላክ ሳናቋርጥ ልናመልከው ይገባዋል!!  እርሱ አምልኮ የተገባው ነው!!

ደግሞም ሁሉን የፈጠረ አላመልክም የሚለውንም የፈጠረውና እንደፈቃዱ ያደረገው እርሱ ነው::  በምድር ገዛን ያሉ ሁሉ ጊዜያዊ ሲሆኑ የእኛ ጌታ ግን ለዘላለም ይገዛል:: ስለዚህ ሽማግሌዎቹም:-

አንተ ሁሉን ፈጥረሃልና 

ስለ ፈቃድህም ሆነዋልና ተፈጥረውማልና 

ክብር ውዳሴ ኃይልም ልትቀበል ይገባሃል፡

አሜን!

ስለዚህ ዓለምና ሞላዋ በውስጥዋም ያለው ሁሉ የጌታ ነውና ፍጥረት ሁሉ ሊያመልከው ይገባል::  አንድም ፍጥረት በፈቃዱ አልመጣም ፈጣሪው እግዚአብሔር ፈጠረው እንጂ!  አምላካችን ትልቅ ነው::

የተፈጠርነው እርሱን ለማምለክ ነው በሰማይም የሚጠብቀን ይህ አምልኮ ነው ሌላው የአገልግሎት ዘርፍ ሁሉ ይታጠፋል::  እናምልከው ስለሚገባው!

የዮሐንስ ራእይ 5: 1-2

1፤ በዙፋኑ ላይም በተቀመጠው በቀኝ እጁ ላይ በውስጥና በኋላ የተጻፈበት በሰባትም ማኅተም የተዘጋ መጽሐፍን አየሁ።  2፤ ብርቱም መልአክ፦ መጽሐፉን ይዘረጋ ዘንድ ማኅተሞቹንም ይፈታ ዘንድ የሚገባው ማን ነው? ብሎ በታላቅ ድምፅ ሲያውጅ አየሁ።

ይህ መጽሐፍ ምንድነው? በአብ እጅ በሰባት ማኅተም የታተመ? ልክ እንደ ዮሃንስ ሁሉ ህዝቅኤልም አይቷል  የተጻፈበትንም ነግሮናል:: በሕዝቅ 2: 10፤ በፊቴም ዘረጋው፥ በውስጥና በውጭም ተጽፎበት ነበር፤ ልቅሶና ኀዘን ዋይታም ተጽፎበት ነበር።  የሚገርመው በፊትም በኃላም ነው የተጻፈበት::

ይህ መጽሐፍ እስከ ፍጻሜ ዘመን ድረስ ይዘጋ ተብሎ ተዘግቷል:: በዳንኤል 12: 

4፤ ዳንኤል ሆይ፥ አንተ ግን እስከ ፍጻሜ ዘመን ድረስ ቃሉን ዝጋ፥ መጽሐፉንም አትም፤ ብዙ ሰዎች ይመረምራሉ፥ እውቀትም ይበዛል።

ብርቱም መልአክ፦ መጽሐፉን ይዘረጋ ዘንድ ማኅተሞቹንም ይፈታ ዘንድ የሚገባው ማን ነው? ብሎ በታላቅ ድምፅ ሲያውጅ አየሁ።

ብርቱ የሆነው መልአክም መፍታት አይችልም:: አዋጅን ግን አወጀ ማኅተሞቹንም ይፈታ ዘንድ የሚገባው ማን? ብሎ::  እኛን ሊታደግ ከዚህ ፍርድ ሊያወጣ ማንም አልቻለም::  ማንም መብትም ብቃት የለውም::  መዳናችን እንደው እንደቀልድ የምንይዘው አይደለም የከበረ መሆኑን እንረዳ::

ስለዚህ የከበረ ደህንነት ጌታን እናክብረው::

የዮሐንስ ራእይ 5: 3-5

3፤ በሰማይም ቢሆን በምድርም ላይ ቢሆን ከምድርም በታች ቢሆን መጽሐፉን ሊዘረጋ ወይም ሊመለከተው ማንም አልተቻለውም።

4፤ መጽሐፉን ሊዘረጋ ወይም ሊመለከተው የሚገባው ማንም ስላልተገኘ እጅግ አለቀስሁ።

5፤ ከሽማግሌዎቹም አንዱ፦ አታልቅስ፤ እነሆ፥ ከይሁዳ ነገድ የሆነው አንበሳ እርሱም የዳዊት ሥር መጽሐፉን ይዘረጋ ዘንድ ሰባቱንም ማኅተም ይፈታ ዘንድ ድል ነሥቶአል፡ አለኝ።

በሰማይም በምድርም ከምድርም በታች ይህንን መጽሐፍ ሊፈታ አይደለም ሊመለከተው እንኳን ማንም አልቻለም::  ማህተሞቹን ሊፈታ የተገባው ማን ነው? ብሎ ነው መልአኩም እየጠየቀ ያለው::  ብርቱ ጉልበተኛ ወይም ባለስልጣን አይደለም ጥያቄው የተገባው ማን ነው::  ይህንን ለማድረግ የሚችል ባለመብት ማነው ነው ጥያቄው::

ማንም ባልተገፕ ጊዜ ዮሃንስ አለቀሰ ይህ የሚያሳየው በሰማይ ሁሉም እንዴት  ባለ ጭንቀት ውስጥ እንደነበሩና  ዮሃንስም ራዕይ ብቻ ሳይሆን እያየ ያለው እየተካሄደ ያለ ሴረሞኒው ላይ እንደተገኘ ነው::  በእግዚአብሔር ቀን በመንፈስ ነበርኩ እንዳለው ማለት ነው::  እርሱም እየተካሄደ ባለው ስርአት ውስጥ ተካፋይ ነበረ::

ማንም አልተገኘም ማህተሞቹን ለመፍታት የተገባው::  ከሽማግሌዎቹም አንዱ፦ አታልቅስ፤ እነሆ፥

1. ከይሁዳ ነገድ የሆነው አንበሳ እርሱም 2. የዳዊት ሥር መጽሐፉን ይዘረጋ ዘንድ ሰባቱንም ማኅተም ይፈታ ዘንድ ድል ነሥቶአል፡ አለኝ።  ሃሌሉያ!!!!!

ሃሌሉያ!!!!!  ሃሌሉያ!!!!!  ሃሌሉያ!!!!!

ድል የነሳው ጌታ እንዴት የተገባውሆነ ብለን ብንል:- ያዕቆብ ልጆቹን ሲባርክ ይሁዳን (የይሁዳ አንበሳ ያስባለውን እናገኛለን)

ኦሪት ዘፍጥረት 49

8፤ ይሁዳ፥ ወንድሞችህ አንተን ያመሰግኑሃል፤ እጅህ በጠላቶችህ ደንደስ ላይ ነው፤ የአባትህ ልጆች በፊትህ ይሰግዳሉ።9፤ ይሁዳ የአንበሳ ደቦል ነው፤ ልጄ ሆይ፥ ከአደንህ ወጣህ፤ እንደ አንበሳ አሸመቀ፥ እንደ ሴት አንበሳም አደባ፤ ያስነሣውስ ዘንድ ማን ይችላል?

10፤ በትረ መንግሥት ከይሁዳ አይጠፋም፥ የገዥም ዘንግ ከእግሮቹ መካከል፥ ገዥ የሆነው እስኪመጣ ድረስ፤ የአሕዛብ መታዘዝም ለእርሱ ይሆናል።

የዳዊት ስር :-

ትንቢተ ኢሳይያስ 11

1፤ ከእሴይ ግንድ በትር ይወጣል፥ ከሥሩም ቍጥቋጥ ያፈራል። 10፤ በዚያም ቀን እንዲህ ይሆናል፤ ለአሕዛብ ምልክት ሊሆን የቆመውን የእሴይን ሥር አሕዛብ ይፈልጉታል፤ ማረፊያውም የተከበረ ይሆናል።

የሐዋርያት ሥራ 13

22፤ እርሱንም ከሻረው በኋላ ዳዊትን በእነርሱ ላይ እንዲነግሥ አስነሣው፥ ሲመሰክርለትም፦ እንደ ልቤ የሆነ ሰው ፈቃዴንም ሁሉ የሚያደርግ የእሴይን ልጅ ዳዊትን አገኘሁ፡ አለ። 23፤ ከዚህም ሰው ዘር እግዚአብሔር እንደ ተስፋው ቃል ለእስራኤል መድኃኒትን እርሱም ኢየሱስን አመጣ።

እግዚአብሔር አስቀድሞ ስለደህንነታችን እየሰራ ነበረ እንጂ የይድረስ ይድረስ ወይም አጋጣሚ የሚባል ነገር የለም ገና በዘፍጥረት 3 ላይ እመጣለሁ እንዳለ ይህ የተገባው ጌታ ትንቢቱንና የሰጠውን ቃል ፈጽሞ በመካከላችን መቶ ድል በመንሳት ታደገን! ስሙ ይባረክ!!

የዮሐንስ ራእይ 5: 6-8
6፤ በዙፋኑና በአራቱ እንስሶች መካከልም በሽማግሌዎችም መካከል እንደ ታረደ በግ ቆሞ አየሁ፥ ሰባትም ቀንዶችና ሰባት ዓይኖች ነበሩት እነርሱም ወደ ምድር ሁሉ የተላኩ የእግዚአብሔር መናፍስት ናቸው።
7፤ መጥቶም በዙፋን ላይ ከተቀመጠ ከዚያ ከቀኝ እጁ መጽሐፉን ወሰደው።
8፤ መጽሐፉንም በወሰደ ጊዜ አራቱ እንስሶችና ሀያ አራቱ ሽማግሌዎች በበጉ ፊት ወደቁ፥ እያንዳንዳቸውም በገናንና የቅዱሳን ጸሎት የሆነ ዕጣን የሞላበትን የወርቅ ዕቃ ያዙ።

ከሽማግሌዎቹ አንዱ ለዮሃንስ አታልቅስ፤ እነሆ፥ ከይሁዳ ነገድ የሆነው አንበሳ እርሱም የዳዊት ሥር መጽሐፉን ይዘረጋ ዘንድ ሰባቱንም ማኅተም ይፈታ ዘንድ ድል ነሥቶአል፡ አለው:: ይህንንም የይሁዳ አንበሳ ሲመለከት ያየው አንበሳ ሳይሆን እንደታረደ በግ ሆኖ ነው ያየው::

ይህም በግ ለየት ያለ አቋም ነው ያለው:- – ሰባትም ቀንዶችና

  • ሰባት ዓይኖች ነበሩት

እነዚህ ዓይኖች ወደ ምድር ሁሉ የተላኩ የእግዚአብሔር መናፍስት ናቸው። ተመሳሳይ ነገር እናያለን በዘካርያስ 4: 10፤ የጥቂቱን ነገር ቀን የናቀ ማን ነው? እነዚህ ሰባቱ ደስ ብሎአቸው በዘሩባቤል እጅ ቱንቢውን ያያሉ፤ እነዚህም በምድር ሁሉ የሚዘዋወሩ የእግዚአብሔር ዓይኖች ናቸው።

በግ ስናይ መሸነፍን እንዳናስብ እንደአንበሳ ሆኖ ባይሰባብር እንደበግ ሆኖ መስዋአት ሆኖ ድል ነስቷል:: ስሙ ይባረክ:: ስለዚህም በዙፋኑ ላይ ከተቀመጠው እጅ መጽሐፉን ወሰደ ማኅተሞቹንም ፈታ:: ሃሌሉያ!!!

ለዚህ በግ የቀረበው አምልኮ:- ሁሉም በፊቱ ወደቁ አራቱ እንሰሶችና ሃያ አራቱ ሽማግሌዎች ከዛም በእያንዳንዳቸው እጅ በበገና የታጀበ የቅዱሳን ጸሎት ነው ያቀረቡለት:: እንዴት ደስ ይላል?! ዛሬ በሚቀርበው እጣን ውስጥ የእያንዳንዳችን ጸሎት በፊቱ ይቀርባል:: ሃሌሉያ! በፊቱ ተቀባይነት አለን ጸሎታችንም ይሰማል:: ጌታ አይንቀውም እንደእጣን በፊቱ ይቀርባል::

ድል ለነሳው ለታረደው በግ አምልኮና ክብር ይብዛለት! አሜን

የዮሐንስ ራእይ 5: 9-14


9-10፤ መጽሐፉን ትወስድ ዘንድ ማኅተሞቹንም ትፈታ ዘንድ ይገባሃል፥ ታርደሃልና፥ በደምህም ለእግዚአብሔር ከነገድ ሁሉ ከቋንቋም ሁሉ ከወገንም ሁሉ ከሕዝብም ሁሉ ሰዎችን ዋጅተህ ለአምላካችን መንግሥትና ካህናት ይሆኑ ዘንድ አደረግሃቸው፥ በምድርም ላይ ይነግሣሉ፡ እያሉ አዲስን ቅኔ ይዘምራሉ።
11፤ አየሁም፥ በዙፋኑም በእንስሶቹም በሽማግሌዎቹም ዙሪያ የብዙ መላእክትን ድምፅ ሰማሁ፤ ቍጥራቸውም አእላፋት ጊዜ አእላፋትና ሺህ ጊዜ ሺህ ነበር፥
12፤ በታላቅም ድምፅ አሉ፦ የታረደው በግ ኃይልና ባለ ጠግነት ጥበብም ብርታትም ክብርም ምስጋናም በረከትም ሊቀበል ይገባዋል።
13፤ በሰማይና በምድርም ከምድርም በታች በባሕርም ላይ ያለ ፍጥረት ሁሉ በእነርሱም ውስጥ ያለ ሁሉ፦ በረከትና ክብር ምስጋናም ኃይልም ከዘላለም እስከ ዘላለም በዙፋኑ ላይ ለተቀመጠው፥ ለበጉም ይሁን፡ ሲሉ ሰማሁ።
14፤ አራቱም እንስሶች፦ አሜን አሉ፥ ሽማግሌዎቹም ወድቀው ሰገዱ።

የብርቱው መልአክ ጥያቄ ማነው የተገባው ማኅተሙን ሊፈታ ነበረ መልሱንም በአዲስን ቅኔ ዘሙሩ :-

መጽሐፉን ትወስድ ዘንድ ማኅተሞቹንም ትፈታ ዘንድ ይገባሃል፥
ለምን ተገባው?

  • ታርደሃልና፥ ጌታ ስለታረደ ይገባዋል
  • በደምህም ለእግዚአብሔር
    ከነገድ ሁሉ
    ከቋንቋም ሁሉ
    ከወገንም ሁሉ
    ከሕዝብም ሁሉ – የአብርሃም በረከት ለህዝብ ሁሉ ደረሰ በዘፍ 12:1-3 እንደተናገረው:: ስለዚህ ጌታ በመታረድ የእዳ ጽህፈታችንን አስወግዶ ሙታን የነበርነውን ከእርሱ ጋር አስነስቶ ህያዋን አደረገን:: በፈቃዱም ዋጅቶን ለአምላካችን መንግሥትና ካህናት አደረገን ይህም ብቻ አይደለም በምድርም ላይ እንነግሳለን፡ ይላል ዝማሬው አይገርምም?! እልፍ አእላፋትም ዘመሩት:: ጌታ ያደረገልን ይገርማል ስሙ ይባረክ::

አምልኮው ቀጠለ:-

በታላቅም ድምፅ አሉ፦
የታረደው በግ
ኃይልና
ባለ ጠግነት
ጥበብም
ብርታትም
ክብርም
ምስጋናም
በረከትም ሊቀበል ይገባዋል።
አሜን!

አምልኮው የመሰለኝ በሰማይ ብቻ ነበረ የሚገርመው ነገር ግን ቃሉ የሚለን ፍጥረት ሁሉ
በሰማይና
በምድርም
ከምድርም በታች
በባሕርም ላይ ያለ ፍጥረት ሁሉ
በእነርሱም ውስጥ ያለ ሁሉ፦

ይህ ሁሉ ፍጥረት ምን አለ? በረከትና ክብር ምስጋናም ኃይልም ከዘላለም እስከ ዘላለም በዙፋኑ ላይ ለተቀመጠው፥ ለበጉም ይሁን፡ ሲሉ ሰማሁ። አሜን ይሁንልህ ጌታዬ!


አራቱም እንስሶች፦ አሜን አሉ፥ ሽማግሌዎቹም ወድቀው ሰገዱ

እንዴት ደስ ይላል ክብርና አምልኮ ሁሉ ለታረደው በግ ይሁን:: አሜን!!!!
ዛሬ አምልኳችንን ወደፊቱ እናምጣ የታረደው በግ የተገባው ነውና::

የዮሐንስ ራእይ 6

1፤ በጉም ከሰባቱ ማኅተም አንዱን በፈታ ጊዜ አየሁ፥ ከአራቱም እንስሶች አንዱ ነጐድጓድ በሚመስል ድምፅ፦ መጥተህ እይ፡ ሲል ሰማሁ።

2፤ አየሁም፥ እነሆም፥ አምባላይ ፈረስ ወጣ፥ በእርሱም ላይ የተቀመጠው ቀስት ነበረው፥ አክሊልም ተሰጠው፥ ድልም እየነሣ ወጣ ድል ለመንሣት።

በጉ ማኅተሞቹን መፍታት ሲጀምር የመጀመሪያው አምባላይ ፈረስ ወጣ ይላል በእርሱም ላይ የተቀመጠው ቀስት ነበረው፥ አክሊልም ተሰጠው፥ ድልም እየነሣ ወጣ ድል ለመንሣት።

ይህ መልክተኛ ድል እየነሳና ድል ለመንሳት ስልጣን ተሰቶት ነው የወጣው:: በዘካርያስ 1: 7-11 እና  6:1-8 ላይ ተደግሞ እናየዋለን::

ትንቢተ ዘካርያስ 6

5፤ መልአኩም መልሶ፦ እነዚህ በምድር ሁሉ ጌታ ፊት ከቆሙበት ስፍራ የሚወጡ አራቱ የሰማይ ነፋሳት ናቸው።

ስለነፋሳት ስናስብ ፍርድን የሚያሳዮ ናቸው ለምሳሌ 

ትንቢተ ኤርምያስ 49

36፤ ከአራቱም ከሰማይ ማዕዘናት አራቱን ነፋሳት በኤላም ላይ አመጣለሁ፥ ወደ እነዚያም ነፋሳት ሁሉ እበትናቸዋለሁ፤ ከኤላም የተሰደዱ ሰዎች የማይደርሱበት ሕዝብ አይገኝም።

 እንዲሁም 

ትንቢተ ዳንኤል 11

4፤ እርሱም በተነሣ ጊዜ መንግሥቱ ይሰበራል፤ እስከ አራቱ የሰማይ ነፋሳት ይከፋፈላል። ለዘሩ ግን አይከፋፈልም፥ እንደ ገዛበትም አገዛዝ አይሆንም፤ መንግሥቱ ይነቀላልና፤ ከእነዚህም ለሌሎች ይሆናልና።

ፍርድ ተጀምሯል እግዚአብሔር በጽድቅ ይፈርዳል::

የዮሐንስ ራእይ 6

3፤ ሁለተኛውንም ማኅተም በፈታ ጊዜ ሁለተኛው እንስሳ፦ መጥተህ እይ፡ ሲል ሰማሁ።

በጉ እነዚህ ማኅተሞች በተፈቱ ቁጥር የሚሆን ነገር አለ::  

የመጀመሪያው ሲፈታ ቀስት የያዘ ፈረሰኛ ወጣ አክሊል ተሰቶት ድል እንዲነሳ ወጣ::

ሁለተኛው ሲፈታ:-   ዳማ ፈረስ ወጣ፥ በእርሱም ላይ ለተቀመጠው ሰላምን ከምድር ይወስድ ዘንድ ሰዎችም እርስ በርሳቸው እንዲተራረዱ ሥልጣን ተሰጠው፥ ታላቅም ሰይፍ ተሰጠው።

ሶስተኛው ሲፈታ:-እነሆም፥ ጕራቻ ፈረስ ወጣ፥ በእርሱም ላይ የተቀመጠው በእጁ ሚዛን ያዘ። የምግብም ዋጋ እንዲወደድ የሚያደርግ ነው ከዘይትና ከወይን ውጪ::

አራተኛውም ሲፈታ:- ሐመር ፈረስ ወጣ፥ በእርሱም ላይ የተቀመጠው ስሙ ሞት ነበረ። ሲኦልም ተከተለው፤ በሰይፍና በራብም በሞትም በምድርም አራዊት ይገድሉ ዘንድ ከምድር በአራተኛዋ እጅ ላይ ሥልጣን ተሰጣቸው።

ይህ ንን የፍርድ ቃል በሕዝቅኤል 14

21፤ ጌታ እግዚአብሔርም እንዲህ ይላል፦ ይልቁንስ ሰውንና እንስሳን ከእርስዋ አጠፋ ዘንድ በኢየሩሳሌም ላይ አራቱን ክፉ ፍርዶቼን፥ ሰይፍንና ራብን ክፉዎችንም አውሬዎች ቸነፈርንም፥ ስሰድድባት!

አምላካችን እንደዚሁ አይፈርድም ምክንያት ሲኖር እንጂ::  በዘሌዋውያን (26: 18-33) 26: 18፤ እስከዚህም ድረስ ባትሰሙኝ፥ ስለ ኃጢአታችሁ በቅጣታችሁ ላይ ሰባት እጥፍ እጨምራለሁ።

ፍርድ አለ በክርስቶስ ግን ሆነን ማምለጥና ማስመለጥ አለ የጻድቅ ሰው ጸሎት በስራዋ እጅግ ኃይልን ታደርጋለችና እንበርታ::  እነዚህ አራት ፈረሰኞች እየሰሩ ይሆናል ማየት ያለብን በክርስቶስ ያገኘነውን መዋጀት ነው::  ከምድር  ወደ ሰማይ ቤታችን መሄዳችን አይቅርም::

የዮሐንስ ራእይ 6: 9-17

9፤ አምስተኛውንም ማኅተም በፈታ ጊዜ፥ ስለ እግዚአብሔር ቃልና ስለ ጠበቁት ምስክር የታረዱትን የሰዎች ነፍሳት ከመሠዊያ በታች አየሁ።

12፤ ስድስተኛውንም ማኅተም በፈታ ጊዜ አየሁ፥ ታላቅም የምድር መናወጥ ሆነ፥ ፀሐይም እንደ ማቅ ጠጕር ጥቁር ሆነ፥ ጨረቃም በሞላው እንደ ደም ሆነ፥

17፤ ታላቁ የቁጣው ቀን መጥቶአልና፥ ማንስ ሊቆም ይችላል? አሉአቸው።

በመጀመሪያው የአራቱ ማኅተሞች መፈታት አራት ፈረሰኞችን የተለያየ ፍርድ አስይዞ ሲልክ አምስተኛው ግን ለየት ይላል::  ይኸውም በክርስቶስ ላይ ባለ እምነታቸው  የተነሳ የተገደሉ ቅዱሳንን ነፍስ እናያለን::  እነርሱም በታላቅ ድምፅም እየጮኹ፦ ቅዱስና እውነተኛ ጌታ ሆይ፥ እስከ መቼ ድረስ አትፈርድም ደማችንንስ በምድር በሚኖሩት ላይ እስከ መቼ አትበቀልም? ይላሉ::  ጊዜው ገና እንደሆነና እነርሱ ግን ነጭ ልብስ ለብሰው እንዲያርፉ ተደረጉ::  አምላካችን የተሸነፈ ይመስላል ከሞት ልጆቹን ማስጣል ያቃተው ነገር ግን ከፍርድ አያመልጡም የገደልዋቸው:;  እስጢፋኖስን ሊቀበለው ሲነሳ እናያለን ገዳዮቹን ከማባረር ይልቅ::  የጌታ አሰራር ከአእምሮ በላይ ነው:: 

ወደ ስድስተኛው ማኅተም ስንሄድ ታላቅም የምድር መናወጥ ሆነ፥ ፀሐይም እንደ ማቅ ጠጕር ጥቁር ሆነ፥ ጨረቃም በሞላው እንደ ደም ሆነ፥ በለስም በብርቱ ነፋስ ተናውጣ ቃርያዋን ፍሬ እንደምትጥል የሰማይ ከዋክብት ወደ ምድር ወደቁ፥

ይህንን ቃል የሚመስል ፍርድ በኢሳ 13:1-22 እናገኘዋለን እንዲሁን በኢዮኤል 2:10, 30-31 የምድር ፍጻሜ ላይሆን ይችላል የመንግስት/ የአገር መውደቅ ሊሆን ይችላል:: ኢሳያስ ያየው የባቢሎንን መውደቅ ነበር:: ብርሃንን አያዩም ይሞታሉ ታላላቆቻቸውም ደግሞ ከዋክብት እንደሚወድቁት ይወድቃሉ:: በመሸነፍ ውስጥ የት ልግባ ይላሉ ሹማምንቶቹ ምክንያቱም እግዚአብሔር እየፈረደ ነውና ወዴትም ማምለጥ አይቻልም:: ማንም በዙፋንም ከተቀመጠው ፊት ከበጉም ቍጣ ሰውሩን ቢሉም የሚያድን የለም:: አምላካችን ይፈርዳል::

የዮሐንስ ራእይ 7: 1-8

2፤ የሕያው አምላክ ማኅተም ያለውም ሌላ መልአክ ከፀሐይ መውጫ ሲወጣ አየሁ፥ ምድርንና ባሕርንም ሊጐዱ ለተሰጣቸው ለአራቱ መላእክት በታላቅ ድምፅ እየጮኸ፦

3፤ የአምላካችንን ባሪያዎች ግምባራቸውን እስክናትማቸው ድረስ ምድርን ቢሆን ወይም ባሕርን ወይም ዛፎችን አትጕዱ፡ አላቸው።

በዚህ ክፍል ላይ የሚያስገርም ነገር እናያለን እርሱም ንፋሳት ሲያዙ::  እንዴት ንፋስ ይያዛል? !  በምዕራፍ 6 ላይ ያለው መከራ ሁሉ ሲወጣ አይተናል:.  እዚህ ምዕራፍ ላይ ደግሞ ሲዘገዩ::  ምክንያቱም እግዚአብሔር ህዝቡን ሊያትም ፈለገ::  ይህ ሁሉ የጌታን መምጣት የሚያሳይ ነው::  የጌታን መምጣት ወንጌልን በማስፋፋት እንድናፋጥን ተነግሮናልና በሄድንበት ሁሉ ሰዎችን የምናጠምድ እንሁን::

ሌላው በሆል ፉድ እስቶር ውስጥ አንድ ነገር አየሁኝ የእጅ እስካነር ችፕስ ያላቸው ሰዎች እጃቸው ላይ አሉ ማለት ነው ይህ ችፕስ እየተሰጠ ነው ማለት ነው ካርድ ወደፊት አያስፈልግም ማለት ነው::  አይናችን እያየ ቃሉ እየተፈጸመ ነውና ጨርቄን ማቄን የምንልበት ጊዜ አይመስለኝም::  በጌታ ጸንተን በንቃት  ማድረግ ያለብንን እያደረግን እንበርታ::  

እዚህ ክፍል ላይ 144 ሺ ያህል እንደታተሙ እናያለን ምዕራፉን ደግሞ ወረድ ብለን ቁጥር 8 ላይ ማንም የማይቆጥራቸው ይላል::  ስለዚህ በመጨረሻው ዘመን ወደ ጌታ ዘወር የሚሉ አይሁዶች ይሆኑ?  እኛ አሁን በመንፈስ ቅዱስ ታትመናል ይላል ቃሉ:;  አጥፊው በግብጽ ያልፍ የነበረው ደሙን ሲያይ እንደሆነ እንዲሁ ዛሬ የክርስቶስ ደም ማምለጫ ነው ለህዝቡ:: 

ጌታ በደጅ ነው:: ማራናታ!!

የዮሐንስ ራእይ 7: 9

9፤ ከዚህ በኋላ አየሁ፥ እነሆም፥ አንድ እንኳ ሊቆጥራቸው የማይችል ከሕዝብና ከነገድ ከወገንም ከቋንቋም ሁሉ እጅግ ብዙ ሰዎች ነበሩ፤ ነጭ ልብስም ለብሰው የዘንባባንም ዝንጣፊዎች በእጆቻቸው ይዘው በዙፋኑና በበጉ ፊት ቆሙ፤

ዮሃንስ ያየው ይገርማል  እያንዳንዳችን እዚህ ሰልፍ ውስጥ አለንበትና ጌታን እናመስግን::   

ያየው እስኪ እንመልከት

1.  የሰውን ብዛት ማንም  ሊቆጥራቸው የማይችል :-  የጌታ ዘር ብዙ ነው ገንይም እንበዛለን ሰዎችን ከሲኦል እንናጠቃለን::

2.  ከሕዝብና ከነገድ ከወገንም ከቋንቋም ሁሉ :- ለዚህ ነው ወንጌል በምድር ሁሉ መሰበክ ያለበት ሁሉ እንዲደርሰውና ወደ ጌታ ዘወር እንዲል::  ይህንን ቃል ኪዳን ጌታ ከአብርሃም ጋር ነበር የገባው በዘፍ 12:1-3  በእርሱ በኩል ሁሉን እንደሚደርስ ይኸው ዛሬ የዛ ቃል ኪዳን ተካፋዮች ሆነን  በቤቱ አለን::  ስሙ ይባረክ!!

3. ነጭ ልብስ ለብሰው :- ይህንን ያለበሰን እራሱ ጌታ ነው ::  ጽድቃችን እየሱስ ተባረክ!

4. የዘንባባ ዝንጣፊ በእጃቸው ይዘው:- ጌታ እየሱስም ወደ እየሩሳሌም በአህያ ውርንጫ ተቀምጦ በዮሐንስ 12: 13፤ የዘንባባ ዛፍ ዝንጣፊ ይዘው ሊቀበሉት ወጡና፦ ሆሣዕና፤ በጌታ ስም የሚመጣ የእስራኤል ንጉሥ የተባረከ ነው፡ እያሉ ጮኹ።

ይህንኑ በሰማይ ሲደገም እናያለን!  ጌታችን ድል ነስቶ በዙፋኑ ላይ ነውና ጌታን እናመስግን::

ማራናታ!

የዮሐንስ ራእይ 7: 10

10፤ በታላቅም ድምፅ እየጮሁ አሉ፦ በዙፋኑ ላይ ለተቀመጠው ለአምላካችንና ለበጉ ማዳን ነው። 

እነዚህ ማንም ሊቆጥራቸው የማይችል ሰዎች በበጉና በዙፋኑ ፊት የዘንባባ ዝንጣፊ ይዘው ማምለክ ነው የቀጠሉት::  በሰማይ የሚቀርልን ነገር ማምለክና በጌታ መደነቅ ነው::  መንፈሳዊዉን ዓለም እንደሚገባ ተረድተናል ለማለት ይከብደኛል::  ብዙ የምናውቀው እዛው ስንደርስ ይመስለኛል::  አሁን በድንግዝግዝ ነው የምናውቀው ስንደርስ ግን ሁሉ ግልጽ ይሆናል::  ማንም አያስገድድም ጌታን እንድናመልክ የምናየው ነገር ነው ዝም ብለን እንዳንቆም የሚያደርገን::  የክብሩ ታላቅነትና  የእኛን ታናሽነት ስናይ ነፍስም አይቀርልን መወደዳችን እየገረመን እናመልካለን!!!

በአምልኳቸው ውስጥ እንዴት እዚህ ስፍራ ላይ እንደተገኙ ይገልፃሉ:- 

ከሁሉም በፊት ደስ የሚለው በታላቅም ድምፅ እየጮሁ ነበረ የሆነላቸውን ለበጉ ለእየሱስ የሚገልጡት፦ በዙፋኑ ላይ ለተቀመጠው ለአምላካችንና ለበጉ ማዳን ነው።  ማዳን የማን ነው? የአምላካችንና የበጉ ነው::  ማንም ተገብቶት አይደለም በዛ ስፍራ የተገኘው ስላዳነን ብቻ ነው እርሱ ተንገላቶ ከጨለማው ኃይል ስር ፈልቅቆ አውጥቶ ነው ለዚህ ድል ያበቃን::  ሃሌሉያ!!

ስለዚህም በዙፋኑ ላይ ለተቀመጠው ለበጉና ለአምላካችን ክብር ይሁን!!  የተከፈለው ዋጋና ፍቅሩ ገብቶን  እናመስግን እናምልከው እንገዛለት::  እርሱ ክብር የተገባው ነውና!! 

ደግሞም ዛሬ ወደዛ ቁጥር ላይ የሚጨመሩ ከሲኦል የሚያመልጡ ሰዎችን እንደሊድያ ልባቸውን እየከፈተ ይስጠንና የአባታችንን ቤት እንሙላው ሰዎች ከጨለማው አገዛዝ ያምልጡ የበጉ የእየሱስ ልፋት ዛሬም ማዳንን ያድርግ:: ሃሌሉያ!!

የዮሐንስ ራእይ 7: 11-12

11፤ መላእክቱም ሁሉ በዙፋኑና በሽማግሌዎቹ በአራቱም እንስሶቹ ዙሪያ ቆመው ነበር፤ በዙፋኑም ፊት በግምባራቸው ተደፉ፥ ለእግዚአብሔርም እየሰገዱ፦

12፤ አሜን፥ በረከትና ክብር ጥበብም ምስጋናም ውዳሴም ኃይልም ብርታትም ከዘላለም እስከ ዘላለም ድረስ ለአምላካችን ይሁን፤ አሜን፡ አሉ። 

መልአክቱም በሽማግሌዎቹ በአራቱም እንስሶቹ ዙሪያ ቆመው ነበር፤  ማንም ሊቆጥራቸው ያልቻለው ነጭ ልብስ የለበሱት ማዳን የአምላካችንና የበጉ ነው ብለው ሲያመልኩ ግን ቆመው ማየት አልቻሉም:: 

ስለዚህም 

1. በዙፋኑም ፊት በግምባራቸው ተደፉ፥  በዚህ ክቡር ጌታ ፊት እንዴት ይቆማል ? 

2. ለእግዚአብሔርም እየሰገዱ፦ በግምባራቸው መደፋት ብቻ አይደለም በዛው ስግደትን ቀጠሉ መነሳት እንደገናም መውደቅ መነሳት መውደቅ ሆነ::

3. አሜን፥ ብለው ከሰው ጋር ከተስማሙ በኃላ የራሳቸውን አምልኮ ቀጠሉ:-

በረከትና 

ክብር 

ጥበብም 

ምስጋናም 

ውዳሴም 

ኃይልም 

ብርታትም 

ከዘላለም እስከ ዘላለም ድረስ ለአምላካችን ይሁን፤ አሜን፡ አሉ። 

እኛም ዛሬ አሜን እንላለን ለዚህ ጌታ!!

የታደገን በግ ስሙ ይባረክ!

የዮሐንስ ራእይ 7: 13-14

13፤ ከሽማግሌዎቹም አንዱ ተመልሶ፦ እነዚህ ነጩን ልብስ የለበሱ እነማን ናቸው? ከወዴትስ መጡ? አለኝ።

14፤ እኔም፦ ጌታ ሆይ፥ አንተ ታውቃለህ፡ አልሁት። አለኝም፦ እነዚህ ከታላቁ መከራ የመጡ ናቸው፥ ልብሳቸውንም አጥበው በበጉ ደም አነጹ።

ምዕራፉ የሚጀምረው የአምላካችንን ባሪያዎች ግምባራቸውን እስክናትማቸው ድረስ ምድርን ቢሆን ወይም ባሕርን ወይም ዛፎችን አትጕዱ፡ በሚለው መልአክ ነው እነዚህ የእግዚአብሔር ባሪያዎች ሊመጣ ካለው ፍርድ እግዚአብሔር ያሰባቸው ናቸው እርሱ ህዝቡን አይተውምና::  ደግሞም ከሌላው ጋር አብረው እንዳይገኙ ምልክት ተደረገባቸውና ከታላቁ መከራ የመጡ ተባሉ::

በ ትንቢተ ዳንኤል 12: 1፤ በዚያም ዘመን ስለ ሕዝብህ ልጆች የሚቆመው ታላቁ አለቃ ሚካኤል ይነሣል፤ ሕዝብም ከሆነ ጀምሮ እስከዚያ ዘመን ድረስ እንደ እርሱ ያለ ያልሆነ የመከራ ዘመን ይሆናል፤ በዚያም ዘመን በመጽሐፉ ተጽፎ የተገኘው ሕዝብህ ሁሉ እያንዳንዱ ይድናል።

ከሽማግሌዎቹ አንዱ እነዚህ ነጩን ልብስ የለበሱ እነማን ናቸው? ከወዴትስ መጡ? ብሎ የጠየቀው ጠፍቶት አይደለም ለዮሃንስ የሚነግረው ነገር ስላለ እንጂ::  

እነማን ናቸው? ልብሳቸውንም አጥበው በበጉ ደም አነጹ። ሌላ ማንነት የላቸውም ማንነታቸው የእየሱስ ደም በመፍሰሱ ጽድቅን ማለትም ነጩን የማይገባቸውን የለበሱ ናቸው::  ከዚህ አገር ከዚህ ዘር ተብሎ ማንነት ያልተሰጣቸው::  ሃሌሉያ!  የምታወቀው በእርሱ ውስጥ ነው::

ከወዴትስ መጡ? 

እነዚህ ከታላቁ መከራ የመጡ ናቸው፥

ጌታ እየሱስም ይህንኑ ነግሮናል  በማቴዎስ 24: 21፤ በዚያን ጊዜ ከዓለም መጀመሪያ ጀምሮ እስከ ዛሬ ድረስ ያልሆነ እንግዲህም ከቶ የማይሆን ታላቅ መከራ ይሆናልና።

ዓለምም ምኞትዋም ያልፋሉ ዓይናችን በጌታ ላይ ይሁን ሁሉ አልፎ ይህንን በዓይናችን የምናይበት ዘመን ይመጣልና:: በሰማይ ተገኝተን ጌታን የምናመልክበት ጊዜ ይመጣል:: ቃል እንደተገባው ምልክት ተደረገባቸውና ከያሉበት እየተለቀሙ በዙፋኑና በበጉ ፊት ዘንባባን ይዘው ማምለክ ቀጠሉ:: በመንፈስ ቅዱስ ዕለት ዕለት ተሞሉ እንደሚል ለመምጣቱ በሚያዘጋጀን ጌታ እየተዘጋጀን መምጣቱን በጉጉት እንጠብቅ:: አሜን! ጌታ ይመጣል አይዘገይምም! ማራናታ!

የዮሐንስ ራእይ 7: 15-17

15፤ ስለዚህ በእግዚአብሔር ዙፋን ፊት አሉ፥ ሌሊትና ቀንም በመቅደሱ ያመልኩታል፥ በዙፋኑም ላይ የተቀመጠው በእነርሱ ላይ ያድርባቸዋል።

16፤ ከእንግዲህ ወዲህ አይራቡም፥ ከእንግዲህም ወዲህ አይጠሙም፥ ፀሐይም ትኵሳትም ሁሉ ከቶ አይወርድባቸውም፤ 

17፤ በዙፋኑ መካከል ያለው በጉ እረኛቸው ይሆናልና፥ ወደ ሕይወትም ውኃ ምንጭ ይመራቸዋልና፤ እግዚአብሔርም እንባዎችን ሁሉ ከዓይናቸው ያብሳል። 

በታማኝነት ጌታን ለተከተሉት በደሙ አጥቦ ላነጻቸው ምንድነው የሚጠብቃቸው? 

1.  በእግዚአብሔር ዙፋን ፊት አሉ፥  ምን አይነት ክብር ነው በእርሱ ዙፋን ፊት መገኘት? በዚህ ምድር እንኳን ፕሬዝደንቱን ጨበጥኩት ስንት ዓመት የሚወራ ነገር ነው አይደለም በዋይት ሀውስ እንድትኖር የአሜሪካ ህግ ፈቅዷል ብንባል::  ይህ ዙፋን የከበረ ነው::

2.  ሌሊትና ቀንም በመቅደሱ ያመልኩታል፥  ይህንን አሳብ ስናየው የካህን ስራ ነው ቀንም ለሊትም በቤተ መቅደስ መገኘት::  እኛንም ለመንግስቱና ለአባቱ ካህናት ስላደረገን ቀንና ለሊት በመቅደሱ ተገኝተን እናመልከዋለን::

3. በዙፋኑም ላይ የተቀመጠው በእነርሱ ላይ ያድርባቸዋል። ምን አይነት መታደል ነው ይህ ጌታ በእኛ ላይ ያድርብናል::  አሜን!

4. ከእንግዲህ ወዲህ አይራቡም፥  መቼምየምድር ርሀብ በምግብ ይታገሳል ክብሩን መጠማት ግን ማን ያረካዋል?  ስለዚህ ከክብሩ እንጥእግባለን::

5.  ከእንግዲህም ወዲህ አይጠሙም፥  ማንም የተጠማ ቢኖር ወደ እኔ ይምጣና ይጠጣ እኔ የምሰጠውን ውሃ የሚጠጣ አይጠማም እንዳለን እርካታችን እርሱው ነውና ደግመን እስከማንጠማ ድረስ ያጠግበናል በፊቱ ሆነን::

6. ፀሐይም ትኵሳትም ሁሉ ከቶ አይወርድባቸውም፤ የዓለም ውርጅብኙ ሁሉ ቀጥ ይላል ጠላት በዚህ በዚያ የሚያጣድፈን ሁሉ ይቆማል እረፍት በሰማይ ቀርቶልናል::

7. በዙፋኑ መካከል ያለው በጉ እረኛቸው ይሆናልና፥  እርሱ እራሱ እረኛ ይሆነናል ቅጥረኛ ያልሆነ እረኛ እርሱ ብቻ ነውና::

8. ወደ ሕይወትም ውኃ ምንጭ ይመራቸዋልና፤ ጌታ የህይወት ምንጭ ነው የህይወት ህግ ነው ዛሬም በእኛ ውስጥ የሚሰራው:: እርሱ ህይወት እንዲሆንልንና እንዲበዛልን መጣ:: ይህ ምንጭ ክውስጣችን ይፈልቃል መገኛው ከእርሱ ነውና አይቋረጥም አሜን::

9. እግዚአብሔርም እንባዎችን ሁሉ ከዓይናቸው ያብሳል። ክርስትና መቼም በእንባ የታጀበ ነው ምድር ሰልፍነውና ነገር ግን በሰማይ ለቅሶ የለም:: ሃሌሉያ! ለባርያዎቹ ጌታ ያዘጋጀው ህይወት ይህ ነው:. ስሙ ይባረክ የምናልፍበት ሁሉ ጊዜያዊ ነው ሁሉ ያልፋልና ያለንን ህይወት ጠብቀን እንመላለስሰ እኛ እረኛ ያለን ዓላማ ያለን፤ መድረሻ ያለን ነንና::

ይህ ሁሉ ህዝብ ወደቤቱ ከመከራው በፊት ተሰበሰበ!! ጌታ ለቃሉ ታማኝ ነው::

የዮሐንስ ራእይ 8: 1-2

1፤ ሰባተኛውንም ማኅተም በፈታ ጊዜ እኵል ሰዓት የሚያህል ዝምታ በሰማይ ሆነ።

2፤ በእግዚአብሔርም ፊት የሚቆሙትን ሰባቱን መላእክት አየሁ፥ ሰባትም መለከት ተሰጣቸው።

በሰማይ ዝምታ የሆነበት ምክንያት በትንቢተ ዕንባቆም 2: 20፤ እግዚአብሔር ግን በተቀደሰ መቅደሱ አለ፤ ምድርም ሁሉ በፊቱ ዝም ትበል።

እንዲሁም በትንቢተ ዘካርያስ 2

13፤ እግዚአብሔር ከተቀደሰ ማደሪያው ነቅቶአልና ሥጋ ለባሽ ሁሉ ሆይ፥ በፊቱ ዝም በል።

እግዚአብሔር ሊፈርድ ሲነሳ ዝምታ ይሆናል ማን ምን ማለት ይችላል? 

ከዚህም በኃላ ሰባት መላእክት መለከት ይዘው እናያለን::  ከዚህ በፊት ስለነዚህ መላእክት አልተጠቀሰም::  ፍርድ ሲተላለፍ መለከቱን የሚነፉ መላእክት ተዘጋጅተው እየጠበቁት ነው::  ከእግዚአብሔር ፍርድ ማን ያመልጣል ዝም ሲል ከኃጥያት ጋር የተስማማ ወይንም ደግሞ ምንም የማይመስለው ይመስል ህሆናል ነገር ግን ፈራጅ በሰማይ አለ::  ፍርድም ከቤቱ የሚጀምር ፃድቅ አምላክ ነው::  መንገዳችንን እርሱን በመፍራትና በማክበር እንጠብጥብ::

የዮሐንስ ራእይ 8: 3-5

3፤ ሌላም መልአክ መጣና የወርቅ ጥና ይዞ በመሰዊያው አጠገብ ቆመ፤ በዙፋኑም ፊት ባለው በወርቅ መሰዊያ ላይ ለቅዱሳን ሁሉ ጸሎት እንዲጨምረው ብዙ ዕጣን ተሰጠው።

4፤ የዕጣኑም ጢስ ከቅዱሳን ጸሎት ጋር ከመልአኩ እጅ በእግዚአብሔር ፊት ወጣ።

5፤ መልአኩም ጥናውን ይዞ የመሰዊያውን እሳት ሞላበት ወደ ምድርም ጣለው፤ ነጐድጓድና ድምፅም መብረቅም መናወጥም ሆነ።

ሰባቱ መላእክት በተጠንቀቅ ቆመው መለከቱን ለመንፋት እየተጠባበቁ ነው::  በዚህ መሀል ነው ሌላ መልአክ የወርቅ ጥና ይዞ በመሰዊያው አጠገብ የቆመው፤ በዙፋኑም ፊት ባለው በወርቅ መሰዊያ ላይ ለቅዱሳን ሁሉ ጸሎት እንዲጨምረው ብዙ ዕጣን ተሰጠው ይላል የዕጣኑም ጢስ ከቅዱሳን ጸሎት ጋር ከመልአኩ እጅ በእግዚአብሔር ፊት ወጣ።  አሜን!  ጸሎትን የሚሰማ ጌታ በላይ በሰማይ አለ:: ፀሎቱና እጣኑ በፊቱ ሲወጣ ለፀሎት መልስ ይሰጣል::  መልአኩም ጥናውን ይዞ የመሰዊያውን እሳት ሞላበት ወደ ምድርም ጣለው፤ ነጐድጓድና ድምፅም መብረቅም መናወጥም ሆነ ምክንያቱም መልሱን ሲሰጥ በመገኘት ነውና በሲና ተራራ ይኸው ነበረ::   ፀሎታችንን ሰምቶ ችላ የሚል ጌታ አይደለም::

ኦሪት ዘጸአት 19

16፤ እንዲህም ሆነ፤ በሦስተኛው ቀን በማለዳ ጊዜ ነጐድጓድና መብረቅ ከባድም ደመና እጅግም የበረታ የቀንደ መለከት ድምጽ በተራራው ላይ ሆነ፤ በሰፈሩም የነበሩት ሕዝብ ሁሉ ተንቀጠቀጡ።

የሚገርመው ነገር በሚካሄደው ስርአት መካከል የህዝቡን ፀሎት ለመስማትና ለመመለስ ጊዜ የሚሰጠን ጌታ ስሙ ይባረክ::  የቅዱሳን ፀሎት  ይመለሳል በእግዚአብሔር ጊዜ እርሱ ሰምቶ የሚመልስ::

የዮሐንስ ራእይ 8:  6-7

6፤ ሰባቱንም መለከት የያዙ ሰባቱ መላእክት ሊነፉ ተዘጋጁ።

7፤ ፊተኛውም መልአክ ነፋ፤ ደምም የተቀላቀለበት በረዶና እሳት ሆነ፥ ወደ ምድርም ተጣለ፤ የምድርም ሲሶው ተቃጠለ የዛፎችም ሲሶው ተቃጠለ የለመለመም ሣር ሁሉ ተቃጠለ።

ሰባቱን ማኅተም በጉ በፈታ ጊዜ ብዙ ፍርድ ሆንዋል አሁን ደግሞ እነዚህ ሰባት መለከቶች ምን አይነት ፍርድ እንደሚያመጡ እናያለን::  መልአክቱም ተዘጋጅተዋል::

የፊተኛው መልአክ ነፋ፤ 

ደምም የተቀላቀለበት በረዶና 

እሳት ሆነ፥ 

ወደ ምድርም ተጣለ፤ 

የምድርም ሲሶው ተቃጠለ 

የዛፎችም ሲሶው ተቃጠለ 

የለመለመም ሣር ሁሉ ተቃጠለ።

ይህንን የሚመስል ፍርድ በግብጽ ላይ አይተናል በዘጸአት 9: 22-26 እግዚአብሔርም ሙሴን፦ በግብፅ አገር በሰው በእንስሳም በእርሻም ቡቃያ ሁሉ ላይ፥ በግብፅ አገር ሁሉ በረዶ ይሆን ዘንድ እጅህን ወደ ሰማይ ዘርጋ፡ አለው።

የእግዚአብሔር  ፍርድ የማይቀር ነው ከዚህ ሁሉ ፍርድ በፊት ጌታ ህዝቡን ምልክት አድርጎ ከጉዳት እየከለለ ነው:;  ግብጽ ስትመታ እስራኤላውያን ያሉበት ግን ምንም አልተፈጠረም ::

ኦሪት ዘጸአት 9: 26፤ የእስራኤል ልጆች ተቀምጠው በነበሩባት በጌሤም አገር ብቻ በረዶ አልወረደም።

ምድር  በብዙ  መከራ  ውስጥ  ታልፋለች ጌታ ግን ህዝቡን ይጠብቃል ብናልፍም የምንሄደው ወደ ጌታ ነው የሚያስፈራን ነገር የለም የተማመነውና የተደገፍነው ጌታ ድንቅ ነው:: ወደ እጄ የገቡትን ማንም አይነጥቅም ብሎናል::

ዓይኖቻችንን በጌታ ላይ እናድርግ!

የዮሐንስ ራእይ 8: 8-9

8፤ ሁለተኛውም መልአክ ነፋ፤ በእሳት የሚቃጠል ታላቅ ተራራን የሚመስል ነገር በባሕር ተጣለ፤ የባሕርም ሲሶው ደም ሆነ

9፤ በባሕርም ከሚኖሩ ሕይወት ካላቸው ፍጥረቶች ሲሶው ሞተ የመርከቦችም ሲሶው ጠፋ።

እነዚህ ሰባት መላእክት መለከቱን ሲነፉ የሚፈጠር ፍርድ አለ::  ሁለተኛው ሲነፋ የሆነው ታላቅ ተራራ ላይ ነበረ ፍርዱ በኤርምያስ 51: 25፤ አንተ ምድርን ሁሉ የምታጠፋ አጥፊ ተራራ ሆይ፥ እነሆ፥ እኔ በአንተ ላይ ነኝ፥ ይላል እግዚአብሔር፤ እጄንም እዘረጋብሃለሁ፥ ከድንጋዮችም ላይ አንከባልልሃለሁ፥ የተቃጠለም ተራራ አደርግሃለሁ።

ተራራ በመንግስት ይመሰላል እንጂ በገሀድ የሚታየው ተራራ አይደለም::  እንዲሁም በዳንኤል መጽሐፍ 2:35 ላይ እጅ ያልነካት ድንጋይ ተንከባላ ምስሉን ከሰበረችና ካደቀቀች በኃላ ታላቅ ተራራ ሆነች::  ተራራ መንግስትን ይወክላል::  የሚፈረድበት መንግስት/አገር አለ::  ይህ  አገር ፍርድን ሲያገኝ አብሮት የሚጎዳው ብዙ ነው::  የእግዚአብሔር ፍርድ ከባድ ነው ከእርሱ ፍርድ ማን ያመልጣል:: በተሰሎንቄ ላይ የእግዚአብሔር ቃል ክፉ እንዳይገለጥ የሚከለክል በእኛ ውስጥ አለ እኛ ከሄድን በኃላ ክፉም በመሉ ኃይሉ ይሰራል እግዚአብሔር ፍርድን ያመጣል:: 

ታማኙ ጌታ ያስመልጠናል! ስለሚጠፉት ግን ግድ ይበለን ዛሬ ቅን ሳለ ወንጌልን ለፍጥረት ሁሉ እንድናደርስ ጌታ መንቃትን ይስጠን::

ይህንን ሁሉ ውርጅብኝ ዓለም ስታስተናግድ እግዚአብሔር ህዝቡን ግን በምዕራፍ 7 በፊቱ አምጥቶ አከማቸ ከመከራውም ታደገን::  መልአኩ የአምላካችንን ባሪያዎች ምልክት እስክናደርግ ምንም ጉዳት አይጀምር እንዳለ ከውርጅብኙ በፊት ህዝቡን በዙፋኑ ፊት ያቆመው ጌታ ስሙ ይባረክ::

የዮሐንስ ራእይ 8: 10-11

10፤ ሦስተኛውም መልአክ ነፋ፤ እንደ ችቦም የሚቃጠል ታላቅ ኮከብ ከሰማይ ወደቀ፥ በወንዞችና በውኃም ምንጮች ሲሶ ላይ ወደቀ። የኮከቡም ስም እሬቶ ይባላል።

11፤ የውኃውም ሲሶ መራራ ሆነ መራራም ስለተደረገ በውኃው ጠንቅ ብዙ ሰዎች ሞቱ።

የምድር ፍርድ እንደቀጠለ ነው ይህ ሶስተኛው ፍርድ መልአኩ መለከቱን በነፋ ጊዜ እንደ ችቦም የሚቃጠል ታላቅ ኮከብ ከሰማይ ወደቀ፥  የወደቀው ኮከብ ነው ስሙ እሬቶ ይባላል እንዲያጠፋ የመጣውም በወንዞችና በውኃም ምንጮች ሲሶ ላይ ወደቀ።  እንዴት ውሃዎችን ብቻ መጦ ወደቀ ስለዚህ ኮከብ ይባል እንጂ ሌላ ትርጉም አለው::  ያጠቃው ክፍል ወንዞችን (ብዙ ናቸው) እንዲሁም የውሃ ምንጮችን ነው (ይህም ብዙ ቁጥር ነው)::  

በሌላ ክፍል ላይ ስናይ በትንቢተ ኤርምያስ 9: 15፤ ስለዚህ የእስራኤል አምላክ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፦ እነሆ፥ ይህን ሕዝብ እሬትን አበላዋለሁ የሐሞትንም ውኃ አጠጣዋለሁ።

እንደዚሁም 

ትንቢተ ኤርምያስ 23: 15፤ ስለዚህ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፦ እነሆ፥ ከኢየሩሳሌም ነቢያት ዘንድ ርኵሰት በምድር ሁሉ ላይ ወጥቶአልና እሬትን አበላቸዋለሁ የሐሞትንም ውኃ አጠጣቸዋለሁ።

ውሃውን የመታው በእሬት ነው ከላይ በኤርምያስ መጽሐፍ እንደተጠቀሰው:: ይህ ፍርድ ደግሞ የመጣበት ምክንያት እዚህ ቃሉ ላይ  እንደተቀመጠው ከኢየሩሳሌም ነቢያት ዘንድ ርኵሰት በምድር ሁሉ ላይ ወጥቶአልና ነው ምክንያቱ::  ዛሬም ቤተክርስቲያን ውስጥ የምናየው የነብያት ውጥንቅጥ ካልተመለሱ እግዚአብሔር ማንም እንዲጠፋ አይፈልግም አለበለዚያ ግን በጊዜው  ፍርድን ያገኛል:: ስለዚህ ፍርዱ አመጹን የሚመጥን ነው የሚሆነው::  ቅድስናውንና ፍቅሩን ታላቅነቱን ማሳየት ሲገባ ባላሳዩበት ይህ ፍርድ ይወጣል::  እንደዚሁም አምላክ ባልሆነው በአጋንንት መንፈስ የሚጠነቁሉና ህዝቡን ከእግዚአብሔር መንገድ ያጠፉንም ይመለክከታል:: ስቃዮም መራራ ይሆናል አምላካችን አይዘበትበትም::

ዛሬ ጊዜ ሳለ ወደንስሀ ሰዎች እንዲመጡ እንፀልይና እንናገርም::  ይህ ያነበብነው የማይቀር  ነገር ነው::  ጌታ ዓይኖቻችንን ይክፈት በድፍረትም የምንሰብክበትን ፀጋ ይስጠን::

የዮሐንስ ራእይ 8: 12-13

12፤ አራተኛውም መልአክ ነፋ፤ የፀሐይ ሲሶና የጨረቃ ሲሶ የከዋክብትም ሲሶ ተመታ፥ የእነዚህ ሲሶ ይጨልም ዘንድ፥ የቀንም ሲሶው እንዳያበራ፥ እንዲሁም የሌሊት።

13፤ አየሁም፥ አንድም ንስር በሰማይ መካከል እየበረረ በታላቅ ድምፅ፦ ሊነፉ ያላቸው የሦስቱ መላእክት መለከት ስለሚቀረው ድምፅ በምድር ላይ ለሚኖሩት ወዮላቸው፥ ወዮላቸው፥ ወዮላቸው፡ ሲል ሰማሁ።

አራተኛው መልአክ ሲነፋ የተፈጠረው የፀሓይ የጨረቃና የከዋክብት መመታት የገሃዱን ዓለም የብርሃናቱን ነገር አይደለም የሚናገረው ነገር ግን ታላላቅ መንግስታት ላይፍርድ መሆኑን ነው::  ይህም ሲሶው ነው እየተመታ ያለው ሙሉ ለሙሉ ፍርድን ገና አላገኙም::

የሚገርመው ይህ ሁሉ ውርጅብኝ መቼም በአንድ ጀምበር የተደረገ ባይሆንም ዓለም እየተቀበለች ነው የእግዚአብሔርን ፍርድ::  ይህ ሁሉ አልበቃ ብሎ ንስሩ የሚያውጀው ያስደነግጣል የሦስቱ መላእክት መለከት ስለሚቀረው ድምፅ በምድር ላይ ለሚኖሩት ወዮላቸው፥ ወዮላቸው፥ ወዮላቸው፡ ሲል ሰማሁ።  ዓለም እየተፈረደባት ነው ሞትን ናና ውደቅብኝ ተብሎ የሚለመንበት ጊዜ::  

ዛሬ ከጌታ ጋር ያለንን ኅብረታችንን አጥብቀን እንያዝ የሚያስመልጠን እርሱ ብቻ ነው የሚመጣውን ስለሚያውቅ ነው የእግዚአብሔር በግ ሆኖ መስዋዕት የሆነው:: የሌላውም መዳን ያስጨንቀን እንፀልይ ለቤተሰቦቻችን ለጏደኞቻችን ለጎረቤቶቻችን አብረውን ለሚሰሩት እንዲሁም በእግዚአብሔር ቤት ሆነው ለጠፉት ወገኖች እናሳስብ:: ጌታ ፀጋውን ያብዛልን:: በፊቱ ስንቆም እነዚህን ይዤ መጣሁ የምንል ፍሬያችን ደስ የሚያሰኘውና አገልግሎታችንም በእሳት ውስጥ የሚያልፍ ተቃጥሎ የሚጠፋ ገለባ ይዘን እንዳንገኝ እንበርታ በጸጋው::

የዮሐንስ ራእይ 9: 1-2

1፤ አምስተኛውም መልአክ ነፋ፤ ከሰማይም ወደ ምድር ወድቆ የነበረ ኮከብ አየሁ፥ የጥልቁም ጕድጓድ መክፈቻ ተሰጠው።

2፤ የጥልቁንም ጕድጓድ ከፈተው፤ ጢስም ከታላቅ እቶን እንደሚወጣ ጢስ ሆኖ ከጕድጓዱ ወጣ ፀሐይና አየርም በጕድጓዱ ጢስ ጨለሙ።

ይህ እንግዲህ ወየው በምድር ለሚኖሩት ተብሎ አዋጅ ከተነገረ በኃላ ከሶስቱ የከፉ ፍርዶች ውስጥ የመጀመርያው መሆኑ ነው::  አምስተኛው መልአክ መለከቱን ሲነፋ ዮሃንስ ያየው ነገር ከሰማይ ወደ ምድር የወደቀ  ኮከብ ነው::  ኮከብ ሲል መቼም በገሀዱ ዓለም ያለው ኮከብ አይደለም ይህ የሚያሳየው ስልጣን ያለው ስው ወይም መንግስት እንደሆነ ነው::  

ሉሲፈርም የንጋት ኮከብ ነበረ መጀመርያ ሲፈጠር:: በኢሳይያስ 14: 12፤ አንተ የንጋት ልጅ አጥቢያ ኮከብ ሆይ፥ እንዴት ከሰማይ ወደቅህ! አሕዛብንም ያዋረድህ አንተ ሆይ፥ እንዴት እስከ ምድር ድረስ ተቈረጥህ!  ስለዚህ ይህ ፍርድ ስልጣን የነበረውን የሚያዋርድ ነው የሰይጣን ወይም ደግሞ ነገስታትና አገራቸውን ይመለከታል::

ጌታ እየሱስም አጋንንት እንኳን በስምህ ተገዛልን ብለው ሲሉት  በሉቃስ 10: 18፤ እንዲህም አላቸው፦ ሰይጣንን እንደ መብረቅ ከሰማይ ሲወድቅ አየሁ።  

ይህም በኮከብ በተሰጠውመክፈቻ – 

–  የጥልቁንም ጕድጓድ ከፈተው፤ 

–  ጢስም ከታላቅ እቶን እንደሚወጣ ጢስ ሆኖ ከጕድጓዱ ወጣ 

–  ፀሐይና አየርም በጕድጓዱ ጢስ ጨለሙ።  ይህንን ፍርድ በሰዶምና ገሞራ ላይ እናያለን:: አብረሃም በዘፍጥረት 19: 28፤ ወደ ሰዶምና ወደ ገሞራ በዚያች አገር ወዳለውም ምድር ሁሉ ተመለከተ፤ እነሆም የአገሪቱ ጢስ እንደ እቶን ጢስ ሲነሣ አየ። ይህ ፍርድ ነው ምድርን የሚጠብቃት::

ደህንነታችን ምን ያህል የከበረ እንደሆነ እንገንዘብና ለሌሎችም የሚያስሮጠን ጸጋ በእኛ ላይ ይገለጥ ጊዜ የለም ጌታ በደጅ ነው ሰዎችን ለአባታችን መንግስት እንሰብስብ እርሱም ልባቸውን እንደ ሊድያ እየከፈተ ይስጠን:: አሜን!

የዮሐንስ ራእይ 9: 3-4

3፤ ከጢሱም አንበጣዎች ወደ ምድር ወጡ፥ የምድርም ጊንጦች ሥልጣን እንዳላቸው ሥልጣን ተሰጣቸው።

4፤ የእግዚአብሔርም ማኅተም በግምባራቸው ከሌለባቸው ሰዎች በቀር በምድር ያለውን ሣር ቢሆንም ወይም ማናቸውንም የለመለመ ነገር ወይም ማናቸውንም ዛፍ እንዳይጐዱ ተባለላቸው።

ከእስፈሪው አንዱ የሆነው መለከት የጥልቁን ቁልፍ ይከፍት ዘንድ ነው የተሰጠው::  መቼም በጥልቁ ውስጥ ምን/ማን እንዳለ እናውቃለን::  በምሳሌያዊ ንግግር አንበጣ ይባል እንጂ እየወጣ ያለው የሰይጣን ሰራዊት ነው በአንበጣ አምሳል::  አንበጣን እግዚአብሔር ለመቅጣት ሁሌ ይጠቀምበታል እዚህም ላይ ያለው ምሳሌ ይኸው ነው::  የወጣው ሰራዊት አንበጣ ብቻ ሳይሆን ጊንጥም መሆኑ ነው::  እውነትም በምድር ላሉ ወየው!  አጋንንት አይራራም ማሰቃየት ነው ስራው::

የተሰጣቸውም ትዕዛዝ ማንን መንካትና ማንን አለመንካት እንዳለባቸው ይጨምራል::  ከሁሉ በፊት አንድ መልአክ ይህ ፍርድ ከመጀመሩ በፊት የአምላካችንን ባሪያዎች ምልክት እናድርግ ብሎ ነበረና እነሱን እንዲሁም 

በምድር ያለውን ሣር ቢሆንም ወይም ማናቸውንም የለመለመ ነገር ወይም ማናቸውንም ዛፍ እንዳይጐዱ ተባለላቸው።

ስለዚህ የቀረው ማነው እግዚአብሔርን የማይከተሉ ሰዎች ናቸው የሚጠቁት ማለት ነው::  እግዚአብሔርን ስላላወቁ እንዲያውቁና እንዲድኑ ነው በዚህ ውስጥ አለበለዚያ ግን አንድጊዜ ወደ ሞት ከተሻገሩ ወድያ እድል የለም::  ለዘላለም የሚጠብቃቸውን ትንሽዋን ነው እንዲቀምሱት እግዚአብሔር እያደረገ ያለው::

ወንጌልን ለሰዎች መንገር  ምርጫ አይደለም ግዴታችን አድርገን እንቁጠረው የሚጠብቃቸውን ስናይ እንዘንላቸው ቢገፉንም እንታገስ::  ጌታ በጸጋ ሁሉ ይሙላን::

የዮሐንስ ራእይ 9: 5-12

5፤ አምስትም ወር ሊሣቅዩአቸው ተሰጣቸው እንጂ ሊገድሉአቸው አይደለም፤ እነርሱም የሚሣቅዩት ሥቃይ ጊንጥ ሰውን ነድፎ እንደሚሣቅይ ነው።

6፤ በዚያም ወራት ሰዎች ሞትን ይፈልጋሉ አያገኙትምም፥ ሊሞቱም ይመኛሉ ሞትም ከእነርሱ ይሸሻል።

ወየው በምድር ለሚኖሩት የተባለለት አንዱ ቅጣት እንግዲህ ሞት የሌለበት ለተወሰነ ጊዜ እንዲያሰቃዮ የሰው ልጆችን መብት የተሰጣቸውን አጋንንት ነው::  እነዚህ በአንበጣና በጊንጥ የተመሰሉት መናፍስት ንጉስ አላቸው ይላል በምሳሌ 30: 27፤ አንበጣዎች ንጉሥ የላቸውም ሁላቸው ግን በመልካም ሥርዓት ይሄዳሉ ይላል::  ይህ የሚያሳየን ምሳሌያዊ መሆኑን ነው ::

ሞት ከስራው የታገደበት ከባድ  የስቃይ ጊዜ ሰዎች የሚጠብቃቸውን አውቀው ንስሃ እንዲገቡ የመጨረሻ እድል እግዚአብሔር ለሰው ልጆች እየሰጠ ያለበት ነው::  ከተፈቀደላቸው በላይ ማድረግ አይችሉም::  ብዙ ምሳሌያዊ ነገርን እናያለን ለምሳሌ ለጦርነት እንደተዘጋጁ ፈረሶች – ወደ ዘመቻ የወጡ ናቸው::

ጥርሳቸውም እንደ አንበሳ ጥርስ ነበረ፥ እንደ አንበሳ ግን አይደሉም::

እንደ ጊንጥም ጅራት ያለ ጅራት አላቸው በጅራታቸውም መውጊያ አለ፥ ሰዎችንም አምስት ወር እንዲጐዱ ሥልጣን አላቸው። እንደ ጊንጥ የሚያደርጋቸው ስራቸው ነው መውጋታቸው::

ፊተኛው ወዮ አልፎአል፤ እነሆ፥ ከዚህ በኋላ ገና ሁለት ወዮ ይመጣል።  ይህ ሁሉ የሚጠብቃቸው ሰዎች ዛሬ በአጠገባችን ይኖራሉና ወንጌልን ከመናገር ዝም አንበል::  ለሰዎችን መዳን ከመጸለይ አንቦዝን::  ጌታ በደጅ ነው !   

እስከዛሬ ከዓለም ጅማሬ ጀምሮ ያለውን ሁሉ ያደረገ ይህንንም ሲሆን የምናየው እውነት ነውና ወገባችንን ታጥቀን ትኩረታችንን ሁሉ በመንግስቱ ላይ እናድርግ::  ለመታዘዝና ለመላክ እሺ እንበል ተራራ አይሁንብን በጸጋ ነውና የሚሰራው::

ራእይ 9: 13-15

13፤ ስድስተኛውም መልአክ ነፋ፤ በእግዚአብሔርም ፊት ካለ በወርቅ ከተሠራ መሠዊያ ቀንዶች አንድ ድምፅ ሰማሁ፥

14፤ መለከትም ያለውን ስድስተኛውን መልአክ፦ “በታላቁ ወንዝ በኤፍራጥስ የታሰሩትን አራቱን መላእክት ፍታቸው፡” አለው።

15፤ የሰዎችንም ሲሶ እንዲገድሉ ለሰዓቱና ለቀኑ ለወሩም ለዓመቱም ተዘጋጅተው የነበሩ አራቱ መላእክት ተፈቱ።

ስድስተኛው መለከት በተነፋ ጊዜ ድምጽን በእግዚአብሔርም ፊት ካለ በወርቅ ከተሠራው መሠዊያ ቀንዶች ሰማሁ ይላል ዮሃንስ::  ይህ ድምጽ የመጣው ከመሰውያው ነው የቅዱሳን ጸሎት ይሆናል::  በብሉይ ኪዳን መሰዋትንና እጣኑን የሚያቀርቡበት ስፍራ ነውና::

ሌላው የተከናወነው ነገር በታላቁ ወንዝ በኤፍራጥስ የታሰሩትን አራቱን መላእክት እንዲፈቱ ትእዛዝ ተሰጠ::  የዚህ ዓለም ገዢ የተባለው ዲያቢሎስ ብዙ ስልጣን ያላቸውን መልአክት አስከትሎ ነው የወደቀው::  ውጊያችንም ከነዚህ የጨለማው ስልጣናት ጋር ነው::  ሁሉም ግን እንደወደዱ እንዲሰሩ የተለቀቁ አልነበሩም ::  እዚህ ጋር እንደምናየው ገና እየተፈቱ ያሉ እናያለን::

ሲፈቱም የተሰጣቸው  ስራ የዓለምን ሲሶ እንዲገድሉ ለሰዓቱና ለቀኑ ለወሩም ለዓመቱም ተዘጋጅተው የነበሩ አራቱ መላእክት ተፈቱ ይላል::  ከዚህ በፊት የወጡት በአንበጣና በጊንጥ የተመሰሉት መግደል አልተፈቀደላቸውም ነበር::  እነዚህ ግን ስራቸው መንደል ነው::  

እግዚዖ ያስብላል የሰው ልጅ የሚጠብቀው ነገር ይህ ሁሉ እግዚአብሔር ወደ መዳን ሊመራቸው  እንደሆነ ያስተውሉ ይሆን?  ጌታ ሆይ ቤተሰቦቻችንን ሁሉ አሳልፈህ ስጠን ወደ መዳን ይምጡ::  እንዲሁም የምናውቃቸውንም የማናውቃቸውንም ጨምረህ ስጠን ርንደሊድያ ልባቸውን ከፍተህ ስጠን:;  በእየሱስ ስም አሜን!

ራእይ 9: 16-21

16፤ የፈረሰኞችም ጭፍራ ቁጥር እልፍ ጊዜ እልፍ፥ እልፍ ጊዜ እልፍ ነበረ፤ ቁጥራቸውን ሰማሁ።

20፤ በእነዚህም መቅሠፍቶች ያልተገደሉት የቀሩቱ ሰዎች ለአጋንንትና ያዩ ወይም ይሰሙ ወይም ይሄዱ ዘንድ ለማይችሉ ከወርቅና ከብር ከናስም ከድንጋይም ከእንጨትም ለተሠሩ ለጣዖቶች እንዳይሰግዱ ስለ እጃቸው ሥራ ንስሐ አልገቡም፤

21፤ ስለ መግደላቸውም ቢሆን ወይም ስለ አስማታቸው ወይም ስለ ዝሙታቸው ወይም ስለ ስርቆታቸው ንስሐ አልገቡም።

የዚህ ስድስተኛው መለከት የሰው ልጅን ሲሶ የሚያጠፋ ነው ከተባለ መቼም ብዙ መሆን አለበት አጥፊው ወይም ኃይለኛ::  እንደምናየው የማይቆጠር ጭፍራ ነው እልፍ ጊዜ እልፍ፥ እልፍ ጊዜ እልፍ ነበረ፤ ቁጥራቸውን ሰማሁ ይላል ዮሃንስ::  የቀረው ሁለቱ እጅ ነው ሌላውን ያጠፋው ማለት ይከብዳል ምክንያቱም ይህ ጭፍራ ለየት ባለ መንገድ ነው የተገለጠው::

ያጠፉ የነበረውም ከአፋቸውም በወጡት በእሳቱና በጢሱ በዲኑም በእነዚህ ሦስት መቅሰፍቶች የሰዎቹ ሲሶ ተገደለ። ታድያ የትኛው ሰው ነው ይህንን ማድረግ የሚችል::  በዚህም ላይ ፈረሶቹ 

እንደ አንበሳ ራስ ነበረ፥

የፈረሶቹ ሥልጣን በአፋቸውና በጅራታቸው ነውና፤ 

ጅራታቸው እባብን ይመስላልና፥ 

ራስም አላቸው በእርሱም ይጐዳሉ።

ይህ መንፈሳዊ ውጊያ ነው መናፍስት ተለቀው የሚሰሩበይ ጊዜ ነው::  እግዚአብሔርግን ዓላማው ምንድነው? ሰውን ማሰቃየት? በፍጹም አይደለም::  አላማው  ንስሀ እንዲገቡና እንዲድኑ ነው::

ይህንን ሁሉ ያደረገው ጣኦትን ከማምለክ ወደእርሱ ዞር እንዲሉ ነበረ:: በእነዚህም መቅሠፍቶች ያልተገደሉት የቀሩቱ ሰዎች ለአጋንንትና ያዩ ወይም ይሰሙ ወይም ይሄዱ ዘንድ ለማይችሉ ከወርቅና ከብር ከናስም ከድንጋይም ከእንጨትም ለተሠሩ ለጣዖቶች እንዳይሰግዱ ስለ እጃቸው ሥራ ንስሐ አልገቡም፤

እንዲሁም ከክፉ ስራቸው እንዲመለሱና ንስሃ እንዲገቡ ነበረ::  ስለ መግደላቸውም ቢሆን ወይም ስለ አስማታቸው ወይም ስለ ዝሙታቸው ወይም ስለ ስርቆታቸው ንስሐ አልገቡም።

የንስሃ መንፈስ በህዝቡ ላይ ይፍሰስ ያለንበት ዘመን ነፍሰ ገዳይ የበዛበት ዝሙት የበዛበት ሌብነትም የበዛበት ነው::  ጌታ ይርዳን!

ራእይ 10:  1-4

1፤ ሌላም ብርቱ መልአክ ደመና ተጐናጽፎ ከሰማይ ሲወርድ አየሁ፤ በራሱም ላይ ቀስተ ደመና ነበረ፥ ፊቱም እንደ ፀሐይ እግሮቹም እንደ እሳት ዓምዶች ነበሩ፥

2፤ የተከፈተችንም ታናሽ መጽሐፍ በእጁ ያዘ። ቀኝ እግሩንም በባሕር ላይ ግራውንም በምድር ላይ አኖረ፥ እንደሚያገሣም አንበሳ በታላቅ ድምፅ ጮኸ።

3፤ በጮኸም ጊዜ ሰባቱ ነጐድጓድ በየድምፃቸው ተናገሩ።

ይህ ብርቱ  መልአክ ተብሎ የተጠቀሰው በጣ ከጌታ እየሱስ  ጋር የሚመሳሰል ነገር አለው ምናልባትም ጌታ ይሆን? 

– ደመና ተጐናጽፎ ከሰማይ ሲወርድ አየሁ፤ 

– በራሱም ላይ ቀስተ ደመና ነበረ፥ 

– ፊቱም እንደ ፀሐይ 

– እግሮቹም እንደ እሳት ዓምዶች ነበሩ፥ 

– የተከፈተችንም ታናሽ መጽሐፍ በእጁ ያዘ። 

– ቀኝ እግሩንም በባሕር ላይ 

–  ግራውንም በምድር ላይ አኖረ፥ 

–  እንደሚያገሣም አንበሳ በታላቅ ድምፅ ጮኸ  ይላልና ነው የተመሳሰለብኝ:: 

መጽሐፍን የወሰደ እንዲሁም የይሁዳ አንበሳ የሆነ በፍጥረት ሁሉላይ ባለስልጣን ( በምድርም በባህርም ላይ እግሩን ያኖረ) እግሮቹም እንደእሳት የሆኑ ፊቱም እንደ ፀሀይ የሚያበራ ብዙው መግለጫ እርሱን ይመስላል:::  ማንም ይሁን ማን ስልጣን ያለው እንደሆነ ግን ግልጽ ነው::

ይህብርቱ መልአክ ትንሽ መጽሐፍ ይዟል ግን ምንም ነገር ስለመጽሐፍዋ የተነገረ ነገር የለም::  ይኸው መልአክ ጮኸ  በጮኸም ጊዜ ሰባቱ ነጐድጓድ በየድምፃቸው ተናገሩ። ነገር ግን ዮሃንስ የተናገሩትን ሊጽፍ ሲል አትጻፍ ተባለ::  በጊዜው ሁሉ ይገለጣል እውቀታችንም ሙሉ ይሆናል::

ይህ ሁሉ ዝግጅት ጌታ ሊገለጥ የዓለምም ፍጻሜ  ሊሆን ነውናየተዘጋጀን እንሁን!

ራእይ 10: 5-11

5፤ በባሕርና በምድርም ላይ ሲቆም ያየሁት መልአክ ቀኝ እጁን ወደ ሰማይ አሻቅቦ ዘረጋ፥

6፤ ሰማይንና በእርሱም ያሉትን፥ ምድርንና በእርስዋም ያሉትን፥ ባሕርንና በእርሱም ያሉትን በፈጠረው፥ ከዘላለምም እስከ ዘላለም ድረስ ሕያው ሆኖ በሚኖረው ምሎ፦ “ወደ ፊት አይዘገይም፥

7፤ ዳሩ ግን ሰባተኛው መልአክ ሊነፋ ባለው ጊዜ ድምፁም በሚሰማበት ዘመን፥ ለባሪያዎቹ ለነቢያት የምስራች እንደ ሰበከላቸው የእግዚአብሔር ምሥጢር ይፈጸማል፡” አለ።

ወደ ፊት አይዘገይም፥  የእግዚአብሔር ምሥጢር ይፈጸማል  ብሎ ነው የማለው ይህ ምስጢር ምን ይሆን ? ሚስጢር እስኪገለጥ የሚጠበቅ ነው:: 

ዮሃንስ መጽሐፉን ወስዶ ከበላ በኃላ አፉ ላይ እንደማር ጣፈጠው በሆዱ ግን መራራ ሆነ ይላል::  ከዛም በብዙ ወገኖችና በአሕዛብም በቋንቋዎችም በነገሥታትም ላይ እንደ ገና ትንቢት ትናገር ዘንድ ይገባሃል” ተባለልኝ። ይላል የበላውን ቃል ትንቢት መናገር ሊኖርበት ነው::

ጌታ ይመጣል እዚህ ላይ የምናነበው ሁሉ ይፈጸማል::  ተግተን መገኘት ይሁንልን::

ራእይ 11: 1-2

1፤ በትር የሚመስል መለኪያ ለእኔ ተሰጠኝ፥ እንዲህም ተባለልኝ፦ “ተነሥተህ የእግዚአብሔርን መቅደስና መሠዊያውን በዚያም የሚሰግዱትን ለካ።

2፤ በመቅደሱም ውጭ ያለው እድሞ ለአሕዛብ ተሰጥቶአልና ተወው አትለካውም፤ እነርሱም አርባ ሁለት ወር የተቀደሰችውን ከተማ ይረግጡአታል።

ዮሃንስ መለኪያ ተሰቶት ለካ የተባለው:- 

– የእግዚአብሔርን መቅደስና 

– መሠዊያውን 

– በዚያም የሚሰግዱትን 

መቅደሱና መሰውያውን መለካት ይቻላል ግን ሰውን እንዴት ይቻላል?  ዘካርያስም መቅደሱን ሲለካ አይቷል ነገር ግን ያኔ ሲለካ ምናልባትም ዘሩባቤል ሊያድሰው ስለነበረ ነው ቢባል አሁን ለምን ይለካል?

ምሳሌያውት ሊሆንም ይችላል::  እግዚአብሔር ሁሉን እንደሚከታተልና እንደሚያይ ያሳየኛል:: ህዝቡንና ቤቱን ችልይ አይልም እኛ ነን ቤቶቹ በአዲሱ ኪዳን::

በውጪ ያለውን አደባባይ ጌታ ትቶታል ለክቶ ማወቅም አልፈለገም  ምናልባትም በክርስቶስ ሁሉን አንድ አድርጎአልና በአደባባይ የሚቆም የለም ሁሉ ካህን ሆኖ ገብቷል ወደ ቅድስትና ቅድስተ ቅዱሳኑ::  

ሀሰተኛው ክርስቶስ 7 ዓመት ሲገዛ ሶስት አመት ተኩሉን (42 ወር) በፀባይ ከዛም የሚቀጥለውን ደግሞ በማስገደድ ነውና እርሱ መቶ ወደ መቅደሱ የሚገባበት ጊዜ አለ ያኔም ይረግጡታልየተቀደሰውን:: ይህንን ከማየትና ምስክር ከመሆን ያውጣንና ህዝቡን ሲሰበስብ አብረን መሰብሰብ ይሁንልን::

ራእይ 11: 3-6

3፤ ለሁለቱም ምስክሮቼ ማቅ ለብሰው ሺህ ከሁለት መቶ ስድሳ ቀን ትንቢት ሊናገሩ እሰጣለሁ።”

4፤ እነዚህ በምድር ጌታ ፊት የሚቆሙ ሁለቱ ወይራዎችና ሁለቱ መቅረዞች ናቸው።

5፤ ማንምም ሊጐዳቸው ቢወድ እሳት ከአፋቸው ይወጣል ጠላቶቻቸውንም ይበላል፤ ማንም ሊጐዳቸው ቢወድም እንዲሁ ሊገደል ይገባዋል። 

6፤ እነዚህ ትንቢት በሚናገሩበት ወራት ዝናብ እንዳይዘንብ ሰማይን ሊዘጉ ሥልጣን አላቸው፥ ውኃዎችንም ወደ ደም ሊለውጡ በሚፈልጉበትም ጊዜ ሁሉ በመቅሠፍት ሁሉ ምድርን ሊመቱ ሥልጣን አላቸው።

እነዚህ ሁለት ምስክሮች እንደነኤልያስና ሙሴ  ነው የተገለጡት::  ብዙ ሰዎች ኤልያስና ሔኖክ ናቸው ስላልሞቱ መተው ነው ይላሉ ግን ይህንን ለማለት የሚያስረግጥ ነገር ባይኖርም በተለየና በማይቋረጥ ኃይል መገለጣቸውን እናያለን::

– እሳት ከአፋቸው ይወጣል ጠላቶቻቸውንም ይበላል፤ 

– ማንም ሊጐዳቸው ቢወድም እንዲሁ ሊገደል ይገባዋል። 

– ዝናብ እንዳይዘንብ ሰማይን ሊዘጉ ሥልጣን አላቸው፥ 

– ውኃዎችንም ወደ ደም ሊለውጡ 

– በሚፈልጉበትም ጊዜ ሁሉ በመቅሠፍት ሁሉ ምድርን ሊመቱ ሥልጣን አላቸው።

ይህንን ሁሉ ሊያደርጉ የቻሉት የኃይላቸው ምንጭ እራሱ መንፈስ ቅዱዝ ሆኖ ነው:: እነዚህ በምድር ጌታ ፊት የሚቆሙ ሁለቱ ወይራዎችና ሁለቱ መቅረዞች ናቸው።  ይህንኑ መልእክት በዘካርያስም ላይ እናገኛለን ለእያሱና ለዘሩባቤል::  በተጨማሪም በኃይልና በብርታት አይደለም በመንፈሴ ነው እያለ  ያበረታቸው ነበረ::  

በዚህም ስፍራ እነዚህ ሁለት ምስክሮት 1.260 ቀናት ማለትም  ለሶስትና ተኩል ዓመታት ይህንን ምስክርነት ይቀጥላሉ::

ምስክርነቱም እኮ ማቅ ለብሰው ነው የሚለው ይህ ማቅ መልበስ የሚያሳየስ ንስሃን ነው::  በዚህ ሁሉ ጥፋትና መቅሰፍት ውስጥ እግዚአብሔር ንስሃ ግቡ አምልጡ ነው መልእክቱ::

አምላካችን እንዴት ያለ ፍቅር ነው ማንም እንዲጠፋ እእይፈልግም ስሙ ለዘላለም የተባረከ ይሁን:. ልቡ በነፍሳት መዳን ላይ ነውና የእኛም በዛ ላይ ያተኩር::  መጥፋታቸድ እየታየንና እየራራንላቸው እንፀልይ ደግሞም እንመስክር::  ጌታ መንፈስ ቅዱስና አብ ስለእየሱስ ለመመስከር ከፍኛ ጋር አሉ:: 

አሜን!

ራእይ 11: 7-14

7፤ ምስክራቸውን ከፈጸሙ በኋላ ከጥልቁ የሚወጣው አውሬ ይዋጋቸዋል ያሸንፋቸውማል ይገድላቸውማል።

8፤ በድናቸውም በታላቂቱ ከተማ አደባባይ ይተኛል እርስዋም በመንፈሳዊ ምሳሌ ሰዶምና ግብፅ የተባለች ደግሞ ጌታቸው የተሰቀለባት ናት።

እነዚህ ሁለት ምስክሮች የተገደሉት ምስክርነታቸውን ከጨረሱ በኃላነው::  እግዚአብሔር በታላቅ ኃይል አስጠብቋቸዋል ምክንያቱም በምድር ያለው ኃይል ባይችል ነው ከጥልቁ አውሬው ሊዋጋቸው የተገለጠው ::  

እነዚህን ምስክሮች ማንምም ሊጐዳቸው ቢወድ እሳት ከአፋቸው ይወጣል ጠላቶቻቸውንም ይበላል፤ ማንም ሊጐዳቸው ቢወድም እንዲሁ ሊገደል ይገባዋል። ከዚህም የተነሳ ብዙዎች አኤልያስ ነው አንዱ ሁለተኛው ደግሞ ሙሴ ወይም ሄኖክ ብለው የሚገምቱት:: ማንም ይሁን ማን የእግዚአብሔር አላማ ምንድነው? አላማው ወደ እንኡ ኑ ነው:,  የሰው ልጅ ሁሉ ንስሃ እንዲገባና እንዳድን ነው ጥሪው የታተሙትን ካሰብን ብዙ ናቸው ቁጥሩ ሌላ ትርጉም ከሌለው መተ አርባ አራት ሺ ነበረ::

በድናቸውም እንዳይቀበር አቆዩት ስለከተማዋም በአራት በመንፈሳዊ ምሳሌ ተጠቅሳለች:-

1. በታላቂቱ ከተማ – እራስዋን ከፍ ያደረገች

2.  ሰዶምና – ቅድስና የሌለበት

3.  ግብፅ- ባርነት ያለበት

4.  ጌታቸው የተሰቀለባት ናት – የመጨረሻ ክህደት ያለበት::

ህዝብ ሁሉ ደስ አለው ሲሞቱ በኃጥያታቸው የሚወቅስ የለም አስረሽ ምችው ሆነ ይህለነሱ ደስታ ነው እግዚአብሔር ግን እንዴት ከሚመጣው ላድን ብሎ እየተጠበበ ነው::  ስለዚህም የህይወትን መንፈስ ሰደደና ከሞት አስነሳቸው እሬሳቸስ ለቀናት በሜዳ ላይ የተጣለውን የልጆቹን::  ዓለም እጢዋ ዱብ እስኪል ድረስ ደነገጠች ስጦታ መቀያየሩ እንኳን ደስ አለን ሁሉ ቀረ::   

ከሞት መነሳት ብቻ ሳይሆን በሰማይም፦ “ወደዚህ ውጡ፡” የሚላቸውን ታላቅ ድምፅ ሰሙ፤ ጠላቶቻቸውም እየተመለከቱአቸው ወደ ሰማይ በደመና ወጡ።  ሃሌሉያ!! ከዚህ በላይ ምን አይነት ምስክርነት ነው ጌታ መስጠት የሚችለው?!  ስሙ ይባረክ ማንም እንዳይሞት የሚፈልግ ጌታ ስሙ ይባረክ!!

በዚያም ሰዓት ታላቅ የምድር መናወጥ ሆነ፥ ከከተማይቱም አሥረኛው እጅ ወደቀ፥ በመናወጥም ሰባት ሺህ ሰዎች ተገደሉ፥ የቀሩትንም ፍርሃት ያዛቸው፥ ለሰማዩም አምላክ ክብር ሰጡ።  ክብር ይገባዋል!  እንደገና በምድር ለሚኖሩ ወየው ምክንያቱም ሁለተኛው ወዮ አልፎአል፤ እነሆ፥ ሦስተኛው ወዮ በቶሎ ይመጣል።

ጌታ የሚድኑትን ነፍሳት በእኛ ላይ ይጨምርና  ብዙዎችን ያስመልጥ::  አሜን!

ራእይ 11:15-19

15፤ ሰባተኛው መልአክ ነፋ፤ በሰማይም፦ “የዓለም መንግሥት ለጌታችንና ለእርሱ ለክርስቶስ ሆነች፥ ለዘላለምም እስከ ዘላለም ይነግሣል፡” የሚሉ ታላላቅ ድምፆች ሆኑ።

16፤ በእግዚአብሔርም ፊት በዙፋኖቻቸው የተቀመጡ ሀያ አራቱ ሽማግሌዎች በግምባራቸው ተደፍተው ለእግዚአብሔር እየሰገዱ፡

17፤ እንዲህ አሉ፦ “ያለህና የነበርህ ሁሉን የምትገዛ ጌታ እግዚአብሔር ሆይ፥ ትልቁን ኃይልህን ስለ ያዝህ ስለ ነገሥህም እናመሰግንሃለን፤

18፤ አሕዛብም ተቈጡ፥ ቍጣህም መጣ፥ በሙታንም ትፈርድ ዘንድ ዘመን መጣ፥ ለባሪያዎችህም ለነቢያትና ለቅዱሳን ስምህንም ለሚፈሩት ለታናናሾችና ለታላላቆችም ዋጋቸውን ትሰጥ ዘንድ፥ ምድርንም የሚያጠፉትን ታጠፋ ዘንድ ዘመን መጣ።”

19፤ በሰማይም ያለው የእግዚአብሔር መቅደስ ተከፈተ፥ የኪዳኑም ታቦት በመቅደሱ ታየ፥ መብረቅና ድምፅም ነጐድጓድም የምድርም መናወጥ ታላቅም በረዶ ሆነ።

ሁሉም ጌታን ማመስገንና ማምለክ ላይ ነው::  እርሱ ሊመለክ ይገባዋልና:: አሕዛብም ተቈጡ፥ ቍጣህም መጣ፥ በሙታንም ትፈርድ ዘንድ ዘመን መጣ፥ ለባሪያዎችህም ለነቢያትና ለቅዱሳን ስምህንም ለሚፈሩት ለታናናሾችና ለታላላቆችም ዋጋቸውን ትሰጥ ዘንድ፥ ምድርንም የሚያጠፉትን ታጠፋ ዘንድ ዘመን መጣ።”  

ጊዜው ደረሰ!

ይህንን ጌታ አብረን እያመለክን እንዋል!

ራእይ 12: 1-2

1፤ ታላቅ ምልክትም በሰማይ ታየ ፀሐይን ተጐናጽፋ ጨረቃ ከእግሮችዋ በታች ያላት በራስዋም ላይ የአሥራ ሁለት ከዋክብት አክሊል የሆነላት አንዲት ሴት ነበረች።

2፤ እርስዋም ፀንሳ ነበር፥ ምጥም ተይዛ ልትወልድ ተጭንቃ ጮኸች።

ታላቅ ምልክት በሰማይ ሆነ ይህም ስለአንዲት ሴት ነውእርስዋም እስራኤል ናት:: ይህች ሴት ልዮ መገለጫ አላት:-

– ፀሐይን ተጐናጽፋ 

– ጨረቃ ከእግሮችዋ በታች

– አስራ ሁለት ከዋክብት አክሊል የሆነላት – 12 ሐዋርያት

– ፀንሳ ነበር፥ 

– ምጥም ተይዛ ልትወልድ ተጭንቃ ጮኸች። የሚወለደውም የሰይጣንን መንግስት የሚገለባብጠው ህዝቡንም ነፃ የሚያወጣው እየሱስ ነው::  ይህ ክፍል ወደኃላ ወስዶ እንዴት ባለ መወለድ እንደመጣ ሊያሳየን ወደደ አልጋ ባልጋ አልነበረም ማለት ነው አመጣጡ::  ስሙ ይባረክ እንኳን መቶ ታደገን::

ራእይ 12: 3-5

3፤ ሌላም ምልክት በሰማይ ታየ፤ እነሆም ታላቅ ቀይ ዘንዶ፤ ሰባት ራሶችና አሥር ቀንዶችም ነበሩት በራሶቹም ላይ ሰባት ዘውዶች ነበሩ፥

ራእይ 12:4፤ ጅራቱም የሰማይን ከዋክብት ሲሶ እየሳበ ወደ ምድር ጣላቸው። ዘንዶውም ሴቲቱ በወለደች ጊዜ ሕፃንዋን እንዲበላ ልትወልድ ባላት ሴት ፊት ቆመ።

ራእይ 12:5፤ አሕዛብንም ሁሉ በብረት በትር ይገዛቸው ዘንድ ያለውን ልጅ ወንድ ልጅ ወለደች፤ ልጅዋም ወደ እግዚአብሔርና ወደ ዙፋኑ ተነጠቀ።

ከላይ እንዳየነው ይህች ሴት እስራኤል ናት::  ዮሃንሰም ሲነግረን ታላቅ ምልክት ሆነ ነው ያለው ምሳሌያዊነቱን ለማሳየት::  ወደ ዮሴፍ ህልም ስንመጣ ፀሐይን ጨረቃንና ከዋክብቱን ይነግረናል እነማን እንደሆኑ:: ለእርሱ በግብጽ ምድር ገዢ ሆኖ የእስራኤን ሁሉ መሰረት የሆነው ያዕቆብ መቶ እንደሚሰግድለት ነው ያየው ያዕቆብ ደግሞ እስራኤል ነው::  ዘፍጥረት 37:9፤ ደግሞም ሌላ ሕልምን አለመ፥ ለወንድሞቹም ነገራቸው፥ እንዲህም አለ፦ “እነሆ ደግሞ ሌላ ሕልምን አለምሁ፤ እነሆ ፀሐይና ጨረቃ አሥራ አንድ ከዋክብትም ሲሰግዱልኝ አየሁ።”

እስራ ሁለተኛው እንግዲህ የእርሱ ትውልድ መሆኑ ነው::

ሌላው ደግሞ ሁለተኛው ምልክት ታላቅ ቀይ ዘንዶ፤ ሰባት ራሶችና አሥር ቀንዶችም ነበሩት በራሶቹም ላይ ሰባት ዘውዶች ነበሩ፥ ይላል::  ይህ ዘንዶ ስልጣን ወይም ንግስና ያለው ነው ምክንያቱም ዘውድ አለውና የዚህ ዓለም ገዢ ዲያብሎስ እንደሆነ አንዘንጋው:;  ቀይ የሚለውም በደም የተነክከረና ጨካኝ መሆኑን ያሳያል::

እንዲሁም ይህ ዘንዶ በጅራቱ የሰማይን ከዋክብት ሲሶ እየሳበ ወደ ምድር ጣላቸው። የተከተሉትንና ከእርሱ ጋር የተጣሉትን ሲሶ መላእክት ያሳያል::  ዘንዶውም ሴቲቱ በወለደች ጊዜ ሕፃንዋን እንዲበላ ልትወልድ ባላት ሴት ፊት ቆመ። ይህንን በትክክል አድርጏል እየሱስ ክርስቶስ በተወለደ ጊዜ ህፃናትን ሁሉ ሳይራራ አርዷል ግን እግዚአብሔር ከሰማይ ተጠበበናወደ ግብጽ እየሱስን አሸሸው::  ግን ሞክሯል የተወለደውን መድኃኒት ለማጥፋት::

ክብር ለአምላካችን ይሁን ዛሬም ይሞክራል እንጂ ከእግዚአብሔር ጋር ለመወዳደር ነገር ግን የወደቀና የተጣለ ዘንዶ ነው::  ድል ለነሳው ክብር ይሁን!!!! አሜን

ራእይ 12: 6-9

6፤ ሴቲቱም ሺህ ከሁለት መቶ ስድሳ ቀን በዚያ እንዲመግቡአት በእግዚአብሔር ተዘጋጅቶላት ወደ ነበረው ስፍራ ወደ በረሀ ሸሸች።

7፤ በሰማይም ሰልፍ ሆነ፤ ሚካኤልና መላእክቱ ዘንዶውን ተዋጉ። ዘንዶውም ከመላእክቱ ጋር ተዋጋ፥ አልቻላቸውምም፥

8፤ ከዚያም ወዲያ በሰማይ ስፍራ አልተገኘላቸውም።

9፤ ዓለሙንም ሁሉ የሚያስተው፥ ዲያብሎስና ሰይጣን የሚባለው ታላቁ ዘንዶ እርሱም የቀደመው እባብ ተጣለ፤ ወደ ምድር ተጣለ መላእክቱም ከእርሱ ጋር ተጣሉ።

ሴቲቱ በዘንዶው መከራ ስለበዛባት ትሰደዳለች እስዋም እስራኤል ናት::  የምትሰደድበትም ስፍራ ተዘጋጅቶላታል  ልክ እየሱስ ስፍራን ላዘጋጅላችሁ እሄዳለሁ እንዳለው ምሳሌ በምድርም ለዚህ ህዝብ መሸሸጊያ ስፍራ ተዘጋጅቷል::  በዚህ መሀል መልአክቱ ከዘንዶው ጋር ውጊያ ያደርጋሉ ደግሞም ይረቱታል::  ከውጊያውም በኃላ ከዚያም ወዲያ በሰማይ ስፍራ አልተገኘላቸውም ለዲያቢሎስና ለሰራዊቱ::  ሃሌሉያ!!  ተጣሉ!!

ስራው ማሳት በእግዚአብሔር ላይ ሰውን ማሳመፅ የሆነው ተረታ::  ዓለሙንም ሁሉ የሚያስተው፥ ዲያብሎስና ሰይጣን የሚባለው ታላቁ ዘንዶ እርሱም የቀደመው እባብ ተጣለ፤ ወደ ምድር ተጣለ መላእክቱም ከእርሱ ጋር ተጣሉ። አሜን ተጣለ!!  ድሉ ይቀጥላል!

ራእይ 12: 10-12

10፤ ታላቅም ድምፅ በሰማይ ሰማሁ እንዲህ ሲል፦ “አሁን የአምላካችን ማዳንና ኃይል መንግሥትም የክርስቶስም ሥልጣን ሆነ፥ ቀንና ሌሊትም በአምላካችን ፊት የሚከሳቸው የወንድሞቻችን ከሳሽ ተጥሎአልና።

11፤ እነርሱም ከበጉ ደም የተነሣ ከምስክራቸውም ቃል የተነሣ ድል ነሡት፥ ነፍሳቸውንም እስከ ሞት ድረስ አልወደዱም።

12፤ ስለዚህ፥ ሰማይና በውስጡ የምታድሩ ሆይ፥ ደስ ይበላችሁ፤ ለምድርና ለባሕር ወዮላቸው፥ ዲያብሎስ ጥቂት ዘመን እንዳለው አውቆ በታላቅ ቍጣ ወደ እናንተ ወርዶአልና።”

ይህንን አዋጅ ያወጀው ወንድሞች ብሎ ነው የጠራን ጌታ እየሱስ መሆን አለበት ያወጀው መልአክት  ወንድሞቻችን ብለው የሚጠሩን አይመስለኝም::  ዋናው መልእክት በአሁኑ ሰዕት የተከናወነው:- 

– የአምላካችን ማዳንና 

– ኃይል 

– መንግሥትም 

– የክርስቶስም ሥልጣን ሆነ፥ 

– ቀንና ሌሊትም በአምላካችን ፊት የሚከሳቸው የወንድሞቻችን ከሳሽ ተጥሎአልና።  ሃሌሉያ!!  ጠላታችን እረፍት የሚነሳን ተጣለ::

የተጣለውም በምንድነው ብንል:-

– ከበጉ ደም የተነሣ  – የእየሱስ እንደበግ መታረድ ነው ያነፃን:: 

ኤፌሶን 1:7፤ በውድ ልጁም፥ እንደ ጸጋው ባለ ጠግነት መጠን፥ በደሙ የተደረገ ቤዛነታችንን አገኘን እርሱም የበደላችን ስርየት። አሜን! 

– ከምስክራቸውም ቃል የተነሣ ድል ነሡት፥ – የፈለገውን ውሸት ቢያመጣ በህይወታችን ስልየነው ልንክደው አንችልምና እንመሰክራለን የሆነልንንና ያደረገውን::

ነፍሳቸውንም እስከ ሞት ድረስ አልወደዱም። ከተወደድንበት ፍቅር የተነሳ እንወደዋለን ህይወታ ችንም የእርሱ ነው:: ፊልጵስዩስ 1:21፤ ለእኔ ሕይወት ክርስቶስ፥ ሞትም ጥቅም ነውና።

ይህንን ሁሉ ኪሳራ ስላስተናገደ ለማጥፋት ወቷል የዳንን እኛ ለሌሎች መቆምንይ ሌሎችን ማስመለጥ ይሁንልን::

ራእይ 12: 13-17

13፤ ዘንዶውም ወደ ምድር እንደ ተጣለ ባየ ጊዜ ወንድ ልጅ የወለደችውን ሴት አሳደዳት።

17፤ ዘንዶውም በሴቲቱ ላይ ተቈጥቶ የእግዚአብሔርን ትእዛዛት የሚጠብቁትን የኢየሱስም ምስክር ያላቸውን ከዘርዋ የቀሩትን ሊዋጋ ሄደ፤ በባሕርም አሸዋ ላይ ቆመ።

ጥቂት ዘመን እንደቀረው አውቆ ጠላት በታላቅ ቁጣ ወቶ ሴቲቱን ማለትም እስራኤልን አሳደደ::  እስራኤል በተለይም የዳኑትን ማሳደዱ አይደንቅም ምክንያቱም ውጤቱን ያውቀዋልና::  አሁን ዓለማዊነት በጣም ተጠናውቷቸዋል ምንም የኃይማኖተኝነት ምልክት የሌላቸው በዝተዋል::  ስለዚህ እነዚህ የዳኑ ጅውሾች ውጊያው ይበዛባቸዋል ይህንን ለመግፈፍና መሲሁ መቶ ነበር ወደሚለውሀሳብ ለማምጣት::  ጌታም እንዳለው በማቴዎስ 23:39፤ እላችኋለሁና፥ በጌታ ስም የሚመጣ የተባረከ ነው እስክትሉ ድረስ ከእንግዲህ ወዲህ አታዩኝም። ይህንን እየጠበቀ ነው::

እስራኤልን በክንፍ ሲያወጣ አይተናል  በዘጸአት 19:4፤ ‘በግብፃውያን ያደረግሁትን፥ በንስርም ክንፍ እንደተሸከምኋችሁ፥ ወደ እኔም እንዳመጣኋችሁ አይታችኋል። አሁንም እንደዚሁ ያወጣቸዋል ምክንያቱም በስተመጨረሻ የሚመጣው እዛ ነውና::  ጠላት ያንን ነው ማጥፋትና መከላከል የያዘው::  ግን ተሸንፏል::

ዘንዶው እርስዋን ትቶ የእግዚአብሔርን ትእዛዛት የሚጠብቁትን የኢየሱስም ምስክር ያላቸውን ከዘርዋ የቀሩትን ሊዋጋ ሄደ፤ በባሕርም አሸዋ ላይ ቆመ።

ውጊያው የነበረና የሚቀጥል ነው ድሉም የአምላካችን ነው::  ድሉ የታወቀ ውጊያ ውስጥ ነን::  እናስተውል ጠላት እንዳያታልለን እንሸነፋለን ብለን ወደማሰብ እንዳያመጣን ድሉ ተጠናቋል!  ሃሌሉያ ድል ለነሳው ክብር ይሁንለት::

ድል ለነሳው ክብር ይሁን

ራእይ 13:1-2

1፤ አንድም አውሬ ከባሕር ሲወጣ አየሁ፤ አሥር ቀንዶችና ሰባት ራሶች ነበሩት፥ በቀንዶቹም ላይ አሥር ዘውዶች በራሶቹም ላይ የስድብ ስም ነበረ።

2፤ ያየሁትም አውሬ ነብር ይመስል ነበር፥ እግሮቹም እንደ ድብ እግሮች፥ አፉም እንደ አንበሳ አፍ ነበሩ። ዘንዶውም ኃይሉንና ዙፋኑን ትልቅም ሥልጣን ሰጠው።

ከባህር ሲወጣ አየሁት የሚለው አውሬና ዘንዶው (በምእራፍ 12) ያየነው በጣም ይመሳሰላሉ ግን አንድ አይደሉም::  በዳንኤል 7 ላይም እንደተገለፀው ይህ አውሬ በምድር የሚገለጠው የክርስቶስ ተቃዋሚ ብሎ ዮሃንስ ይጠራዋል:: 

1 ዮሐንስ 2:18፤ ልጆች ሆይ፥ መጨረሻው ሰዓት ነው፥ የክርስቶስም ተቃዋሚ ይመጣ ዘንድ እንደ ሰማችሁ አሁን እንኳ ብዙዎች የክርስቶስ ተቃዋሚዎች ተነሥተዋል፤ ይላል ስለዚህም መጨረሻው ሰዓት እንደ ሆነ እናውቃለን። መገለጡ አይቀርም::

ያየሁትም አውሬ 

–  ነብር ይመስል ነበር፥ የግሪክን ኢንፓየር ይመለከታል

–  እግሮቹም እንደ ድብ እግሮች፥ የፐርዥያን ኢንፓየር

– አፉም እንደ አንበሳ አፍ ነበሩ። የባቢሎንን ኢንፓየር

–  ዘንዶውም ኃይሉንና ዙፋኑን ትልቅም ሥልጣን ሰጠው። 

ይህ የሚያሳየው በምድር የተነሱትን ነገስታትና የአገዛዞችን  አይነት ነው::  ከነዚህ ሁሉ የከፋ ግን እየመጣ እንደሆነ ነው  የሚያሳየው ደግሞም  ትልቅም ስልጣን ዘንዶው ሰጠው::  ስልጣንም ብቻ አይደለም ኃይሉንና ዙፋኑን ሁሉ ጨምሮ ሰጠው:: ለምን?  ጊዜው እንዳለቀ አውቆ ሊያጠፋ ስለሆነ ነው::

ይመጣል የተባለው ይመጣል ስለዚህ ስራችንን በጊዜ እንስራ አንዘናጋ ጌታ ጸጋን ይስጠን::

ራእይ 13: 3-6

3፤ ከራሶቹም ለሞት እንደ ታረደ ሆኖ አንዱን አየሁ፥ ለሞቱ የሆነውም ቍስል ተፈወሰ። ምድርም ሁሉ አውሬውን እየተከተለ ተደነቀ፥

4፤ ለዘንዶውም ሰገዱለት፥ ለአውሬው ሥልጣንን ሰጥቶታልና፤ ለአውሬውም፦ “አውሬውን ማን ይመስለዋል፥ እርሱንስ ሊዋጋ ማን ይችላል?” እያሉ ሰገዱለት።

5፤ ታላቅንም ነገርና ስድብን የሚናገርበት አፍ ተሰጠው፥ በአርባ ሁለት ወርም እንዲሠራ ሥልጣን ተሰጠው።

6፤ እግዚአብሔርንም ለመሳደብ ስሙንና ማደሪያውንም በሰማይም የሚያድሩትን ሊሳደብ አፉን ከፈተ።

ይህ አውሬ እየሱስን ለመምሰል ሲጥር እናያለን ለሞት እንደ ታረደ ሆኖ አንዱን አየሁ፥ ይላል የታረደው በግ እየስ ብቻ ነው::

ለሞቱ የሆነውም ቍስል ተፈወሰ። ምድርም ሁሉ አውሬውን እየተከተለ ተደነቀ፥ መዳኑ ሲታወቅ ብዙ ክብር  አመጣለት::  ምድር ሁሉ ወደ ሞት ጎዳና እየነጎደ ነው ያለው የእነዛን የሁለቱንምስክሮች ነገር ረሳና አውሬውን መከተሉን ቀጠሉ ሞቱን ሳያዩ::

ለዘንዶውም ሰገዱለትለአውሬው ሥልጣንን ሰጥቶታልና፤ ለአውሬውም፦ “አውሬውን ማን ይመስለዋል፥ እርሱንስ ሊዋጋ ማን ይችላል?” እያሉ ሰገዱለት? 

ለዚህ አጥፊ ዘንዶ ሰገዱ ለአውሬው ስልጣን ስለሰጠው::  ስግደት ግን የሚገባው የእኛ ጌታ ብቻ ነው ይህ አውሬ ህልሙ ሁሉ ይሄው ነበረ ግን ይህንንም ቢያገኝ ጊዜያዊ ነው:: ማን ይዋጋዋል አውሬውን ብለው በሚያደርገው ነገር ተገርመዋል::

አውሬው ታላቅንም ነገርና ስድብን የሚናገርበት አፍ ተሰጠው፥ በአርባ ሁለት ወርም እንዲሠራ ሥልጣን ተሰጠው። የተሰጠው የሚሳደብበት አፍ መሆኑ ይገርማል::  መሳደብ ሲባል በእግዚአብሔር ላይ መነሳቱን ያሳያል::  አምላክእኔ ነኝ ሲል ስድብና ድፍረት ነው:: አውሬውም  በእግዚአብሔር ስምና በማደሪያው በሰማይም በሚያድሩት ላይ ሊሳደብ አፉን ከፈተ:: ይህ ጊዜያዊ ድል የትም አያደርሰውም::  ጌታ በዚህ አይናወጥ ወይም አይሸነፍ እርሱ በዙፋኑ ከብሮ ይኖራል::  አሜን!

ራእይ 13: 7-18

7፤ ቅዱሳንንም ይዋጋ ዘንድ ድልም ያደርጋቸው ዘንድ ተሰጠው፥ በነገድና በወገንም በቋንቋም በሕዝብም ሁሉ ላይ ሥልጣን ተሰጠው።

8፤ ከዓለምም ፍጥረት ጀምሮ በታረደው በግ ሕይወት መጽሐፍ ስሞቻቸው ያልተጻፉ በምድር የሚኖሩ ሁሉ ይሰግዱለታል።

17፤ የአውሬውም ስም ወይም የስሙ ቍጥር ያለው ምልክት የሌለበት ማንም ሊገዛ ወይም ሊሸጥ እንዳይችል ያደርጋል። ጥበብ በዚህ አለ።

በዚህ ምዕራፍ ላይ እንደምናየው ሀሰተኛው ክርስቶስ በምድር ተገልጦ ስራውን ጀምሯል:: ዓለምን ሁሉ እያሰገደ ነው የሚገርመው በዚህ ውስጥ ስማቸው በህይወት መጽሐፍ የተፃፈ አልሰገዱም ድል እንዲያደርጋቸውም ስልጣን ተሰቶታል::  ድል የሚያደርጋቸው ግን እምነታቸውን በማስተው ሳይሆን በመግደል ነው::  ስልጣኑም በነገድና በወገንም በቋንቋም በሕዝብም ሁሉ ላይ ነው ስለዚህ የቀረ አገር ወይም ስፍራ የለም ሁሉ ተከትሎ እያመለከው ነው።  ምናልባትም ፖለቲካ ይመስል ይሆናል ነገር ግን ይህ ለጠላት የሚቀርብ አምልኮ ነው:: 

ኢኮኖሚውን ይቆጣጠራል ማንም ስሙን ወይም ቁጥሩን ካልተቀበለ በስተቀር መግዛትም መሸጥም አይቻልም::  ጥበቡንም በዚህ ይገልጣል::  ቅዱሳን ያላቸው ምርጫ እንቢ ሲሉ መገደል ብቻ ነው:;  እነዚህ ቅዱሳን እነማንናቸው? ሁለት አይነት አመለካከት አለ አንዱ ቤተክርስቲያን ከሄደች በኃላ የዳኑ ናቸው ሲሆን ሌላው ደግሞ ቤተክርስትያን አልተወሰደችም እርስዋ ናት የምትሰደደው ነው የሚሉት::  በተለያየ ቦታ እንዳየነው ግን ጌታ ድሉን በሰማይ ብቻውን እያከበረ አይደለም::  ምዕራፍ 4 ጀምሮ ቅዱሳንን  እናያለን 24ቱን ሽማግሌዎች ጨምሮ::  እንዲሁም 7:9 ላይም እናያለን:: 

እኔም ይሁንልኝ ብዬ የምለው ቀድሞ መሄዱን ነው::  ለምን በምድር ይተወናል?  በዚህ ሁሉ ውጥንቅጥ ውስጥ?  በቤተክርስቲያን ላይ ያለው የእግዚአብሔር መንፈስ ነው ዛሬ እንደወደደ እንዳይሰራ የሚያደርገው::  ስለዚህ ቅዱሳን ብንወሰድ ነው እንደዚህ በግልፅ ለመገለጥ የበቃው::  በዛም ሆነ በዚህ ለሁለቱም ግምቶች ተዘጋጅቶ መጠበቁ ወሳኝ ነው:: 

እዚህ ክፍል ላይ ሌላ አውሬ እናያለን ከመጀመርያው የሚለየው የመጀመሪያድ ከውሃ ነው የወጣው ይሄ ደግሞ ከምድር::  ስራውም የመጀመሪያው አውሬ እንዲመለክ ማስገደድ ነው:: በኃይል ነው የሚሰራው ራእይ 13:13፤ እሳትንም እንኳ ከሰማይ ወደ ምድር በሰው ፊት እስኪያወርድ ድረስ ታላላቆችን ምልክቶች ያደርጋል።  ልክ የነብይነት ስራ የሚሰራ ነው የሚመስለው::  እርሱ ነው ሰውን ሁሉ የሚያስተው:: 

ሰይጣንና መንግስቱ ተሸንፏል ድል ሁሌም ለጌታና ለአካሉ ነው::

ራእይ 14: 1-5

1፤ አየሁም፥ እነሆም፥ በጉ በጽዮን ተራራ ቆሞ ነበር፥ ከእርሱም ጋር ስሙና የአባቱ ስም በግምባራቸው የተጻፈላቸው መቶ አርባ አራት ሺህ ነበሩ።

2፤ እንደ ብዙ ውኃም ድምፅና እንደ ታላቅ ነጐድጓድ ድምፅ ያለ ከሰማይ ድምፅን ሰማሁ፥ ደርዳሪዎችም በገና እንደሚደረድሩ ያለ ድምፅ ሰማሁ።

3፤ በዙፋኑም ፊት በአራቱም እንስሶችና በሽማግሌዎቹ ፊት አዲስ ቅኔ ዘመሩ፤ ከምድርም ከተዋጁት ከመቶ አርባ አራት ሺህ በቀር ያን ቅኔ ሊማር ለማንም አልተቻለውም።

እነዚህ 144 ሺህ በመጀመርያ የተጠቀሱት  ምዕራፍ 7 ላይ ነበረ ከመቅሰፍቱ በፊት ታተሙ::  በጉ ከነዚህ ሰዎች ጋር በጽዮን ተራራ ቆሞ ነበር፥ በእነርሱም ላይ ስሙና የአባቱ ስም በግምባራቸው ተፅፎ ነበረ::  የሌላውን ምልክት አይደለም የተቀበሉት የጌታቸውን እንጂ::  አውሬውም ገደላቸው አሁን ግን ከንጉሳቸው ጋር መጡ::  ልክ እንደቀጠረን በሐዋርያት ስራ ላይ እንዲሁ እንደሄደ ይመጣል እንደሚል ቃሉን ጠብቆ በዛው ተራራ ላይ መጣ::  አሁን ግን የመጣው ሊፈርድ ነው::

አምልኮንና ዝማሬንም ቀጠሉ ከእነርሱ በቀር ማንም ያልቻለውን  በዙፋኑም ፊት በአራቱም እንስሶችና በሽማግሌዎቹ ፊት አዲስ ቅኔ ዘመሩ፤  ስለ አዘማመራቸውና ድምፃቸው ዮሃንስ እንደዚህ ይላል:-  እንደ ብዙ ውኃም ድምፅና እንደ ታላቅ ነጐድጓድ ድምፅ ያለ ከሰማይ ድምፅን ሰማሁ፥ ደርዳሪዎችም በገና እንደሚደረድሩ ያለ ድምፅ ሰማሁ::

እነዚህ ሰዎች ከሴቶች ጋር ያልረከሱ እነዚህ ናቸው፥ ድንግሎች ናቸውና። በጉ ወደሚሄድበት የሚከተሉት እነዚህ ናቸው። ለእግዚአብሔርና ለበጉ በኵራት እንዲሆኑ ከሰዎች የተዋጁ እነዚህ ናቸው።በአፋቸውም ውሸት አልተገኘም፤ ነውር የለባቸውም። ምን አይነት ህይወት ነው? በዚህ ሁሉ መከራ ውስጥ አልፈው ለጌታ የኖሩ ናቸው::

ጌታ ይወስደናል! ማራናታ!

ራእይ 14: 6-13

6፤ በምድርም ለሚኖሩ ለሕዝብም ለነገድም ለቋንቋም ለወገንም ሁሉ ይሰብክ ዘንድ የዘላለም ወንጌል ያለው ሌላ መልአክ ከሰማይ መካከል ሲበር አየሁ፤

7፤ በታላቅ ድምፅም፦ “የፍርዱ ሰዓት ደርሶአልና እግዚአብሔርን ፍሩ ክብርንም ስጡት፤ ሰማይንና ምድርንም ባሕርንም የውኃንም ምንጮች ለሠራው ስገዱለት፡” አለ።

12፤ የእግዚአብሔርን ትእዛዛት የሚጠብቁት ኢየሱስንም በማመን የሚጸኑት ቅዱሳን ትዕግሥታቸው በዚህ ነው።

13፤ ከሰማይም፦ “ከእንግዲህ ወዲህ በጌታ የሚሞቱ ሙታን ብፁዓን ናቸው።” መንፈስ፦ “አዎን፥ ‘ከድካማቸው ያርፉ ዘንድ፥ ሥራቸውም ይከተላቸዋል ይላል’ ብለህ ጻፍ፡” የሚል ድምፅ ሰማሁ።

እዚህ ስፍራ ላይ የእግዚአብሔርን ፍርድ የሚያስታውቁ መልአክትን እናያለን::  

የመጀመርያው ወንጌልን ለዓለም ሁሉ የሚሰብክ ሲሆን  የፍርዱ ሰዓት ደርሶአልና እግዚአብሔርን ፍሩ ክብርንም ስጡት፤ ሰማይንና ምድርንም ባሕርንም የውኃንም ምንጮች ለሠራው ስገዱለት ይላል:: 

ሁለተኛው የባቢሎንን መውደቅ እያወጀ ተከተለው::  ስለባቢሎን ገና ብዙ እናያለን በሚመጡት ምዕራፎች::

ሦስተኛም መልአክ ተከተላቸው፥ በታላቅ ድምፅ እንዲህ እያለ፦ “ለአውሬውና ለምስሉ የሚሰግድ በግምባሩም ወይም በእጁ ምልክቱን የሚቀበል ማንም ቢኖር፥ እርሱ ደግሞ በቍጣው ጽዋ ሳይቀላቅል ከተዘጋጀው ከእግዚአብሔር ቍጣ ወይን ጠጅ ይጠጣል፥ በቅዱሳንም መላእክትና በበጉ ፊት በእሳትና በዲን ይሳቀያል።

ለቅዱሳኑ የተባለው ግን የእግዚአብሔርን ትእዛዛት የሚጠብቁት ኢየሱስንም በማመን የሚጸኑት ቅዱሳን ትዕግሥታቸው በዚህ ነው። “ከእንግዲህ ወዲህ በጌታ የሚሞቱ ሙታን ብፁዓን ናቸው።” መንፈስ፦ “አዎን፥ ‘ከድካማቸው ያርፉ ዘንድ፥ ሥራቸውም ይከተላቸዋል ይላል’

በዚህ ሁሉ ውስጥ እራሱን ያለ ምስክር የማይሰጥ ጌታ ልጆች አሉት ::  በመጨረሻው ዘመን አውሬው ጊዜ እንደሌለው አውቆ የእግዚአብሔርን ህዝብ መግደል ነው ስራው ጌታም ብፁዓን ብሎ ይጠራቸዋል::  

ራእይ 14:  14-20

14፤ አየሁም፥ እነሆም ነጭ ደመና፥ በደመናውም ላይ የሰውን ልጅ የሚመስል ተቀምጦአል፥ በራሱም ላይ የወርቅ አክሊል በእጁም ስለታም ማጭድ ነበረው።

18፤ በእሳትም ላይ ሥልጣን ያለው ሌላ መልአክ ከመሠዊያው ወጥቶ ስለታም ማጭድ ያለውን፦ “ዘለላዎቹ ፈጽመው በስለዋልና ስለታሙን ማጭድህን ስደድና በምድር ያለውን የወይን ዛፍ ዘለላዎች ቍረጥ፡” ብሎ በታላቅ ድምፅ ጠራ::

እዚህም ቦታ ላይ የሰውን ልጅ የሚመስልና በራሱም ላይ የወርቅ አክሊል  ያደረገ ካለ እየሱስ ማን ሊሆን ይችላል?  በነጭ ደመና ላይ ተቀምጦ በእጁም ስለታም ማጭድ ነበረው። ይህንንም ማጭፍ የሚጠቀመው የደረሰውን መከር ለመሰብሰብ ነው:: “የማጨድ ሰዓት ስለ ደረሰ ማጭድህን ስደድና እጨድ፥ የምድሪቱ መከር ጠውልጓልና፡” ብሎ አንድ ሙልአክ በታላቅ ድምፅ ጮኸ።  ከመድረስም አልፎ ጠውልጏል ነው የሚለው ጌታን ይህን ያህል ነው የታገሰው ሰዎች እንዲድኑ ብሎ:: በወንጌል መጽሐፍ ላይ አንተ ስንዴ ዘራህ እንክርዳዱ ከየት መጣ እናስወግደው ወይ ብለው ቢሉት ተውት አብሮ ይብቀል እንዳለ አብሮ በቅሎ ዛሬ ግን ስንዴው ወደ ጎተራው እየተሰበሰበ ነው በራሱ በጌታ::  በማቴዎስ 13:30፤ ተዉአቸው፤ እስከ መከር ጊዜ አብረው ይደጉ፤ በመከር ጊዜም አጫጆችን፦ እንክርዳዱን አስቀድማችሁ ልቀሙ በእሳትም ለማቃጠል በየነዶው እሰሩ፥ ስንዴውን ግን በጎተራዬ ክተቱ እላለሁ፡’ አለ።” ማቴ 13: 24-43 ጌታ ስለ ሙጨረሻው ዘመን በደንብ ነግሮናል::

እንደገናም ደግሞ  እዚህ ስፍራ ላይ የወይን ዘለላዎች ቁረጥ ይላል::  ቅዱሳን በወይን ግንዱ ላይእንደተተከሉ ቃሉ ይናገራል ይህም ጊዜ ህዝቡን ወደ ቤቲቱ ጌታ እየሰበሰበ ነው::  በእሳትም ላይ ሥልጣን ያለው ሌላ መልአክ ከመሠዊያው ወጥቶ ስለታም ማጭድ ያለውን፦ “ዘለላዎቹ ፈጽመው በስለዋልና ስለታሙን ማጭድህን ስደድና በምድር ያለውን የወይን ዛፍ ዘለላዎች ቍረጥ፡” ብሎ በታላቅ ድምፅ ጠራ::

ይህንን ምዕራፍ ስናይ ለምዕራፍ 13 መልስ ነው::  አውሬው ፈፅሞ ያሸነፈና ነገርር ሁሉ የተጠናቀቀ ይመስላል ነገር ግን የእግዚአብሔርን ቁጣ መገለጥ ስናይ ህዝቡን ሰብስቦ ሲያበቃ በቁጥር 20፤ የወይኑም መጥመቂያ ከከተማ ውጭ ተረገጠ፥ እስከ ፈረሶች ልጓምም የሚደርስ ደም ርቀቱ ሺህ ስድስት መቶ ምዕራፍ ሆኖ ከመጥመቂያው ወጣ። ውጊያው ከእየሱስ ጋር ይሆናል ይህም አርማጌዶንን የሚገልፅ ይመስላል ምክንያቱም ምዕራፉን ስንጀምር በጉ በጽዮን ተራራ ላይ ተገልጧል::

ድል ለአምላካችንና ለእኛም ለህዝቡ ነው!!!!  ክብር ይሁንለት!

ራእይ 15:1-4

1፤ ሌላም ታላቅና ድንቅ ምልክት በሰማይ አየሁ፤ የእግዚአብሔር ቍጣ በእነርሱ ስለሚፈጸም ኋለኛዎቹን ሰባት መቅሠፍቶች የያዙ ሰባት መላእክት ታዩ።

2፤ በእሳትም የተቀላቀለውን የብርጭቆ ባሕር የሚመስለውን አየሁ፥ በአውሬውና በምስሉም በስሙም ቍጥር ላይ ድል ነሥተው የነበሩት የእግዚአብሔርን በገና ይዘው በብርጭቆ ባሕር ላይ ሲቆሙ አየሁ።

3-4፤ “ሁሉን የምትገዛ ጌታ አምላክ ሆይ፥ ሥራህ ታላቅና ድንቅ ነው፤ 

የአሕዛብ ንጉሥ ሆይ፥ 

መንገድህ ጻድቅና እውነተኛ ነው፤ 

ጌታ ሆይ፥ የማይፈራህና ስምህን የማያከብር ማን ነው? 

አንተ ብቻ ቅዱስ ነህና፥ 

የጽድቅም ሥራህ ስለ ተገለጠ አሕዛብ ሁሉ ይመጣሉ በፊትህም ይሰግዳሉ፡” እያሉ የእግዚአብሔርን ባሪያ የሙሴን ቅኔና የበጉን ቅኔ ይዘምራሉ።

ዮሃንስ ታላቅና ድንቅ ምልክት በሰማይ አየሁ፤  ሲል ምን ይሆን ያሰኛል ያየው ግን የእግዚአብሔር ን ቍጣና  በእነርሱ ስለሚፈጸም ኋለኛዎቹን ሰባት መቅሠፍቶች የያዙ ሰባት መላእክት ነበረ።   ይህንኑ ቃል በዘሌዋውያን 26:21፤ “ ‘በእንቢተኝነትም ብትሄዱብኝ ባትሰሙኝም፥ እንደ ኃጢአታችሁ መጠን በመቅሠፍት ላይ ሰባት እጥፍ እጨምራለሁ።  ይህንኑ ነው በምድር ላይ እያደረገ ያለው እንደተናገረው::

እነዚህ ሰባት መቅሰፍቶች በማይታዘዙት ላይ የመጡ ናቸው:: ለታዘዙትና አውሬውን ድል ነስተው ለመጡት  ደግሞ:- የእግዚአብሔርን በገና ይዘው በብርጭቆ ባሕር ላይ ሲቆሙ አየሁ።  እነዚህ ቅዱሳን ምንም እንኳን አውሬው ድል  እንዲነሳቸው ስልጣን ቢሰጠውም የእርሱን ቁጥር ግን አልተቀበሉም:- በአውሬውና በምስሉም በስሙም ቍጥር ላይ ድል ነስተው የመጡ ናቸው::

እነዚህ ድል የነሱ ቅዱሳን የእግዚአብሔርን ባሪያ የሙሴን ቅኔና የበጉን ቅኔ ይዘምራሉ ይላል::  ለምን ሁለቱ በአንድ ላይ ተጠቀሰ? ምክንያቱም ህግን ፈጽሞ በፍቅር አቅፎናልና ነው ብሉይም አዲስም ኪዳንን አዋህዷል ጌታ::  የሚገርመው  በገናን ይዘው ማምለክ ቀጠሉ የከፈሉት የህይወት ዋጋ በሞት ማለፋቸው ትዝም ሳይላቸው አንተ ይገባሃል እያሉ አምልኳቸውን ቀጠሉ!!!  ሰይጣን ከመጀመሪያውም የአምልኮ መሪ ነበረ ዛሬ ደግሞ የገደላቸው ቅዱሳን የእርሱን ስፍራ ይዘው አመለኩት:- አምልኮ የሚገባውን::  በገና ይዘው ያየነው በምዕራፍ 5 ላይ እንሰሶቹና ሃያ አራቱን ሽማግሌዎች ነበር አሁን ግን ይህ ሰራዊት ያመልካል::  በዝማሬያቸውም ጌታን የአህዛብ ንጉስ እንዲሁም የጽድቅም ሥራህ ስለ ተገለጠ አሕዛብ ሁሉ ይመጣሉ በፊትህም ይሰግዳሉ እያሉ ነው የሚዘምሩት::  እኛም አህዛብ የሆንን አምነንና ጽድቁን አጣጥመን እያመለክነው ነው ደግሞም እናመልካልእን::  ሃሌሉያ!!!

ራእይ 15: 5- ራእይ 16:7

5፤ ከዚህም በኋላ አየሁ፥ የምስክርም ድንኳን መቅደስ በሰማይ ተከፈተ፥

6፤ ሰባቱንም መቅሠፍት የያዙ ሰባቱ መላእክት ከመቅደሱ ወጡ፤ ከተልባ እግርም የተሠራ ጥሩ የጌጥ ልብስ ለበሱ ደረታቸውንም በወርቅ መታጠቂያ ታጠቁ።

8፤ ከእግዚአብሔርም ክብርና ከኃይሉ ጢስ በመቅደሱ ሞላበት፥ የሰባቱ መላእክት ሰባቱ መቅሰፍት እስኪፈጸሙ ድረስ አንድ እንኳ ወደ መቅደሱ ይገባ ዘንድ አልቻለም።

ራእይ 16:1፤ ለሰባቱም መላእክት፦ “ሄዳችሁ የእግዚአብሔርን ቁጣ ጽዋዎች በምድር ውስጥ አፍስሱ፡” የሚል ታላቅ ድምፅ ከመቅደሱ ሰማሁ።

በላይ በሰማይ የምስክርም ድንኳን መቅደስ በሰማይ ተከፈተ ይላል ዮሃንስ:.  ሙሴ እንደምታየው ስራ የተባለው ይህንን እያየ ነበረ::  ሰባቱንም መቅሠፍት የያዙ ሰባቱ መላእክት ከመቅደሱ ወጡ፤ የእግዚአብሔር መታገስ ሁሉ እንዲድኑና ንስሃ እንዲገቡ ነው እንጂ ፍርድማ ይቀጥላል::

ልክ በሙሴ ዘመንና ሰለሞንም ቤተ መቅደሱን ሲያስመርቅ ከእግዚአብሔር ክብር የተነሳ ማንም ሙንቀሳቀስ እንዳልቻለ ሁሉ እዚህም ጋር የምናየው ይህንኑ ነው መልአክቱም መግባት አልቻሉም::  ከእግዚአብሔርም ክብርና ከኃይሉ ጢስ በመቅደሱ ሞላበት፥ የሰባቱ መላእክት ሰባቱ መቅሰፍት እስኪፈጸሙ ድረስ አንድ እንኳ ወደ መቅደሱ ይገባ ዘንድ አልቻለም።

እነዚህ ሰባት መልአክት ሄዳችሁ የእግዚአብሔርን ቁጣ ጽዋዎች በምድር ውስጥ አፍስሱ ተባሉ::  እነርሱም አፈሰሱ ሰዎች ግን እግዚአብሔርን ይሳደቡ ጀመር እንጂ ንስሃ አልገቡም:,  የእግዚአብሔር አላማ ጠላት ላይ መፍረድና ሰዎችን ደግሞ ለማዳን ነበረ::

ይህ ሁሉ ቁጣ በምድር ላይ እየመጣ ያለው መልአክቱ እንደሚሉት:-

እንዲህ ስለፈረድህ ጻድቅ ነህ፤

የቅዱሳንና የነቢያትን ደም ስላፈሰሱ ደምን ደግሞ አጠጥተሃቸዋል፥ የሚገባቸው ነውና::  ከመሰዊያውም እንዲህ ብሎ ሲናገር ሰማሁ፦ “አዎን፥ ሁሉን የምትገዛ ጌታ አምላክ ሆይ፥ ፍርዶችህ እውነትና ጽድቅ ናቸው።

እርሱ እውነተኛ እንጂ ፍርደ ገምድል አይደለም:: ስለተገደሉት ቅዱሳን በቀል ነው::  እረፍት እንዲያደርጉ ተነግሯቸው ነበረ መቼ ነው የምትፈርድልን ሲሉት::  ፍርዱን አየን!

ራእይ 16: 8-21

8፤ አራተኛውም ጽዋውን በፀሐይ ላይ አፈሰሰ፤ ሰዎችንም በእሳት ልታቃጥል ተሰጣት።

10፤ አምስተኛውም ጽዋውን በአውሬው ዙፋን ላይ አፈሰሰ፤ መንግሥቱም ጨለማ ሆነች ከስቃይም የተነሳ መላሶቻቸውን ያኝኩ ነበር፥

15፤ “እነሆ፥ እንደ ሌባ ሆኜ እመጣለሁ፤ ራቁቱን እንዳይሄድ እፍረቱንም እንዳያዩ ነቅቶ ልብሱን የሚጠብቅ ብፁዕ ነው።”

16፤ በዕብራይስጥም አርማጌዶን ወደሚባል ስፍራ አስከተቱአቸው።

17፤ ሰባተኛውም ጽዋውን በአየር ውስጥ አፈሰሰ፤ ከመቅደሱም ውስጥ፦ “ተፈጽሞአል፡” የሚል ታላቅ ድምጽ ከዙፋኑ ወጣ።

ሰባቱ መቅሰፍቶች በዚህ ምዕራፍ ላይ በምድር ሲፈሱ እናያለን::  ከነዚህም መካከል:- 

ፀሃይ እንድታቃጥል ተሰጣት ይህ ማለት የኦዞን መቀደድ እያሉ የሚሉት ይሆን ወይስ ከዛም የከፋ ይመጣል? ለበረከት የተሰጠን ፀሃይ ለጥፋት ልትሆን ነው::  

ጨለማም በምድር ላይ እንዲሆን ልክ ግብፅ ላይ እንደመጣው መቅሰፍት :  

የኤፍራጥስ ወንዝ መድረቅ ማለትም ለጦርነቱ ለመክተት ለምድር ነገስታት  የተዘጋጀ ነው::  አሁንም ወንዙ እየደረቀ ነው:: መጨረሻው ላይ እንዳለን እናስተውል::

ይህ ሁሉ ግን ሲኦልን ቅመሱትና ንስሃ ግቡ ወደ እኔ ተመለሱ እያለ ባለበት የሰው ልጅ ግን የቀናው መሳደብ ነበረ:: ስለዚህ ጌታ ተፈጸመ አለ ትዕግስት አበቃ ልብስህን ጠብቅ እንደሌባ እመጣለሁ አለ::

በእንቁራሪት የተመሰለ አሳች መንፈስ ነገስታትን ሁሉ ወደ አርማጌደን አሰለፈ መንግስታት ከእግዚአብሔር ጋር ሊዋጉ::  ውጤቱ የታወቀ ነው::  በጉም በጽዮን ተራራ ላይ ተገጧል ድል ይነሳል::  ማንም አይቶት የማያውቅ የመሬት መናወጥ ሆነ ደሴቶችም ሸሹ ተራሮችም አልተገኙም ይህ የእግዚአብሔር ቀን ነው!  ድል ለነሳው ክብር ይሁን! 

ጌታ ይመጣል!  ልብሳችንን ለብሰን ተዘጋጅተን ሳንዘናጋ እንጠብቅ!

ራእይ 17: 1-18

1፤ ሰባቱንም ጽዋዎች ከያዙ ከሰባቱ መላእክት አንዱ መጥቶ፦ “ና በብዙም ውኃዎች ላይ የተቀመጠችውን የታላቂቱን ጋለሞታ ፍርድ አሳይሃለሁ፤

ራእይ 17:6፤ ሴቲቱም በቅዱሳን ደምና በኢየሱስ ምስክሮች ደም ሰክራ አየኋት። ባየኋትም ጊዜ እጅግ ታላቅ ድንቅ አደነቅሁ።

8፤ ያየኸው አውሬ አስቀድሞ ነበረ፥ አሁንም የለም፥ ከጥልቁም ይወጣ ዘንድ አለው፥ ወደ ጥፋትም ይሄዳል፤ ስሞቻቸውም ከዓለም ፍጥረት ጀምሮ በሕይወት መጽሐፍ ያልተጻፉ በምድር የሚኖሩ አውሬው አስቀድሞ እንደነበረ አሁንም እንደሌለ፥ ነገር ግን እንዳለ ሲያዩ ያደንቃሉ። 9፤ “ጥበብ ያለው አእምሮ በዚህ ነው። ሰባቱ ራሶች ሴቲቱ የተቀመጠችባቸው ሰባት ተራራዎች ናቸው፥ 10፤ ሰባት ነገሥታት ደግሞ ናቸው፤ አምስቱ ወድቀዋል አንዱም አለ፥ የቀረውም ገና አልመጣም፤ ሲመጣም፥ ጥቂት ጊዜ ሊቆይ ይገባዋል።

14፤ እነዚህ በጉን ይወጋሉ፤ በጉም የጌቶች ጌታና የነገሥታት ንጉሥ ስለ ሆነ እነርሱን ድል ይነሣል፥ ከእርሱም ጋር ያሉ የተጠሩና የተመረጡ የታመኑም ደግሞ ድል ይነሣሉ።”

ሰባቱን የእግዚአብሔርን ቁጣ የያዙ መልአክት በምዕራፍ 16 እድወጡና ቁጣውም በምድር እንዳፈሰሰው አይተናል::  ግን እነማን ተቀጡ የሚለውንም ትንሽ ነግሮናል:- 

ራእይ 16:6፤ የቅዱሳንና የነቢያትን ደም ስላፈሰሱ ደምን ደግሞ አጠጥተሃቸዋል፥ የሚገባቸው ነውና።” ይላል::  ይህ ምዕራፍ ጠለቅ ብሎ ከነምክንያቱ ይመልስልናል:: የምትቀጣውም በብዙም ውኃዎች ላይ የተቀመጠችው ታላቂቱ ጋለሞታ ናት::

ያየሃትም ሴት በምድር ነገሥታት ላይ የምትነግሥ ታላቂቱ ከተማ ናት።”  አለኝም፦ “ጋለሞታይቱ የተቀመጠችባቸው ያየሃቸው ውኃዎች፥ ወገኖችና ብዙ ሰዎች አሕዛብም ቋንቋዎችም ናቸው። ሰባቱ ራሶች ሴቲቱ የተቀመጠችባቸው ሰባት ተራራዎች ናቸው፥ ሰባት ነገሥታት ደግሞ ናቸው::  ሴቲቱም በቅዱሳን ደምና በኢየሱስ ምስክሮች ደም ሰክራ አየኋት እንደሚል ቅጣትዋን ትቀበላለች:: በዓለም ሁሉ የተንሰራፋ ግድያ ነው የተፈጸመው በእግዚአብሔር ምርጦች ላይ ስለዚህ ፍርድ ግድ ነው:: እነዚህ ነገስታት ለጠላት የተገዙ እርሱ እንደወደደ የሚዘውራቸው ናቸው::

እነዚህ ህዝቦችና ነገስታት ፍጥረት መሆናቸውን ረስተው ከፈጣሪ ጋር ለመዋጋት አሰቡ::  ሁሉ ተሰብስበው በጉን ሲዋጉ በጉ በድል አድራጊነት ይወጣል::  ይህ ብቻ አይደለም  ከእርሱም ጋር ያሉ የተጠሩና የተመረጡ የታመኑም ደግሞ ድል ይነሣሉ።” እርሱ ባገኘው ድል የዳኑትም ድል ይነሳሉ ይላል::  ምን አይነት ጌታ ነው? ስሙ ይባረክ! ጌታ ሁሌም ድል ይነሳል! 

ድል ለነሳው ክብር ይሁን::

ራእይ 18: 1-24

1፤ ከዚህ በኋላ ታላቅ ስልጣን ያለው ሌላ መልአክ ከሰማይ ሲወርድ አየሁ፥ ከክብሩም የተነሣ ምድር በራች።

2፤ በብርቱም ድምፅ እንዲህ ብሎ ጮኸ፦ “ታላቂቱ ባቢሎን ወደቀች፥ ወደቀች፥ የአጋንንትም ማደሪያ ሆነች፥ የርኵሳንም መናፍስት ሁሉ መጠጊያ የርኵሳንና የተጠሉም ወፎች ሁሉ መጠጊያ ሆነች፤

4፤ ከሰማይም ሌላ ድምፅ ሰማሁ እንዲህ ሲል፦ “ሕዝቤ ሆይ፥ በኃጢአትዋ እንዳትተባበሩ ከመቅሠፍትዋም እንዳትቀበሉ ከእርስዋ ዘንድ ውጡ፤

5፤ ኃጢአትዋ እስከ ሰማይ ድረስ ደርሶአልና፥ እግዚአብሔርም ዓመፃዋን አሰበ።

በዚብ ምዕራፍ ላይ የምናየው የባቢሎንን መቀጣትና መጥፋት ነው::  በምዕራፍ 17ም ላይ ይህንኑ አይትእናል ታድያ ሁለት ባቢሎን አለ ወይስ በመንፈሳዊውና በኢኮኖሚው ነው ሁለት የሆኑት?  ይህችኛዋ እየደቀቀች ያለችው በሃብትዋ ነው:: 

እግዚአብሔርም  ሕዝቤ ሆይ፥ በኃጢአትዋ እንዳትተባበሩ ከመቅሠፍትዋም እንዳትቀበሉ ከእርስዋ ዘንድ ውጡ፤ ይላል::  በዚህ ዘመንም ህዝብ አለው አምላካችን ጠላት በብዙ ኃይሉ እየሰራና ቅዱሳንን እየገደለ ባለበት ጊዜ::

የመጨረሻው ሰዓት ነውና ሁሉ የጠላት አሰራር እየተደመሰሰ ያለበት ጊዜ ነው::  ማን ከበጉ ጋር ተዋግቶ ያሸንፋል?  ቅጣቱን ሁሉ ይቀበላል በጠላት እጅ ላለፉት ጌታ ይይልይቸው ሌሎችምአሉና እስኪመጡ አረፍ በሉ ነበረ::  ይኸድ አሁን ዘመን መቶ ለልጆቹ እየተበቀለና ክቡር መሆኑን እያሳየ ነው::  ባቢሎን ወደቀች!

ጌታ ይከብራል ይነግስማል::  አሜን!

ራእይ 19: 1- 1-4

1-2፤ ከዚህ በኋላ በሰማይ፦ “ሃሌ ሉያ፤ በዝሙትዋ ምድርን ያጠፋችይቱን ታላቂቱን ጋለሞታ ስለ ፈረደባት፥ የባሪያዎቹንም ደም ከእጅዋ ስለ ተበቀለ፥ ፍርዶቹ እውነትና ጽድቅ ናቸውና ማዳንና ክብር ኃይልም የአምላካችን ነው፡” ብሎ ሲናገር እንደ ብዙ ሕዝብ ታላቅ ድምፅ ያለ ድምፅን ሰማሁ።

3፤ ደግመውም አሉ፦ “ሃሌ ሉያ፤ ጢስዋም ለዘላለም እስከ ዘላለም ይወጣል።”

4፤ ሀያ አራቱም ሽማግሌዎችና አራቱ እንስሶች በፊታቸው ተደፍተው በዙፋኑ ላይ ለተቀመጠው ለእግዚአብሔር፦ “አሜን፥ ሃሌ ሉያ፡” እያሉ ሰገዱለት።

እዚህ ስፍራ ላይ እግዚአብሔርን እያመለኩበት ያለው ምክንያት በባቢሎን መቀጣት ምክንያት ነው::  

1.  የባሪያዎቹንም ደም ከእጅዋ ስለ ተበቀለ፥ 

በምዕራፍ 6:10-11፤ በታላቅ ድምፅም እየጮኹ፦ “ቅዱስና እውነተኛ ጌታ ሆይ፥ እስከ መቼ ድረስ አትፈርድም ደማችንንስ በምድር በሚኖሩት ላይ እስከ መቼ አትበቀልም?” አሉ። 11፤ ለእያንዳንዳቸውም ነጭ ልብስ ተሰጣቸው፥ እንደ እነርሱም ደግሞ ይገደሉ ዘንድ ያላቸው የባሪያዎች ባልንጀራዎቻቸውና የወንድሞቻቸው ቍጥር እስኪፈጸም ድረስ፥ ገና ጥቂት ዘመን እንዲያርፉ ተባለላቸው። ልክ እንደተናገረው ቁጥሩ ሲፈጸም ፍርዱን አደረገ::  

እንዲሁም ደግሞ  በራእይ 18:24፤ በእርስዋም ውስጥ የነቢያትና የቅዱሳን ደም በምድርም የታረዱ ሁሉ ደም ተገኘባት።”

2.  ፍርዶቹ እውነትና ጽድቅ ናቸውና 

የእግዚአብሔር ፍርድ ጽድቅን የተሞላ ነው::  በራእይ 16:5፤ የውኃውም መልአክ እንዲህ ብሎ ሲናገር ሰማሁ፦ “ያለህና የነበርህ ጌታ ሆይ፥ ቅዱስ ሆይ፥ እንዲህ ስለፈረድህ ጻድቅ ነህ፤

3.  ማዳንና ክብር ኃይልም የአምላካችን ነው፡”

ይህንን በሰሙ ጊዜ ሀያ አራቱም ሽማግሌዎችና አራቱ እንስሶች በፊታቸው ተደፍተው በዙፋኑ ላይ ለተቀመጠው ለእግዚአብሔር፦ “አሜን፥ ሃሌ ሉያ፡” እያሉ ሰገዱለት።

ዛሬም እኛ ሃሌ ሉያ እያልን ለዚህ ፃድቅ ለሆነ ፈራጅ እያመለክን እንሰግድለታለን::  የምናየውን ሁሉ ውጥንቅጥ ፀጥ አድርጎ የሰላሙን መንግስት በሰማይ ለዘረጋው ወደ እርሱም ለሚወስደን ጌታ ክብር ይሁንለት::  እናመልከዋለን፦ እንባርከዋለን ደግሞም እንገዛለታለን፦ እንታዘዘውማለን:: አሜን!!!

ራእይ 19: 5-10

5፤ ድምፅም እንዲህ ሲል ከዙፋኑ ወጣ፦ “ባሪያዎቹ ሁሉ እርሱንም የምትፈሩት ታናናሾችና ታላላቆች ሆይ፥ አምላካችንን አመስግኑ፡”

6፤ እንደ ብዙ ሕዝብም ድምፅ፥ እንደ ብዙ ውኃዎችም ድምፅ፥ እንደ ብርቱም ነጐድጓድ ድምፅ ያለ ድምፅ ሰማሁ እንዲህ ሲል፦ “ሃሌ ሉያ፤ ሁሉን የሚገዛ ጌታ አምላካችን ነግሦአልና።

7፤ የበጉ ሰርግ ስለ ደረሰ ሚስቱም ራስዋን ስላዘጋጀች ደስ ይበለን ሐሤትም እናድርግ ክብርንም ለእርሱ እናቅርብ።

8፤ ያጌጠና የተጣራ ቀጭን የተልባ እግር ልብስ እንድትጐናጸፍ ተሰጥቶአታል። ቀጭኑ የተልባ እግር የቅዱሳን ጽድቅ ሥራ ነውና።”

9፤ እርሱም፦ “ ‘ወደ በጉ ሰርግ እራት የተጠሩ ብፁዓን ናቸው፡’ ብለህ ጻፍ፡” አለኝ። ደግሞም፦ “ይህ የእግዚአብሔር እውነተኛ ቃል ነው፡” አለኝ።

10፤ ልሰግድለትም በእግሩ ፊት ተደፋሁ። እርሱም፦ “እንዳታደርገው ተጠንቀቅ፤ ከአንተ ጋር የኢየሱስም ምስክር ካላቸው ከወንድሞችህ ጋር አብሬ ባሪያ ነኝ፤ ለእግዚአብሔር ስገድ፤ የኢየሱስ ምስክር የትንቢት መንፈስ ነውና፡” አለኝ።

በብዙዎች እየተመለከ ነው የእኛ ጌታ ድምፃቸው ይገርማል ቃሉ እንደሚል  እንደ ብዙ ሕዝብም ድምፅ፥ እንደ ብዙ ውኃዎችም ድምፅ፥ እንደ ብርቱም ነጐድጓድ ድምፅ ያለ ድምፅ ሰማሁ::  ይህ ህዝብ እኮ አስር ሺ ወይም አንድ ሚልየን ብቻ አይደለም በጣም ብዙ ነው በጌታ ፀድቆ ለአምልኮ የሚቆመው ወደ ሰርጉም የታደመው::ሃሌሉያ እንዴት የሚናፈቅ ቀን ነው በአንድ ድምፅና ቋንቋ ጌታን እንደዚህ ድብልቅ በሚያደርግ አምልኮ ስፍራውን ሁሉ መሙላት?  “ባሪያዎቹ ሁሉ እርሱንም የምትፈሩት ታናናሾችና ታላላቆች ሆይ፥ አምላካችንን አመስግኑ፡” እንደሚል እናመስግነው የበጉ ሰርግ ደርሷልና ሙሽራይቱም እራስዋን አዘጋጅታለች::

ከእርስዋ መዘጋጀት በላይ እርሱ እንዴት እንዳዘጋጃት እንይ:-

ያጌጠና የተጣራ ቀጭን የተልባ እግር ልብስ እንድትጐናጸፍ ተሰጥቶአታል። ቀጭኑ የተልባ እግር የቅዱሳን ጽድቅ ሥራ ነውና።” ይህንን የጽድቅ ስራ የሰራው ማነው እራሱ ነው በመስቀል ላይ ስሙ ይባረክ::  እርሱ እራሱ ነው ቤተክርስቲያኑን ያዘጋጀው አስጊጦና አዲስን የፅድቅ ልብስ አልብሶ::  ሃሌሉያ ጌታ ሊመሰገን ይገባዋል::

ደግሞም “ ‘ወደ በጉ ሰርግ እራት የተጠሩ ብፁዓን ናቸው፡’ ብለህ ጻፍ፡” አለኝ። ደግሞም፦ “ይህ የእግዚአብሔር እውነተኛ ቃል ነው፡” ብፁአን ተብለን ተጠራን እርሱ በሰራው ፅድቅ::

መለአኩ እንዳለው የኢየሱስም ምስክር ካላቸው ከወንድሞችህ ጋር አብሬ ባሪያ ነኝ፤ ለእግዚአብሔር ስገድ፤ አለው ስግደት ለመለአክት አይገባም ለበጉ እንጂ!  የኢየሱስ ምስክር የትንቢት መንፈስ ነውና፡” አለኝ። የእየሱስ መንፈስ ስለእርሱ ይመሰክራል ክብርንም ለእርሱ ያመጣል እንጂ ፍጥረት እንዲቀበል አምልኮን አያደርግም:.  ስለዚህ ከእኛ ጋር መልአክት ጌታን ያመልካሉ::

 “ሃሌ ሉያ፤ ሁሉን የሚገዛ ጌታ አምላካችን ነግሦአልና። አሜን!!!

ራእይ 19: 11-15

11፤ ሰማይም ተከፍቶ አየሁ፥ እነሆም አምባላይ ፈረስ፥ የተቀመጠበትም የታመነና እውነተኛ ይባላል፥ በጽድቅም ይፈርዳል ይዋጋልም።

12፤ ዓይኖቹም እንደ እሳት ነበልባል ናቸው፥ በራሱ ላይም ብዙ ዘውዶች አሉ፥ ከእርሱም በቀር አንድ እንኳ የማያውቀው የተጻፈ ስም አለው፤

13፤ በደምም የተረጨ ልብስ ተጐናጽፎአል፥ ስሙም የእግዚአብሔር ቃል ተብሎአል።

15፤ አሕዛብንም ይመታበት ዘንድ ስለታም ሰይፍ ከአፉ ይወጣል፤ “እርሱም በብረት በትር ይገዛቸዋል፤” እርሱም ሁሉን የሚገዛ የእግዚአብሔርን የብርቱ ቍጣውን ወይን መጥመቂያ ይረግጣል።

ሰማይ ተከፍቶ ዮሃንስ ያየው ማንን ነው?  እየሱስን ነው እርሱም በፈረሱ ላይ ተቀምጧል:-

1.  የታመነና 

2.  እውነተኛ ይባላል፥ 

3.  በጽድቅም ይፈርዳል 

4.  ይዋጋልም

5.  ዓይኖቹም እንደ እሳት ነበልባል ናቸው፥ 

6.  በራሱ ላይም ብዙ ዘውዶች አሉ፥ 

7.  ከእርሱም በቀር አንድ እንኳ የማያውቀው የተጻፈ ስም አለው፤

8.  በደምም የተረጨ ልብስ ተጐናጽፎአል፥ 

9.  ስሙም የእግዚአብሔር ቃል ተብሎአል።

ይህ እውነተኛና የታመነው በጽድቅም የሚፈርደው ጌታ ይዋጋል::  እየሄደ ያለው ወደ ጦርነት ቢሆንም ቅሉ እንደጦረኛ የታጠቀው መሳሪያ የለውም:: ታድያ በምን ይዋጋል?  መልሱ በቃሉ ነው::  አሕዛብንም ይመታበት ዘንድ ስለታም ሰይፍ ከአፉ ይወጣል::  የጌታ ስም ማነው ብንል? ስሙም የእግዚአብሔር ቃል ተብሎአል።  

ልብሱ በደምየተረጨ እንደሆነ ይነግረናል የማን ደም ይሆን ገና ጦርነቱ አልተጀመረ? የራሱ ይሆን? የሚገርመው አስከትቶ የመጣውን ጦር ስናይ:- በሰማይም ያሉት ጭፍራዎች ነጭና ጥሩ ቀጭን የተልባ እግር ልብስ ለብሰው በአምባላዮች ፈረሶች ተቀምጠው ይከተሉት ነበር። እነሱም መሳሪያ አልያዙም::  ምን አይነት ዘመቻ ነው?  በጉ ብቻውን በቂ ነው ተከታዮቹ መዋጋትም አያስፈልገንም ድሉን ከእርሱ ጋር ማጣጣም እንጂ!!  በነበልባል አይኖቹ እያየ ፍርድን እዛው ይሰጣል እርሱ የታገሰው ሰዎች እንዲድኑ ነበረ::

በራሱ ላይ ብዙ ዘውድን የጫነውጌታ ድል የሚነሳና ፃድቅ ጌታ ነውክብር ይሁንለት!!

ራእይ 19: 16-21

16፤ በልብሱና በጭኑም የተጻፈበት፦ “የነገሥታት ንጉሥና የጌታዎች ጌታ፡” የሚል ስም አለው።

:9፤ በፈረሱም የተቀመጠውን ጭፍራዎቹንም ይወጉ ዘንድ አውሬውና የምድር ነገሥታት ጭፍራዎቻቸውም ተከማችተው አየሁ።

20፤ አውሬውም ተያዘ በእርሱም ፊት ተአምራትን እያደረገ የአውሬውን ምልክት የተቀበሉትን ለምስሉም የሰገዱትን ያሳተ ሐሰተኛው ነቢይ ከእርሱ ጋር ተያዘ፤ ሁለቱም በሕይወት ሳሉ በዲን ወደሚቃጠል ወደ እሳት ባሕር ተጣሉ።

21፤ የቀሩትም በፈረስ ላይ ከተቀመጠው ከአፉ በሚወጣው ሰይፍ ተገደሉ፤ ወፎችም ሁሉ ከሥጋቸው ጠገቡ።

የፍጥረት ድፍረት ይገርማል ከእየሱስ ጋር ለመዋጋት ማሰባቸው!!  እርሱ ግን ከአፉ በሚወጣው ሰይፍ ተዋጋ ተገደሉም::  በቁጥር 12፤ ዓይኖቹም እንደ እሳት ነበልባል ናቸው፥ በራሱ ላይም ብዙ ዘውዶች አሉ፥ ከእርሱም በቀር አንድ እንኳ የማያውቀው የተጻፈ ስም አለው፤ በዚህ ክፍል ደግሞ ጌታችን በልብሱና በጭኑም የተጻፈበት፦ “የነገሥታት ንጉሥና የጌታዎች ጌታ፡” የሚል ስም አለው።  ይህንን ስም ስም ነው ብለው ሌሎች ላያውቁት ይችላሉ እኛ ግን ህዝቦቹ ይህንን ስም እናውቃለን እርሱ የነገሥታት ንጉሥና የጌታዎች ጌታ ነው::

ሃሌሉያ!!!!!

ንጉሳችን ታላቁን ፍርድ እዚህ ስፍራ ላይ ሲያደርግ  እናያለን::  የዚህ ሁሉ ውጥንቅጥ ፈጣሪ  የሆነው አውሬውም ተያዘ በእርሱም ፊት ተአምራትን እያደረገ የአውሬውን ምልክት የተቀበሉትን ለምስሉም የሰገዱትን ያሳተ ሐሰተኛው ነቢይ ከእርሱ ጋር ተያዘ፤ ሁለቱም በሕይወት ሳሉ በዲን ወደሚቃጠል ወደ እሳት ባሕር ተጣሉ።  የዚህ ሁሉ ሰው መጥፋት ምክንያት ይህ አውሬ ነው:: ጌታችንም ይህንን ጠላት ከነህይወቱ ወደ እሳት ይጥለዋል ልንፈራው ሳይሆን ፍርዱን እንደሚያገኝ አውቀን በድፍረት እንመላለስ::  ጠላት ተሸንፏል የነገስታት ንጉስ ነግሷል:::

አሜን ክብር ይሁንለት!!!

ራእይ 20: 1-3

1፤ የጥልቁንም መክፈቻና ታላቁን ሰንሰለት በእጁ የያዘ መልአክ ከሰማይ ሲወርድ አየሁ።

2፤ የቀደመውንም እባብ ዘንዶውን እርሱም ዲያብሎስና ሰይጣን የተባለውን ያዘው፥

3፤ ሺህ ዓመትም አሰረው፥ ወደ ጥልቅም ጣለው አሕዛብንም ወደ ፊት እንዳያስት ሺህ ዓመት እስኪፈጸም ድረስ በእርሱ ላይ ዘግቶ ማኅተም አደረገበት፤ ከዚያም በኋላ ለጥቂት ጊዜ ይፈታ ዘንድ ይገባዋል።

የሚገርመው ነገር አንድ መልአክ ነው እባብ ዘንዶውን እርሱም ዲያብሎስና ሰይጣንን የያዘውና ያሰረው ብዙ ግርግር አላስፈለገም::  ስለያዘው መልአክም ምንም መግለጫና ስልጣኑን ነገር ሲነገር አናይም ስልጣን ያለው ወይም ታላቅ መልአክ አይደለም የመጣው::  ጊዜው ሲደርስ እንደዚህ በቀላል ይያዛል ለእግዚአብሔር አቻ ወይም እኩያ አይደለም ሰይጣን ፍጥረት ነው ስለተለቀቀ እንጂ ዓለምን ያመሰው ይህንን ያህል የወደደውን ለማድረግ ስልጣን ስላለው አይደለም::  ከአዳም የወሰደው ስልጣን ሁሉ ተወስዶበታል በሁለተኛው አዳም:: መልአኩም ያደረገበትን ስናይ:- 

–  ሺህ ዓመትም አሰረው፥ 

–  ወደ ጥልቅም ጣለው 

–  አሕዛብንም ወደ ፊት እንዳያስት ሺህ ዓመት እስኪፈጸም ድረስ በእርሱ ላይ ዘግቶ ማኅተም አደረገበት፤ 

–  ከዚያም በኋላ ለጥቂት ጊዜ ይፈታ ዘንድ ይገባዋል።

ይህንን ሁሉ ያደረገበት አንድ መልአክ ነው::  ጊዜው ሲደርስ ባይፈታው እራሱን እንኳን ነፃ የማያወጣ ተራ ፍጥረት ነው::  የሚደረግበት ነገር ደስ ይላል መታሰር ወደ ጥልቅ መጣል::  እርሱ የሚያውቀው ማሳት ነው ይሄውም  አቅም ከእርሱ ተወሰደበት::  ተዘግቶበት ማኅተምም ተደረገ መልሶ እንዳያስት::  ሽንገላው ከሄዋን አንስቶ እስከዛሬ የሰውን ልጅ አሰቃይቷል ከእግዚአብሔርም ጋር አጣልቷልና ይህ የተደረገበት ይገባዋል::

እዚህ ስፍራ እባቡ ሲታሰር እርሱ እየሾመ ና የላካቸው ከውሃ የወጣው አውሬና ህዝብን ሁሉ ተአምራት እያደረገ ያሳተስ ነብይ በህይወት የነበሩ ናቸውና ከነህይወታቸው ወደ እሳት ባህር ጌታ እንደጣላቸው ቅጣታቸውንም እንዳገኙ በምዕራፍ 19 አይተናል::

ይህ ሁሉ ዝግጅት ጌታ በምድር አንድሺ አመት ስለሚነግስ ነው::  ጠላት ምንም እድል የሌለው የተሸነፈ ኪሳራን የተቀዳጀ ፍጥረት ነው:: የእኛ ጌታ ግን በዙፋኑ ላይ ከብሮ ነገሮችን ሁሉ ባቀደው መሰረት እየተገበረ ያለ ንጉስ ነው::  ስሙ ከዘላለም እስከ ዘላለም ከፍ ይበል::   በምድርም ከህዝቡ ጋር ይነግሳል::  አሜን!!

ራእይ 20: 4-6

4፤ ዙፋኖችንም አየሁ፥ በእነርሱም ላይ ለተቀመጡት ዳኝነት ተሰጣቸው፤ ስለ ኢየሱስም ምስክርና ስለ እግዚአብሔር ቃል ራሶቻቸው የተቈረጡባቸውን ሰዎች ነፍሳት፥ ለአውሬውና ለምስሉም ያልሰገዱትን ምልክቱንም በግምባራቸው በእጆቻቸውም ላይ ያልተቀበሉትን አየሁ፤ ከክርስቶስም ጋር ሺህ ዓመት ኖሩና ነገሡ።

ራእይ 20:5፤ የቀሩቱ ሙታን ግን ይህ ሺህ ዓመት እስኪፈጸም ድረስ በሕይወት አልኖሩም። ይህ የፊተኛው ትንሣኤ ነው።

ራእይ 20:6፤ በፊተኛው ትንሣኤ ዕድል ያለው ብፁዕና ቅዱስ ነው፤ ሁለተኛው ሞት በእነርሱ ላይ ሥልጣን የለውም፥ ዳሩ ግን የእግዚአብሔርና የክርስቶስ ካህናት ይሆናሉ ከእርሱም ጋር ይህን ሺህ ዓመት ይነግሣሉ።

ህይወታቸውን በጌታ ምክንያት ያጡት ከእርሱ ጋር እንዲኖሩ ይነሳሉ::  እነዚህ ሰዎች ቢኖሩ 80 ወይም ግፋ ቢል 120 ዓመት ነበረ ህይወታቸውን ጠላት ባያጠፋው ኖሮ ጌታ ግን የተሻለ እድል ሰጣቸውና ለአንድ ሺ ዓመት ከእርሱ ጋር ይኖራሉ::  መነሳት ብቻ አይደለም በ2:26-27፤ ድል ለነሣውና እስከ መጨረሻም ሥራዬን ለጠበቀው እኔ ደግሞ ከአባቴ እንደ ተቀበልሁ በአሕዛብ ላይ ሥልጣንን እሰጠዋለሁ፥ በብረትም በትር ይገዛቸዋል፥ እንደ ሸክላ ዕቃም ይቀጠቀጣሉ፤ እንደቃሉ ስልጣንም ይሰጣቸዋል::

ሌሎቹ ሙታን ግን በዚህ ጊዜ አይነሱም:: 

ይህ ፊተኛው ትንሳኤ በእየሱስ ምክንያት ያለፉት የሚነሱበት ነው ካህናትም ይሆናሉ ይላል ምክንያቱም ስለ ኢየሱስም ምስክርና ስለ እግዚአብሔር ቃል ራሶቻቸው የተቈረጡባቸውን ሰዎች ነፍሳት፥ ለአውሬውና ለምስሉም ያልሰገዱትን ምልክቱንም በግምባራቸው በእጆቻቸውም ላይ ያልተቀበሉት ናቸውና::

እስከመጨረሻው መፅናት ይሁንልን::

ራእይ 20: 7-10

7፤ ሺሁም ዓመት ሲፈጸም ሰይጣን ከእስራቱ ይፈታል፥

8፤ በአራቱም በምድር ማዕዘን ያሉትን አሕዛብ፥ ጎግንና ማጎግን፥ እንዲያስታቸው ለሰልፍም እንዲያስከትታቸው ይወጣል፤ ቍጥራቸውም እንደ ባሕር አሸዋ የሚያህል ነው።

9፤ ወደ ምድርም ስፋት ወጡ የቅዱሳንንም ሰፈርና የተወደደችውን ከተማ ከበቡ፤ እሳትም ከሰማይ ከእግዚአብሔር ዘንድ ወርዳ በላቻቸው።

10፤ ያሳታቸውም ዲያብሎስ አውሬውና ሐሰተኛው ነቢይ ወዳሉበት ወደ እሳቱና ወደ ዲኑ ባሕር ተጣለ፥ ለዘላለምም እስከ ዘላለም ቀንና ሌሊት ይሣቀያሉ።

የሺ ዓመቱ መንግስት የሚመራው በጌታ እየሱሰ ነው::  ሰይጣንም ታስሯል ሰው ሁሉ በነፃነት ያለ ተፅኖ ጌታውን እያመለከ በሰላም የሚኖርበት ዘመን ነው::  ልክ ሰይጣን ሲፈታ የባከነውን ጊዜ ማካካስ የፈለገ ይመስላል::  ከምኔው የሚከተለው ሰራዊት መለመለ::  በምድር ላይ የነበራት ሰዎች እኮ ከታላቁ መከራ የመጡ ናቸው ህይወታቸውን ሳይሰስቱ በሞት ያከበሩት ነበሩ::  ትውልዳቸው ምንም እንኳን በዚህ እግዚአብሔርን በማወቅ ቢያድግም ወደ ክፉ የሚገፋው ጠላት ባይኖርም እንኳን ይኸው ከጠላት ጋር ለመግጠም ጊዜም አልወሰደበትም:: ቍጥራቸውም እንደ ባሕር አሸዋ የሚያህል ነው ይላል። እንዴት እንደዚህ ሊሆን ቻለ? የሰው ክፋት ውስጡ ነው ማለት ነው:: ይግርማል!

ይህም በጠላት የሚመራ ሰራዊት የቅዱሳንን ሰፈርና የተወደደችውን ከተማ ከበቡ፤ እሳትም ከሰማይ ከእግዚአብሔር ዘንድ ወርዳ በላቻቸው። እግዚአብሔር ላይ መፍረድ አይቻልም ምን ማድርእግ ይቻላል ይህ ሁሉ ህዝብ እንደገና በጠላት ተታለለ::  በደሙ አጥቦ መንፈሱን ሰቶ ቤተክርስቲያንን ነበረ በምድር ላይ እንድትኖር የፈቀደው ታድያ ከመቼው የሰው ልጅ ጌታውን ጥሎ ከጠላቱ ጋር አበረ?!

ፍርዱ በሰዎቹ ላይ ብቻ ሳይሆን ባሳታቸውም ላይ ነበረ::  ያሳታቸውም ዲያብሎስ አውሬውና ሐሰተኛው ነቢይ ወዳሉበት ወደ እሳቱና ወደ ዲኑ ባሕር ተጣለ፥ ለዘላለምም እስከ ዘላለም ቀንና ሌሊት ይሣቀያሉ።

የጠላት ፍፃሜ በእሳት ባህር መኖር ነው ፍርዱንም ያገኛል::  አምላካችን ለዘላለም ይነግሳል!  ክብር ይሁንለት!

ራእይ 20:11፤ ታላቅና ነጭ ዙፋንን በእርሱም ላይ የተቀመጠውን አየሁ፥ ምድርና ሰማይም ከፊቱ ሸሹ ስፍራም አልተገኘላቸውም።

ይህ ዙፋን ታላቅ የተባለበት ምክንያት ከዚህ የሚበልጥ ስልጣን እንደሌለ ለማሳየት ሲሆን ነጭ መሆኑ ደግሞ ንፁህነቱንና ቅድስናውን ያሳያል::  የእኛ ጌታ በጽድቅ ይዳኛል ዳኝነቱም እንከን የለውም::  ለምን ምድርና ሰማይም ከፊቱ ሸሹ ስፍራም አልተገኘላቸውም?  ከሱ ፊትስ ወዴት ተሸሽቶ መደበቅ ይቻላል? 

ዙፋን የተዘረጋው በክርስቶስ ለምናምነው አይደለም ለማያምኑት ነው የእኛ ኃጥያት አንድ ጊዜ በክርስቶስ ላይ ሆነ::  በልጁ የሚያምን አይፈረድበትም ያላመነው ግን ይፈረድበታል::  ይህ ማለት ግን ያለምንም ኢንቨንተሪ ወደ መንግስቱ ይገባል ማለት አይደለም እንዴት እንዳገለገልን ጌታ ይመዝናል ስራችንን::  በክርስቶስ የፍርድ ወንበር ፊት እንቆማለን ለሽልማት::  ለሰባቱ አብያተ ክርስትያናት በተፃፈው ክፍል ላይ ድል ለነሳ የተለያየ ሽልማት እንዳለ እናያለን::  ይህንን ደግሞ ጳውሎስ በአንደኛም በሁለተኛውም የቆሮንቶስ መልክቱ ነግሮናል::  እንዴት ነው ይህንን ጌታ እያገለገልን ያለነው?  ዛሬ እድሉ እያለን ምን እየሰራን ነው?

1 ቆሮንቶስ 3:12፤ ማንም ግን በዚህ መሠረት ላይ በወርቅ ቢሆን በብርም በከበረ ድንጋይም በእንጨትም በሣርም ወይም በአገዳ ቢያንጽ፥ የእያንዳንዱ ሥራ ይገለጣል፤ 13፤ በእሳት ስለሚገለጥ ያ ቀን ያሳያልና፥ የእያንዳንዱም ሥራ እንዴት መሆኑን እሳቱ ይፈትነዋል።

14፤ ማንም በእርሱ ላይ ያነጸው ሥራ ቢጸናለት ደመወዙን ይቀበላል፤

15፤ የማንም ሥራ የተቃጠለበት ቢሆን ይጎዳበታል፥ እርሱ ራሱ ግን ይድናል ነገር ግን በእሳት እንደሚድን ይሆናል።

2 ቆሮንቶስ 5:10፤ መልካም ቢሆን ወይም ክፉ እንዳደረገ፥ እያንዳንዱ በሥጋው የተሠራውን በብድራት ይቀበል ዘንድ ሁላችን በክርስቶስ በፍርድ ወንበር ፊት ልንገለጥ ይገባናልና።

ጌታ ማስተዋልን ይስጠን ፀጋውንም ያብዛልን! 

ራእይ 20: 12-15

12፤ ሙታንንም ታናናሾችንና ታላላቆችን በዙፋኑ ፊት ቆመው አየሁ፥ መጻሕፍትም ተከፈቱ፤ ሌላ መጽሐፍም ተከፈተ እርሱም የሕይወት መጽሐፍ ነው፤ ሙታንም በመጻሕፍት ተጽፎ እንደ ነበረ እንደ ሥራቸው መጠን ተከፈሉ።

13፤ ባሕርም በእርሱ ውስጥ ያሉትን ሙታን ሰጠ፥ ሞትና ሲኦልም በእነርሱ ዘንድ ያሉትን ሙታን ሰጡ፥ እያንዳንዱም እንደ ሥራው መጠን ተከፈለ።

14፤ ሞትና ሲኦልም በእሳት ባሕር ውስጥ ተጣሉ። ይህም የእሳት ባሕር ሁለተኛው ሞት ነው።

15፤ በሕይወትም መጽሐፍ ተጽፎ ያልተገኘው ማንኛውም በእሳት ባሕር ውስጥ ተጣለ።

የገረመኝ ነገር ሞት በእርሱ ዘንድ ያለውን ሙታን ሰጠ ማለቱ ነው:: ሞትም ስፍራ አለው ማለት ነው ሙታንን የሚያስቀምጥበት?  ሲኦል እሺ ይስጥ ባህርም እሺ የሞት ግን እንደዚህ መሆኑ ገርሞኛል:: 

የነጩ ዙፋን ፍርድ ክርክር የለውም ስሙ በህይወት መጽሐፍ ያልተገኘ ሁሉ ይፈረድበታል::  በክርስቶስ ላለነው ፍርድ የለብንም በአባትና በመልአክቱ ፊት እመሰክራለሁኝ እንዳለን የምንፈራው ምን እሆን ይሆን ብሎ የሚያስብለን ነገር የለም::  የፍርድ ቀን እንዳለ ጌታምነግሮን የለም? በማቴዎስ 11:22፤ ነገር ግን እላችኋለሁ፥ በፍርድ ቀን ከእናንተ ይልቅ ለጢሮስና ለሲዶና ይቀልላቸዋል።

ሞትና ሲኦልም በእሳት ባሕር ውስጥ ተጣሉ። ሞት ማለት ከህይወት መለየት ብቻ ሳይሆን እራሱን የያዘ ማንነት ያለው ነው ማለት ነው::  ሲኦል ማለት እራሱ እሳት ያለበት ቦታ አይደለም ማለት ነው?  እንደገና ወደ እሳት ባህር የሚጣለው::  ይህም የእሳት ባሕር ሁለተኛው ሞት ነው።

ስሙ በህይወት መጽሐፍ ላይ ያልተገኘው ሁሉ ወደ እሳት ባህር ነው የሚጣለው::  አይዘገንንም?  ዛሬ ቀን ሳለ ለጌታ ሰዎችን እንድንዋጅ ለክብሩ በወንጌል እንድንደርስ ጌታ ይርዳን::  ምርኮ ለጌታ በእኛ ውስጥ ይምጣለት::  መናጠቅ ይሁን ዛሬ!

ጌታ ሆይ የሰዎችን ልብ እንደ ሊድያ ልብ ከፍተህ ስጠን!  እየሱስ በፍጥረት ሁሉ ዘንድ ይሰበክ ሲኦል ይክሰር ዛሬ

አሜን!

ራእይ 21: 1-8

1፤ አዲስ ሰማይንና አዲስ ምድርንም አየሁ፥ ፊተኛው ሰማይና ፊተኛይቱ ምድር አልፈዋልና፥ ባሕርም ወደ ፊት የለም።

2፤ ቅድስቲቱም ከተማ አዲሲቱ ኢየሩሳሌም፥ ለባልዋ እንደ ተሸለመች ሙሽራ ተዘጋጅታ፥ ከሰማይ ከእግዚአብሔር ዘንድ ስትወርድ አየሁ።

3፤ ታላቅም ድምፅ ከሰማይ፦ “እነሆ፥ የእግዚአብሔር ድንኳን በሰዎች መካከል ነው ከእነርሱም ጋር ያድራል፥ እነርሱም ሕዝቡ ይሆናሉ እግዚአብሔርም እርሱ ራሱ ከእነርሱ ጋር ሆኖ አምላካቸው ይሆናል፤

4፤ እንባዎችንም ሁሉ ከዓይኖቻቸው ያብሳል፥ ሞትም ከእንግዲህ ወዲህ አይሆንም፥ ኀዘንም ቢሆን ወይም ጩኸት ወይም ሥቃይ ከእንግዲህ ወዲህ አይሆንም፥ የቀደመው ሥርዓት አልፎአልና፡” ብሎ ሲናገር ሰማሁ። 

7፤ ድል የሚነሣ ይህን ይወርሳል አምላክም እሆነዋለሁ እርሱም ልጅ ይሆነኛል።

የአዲስ ሰማይንና አዲስ ምድር መጠቀስ ብዙ ነገርን ይለውጣል::  አዲስ ሲባል ለባልዋ እንደ ተሸለመች ሙሽራ የተዘጋጀ የሚያምርም ነው የምትወርደውም ከእግዚአብሔር ዘንድ ነው::  አዲስ የሚሆነው ምድሩና ሰማዩ ብቻ ሳይሆን አሰራሩም አዲስ ነው::  እራሱ ጌታ ይገኛል:-

እነሆ፥ የእግዚአብሔር ድንኳን በሰዎች መካከል ነው ከእነርሱም ጋር ያድራል፥  በሙሴ ዘመን ነው ድንኳን የነበረው እግዚአብሔር ብቻውንእንጂ በሰፈሩ መካከል አልነበረም በእሳትና በደመና ይመራቸው ነበር::  የሚነጋገረውም ከሙሴ ጋር ብቻ ነበር::  ይህ ግን ተቀየረና ሁላችንንም ህዝቡ አደረገን::

እነርሱም ሕዝቡ ይሆናሉ እግዚአብሔርም እርሱ ራሱ ከእነርሱ ጋር ሆኖ አምላካቸው ይሆናል፤

ከእኛ ጋር መሆኑ የሚታወቀው:- 

– እንባዎችንም ሁሉ ከዓይኖቻቸው ያብሳል፥ 

– ሞትም ከእንግዲህ ወዲህ አይሆንም፥ 

– ኀዘንም ቢሆን ወይም 

– ጩኸት ወይም 

– ሥቃይ ከእንግዲህ ወዲህ አይሆንም፥ 

– የቀደመው ሥርዓት አልፎአልና፡

– መገኘት የማይገባውም አይገኝም:-የሚፈሩና የማያምኑ የርኵሳንም የነፍሰ ገዳዮችም የሴሰኛዎችም የአስማተኛዎችም ጣዖትንም የሚያመልኩ የሐሰተኛዎችም ሁሉ ዕድላቸው በዲንና በእሳት በሚቃጠል ባሕር ነው፤ ይኸውም ሁለተኛው ሞት ነው።

ይህንን ሁሉ የሚያስቀር አዲስ አሰራር ጌታ ያመጣል:: መንግስተ  ሰማይን ልዩ የሚያደርገው በወርቅ መሰራቱ ወይም የሳሩና የአትክልቱ ማማር ሳይሆን የእግዚአብሔር መገኘት ነው:: የተሰጠንም የተስፋ ቃል ድል የሚነሣ ይህን ይወርሳል አምላክም እሆነዋለሁ እርሱም ልጅ ይሆነኛል። አሮጌው አልፏል!  ይህንን ሁሉ የሚያወርሰን በልጁ ስለዋጀን እንጂ የተገባን ሆነን አይደለም::  ስሙ ይባረክ! 

ራእይ 21: 9-27

10-11፤ በመንፈስም ወደ ታላቅና ወደ ረጅም ተራራ ወሰደኝ፥ የእግዚአብሔርም ክብር ያለባትን ቅድስቲቱን ከተማ ኢየሩሳሌምን ከሰማይ ከእግዚአብሔር ዘንድ ስትወርድ አሳየኝ፤ ብርሃንዋም እጅግ እንደ ከበረ ድንጋይ እንደ ኢያሰጲድ ድንጋይ ሆኖ እንደ ብርሌ የጠራ ነበረ፤

22፤ ሁሉንም የሚገዛ ጌታ አምላክና በጉ መቅደስዋ ናቸውና መቅደስ በእርስዋ ዘንድ አላየሁም።

23፤ ለከተማይቱም የእግዚአብሔር ክብር ስለሚያበራላት መብራትዋም በጉ ስለ ሆነ፥ ፀሐይ ወይም ጨረቃ እንዲያበሩላት አያስፈልጓትም ነበር።

24፤ አሕዛብም በብርሃንዋ ይመላለሳሉ፥ የምድርም ነገሥታት ክብራቸውን ወደ እርስዋ ያመጣሉ፤

25፤ በዚያም ሌሊት ስለሌለ ደጆችዋ በቀን ከቶ አይዘጉም፥

27፤ ለበጉም በሆነው በሕይወት መጽሐፍ ከተጻፉት በቀር፥ ጸያፍ ነገር ሁሉ ርኵሰትና ውሸትም የሚያደርግ ወደ እርስዋ ከቶ አይገባም።

ስፍራን ላዘጋጅ እሄዳለሁ እንዳለን አዘጋጅቶ እርሱ ባለበት እንድንገኝ  ይወስደናል::  ቅድስቲቱ ከተማ ኢየሩሳሌም አሁን ማሰብ ከምንችለው በላይ ልዮ ቦታ ነው ነገር ግን የምንደነቀው በስፍራው ማማር ሳይሆን በእግዚአብሔር ክብር ነው:: ለከተማይቱም የእግዚአብሔር ክብር ስለሚያበራላት መብራትዋም በጉ ስለ ሆነ፥ ፀሐይ ወይም ጨረቃ እንዲያበሩላት አያስፈልጓትም ነበር። ምን አይነት ስፍራ ነው? ክብሩ የሚያበራበት?!  በጉ መብራት የሆነበት ስፍራ!  የተፈጥሮው መብራቶችም አያስፈልጉም በዚያ ቀንና ለሊት የለም::  ሁሉንም የሚገዛ ጌታ አምላክና በጉ መቅደስዋ ናቸውና መቅደስ በእርስዋ ዘንድ አላየሁም። መኖርያችን እርሱ ነው!! በምንም ነገር ላይ ጥገኛ አንሆንም::

ይህ ስፍራ ሁሉ አዲስ የሆነበት ነው:: ድካም የለም ለሊት የተሰጠን ስጋችን እንንዲያርፍ ነው ያኔ ግን ለአሰራሩ እንዲመች አድርጎ ይለውጠናል ከመቅጽበት ያንን የማይሞተውን እንለብሳለን::  ሃሌሉያ!!!

በምድር ወርቅና የከበሩ ድንጋዮች በግራም ይገዛሉ እዛ ስንሄድ በሮቹ ከአንድ ወጥ እንቁ የተሰሩ እንዲሁም ከወርቅ የተሰራ ነው:: ወርቁና እንቁውን የሚያስንቅ የእግዚአብሔር ክብር ግን ገና ያስደንቀናል::

በዛም መገኘት የሚችሉት ለበጉም በሆነው በሕይወት መጽሐፍ ከተፃፉት  በቀር፥ ጸያፍ ነገር ሁሉ ርኵሰትና ውሸትም የሚያደርግ ወደ እርስዋ ከቶ አይገባም።  ይህንን ቀን እናፍቃለሁ!!

 በክብሩ እየሰከሩ ማምለክ ብቻ ያለበት ስፍራ ማንም ማንንም የማያይበት የሁሉ አይኖች በጌታቸው ላይ የሚሆንበት ሰይጣንና ሰራዊቱ የሌሉበት በሰላምና በእረፍት  የተሞላ ስፍራ:.  ለቅሶ ህመም ችግር የሌለበት ስፍራ ለምርጦቹ ያዘጋጀው ስፍራ::  ዋው ምን እንላለን ጌታ ሆይ ተመስገን አሁን  የምናልፍበትን ውጣ ውረድ ሁሉ የሚያስረሳ ተስፋ ስለሰጠኸን ተባረክ::

ስምህም ይወደስ!!

ራእይ 22: 1-2

1፤ በአደባባይዋም መካከል ከእግዚአብሔርና ከበጉ ዙፋን የሚወጣውን እንደ ብርሌ የሚያንጸባርቀውን የሕይወትን ውኃ ወንዝ አሳየኝ።

ራእይ 22:2፤ በወንዙም ወዲያና ወዲህ በየወሩ እያፈራ አሥራ ሁለት ፍሬ የሚሰጥ የሕይወት ዛፍ ነበረ፥ የዛፉም ቅጠሎች ለሕዝብ መፈወሻ ነበሩ።

ዮሃንስ መቼም በተቻለ መጠን በምድርኛ ቋንቋ አዲሲቱን ስፍራ ሊገልጥልን ሞክሯል:: ከዙፋኑ መካከል የህይወት ውሃ ይወጣል::  ይህም ውሃ የህይወትን ዛፍ ያጠጣል የዛፉም ቅጠሎች ለሕዝብ መፈወሻ ነበሩ::  ይህ የህይወት ዛፍ ነበረ የመባረራችን ምንጭ አሁን ግን ለመፈወሻነት የሚውል ሆነ::  አዳምና ሄዋን ከተባረሩ በኃላ እንዳይደርሱበት ይጠበቅ ነበር ከዚህ በኃላ ግን አይጠበቅም::  ምንም እንኳን የሰዓት  ኮንሰፕት ባይኖርም ፍሬውን ግን ይህ ዛፍ በየወሩ ይሰጣል::  የሚያፈራውም አስራ ሁለት ነው::  በዛ ስፍራ የሚሆነው የሰው ቁጥር ግን ከመቆጠር የሚበልጥ ነው:: ምናልባትም አገልግሎቱ ሌላ ይሆን ይሆናል::  ቅጠሉ ለመፈወሻ ይሆናል እዚህ ስፍራ ደግሞ ህመም የለም ስቃይ የለም::  ስንሄድ እንረዳዋለን::  ሁሉ የሚደንቅ እንደሚሆን እርግጠኛ ነኝ::

እንኳን እርሱ አባት ሆነን!

ራእይ 22: 3-4

3፤ ከእንግዲህም ወዲህ መርገም ከቶ አይሆንም። የእግዚአብሔርና የበጉም ዙፋን በእርስዋ ውስጥ ይሆናል፥ ባሪያዎቹም ያመልኩታል፥ ፊቱንም ያያሉ፥

4፤ ስሙም በግምባሮቻቸው ይሆናል።

አዲሲቱ እየሩሳሌም ውስጥ መርገም ከቶ የለም::  መርገሙማ በምድርበክርስቶስ ደም ታጥቦ ቀረልን ይህች ስፍራ ከዛ የነፃች ናት::  አዲሱን ልብስ ለብሰን በእርሱ ስራ ተውበን የምንኖርበት ስፍራ ነው::  

ይህ ስፍራ የእግዚአብሔርና የበጉም ዙፋን በእርስዋ ውስጥ ይሆናል ሌላ መቅደስም የለም ሌላ ብርሃንም አያስፈልግም ጨለማና መከራ ስቃይ እንባ በዚህ ስፍራ የላቸውም::  እርሱ በዙፋኑ ላይ ነው ይመለካል ይከበራል!

ሽልማታችን የሚሆነው፥ ፊቱንም እያየንማምለካችን ነው:: አቤት እንዴት ያለ ቀን ነው ያ ቀን?!  የናፈቅነውን ጌታ ፊት ለፊት እያዩ በመደነቅ ማምለክ!!  አሜን ሃሌሉያ!

በዚህ ብቻ አያበቃም ስሙም በግምባሮቻችን ይሆናል።  አሜን ስሙን በግንባራችን ለሚፅፈው ክብር ይሁን::  ያለህን ጠብቅ በቶሎ እመጣለሁ ነው ጌታ የሚለውና ዕለት ዕለት በመንፈስ ቅዱስ በመሞላት እርሱን እንጠባበቅ:: ሽልማታችንን እናገኛለን::  በፊቱ ከመሆን የሚበልጥ ምን ይኖር ይሆር ይሆን?!

ላሰበን ጌታ ክብር ይሁን!!! የሚጠብቀን የከበረ ህይወት ነውና ዛሬ የከበበንን እያራገፍን ወደፊት እንግፋ የዝች ምድር ነገር ማብቅያ አለው ለዘላለም አይደለም::

ራእይ 22:5፤ 

ከእንግዲህም ወዲህ ሌሊት አይሆንም፥ ጌታ አምላክም በእነርሱ ላይ ያበራላቸዋልና የመብራት ብርሃንና የፀሐይ ብርሃን አያስፈልጋቸውም፤ ለዘላለምም እስከ ዘላለም ይነግሣሉ።

ይህ የምንወርሰው ስፍራ እንዴት ያለ ነው? 

*  መርገም የሌለበት – የምድር ኩነኔ የለም

*  የእግዚአብሔርና የበጉም ዙፋን በእርስዋ ውስጥ ይሆናል – ፍጹም የሆነ አስተዳደር ይሆናል

*  ባሪያዎቹም ያመልኩታል፥  አምልኮ ይበዛል

*  ፊቱንም ያያሉ፥ ፊቱን እያየን እንለመልማለን 

*  ስሙም በግምባሮቻቸው ይሆናል – የርሱ መሆናችን ይታወቃል

*  ለሊት የሌለበት – ጨለማውን ገፎ አስወግዶታል::

*  አምላካችን የሚያበራበት – እርሱ እራሱ ያበራልና አርቲፊሻል ወይም የተፈጥሮም ብርሃናት አያስፈልጉም::

*  ለዘላለም የምንነግስበት – ለመንግስቱ ፍፃሜ የለውምና ልጆቹ አብረን እንነግሳለን::

አቤት እንዴት ድንቅ ነው?! አሰራሩ ሁሉ ከአእምሮ በላይ ነውና ጌታን እንባርክ:: በፊቱ የከበርንበት መክበር የምድርን ነገር ሁሉ የሚያስረሳና ወደ አምልኮ የሚወስድ ነው::  ዕለት ዕለት በመንፈስ ቅዱስ ተሞሉ እንዳለን ዛሬም አባት ሆይ ሙላን ወደ ፀጋ ዙፋንህም እንቀርባለን ፀጋን እንቀበል ዘንድ በፀጋህ ሁሉ ሙላን::  ስትጠራን የተዘጋጀን እንሁን ከራሳችን አልፈን ሌላውን የምናዘጋጅ አድርገን::  አሜን!

ራእይ 22: 6-7

6፤ እርሱም፦ “እነዚህ ቃሎች የታመኑና እውነተኛዎች ናቸው፥ የነቢያትም መናፍስት ጌታ አምላክ በቶሎ ሊሆን የሚገባውን ነገር ለባሪያዎቹ እንዲያሳይ መልአኩን ሰደደ።”

7፤ “እነሆም፥ በቶሎ እመጣለሁ። የዚህን መጽሐፍ ትንቢት ቃል የሚጠብቅ ብፁዕ ነው፡” አለኝ።

በዚህ መጽሐፍ የተፃፈው ሁሉ የታመነና  እውነተኛ ነው::ይህም የትንቢት መንፈስ መልአኩን ልኮ ለእኛ እንዲፃፍና እንዲደርስ አደረገ::  ይህንን መልክት የላከልን በቶሎ ሊሆን የሚገባውን ነገር  እንድናውቅ ነው::

 ምንም እንኳን መልአኩ በቶሎ ሊሆን የሚገባውን ነገር  እንደሆነ ቢናገርም ክብደት ለመስጠት እራሱ ጌታ በቶሎ እመጣለሁ። የዚህን መጽሐፍ ትንቢት ቃል የሚጠብቅ ብፁዕ ነው፡ ብሎ አለ:: 

ዛሬም መልክቱ ያው ነው ቶሎ እመጣለሁ ቃሌን እያደረጋችሁ ጠብቁኝ ነው::  ጌታ ይመጣል!  ማራናታ!!

ራእይ 22:  8-13

10፤ ለእኔም፦ “ዘመኑ ቀርቦአልና የዚህን መጽሐፍ ትንቢት ቃል በማኅተም አትዝጋው።

11፤ ዓመፀኛው ወደ ፊት ያምፅ፥ ርኵሱም ወደ ፊት ይርከስ፥ ጻድቁም ወደ ፊት ጽድቅ ያድርግ፥ ቅዱሱም ወደፊት ይቀደስ፡” አለ።

12፤ “እነሆ፥ በቶሎ እመጣለሁ፥ ለእያንዳንዱም እንደ ሥራው መጠን እከፍል ዘንድ ዋጋዬ ከእኔ ጋር አለ።

13፤ አልፋና ዖሜጋ፥ ፊተኛውና ኋለኛው፥ መጀመሪያውና መጨረሻው እኔ ነኝ።

ራዕዩን አይቶ ሲጨርስ ዮሃንስ በሰማሁትና ባየሁትም ጊዜ ይህን ባሳየኝ በመልአኩ እግር ፊት እሰግድ ዘንድ ተደፋሁ። እርሱም፦ “እንዳታደርገው ተጠንቀቅ፤ ከአንተ ጋር ከወንድሞችህም ከነቢያት ጋር የዚህንም መጽሐፍ ቃል ከሚጠብቁ ጋር አብሬ ባሪያ ነኝ፤ ለእግዚአብሔር ስገድ፡” አለኝ።

መልአክት ከእኛ ጋር አብረው የሚያገለግሉ ናቸው::  አምልኮ ከሰውም ከመልአክም የሚገባው አምላካችን ብቻ ነው::  ጌታ ደግሞ ደጋግሞ የነገረን ነገር እነሆ፥ በቶሎ እመጣለሁ፥ ለእያንዳንዱም እንደ ሥራው መጠን እከፍል ዘንድ ዋጋዬ ከእኔ ጋር አለ።

እንደ ስራችን የሚከፍለን እራሳችንን ያዳንን ስለሆንን ሳይሆን በእርሱ ምን ያህል ታምነን ኖርንና አገለገልንን ነው ጥያቄው:: በእርሱ ተደግፈን መመላለስ ይሁንልን:: ጌታ እንድንፅናናበት የሚፈልገው መምጣቱን ነው::  ጠላትም ሊያስጥለን የሚፈልገው ይህንኑ ተስፋ ነው::  ጌታ  ካልመጣ ምንድነው ተስፋችን? እርሱ ግን እንዳለን ይመጣል::  ምክንያቱም አልፋና ዖሜጋ፥ ፊተኛውና ኋለኛው፥ መጀመሪያውና መጨረሻው እኔ ነኝ ብሏልና:: ጽድቅን በማድረግ እንቀጥል የዓለም ሐጥያት እያንገሸገሸ ከኃጥያት ኃጥያት በማማረጥ ላይ ነን ጊዜው እየከፋ ነው የሚሄደውና ዓይናችንን በጌታና በመምጣቱ ላይ እናድርግ::  እንዳለን ይመጣል!  እንዲያውም ጊዜው ቀርቧል:: ማራናታ! 

ራእይ 22:14-16

14፤ “ወደ ሕይወት ዛፍ ለመድረስ ሥልጣን እንዲኖራቸው በደጆችዋም ወደ ከተማይቱም እንዲገቡ ልብሳቸውን የሚያጥቡ ብፁዓን ናቸው። 

15፤ ውሻዎችና አስማተኞች ሴሰኛዎችም ነፍሰ ገዳዮችም ጣዖትንም የሚያመልኩት ውሸትንም የሚወዱና የሚያደርጉ ሁሉ በውጭ አሉ።

16፤ “እኔ ኢየሱስ በአብያተ ክርስቲያናት ዘንድ ይህን እንዲመሰክርላችሁ መልአኬን ላክሁ። እኔ የዳዊት ሥርና ዘር ነኝ፥ የሚያበራም የንጋት ኮከብ ነኝ።”

አዳምና ሄዋን ወደ ህይወት ዛፍ እንዳይደርሱ እግዚአብሔር በኪሩብ አስጠበቀው::  በክርስቶስ ለዳነው በበጉ ደም ለታጠብነው ብጹአን ለተባልነው ደግሞ ወደ ሕይወት ዛፍ ለመድረስ ሥልጣን እንዲኖራቸው በደጆችዋም ወደ ከተማይቱም እንድንገባ ተፈቀደልን::  በራሳችን ጽድቅ ሳይሆን በበጉ ስራ ኃጥያታችንም በደሙ ተወግዶ መድረስ ቻልን::

እኛ ወደ ህይወት ዛፍና ወደ አዲሲቱ እየሩሳሌም ስንገባ በውጭ ደግሞ የሚቀሩ አሉ::  ዛሬ በዓለም ሳለን ውሸቱ ሌብነቱ የሚደነቅና የሚበረታታ ነው በእነርሱ ዓይን ቃሉን ለምናውቅ ደግሞ በውጭ እንደሚቀሩ እናውቃለንና ሳንዘናጋ ይህንን የምስራች ወንጌል እንመስክር::

የራዕይን መጽሐፍ በዝችበአንድ አረፍተ ነገር  አፀናው ከእሱ እንደሆነም አረጋገጠልን:- እኔ ኢየሱስ በአብያተ ክርስቲያናት ዘንድ ይህን እንዲመሰክርላችሁ መልአኬን ላክሁ። እኔ የዳዊት ሥርና ዘር ነኝ፥ የሚያበራም የንጋት ኮከብ ነኝ::  ስለመሲህነቱም:- በኢሳይያስ 11:1፤ ከእሴይ ግንድ በትር ይወጣል፥ ከሥሩም ቍጥቋጥ ያፈራል። እንደሚል ቃሉ ይህ መሲህ ስራውንጨርሶ ስፍራም አዘጋጅቶሊወስደን እየተዘጋጀ ነው::

የንጋት ኮከብ:- በዘኍልቍ 24:17፤ አየዋለሁ፥ አሁን ግን አይደለም፤ እመለከተዋለሁ፥ በቅርብ ግን አይደለም፤ ከያዕቆብ ኮከብ ይወጣል፥ ከእስራኤል በትር ይነሣል:: ጊዜው ደርሶ ተገልጧል ጌታችን::

ስሙ ይባረክ!!

ራእይ 22:17-22

17፤ መንፈሱና ሙሽራይቱም፦ “ና፡” ይላሉ። የሚሰማም፦ “ና፡” ይበል። የተጠማም ይምጣ፥ የወደደም የሕይወትን ውኃ እንዲያው ይውሰድ።

20፤ ይህን የሚመሰክር፦ “አዎን፥ በቶሎ እመጣለሁ፡” ይላል።  አሜን፥ ጌታ ኢየሱስ ሆይ፥ ና።

በመንፈስ ቅዱስ ታግዘን እያንዳንዳችን ደግሞም እንደክርስቶስ አካልና ሙሽራ *ና *  እንላለን ::  እርሱ ይምጣልን!

የሚሰማም፦ “ና፡” ይበል። ያልዳነው ጌታን የማያውቀው ሁሉ ይህንን ጥሪ ይጣራ የህይወን ራስ እየሱስን ወደ ልቡም ወደ ምድርም  ይጥራ::  ጌታን የተጠማም ይምጣ፥ የወደደም የሕይወትን ውኃ እንዲያው ይውሰድ::  ይህ የህይወት ራስ እየሱስ ወደ እርሱ ለሚመጡት ሁሉ የህይወትን ውሃ ማንንም ሳይሙርጥና ሳያዳላ ይሰጣል:: ስሙ ይባረክ!

ጌታችን ሆይ ና ብለን ስንጣራ መልሱ፦ “አዎን፥ በቶሎ እመጣለሁ፡” ይላል።  አሜን፥ ጌታ ኢየሱስ ሆይ፥ ና። ማራናታ

ይህንን መጽሐፍ እንዳየነው ብዙ ነገር እንደሚካሄድ አየንበት::  የጌታን ክብርና ግርማ በሰማይም ያለውን አምልኮና ዝግጅት አይተናል::  የእኛ ስራ በጌታ ፀጋ ተደግፈን ዛሬ እንደሚመጣ እየተጠባበቅንና እንዲመጣም እየተጣራን መኖር ፤  ምን ያህል እንደተወደድን አውቀን ጠላታችንን ፀንተን መቃወም፤  ስፍራንም እንዳዘጋጀልን አውቀን ሃሴት ማድረግ ፤  ወንጌልንም ለፍጥረት ሁሉ መስበክ ነው ወደዚህ ጌታ ካልመጡ የሚጠብቃቸው የእሳት ባህር ነውና::  

የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ጸጋ ከሁላችን ጋር ይሁን፤ አሜን።

የራዕይን መጽሐፍ በዚህ አጠናቀናል::

ማራናታ!

የያዕቆብ መልእክት

የያዕቆብ መልእክት 1: 1-4

2-3፤ ወንድሞቼ ሆይ፥ የእምነታችሁ መፈተን ትዕግሥትን እንዲያደርግላችሁ አውቃችሁ፥ ልዩ ልዩ ፈተና ሲደርስባችሁ እንደ ሙሉ ደስታ ቍጠሩት  4፤ ትዕግሥትም ምንም የሚጎድላችሁ ሳይኖር ፍጹማንና ምሉዓን ትሆኑ ዘንድ ሥራውን ይፈጽም።

ክርስትና  ፈተና እንዳለው እየሱስ ቁልጭ አድርጎ ነግሮን ነው የሄደው አልዋሸንም::  የሚፈተነውም እምነታችን ነው!  ሲፈተንም የሚያፈራው ትዕግስትን ነው::  በመከራ መታገስ ምክንያቱም ዓለም ባሰመረችልን መንገድ የምንሄድ አይደለንም እኛ የምንኖርለት የሞተልን ጌታ አለ::  በአጭር መንገድ እየሄድን የማይገባንም እያደረግን ጌታን አናስከብረውም ፈታኙ ይመጣልና ሊነቀንቀንና ሊነቅለን::  በዚህ ውስጥ ዓለማውያን እንደሚያደርጉት እያመቻመችን አንጏዝም እውነትን እንይዛለን::  አልተዋችሁም ያለንንም ጌታ ከምናልፍበት መከራ ይልቅ ልናምነው ይገባል በጌታችን መወራረድ አለብን::  እነሲድራቅ ሚሳቅ እኮ የተጠየቁት መስገድ ነበረ በባእድ አገር ማን እንዳያያቸው ነው?  በሁሉም ላይ የመጣ ነው ብለው አላጎበደዱም ብንጠፋም እንጥፋ እንጂ አንሰግድም ብለው አልጠፉም ያከበሩት ጌታ በእሳት ውስጥ ተገኘ::  በምናልፍበት ነገር ሁሉ ውስጥ መውጫውን ይሰጠናልና በጽድቅ  እንሂድ ምንም ይሁን ምን::  ወንድሞች እንኳን ምናለበት ቢሉን አንስማ::  እምነታችን እየተፈተነ ነውና ያለ እምነት ደግሞ ጌታን ደስ ማሰኘት አይቻልም!! 

ጌታ ሆይ እኔንና ወገኖቼን በምናልፍበት ፈተና ሁሉ የምንጸናበትን ጸጋ ትሰጠን ዘንድ ትግስትም ስራውን  በእኛ ላይ ይፈጽም በአንተ መታመናችን ይታይ!  አሜን!

ይህንን ቃልሳሰላስል ውዬ ውስጤ እያደገ መጣ::  ያዕቆብ  ይህንን መልእክት የጻፈው ለተበተኑ ለአሥራ ሁለቱ ወገኖች፤ ነው::  የተበተኑት በመከራ ነው እርሱ ግን እንደሙሉ ደስታ ቀጠሩት ይላቸዋል!  እንዴት ይቻላል ያስብላል ግን ይቻላል:::  ደስታ ከውጭ በምናየው አይደለም የሚመጣው እሱማ ይመጣል ይሄዳል ሁኔታ በተቀየረ ቁጥር::  እኛ ደስ ሊለን የሚገባው በጌታ ነው በማንነቱ ብቻ!!!  ዓይናችንን ከሁኔታ ላይ እናንሳና በጌታ ላይ እናድርግ  ያኔ የእኛ ነገር ከፍና ዝቅ አይልም::  በሚያጸናው ጌታ ላይ እንጽና!  የዓለምን ስብከት ወደጎን እናድርገው እሱ ለእኛ አይደለም ዓለም እንደሚያስብ አናስብ በአእምሯችን መታደስ እንለወጥ ከዚህ ዓለም አይደለንምና የምድርን ቀመር አንጠቀምም::  ነፍሳችንን እናንቃት በእግዚአብሔር ታመኚ እንበላት የመጣው መከራ እምነታችንን አጥብቆት ይሄዳል እንጂ አዳክሞን አይሄድም::  ጌታ ማስተዋልን ይስጠን::

እምነት ሲፈተን መታመናችን ይበዛል::  ትላንትናን ያሻገረን ዛሬም አለ ብለን እንታመናለን::  ይህ ትዕግስት ምንም እስከማይጎድለን ድረስ ፍጹምና ምሉዓን እስክንሆን ስራውን ይፈጽም ጌታ ሲሰራ እስከመጨረሻው ነው ምክንያቱም  ስራው ግሩምና ድንቅ ነውና::   እምነታችን እንደወርቅ ነጥሮ ይወጣና ለምስጋናም ይሆናል::  እንመነው ብቻ ጌታን::   ጳውሎስና ሲላስ በምሪት መተው የት ነው የተገኙት እስር ቤት በስቃይ ግን ጌታ መጣ አልመጣም? ከእነርሱጋር ተገኝቶ የነሱን ብቻ ሳይሆን በእስር ቤት ያሉትን ሁሉ ፈታ::  ከእኛ ያለፈ ስራ ሊሰራ ሲል እንፍቀድለት ሙልጭልጭ እያልን አናስቸግር እንደበሰለ  ደቀ መዝሙር እንከተለው እርሱ ወደ እረፍት ውሀ ዘንድ  ይመራናል::  ብቻ እንታመን ብልጣብልጥ አንሁን!!  እናስተውል መከራ የለም አይደለም ያለን አይዟችሁ አሸንፌአለሁ እንጂ!  እንበረታታ የደከሙትንም እናበርታ!  

የያዕቆብ መልእክት 1: 5-8

5፤ ከእናንተ ግን ማንም ጥበብ ቢጎድለው፥ ሳይነቅፍ በልግስና ለሁሉ የሚሰጠውን እግዚአብሔርን ይለምን፥ ለእርሱም ይሰጠዋል። 6፤ ነገር ግን በምንም ሳይጠራጠር በእምነት ይለምን፤ የሚጠራጠር ሰው በነፋስ የተገፋና የተነቃነቀ የባሕርን ማዕበል ይመስላልና።7-8፤ ሁለት አሳብ ላለው በመንገዱም ሁሉ ለሚወላውል ለዚያ ሰው ከጌታ ዘንድ አንዳች እንዲያገኝ አይምሰለው።

ጥበብ የጎደለንከሆነ ነው ይህንን ጸሎት መጸለይ ያለብን ግን ጥበብ አልጎደለኝም የሚል ይኖር ይሆን?  ያዕቆብ ጥበብን ለምኑ ሲለን ስለተለማመደው ነው በእየሩሳሌም ያለችውን ቤተክርስቲያን ከሚመሩት አንዱ ነበረ::  በዚህ አገልግሎት ውስጥ  ስንቱን በገደሉበት ቦታ ላይ ማገልገል በደንብ ጥበብ የሚያስፈልገው ቦታ ላይ ነው ያለው::  ሌላው ጳውሎስ አእማዕድ ወደሚሆኑት ሄድኩኝ አህዛብ ምን ማድረግ እንዳለባቸስ ህግን ይጨምሩ ወይስ እኔ የማገለግለው ልክ ነው ብሎ ሲመጣ የመጨረሻውን የጥበብ ንግግር ተናግሮ እኛንም ክህግ ነጻ ያደረገን ይህ ሰው ነው::  እኛና መንፈስ ቅዱድ ይህንን ወስነናል ብሎ ለጣኦት ከተሰዋ ከዝሙት እንድንርቅ ያለው እርሱ ነበር::  ጥበብ ስንል የጊዜውን ነገር አውቀን ውሳኔ ማድረግ ነው እንደ ይሳኮር ልጆች ዘመኑን ያውቁ ነበር እንዲሁም ኢሳያስ እንደሚል የተማረ ምላስ ይሰጣል::  የጥበብ መጀምርያውም እግዚአብሔርን ምመፍራት ነው::  በተለይ ውሳኔ መወሰን የሚቸግረን ከሆነ ሳናመነታ ጥበብን እንጠይቅ እርሱም ሳይታዘበን በልግስና ይሰጠናል::  ያለ ጥበብ የየቀኑን ኑሮ መኖር ከባድ ነው ሁሉነገር ውሳኔ ያስፈልገዋል ነገሮች ጥርት ብለው ሊታዩን ይገባል::  እንግዲህ ዛሬ እንጀምር ጥበብን መጠየቅ መወሰን አቅቶን በተንጠለጠሉብን ነገሮች ሁሉ ላይ እርሱም ጥበብን ይሰጠናል::  ስለ ጥበብ ከመማር ይልቅ መለማመድ ይበልጣልና  አምነን እንጠይቅና እንቀበል::  እራሴን ሳይ በብዙ ያስፈልገኛል::  ጌታ ሆይ ጥበብን በእኔም በወገኖቼም ላይ አድርግ ::  በእየሱስ ስም! አሜን!!

የያዕቆብ መልእክት 1: 9-11

9-10፤ የተዋረደው ወንድም ግን በከፍታው፥ ባለ ጠጋም በውርደቱ ይመካ፤ እንደ ሣር አበባ ያልፋልና። 11፤ ፀሐይ ከትኵሳት ጋር ይወጣልና፥ ሣርንም ያጠወልጋልና፥ አበባውም ይረግፋልና፥ የመልኩም ውበት ይጠፋልና፤ እንዲሁ ደግሞ ባለ ጠጋው በመንገዱ ይዝላል።

መግቢያው ላይ እንደሚናገረው እነዚህ አይሁዶች ተበትነው በስደት ባሉበት ነው ይህ መልክት የተጻፈላቸው::  ባለጠጋ የነበሩ አሁን ደህይተዋል ስለዚህ በምድር ሀብት ላይ በዝቅታቸውም ላይ እንዳይሆን ዓይናቸው እየመከራቸው ነው :: ባለጠጋም ብትሆኑ ያልፋል ደሀም ብትሆኑ ያልፋል ግን ትህትናን ልበሱ ምንም ይሁን ምን የሀብት ደረጃችሁ እንደ እየሱስ ሁኑ እርሱ እኔ በልቤ ትሁት ነኝ አለ ቤት እንኳን አልነበረውም የሰማይና የምድር ፈጣሪ ሆኖ ሳለ::  ከከፍታ ወደዝቅታ ብትወርዱም ሆነ ከዝቅታ ወደ ከፍታ ብትወጡ ይህ በእናንተ ባህሪ ላይ ለውጥ ማምጣት የለበትም ሙሴም በምድር ላይ ካሉት ሰዎች ሁሉ ይልቅ እጅግ ትሑት ሰው ነበረ ይላል ቃሉ የዋህና ትሁት እንድንሆን ጌታ ይፈልጋል:: የዋሆች ብፁዓን ናቸው፥ ምድርን ይወርሳሉና ይላል ቃሉ::

የሀብት ደረጃ በእኛ ላይ ተጽኖ ማምጣት የለበትም ሁሉ እንደ ሳር አበባ ያልፋልና ገንዘብ እንዳይገዛን ነገር ህን መገልገያችን እንደሆነ ብቻ አስበን መገዛት ለሚገባን ለንጉሳችን እንገዛ ሁሉም አላፊ ነውና::  ጠላት በተንኮሉ ከዚህ ሀሳብ አያውጣን ምድርን እንናቅ መንገደኞች ነን እኛ::  በምናልፍበት ዝቅታ ሁሉ እምነታችን ተፈትኖ እየዳበረ እንገስግስ ወዳሰበልን መድረሻ::  የአባቴ ብሩካን ተብለን እንድንጠራ የታመሙትን እንጠይቅበት:  የታሰሩትንም እንጎብኝበት ገንዘባችንን በስራ ላይ እናውለው::

የያዕቆብ መልእክት 1: 12-15

12፤ በፈተና የሚጸና ሰው የተባረከ ነው፤ ከተፈተነ በኋላ ለሚወዱት ተስፋ ስለ እርሱ የሰጣቸውን የሕይወትን አክሊል ይቀበላልና።  13፤ ማንም ሲፈተን፦ በእግዚአብሔር እፈተናለሁ፡ አይበል፤ እግዚአብሔር በክፉ አይፈተንምና፤ እርሱ ራሱስ ማንንም አይፈትንም።  14፤ ነገር ግን እያንዳንዱ በራሱ ምኞት ሲሳብና ሲታለል ይፈተናል።

በፈተና መጽናት የህይወት አክሊልን ያሸልማል::  በፈተና የሚፈተነውም ከላይ እንደነገረን እምነታችን ነው::  ስንፈተን ግን እግዚአብሔር እየፈተነኝ ነው የሚል ድምዳሜ ነው ያለን እግዚአብሔር በቃሉናበመንፈሱ ያሳድገንና ይለውጠናል እንጂ እንድንለወጥ ብሎ መከራንና ፈተናን ወደ እኛ አይልክም::  በአእምሯችን መታደስ መለወጥ ያለብን ለዚህ ነው አለበለዚያ ግን የምናስበው ካልተቀደሰና ምኞታችን ካልተለወጠ የሚሆነውን እየነገረን ነው::

ምኞት ፀንሳ  –> ኃጥያትን –> ኃጥያትን አድጎ ሞትን ይወልዳል::

አንዱ ፕሮሰስ ከተጀመረ የተቀረው እየተወለደ ይሄዳል::  ስለዚህ የራሳችንን ምኞት ሳናስገዛ እየተሳብንና እየተታለልን ብንፈተን እግዚአብሔርን እዚህ ውስጥ አንጨምረው::  በፈተና ለሚፀና የህይወት አክሊል ይጠብቀዋል! 

ሲያመንም እግዚአብሔር እያስተማረኝ ነው የምንል አለን ይህ ከቃሉ ጋር አብሮ አይሄድም እርሱ ህመማችንን ተቀበለ እያለን ቃሉ እንደገና ደግሞ ህመምን ሰጠን የሚለው አሳብ አብሮ አይሄድም::  እግዚአብሔር አሳቡን በግብር ይውጣ የሚቀያይር አይደለም እኛ እንኳን ለልጆቻችን የማናደርገውን ያደርጋል ብለን ማሰብ እርሱንና ቃሉን አለማወቅ ነው::  እንደቃሉ እንኑር!  አንድ ነገር እርግጠኛ እንሁን አሁን ያለንበትም ይሁን ወደፊት ያለው ፈተና ከእግዚአብሔር አይደለም እርሱ ግን መውጫውን እንደሚሰጠንና ሊረዳን አብሮን እንዳለ እርግጠኞች እንሁን!! እርሱ ማንንም አይፈትንም!!! ስሙ ይባረክ!

የያዕቆብ መልእክት 1: 16-18

16፤ የተወደዳችሁ ወንድሞቼ ሆይ፥ አትሳቱ። 17፤ በጎ ስጦታ ሁሉ ፍጹምም በረከት ሁሉ ከላይ ናቸው፥ መለወጥም በእርሱ ዘንድ ከሌለ በመዞርም የተደረገ ጥላ በእርሱ ዘንድ ከሌለ ከብርሃናት አባት ይወርዳሉ።

18፤ ለፍጥረቱ የበኵራት ዓይነት እንድንሆን በእውነት ቃል አስቦ ወለደን።

ከላይ እንዳየነው እግዚአብሔር አይፈትንም ብለናል ምክንያቱም  

1.  በጎ ስጦታ ሁሉ ፍጹምም በረከት ሁሉ ከላይ ናቸው፥  አምላካችን ፍጥረትን እንኳን ሲፈጥር በዘፍጥረት ላይ ሁሉም መልካም አድርጎ ነው የፈጠረው እንጂ የሚጎዳ ነገር ፈተናንም የሚያመጣ ነገር አላስቀመጠም ስለዚህ እግዚአብሔር ሊፈትነን ባህሪውም አይደለም መልካም ስጦታ ብቻ ነው ያለው::  ይህንን አሳብ አእምሮአችን ውስጥ ማስገባት አለብን አትሳቱ! እንደሚል እንዳንስት::  በምናልፍበት ፈተና ውስጥ እጅህ የለበትምንይ ተመስገን ልትረዳኝ መተሀልና ተመስገን እያልን በምስጋና እንሞላ አምላካችን ለእኛ ነው የሚያደላው::  በጠላት ሽንገላ እንዳንታለልና ጌታን እንዳናማው እርሱ ፍጹም ነው ስሙ ይባረክ::

2.  መለወጥም በእርሱ ዘንድ ከሌለ የሚገርመው አንድ ቀን አሳቡን ቀይሮ ይፈትነናል እንዳንል አምላካችን አይለወጥም::  በጎ ስጦታ ሁሉ ከእርሱ ዘንድ ነው:: 

3. በመዞርም የተደረገ ጥላ በእርሱ ዘንድ ከሌለ ከብርሃናት አባት ይወርዳሉ።  አምላካችን በብርሀን ውስጥ ያለ እንጂ ጨለማ ፈጽሞ በእርሱ ዘንድ የለም እኛንም ሲጠራን ወደሚደነቅ ብርሀኑ ጠራን እኛም በብርሀን እንመላለሳለን!!  ጥላ የለውም ጨለማ ሲኖር ነው ጥላ የሚኖረው የእኛ አምላክ ግን ማንም ሊቀርበው በማይችል ብርሀን ውስጥ ይኖራል!!  

ይህ ጌታ ለፍጥረቱ የበኵራት ዓይነት እንድንሆን በእውነት ቃል አስቦ ወለደ::  እናስተውል በእውነት  ቃል አስቦ ነው የወለደን!!!  ልጅነታችን የማይቀየር ነው ምክንያቱም እርሱ አይቀይርምና አሳቡን ሃሌሉያ!!!! የነገስታት ንጉስ አስቦ ወለደኝ በመስቀል ምጥ ማን ከእርሱ ይለየኛል መከራ ወይስ ስደት ውይስ ምን ይሆን ይህች ዓለም በእኔ ላይ የምትወረውረው ምንም ነገር ከእርሱ አይለየኝም እርሱ በእኔ እኔም በእርሱ ውስጥ እኖራለሁ::  አሜን

የያዕቆብ መልእክት 1: 19-25

19፤ ስለዚህ፥ የተወደዳችሁ ወንድሞቼ ሆይ፥ ሰው ሁሉ ለመስማት የፈጠነ ለመናገርም የዘገየ ለቍጣም የዘገየ ይሁን፤ 21፤ ስለዚህ ርኵሰትን ሁሉ የክፋትንም ትርፍ አስወግዳችሁ፥ ነፍሳችሁን ማዳን የሚችለውን በውስጣችሁም የተተከለውን ቃል በየዋህነት ተቀበሉ። 22፤ ቃሉን የምታደርጉ ሁኑ እንጂ ራሳችሁን እያሳታችሁ የምትሰሙ ብቻ አትሁኑ።

እነዚህ ሰዎች ካላቸው ነገር ሁሉ በወንጌል ምክንያት ከስፍራቸው የተነቀሉና በየቦታው የተበተኑ ናቸው::  ስለዚህ ባሉበት የስደት ህይወት ውስጥ ሲያባብላቸው አናይም ያዕቆብ እንዲያውም ቁጣንና መናገሩን ቀንሱ እግዚአብሔር በክፉ እየፈተናችሁ አይደለም መልካም አምላክ ነውና ጆሮአችሁን ለቃሉ ክፈቱና ስሙ እያላቸው ነው::

እንዲሁም የክፋትንም ትርፍ አስወግዳችሁ፥ ማለትም እርሱ የጠራችሁ መልካም ነውና እምነታችሁ ሲፈተን በርቱ የክፋትን ትርፍ እስወግዱመልካምነት ብቻ ይገኝ በእናንተ ዘንድ እያላቸው ነው::  ዛሬ የሚገፋን ትክክል ባልሆነ መንገድ የሚቃወመንን ሁሉ መልካም በማድረግ ነው የምናሸንፈው እንጂ በክፋት አይደለም:: ነፍሳችሁን ማዳን የሚችለውን በውስጣችሁም የተተከለውን ቃል በየዋህነት ተቀበሉ ይላቸዋል::  እዚህ ያደረሳቸው እውነትን ማወቃቸው ነው ስለዚህ ያንን እውነት ያዙት አርነት የወጣችሁበትን ቃል እናም ጽኑ እያላቸው ነው::  ቃሉን የምታደርጉ እንጂ የምትሰሙ ብቻ አትሁኑ ቃሉ የሚለው አምላክህን በሙሉ ኃይልህ ውደድ ባልንጀራህንም ውደድ ስለዚህ ክፋት ቦታ የለውም መልካም የሆነው አምላክ ወደ ቤቱ ጠርቶን እርሱን እንድንመስል ወስኗልና!!  በቃሉ እንኑር ቁጣንና ብዙ ንግግርን አስወግደን ከጌታ ዘንድ ለመስማት የፈጠንን እንሁን ሰምተንም እንታዘዝ!!  የጌታ ጸጋ ይርዳን ጥበቡንም ይጨምርልን!!

የያዕቆብ መልእክት 1: 26-27

26፤ አንደበቱን ሳይገታ ልቡን እያሳተ እግዚአብሔርን የሚያመልክ የሚመስለው ማንም ቢኖር የእርሱ አምልኮ ከንቱ ነው። 27፤ ንጹሕ የሆነ ነውርም የሌለበት አምልኮ በእግዚአብሔር አብ ዘንድ ይህ ነው፤ ወላጆች የሌላቸውን ልጆች ባልቴቶችንም በመከራቸው መጠየቅ፥ በዓለምም ከሚገኝ እድፍ ሰውነቱን መጠበቅ ነው።

እዚህ ክፍል ላይ እንደምናየው እግዚአብሔር  ምን  አይነት  አምልኮ  እንደሚወድና  የቱን እንደሚጠላ  ቁልጭ  አድርጎ  ይነግረናል  ያዕቆብ:: 

1. የሚጠላው አምልኮ:- 

1. 1. አንደበቱን የማይገታን  ሰው አምልኮ

ጌታ ሰውየውን አይደለም የሚጠላው ነገር ግን እንደፈለገ አፉን ሳይቆጣጠር በዋለበት አንደበት ለእርሱ ደግሞ አምልኮን ዝማሬን ፀሎትን ሲያመጣለት  ነው::  ከአንደበታችን መውጣት  ያለበት  ቃል  በጸጋ  የተቀመመ  የሚያንጽ  መሆን  አለበት:: ጴጥሮስም እንደሚለን ሕይወትን ሊወድ መልካሞችንም ቀኖች ሊያይ የሚፈልግ ሰው፥ መላሱን ከክፉ ከንፈሮቹንም ተንኰልን ከመናገር ይከልክል፤ ይላል::  በአንድ አፍ መልካምም ክፉም መነገር የለበትም::  አንደበት የፍጥረትን ሩጫ ታቃጥላለችና አንደበታችንን እንግታ!

1. 2. ልቡን እያሳተ :-  ልብ ለመሳት ቀላል ነው::  ልባችን የሚከተለው አስተሳሰባችንን ነውና ስለዚህ ነው ቃሉ  በአእምሯችሁ መታደስ ተለወጡ ይህንን ዓለም አትምሰሉ የሚለን:: ምክንያቱም  በልብ ያለው ሞልቶ በአፍ ይወጣልና  ውስጣችን የሞላው ምንድነው?!  ጌታም እንዳለ ምግብ ወደ እዳሪ ነው ከልብ የሚወጣው ግን እርሱ ሰውን ያረክሳል::  ልባችን የህይወት መውጫ ነውና ተግተን በቃሉ እንሙላውና እንጠብቀው:: ልባችን የእግዚአብሔር እርሻ ነው  የተዘራውን እንመርምር መራራ ስር አድጎ ሩጫችንን እንዳያሰናክልብን ቃሉን በውስጣችን ይሸሽግልን!!

2.  የሚወደው አምልኮ (ንጹሕ የሆነ ነውርም የሌለበት አምልኮ):-

2.1.  ወላጆች የሌላቸውን ልጆች –  ብዙ ጊዜ አምልኮ ሲባል ወደ ልባችን የሚመጣው ዝማሬ ነው ግን በተግባርም ማምለክ አለና ዙሪያ ገባችንን እንይ በህፃናት ላይ አንጨክን ባገኘነው አጋጣሚ ሁሉ እንርዳ በተለይ ወላጅ ከሌላቸውን::

2.2.  ባልቴቶችንም በመከራቸው መጠየቅ፥  በእድሜ የገፉትን ለራሳቸው ምንም ማድረግ ያልቻሉትንም እናቶችና አባቶችን እንርዳ::  ለደሀ የሰጠ ለእግዚአብሔር አበደረ እንደሚል ብድራትን እንቀበላለን::  በዙሪያችን ብዙ አሉ እንደው ችላ ብለን ካላለፍን በቀር::

2.3.  በዓለምም ከሚገኝ እድፍ ሰውነቱን መጠበቅ ነው። ይህ ግልጽ ነው እራስን መጠበቅ ምክንያቱም እኔ የእግዚአብሔር መንፈስ ማደሪያ ነኝና ዓለምን መውደድ በእኔ ውስጥ ሊገኝ አይገባውም::  እኔነቴን ሰጠሁህ ጌታዬ!

ጌታን እንደሚገባው ማምለክ እንድንችል ተምረናልና ቃሉን በተግባር እንኑረው እንጂ አንብበን ብቻ አንለፈው::  ጸጋ ይብዛልን!

የያዕቆብ መልእክት 2: 1-13

1፤ ወንድሞቼ ሆይ፥ በክብር ጌታ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ያለውን እምነት ለሰው ፊት በማድላት አትያዙ። 3፤ የጌጥ ልብስም የለበሰውን ተመልክታችሁ፦ አንተስ በዚህ በመልካም ስፍራ ተቀመጥ፡ ብትሉት፥ ድሀውንም፦ አንተስ ወደዚያ ቁም ወይም ከእግሬ መረገጫ በታች ተቀመጥ፡ ብትሉት፥ ራሳችሁን መለያየታችሁ አይደለምን?

ወንጌል ካልገባን በትክክል በደሀና በሀብታም መካከል መለያየት እናሳያለን::  ምክንያቱም ወንጌል ለክርስቶስ መሞት ነውና ያልሞተ በስጋ ዓይኑ እያየ ይለያል የሞተ ግን የስጋን ሳይሆን የመንፈስን እውነት ያያል እርሱም ሁሉ በክርስቶስ  አንድ እንደሆነ::  እኛ የክርስቶስ አካል አባል ነን እንግዲህ ወርቅ ሲለብስ ተለይቶ አንገቱ ላይ ወርቅ አለ አንገቱ ሀብታም ነው ጀርባው ግን ደሀ ነው ይባላል?!  አይባልም አካሉ በሙሉ በአንድ ስም ነው የሚጠራው  ራሱ ለብቻ እግሩ ለብቻ አይጠራም::  እንግዲህ የእኛ ራስ ማነው ክርስቶስ አይደለምን?  ቅዱሳንን ሁሉ በአንድ ዓይን ማየት አለብን ሁሉም ሰው ከኔ ይሻላል የሚለውን እውነት ጠንቅቄ ማወቅ አለብኝ አባባል አይደለምና ወይም አጉል ትህትናም አይደለም እውነት እንጂ::  ዓይኖቼ ከተከፈቱ በሁሉ ውስጥ ክርስቶስን ነውና የማየው ሁሉ ይበልጠኛል ለማለት አልግደረደርም::  

የወንጌል እውነት ከገባን የምናተኩረው የሰው መዳን ላይ እንጂ በስጋ ስላለው ኃብትና ድህነት ላይ አይሆንም የሁሉ ነብስ ለጌታ ዋጋ አለው እራቁታችንን እንደመጣን እንዲሁ ምንም ሳንይዝ ለምንሄደው የዓለም ትርፍ ሰውን አንለያይ::  ልብን የሚመረምር ጌታ ያየናል::  ሁሉን በአንድ ዓይን ማየት ይሁንልን::

የያዕቆብ መልእክት 2: 5፤ የተወደዳችሁ ወንድሞቼ ሆይ፥ ስሙ፤ እግዚአብሔር በእምነት ባለ ጠጎች እንዲሆኑ ለሚወዱትም ተስፋ ስለ እርሱ የሰጣቸውን መንግሥት እንዲወርሱ የዚህን ዓለም ድሆች አልመረጠምን? 

መንግስትን ሊያወርስ ጌታ የመረጠውን ክቡር ሰው እንውደድ ያለ መለያየት::  ፍቅራችን ያለግብዝነት ለሁሉ ይሁን!! ማስተዋልን ጌታ ይስጠን::

የያዕቆብ መልእክት 2: 14-26

14፤ ወንድሞቼ ሆይ፥ እምነት አለኝ የሚል፥ ሥራ ግን የሌለው ሰው ቢኖር ምን ይጠቅመዋል? እምነቱስ ሊያድነው ይችላልን?  17፤ እንደዚሁም ሥራ የሌለው እምነት ቢኖር በራሱ የሞተ ነው። 20፤ አንተ ከንቱ ሰው፥ እምነት ከሥራ ተለይቶ የሞተ መሆኑን ልታውቅ ትወዳለህን?

ይህንን ክፍል ሙሉውን ስናነብ የሚመስለው፤ መዳን ማለት እምነት ሲደመር ስራ ነው አይደል ግን እንደዛ አይደለም::

መዳን በእየሱስ በማመን ብቻ ነው ማንም እንዳይመካ እያለ እያስጠነቀቀ ጳውሎስ ነግሮናል::

ያዕቆብ የሚለው ግን አንድ ጊዜ ከዳናችሁ በኃላ ያለውን ኑሮ በስራ አሳዩ ነው::  ለምን ክርስቶስን ወደ መምሰል እንለወጣለን ታድያ?!  የመንፈስስ  ፍሬ ጥቅሙ ምን ላይ ነው?!  ፍቅር ፥  ቸርነት ፥  በጎነት ፥  ትዕግስት?  ይህ ሁሉ የሚያስፈልገን እኮ በዓለም ስንኖር ብርሃን ሆነን እንድንመላለስ ነው:: ስለዚህ ስራ ሰርቼ ነው ደህንነቴን የያዝኩት ወይም እየጠበኩት ህይወቴን ያለሁት ብለን ካሰብን ስተናል::  የዳነው በጸጋ ነው እግዚአብሔር አብ አንድ ጊዜ በልጁ ደስ ተስኝቶ እርሱን ስሙት ብሎናል::

መልክቱ የተጻፈላቸው አይሁድ ናቸውና የቱን ህግ ጠብቀው የቱን እንደሚተው፥ እንዴት እንደሚጸልዩ፥  ማኅበራዊ ኑሮአቸው እንዴት መሆን እንዳለበት ነው የሚነግራቸው::  ምክንያቱም ስደት ላይ ችግር ውስጥ ናቸው አንዳንዱ ተርቦ ሌላው ጠግቦ የወንድሙን መራብ እንኳን አያስተውልም ይህንን እንዲያስተካክሉም ነው::  ሀብታሞቹ መተው ቤተክርስቲያንን እንዳይቆጣጠሩ ግን ሰው ሁሉ እኩል እንደሆነ እንዲያውቁ ፥  ወላጆቻቸውን በዚሁ በመከራው ያጡትን ህፃናት እንዳረዱ::  ጧሪ ያጡትንም እንዲያስቡ ጠለቅ ያለ የቀን ከቅን ኑሮአቸውን ነው የሚዳስሰውና እንዲያስተካክሉ የፃፈላቸው::  ይህ ሰው የእየሩሳሌምዋን ቤተክርስቲያን ከሚመሩት መካከል እንደመሆኑ ይህንን ጽፏል::

ዛሬም እኛ በፍቅር እየተመላለስን በዙሪያችን ያለውን መማረክ አለብን ክርስትና የቃል ሽምደዳ ሳይሆን ቃሉን መኖር ነውና እምነታችንን ለሌሎች መግለጥ እንድንችል ጌታ ይርዳን:: 

የያዕቆብ መልእክት 3: 1-12

2፤ ሁላችን በብዙ ነገር እንሰናከላለንና፤ በቃል የማይሰናከል ማንም ቢኖር እርሱ ሥጋውን ሁሉ ደግሞ ሊገታ የሚችል ፍጹም ሰው ነው። 5፤ እንዲሁም አንደበት ደግሞ ትንሽ ብልት ሆኖ በታላላቅ ነገር ይመካል። እነሆ፥ ትንሽ እሳት እንዴት ያለ ትልቅ ጫካ ያቃጥላል። 6፤ አንደበትም እሳት ነው። አንደበት በብልቶቻችን መካከል ዓመፀኛ ዓለም ሆኖአል፤ ሥጋን ሁሉ ያሳድፋልና፥ የፍጥረትንም ሩጫ ያቃጥላል፥ በገሃነምም ይቃጠላል። 9፤ በእርሱ ጌታንና አብን እንባርካለን፤ በእርሱም እንደ እግዚአብሔር ምሳሌ የተፈጠሩትን ሰዎች እንረግማለን፤

አንደበት :- 

ትንሽ ብልት ነው

እሳት ነው

ሥጋን ሁሉ ያሳድፋል

የፍጥረትንም ሩጫ ያቃጥላል በገሃነምም ይቃጠላል

አብን እንባርክበታለን

ሰዎች እንረግማለን?

የሚገርመው ነገር ይህች ትንሽ የሆነች ብልት እንዴት ማንነታችንን መቆጣጠር እንደምትችል ነው የሚያሳየው::  አንደበት ቀላል ስራ የለውም በህይወታችን ውስጥ::  ቃሉ እንደሚል በብዙ ነገር እንሰናከላለንና፤ በቃል የማይሰናከል ማንም ቢኖር እርሱ ሥጋውን ሁሉ ደግሞ ሊገታ የሚችል ፍጹም ሰው ነው። ፍጹም የሚያስብል ውጤትን የሚያስገኝ ነው አንደበትን መግዛት::  ልክ አንድ የምንጭ ውሀጋር ሄደን የጣፈጠን ውሀ ቀድተን  ነገ ስንመለስ የመረረ እንደማይሆን እንዲሁ አንደበታችን የሚያወጣው የጣፈጠ መሆን አለበት ሁልጊዜ አንድ አይነት::  እሩጫችንን ነው የሚያጠፋው  የለፋነው ሁሉ ከንቱ ይሆንብናልና እንጠብቅ ከአንደበታችን የሚወጣውን::

በዚሁ አብን እንባርካለን፤ በእርሱም እንደ እግዚአብሔር ምሳሌ የተፈጠሩትን ሰዎች እንረግማለን?!  ሰው ሁሉ በእግዚአብሔር ዓይን እኩል እንደሆነ አንዘንጋ ደሀውን አመናጭቀን ሀብታሙን ተለማምጠን ማናገር የለብንም ይህ ምንጭ አንድ አይነት ውጤት ነው መስጠት ያለበት::

ብዙ ስተን ሊሆን ይችላል ዛሬ ግን ንስሀ እንግባና እንስተካከል ከአንደበታችን መውጣት ያለበት የሚያንጽ በጨው የተቀመመ መሆን አለበት አለበለዚያ ግን አንናገር:: በዚሁ አንደበት ነውና ጌታ ፊት ቀርበን የምንፀልየና የምንባርከው ስለዚህ አናቆሽሸው::  የተቀበልነው መንፈስ ራስን መግዛት የሚያስችል ነው እንጂ ከምንችለው በላይ እንድንዘረጋም አልተጠየቅንም ለጸጋው እራሳችንን አሳልፈን እንስጥ::  በአንደበታችን ያበላሸነውን ያሳዘናቸውን ሰዎች መባረክ እንጀምር የምትባርክ ነፍስ ትባረካለችና::  ጌታ ማስተዋልን ይስጠን::

የያዕቆብ መልእክት 3: 13-18

13፤ ከእናንተ ጥበበኛና አስተዋይ ማን ነው? በመልካም አንዋዋሩ ስራውን በጥበብ የዋህነት ያሳይ። 14፤ ነገር ግን መራራ ቅንዓትና አድመኛነት በልባችሁ ቢኖርባችሁ፥ አትመኩ በእውነትም ላይ አትዋሹ። 17፤ ላይኛይቱ ጥበብ ግን በመጀመሪያ ንጽሕት ናት፥ በኋላም ታራቂ፥ ገር፥ እሺ ባይ ምሕረትና በጎ ፍሬ የሞላባት፥ ጥርጥርና ግብዝነት የሌለባት ናት።

ሁለት አይነት ጥበብ አለ:- 

1.  ላይኛይቱ ጥበብና 

2  የምድር/የስጋ/የአጋንንት ጥበብ

ላይኛይቱ ጥበብ:-  የዋህነት የሞላበት ነው ጌታ እንዳለን እኔ የዋህ በልቤም ትሁት ነኝ ነው ያለን ከማን እንማር ታድያ::  እንዲሁም ይህች ጥበብ 

– ንጽሕት ናት፥ 

–  በኋላም ታራቂ፥ 

–  ገር፥

–  እሺ ባይ 

–  ምሕረት የሞላባት፥ 

–  በጎ ፍሬ የሞላባት፥ 

–  ጥርጥር የሌለባት

–  ግብዝነት የሌለባት ናት

ይህንን እንከተታተል!  የላይኛይቱን ጥበብ እንሞላ ሳይሰስት በልግስና ጸጋን እና ጥበብን ይሰጣልና ወደ ጸጋ ዙፋኑ እንቅረብና እንጠይቅ::  በህይወታችን የጽድቅ ፍሬ እፍርተን ሰላምን ለሚያደርጉት ሰዎች በሰላም ይዘራል። በዚህ ፍሬ ስንመላለስ ዓለም ልታሾፍ ትችላለች ለኛ ለገባን ግን ሰላምን እናገኛለንና ቃሉን እንኑረው::

የምድር/የስጋ/የአጋንንት ጥበብ:-

–  መራራ ቅንዓትና 

–  አድመኛነት በልባችሁ ቢኖርባችሁ ውጤቱ 

          –  ሁከትና

          –  ክፉ ስራ ነው።

ስጋዊ ከሆንን ይህንን ነው  የምናሳየው ፍሬ ሰላም ያጣን አንደበታችንን የማንቆጣጠር  ስጋውያን ነው የምንሆነው::

እኛ ግን ሰማያዊ ነን ለራሳችን የሞትን ነን::  ፍቅር አይቀናም ደግሞም ፍቅር ሁሉን ያምናል አድመኛ አይሆንም ለዚህ ነው ደቀመዛሙርቴ መሆናችሁ በዚህ ይታወቅ ያለን ጌታ::  የመንፈስን ፍሬ እያፈራን በሰላምና በፍቅር እንመላለስ::  የዋህና ትሁት እንሁን እንደጌታ!!

የያዕቆብ መልእክት 4: 1-3

1፤ በእናንተ ዘንድ ጦርና ጠብ ከወዴት ይመጣሉ? በብልቶቻችሁ ውስጥ ከሚዋጉ ከእነዚህ ከምቾቶቻችሁ አይደሉምን? 2፤ ትመኛላችሁ ለእናንተም አይሆንም፤ ትገድላላችሁ በብርቱም ትፈልጋላችሁ፥ ልታገኙም አትችሉም፤ ትጣላላችሁ ዋጉማላችሁ ነገር ግን አትለምኑምና ለእናንተ አይሆንም፤ 3፤ ትለምናላችሁ፥ በምቾቶቻችሁም ትከፍሉ ዘንድ በክፉ ትለምናላችሁና አትቀበሉም።

አንድ ጥያቄ ወደ ውስጤ መጣ ይኸውም ምኞቴ ምንድነው የሚል::  ጌታን መርምረኝ ብዬ በፊቱ ሆንኩኝ::  ያላስተዋልኩት ነገር ውስጤ ይኖርን?  እኔነት ካልሞተ የማስበውም  የምጸልየውም ሁሉ እኔ እኔ በማለት የተሞላ ብቻ ነው::  ጌታ ከእኔነት አውጥቶ ለክብሩ የምንኖር ያድርገን!

እነዚህ ሰዎች ከላይኛይቱ ጥበብ ይልቅ በጠብና ቁጣ የተሞሉ ናቸው::  በእግዚአብሔር ፊት ነገራቸውን በጸሎት ከመፍታት ይልቅ በስጋ ነገሮችን ለማድረግ የሚጣሉ የሚገድሉና መብታቸውን ለማስከበር የሚሟሟቱ ናቸው::  ለዚህ ሁሉ መሰረት የሆነው ምኞታቸው ነው::  ጸሎትን እንኳን ቢጸልዩ የሚጸልዩት በክፉ ልብ ነውና አይሰሙም መልስም የለም ከሰማይ::  

ጸሎታችን ምን አይነት ነው?  የሚያስቸግሩን ሰዎች ይኖራሉ በዙሪያችን ስንጸልይ በቁጣ ንቀላቸው አይከናወንላቸው እኔን እንዳስጨነቁኝ አስጨንቃቸው ነው? አይሰማም በእግዚአብሔር ፊት:;  አስቀድሞ የሚያሳድዷችሁን መርቁ ጸልዩላቸው  ተብለናል::  እንባርካቸው እነዚህን ሰዎች ይከናወኑ የልባቸው አሳብ ይሳካ!  ከዚህ ሁሉ በላይ መዳን ይሁንላቸው!  

ጸሎታችንን እንቃኝ በላይኛይቱ ጥበብ እንሞላ ገር እንሁን ይቅር ባይ እንሁን በጎ ፍሬ የሞላብን እንሁን ያን ጊዜ የጽድቅ ፍሬ የሆነው ሰላም በእኛ ውስጥ ያብባል::  ጌታ እጹብ ድንቅ ቅዱስም አምላክ ነውና በፊቱ ስንቀርብ ክፉ ነገር ይዘን እንቅረብ:

ጌታ ሆይ እርዳን ማስተዋልን ፀጋን ጥበብንም ስጠን!

የያዕቆብ መልእክት 4: 4-5

4፤ አመንዝሮች ሆይ፥ ዓለምን መውደድ ለእግዚአብሔር ጥል እንዲሆን አታውቁምን? እንግዲህ የዓለም ወዳጅ ሊሆን የሚፈቅድ ሁሉ የእግዚአብሔር ጠላት ሆኖአል። 5፤ ወይስ መጽሐፍ፦ በእኛ ዘንድ ያሳደረው መንፈስ በቅንዓት ይመኛል፡ ያለው በከንቱ እንደ ተናገረ ይመስላችኋልን?

አመንዝሮች የሚያስብለው ምንድነው? እግዚአብሔርንም ዓለምንም መውደድ ነው ይህንን ስም የሚያሰጠው::  ለሁለቱም መሆን አንችልም ወይ ዓለምን ወይንም ደግሞ ጌታን::

1ኛ ዮሐንስ:- ዓለምን ወይም በዓለም ያሉትን አትውደዱ፤ በዓለም ያለው ሁሉ እርሱም የሥጋ ምኞትና የዓይን አምሮት ስለ ገንዘብም መመካት ከዓለም ስለ ሆነ እንጂ ከአባት ስላልሆነ፥ ማንም ዓለምን ቢወድ የአባት ፍቅር በእርሱ ውስጥ የለም።

ዓለምን መውደድ የሚመጣው ከመመኘት ይጀምርና ነው ለዚህ ነው ከላይ በቃሉ እንዳየነው የስጋ ምኞት የዓይን አምሮት እንደሆነ የሚነግረን::  ዓለምን መውደድ ከእግዚአብሔር ጋር ጠብ ነው ደግሞም የአባት ፍቅር በእርሱ  የለም ከዛም አልፎ የእግዚአብሔር ጠላት መሆን ነው::  ከባድ ነገር ነው ማንም የቆመ ቢመስለው እንዳይወድቅ  ይጠንቀቅ::  እራሳችንን በጌታ እናስመርምር የተቀበልነው ቅዱሱ መንፈስ ይቀናልና::  አናስቀናው!!! 

በዓለም ያለው ሁሉ ያልፋል እኛና ጌታ ብቻ ነን የምንቀረው ደግሞስ ጌታ ምን አጉድሎብ ን ነው ወደ ዓለም የምንቀላውጠው ይህ ማለት እኮ እረኛችን ያጎደለብን ነገር አለ ማለት ነው::  እርሱ ግን በመልካም መንገድ ሁሉ የሚመራ ቅጥረኛ ያልሆነ ነፍሱን ስለወዳጆቹ አሳልፎ የሰጠ ታማኝ እረኛ ነው:: ሲጸልይልንም በዓለም ሳሉ  ጠብቃቸው ካለ በኃላ እኔ ከዓለም እንዳይደለሁ ከዓለም አይደሉም። እርሱ ተማምኖ ከዓለም አይደሉም ብሎን እኛ እዛ ውስጥ እንዳንገኝ::  ይህንን ሁሉ በጸጋው እንድንረታው ይፈልጋልና ወደ ጸጋ ዙፋኑ እንቅረብ:: ቲቶ 2: 12-13፤ ይህም ጸጋ፥ ኃጢአተኝነትንና ዓለማዊን ምኞት ክደን፥ የተባረከውን ተስፋችንን እርሱም የታላቁን የአምላካችንንና የመድኃኒታችንን የኢየሱስ ክርስቶስን ክብር መገለጥ እየጠበቅን፥ ራሳችንን በመግዛትና በጽድቅ እግዚአብሔርንም በመምሰል በአሁኑ ዘመን እንድንኖር ያስተምረናል፤

ጸጋ እንለምን!

የያዕቆብ መልእክት 4: 6-10

6፤ ነገር ግን ጸጋን አብልጦ ይሰጣል፤ ስለዚህ፦ እግዚአብሔር ትዕቢተኞችን ይቃወማል፥ ለትሑታን ግን ጸጋን ይሰጣል፡ ይላል። 7፤ እንግዲህ ለእግዚአብሔር ተገዙ፤ ዲያብሎስን ግን ተቃወሙ ከእናንተም ይሸሻል፤  8፤ ወደ እግዚአብሔር ቅረቡ ወደ እናንተም ይቀርባል። እናንተ ኃጢአተኞች፥ እጆቻችሁን አንጹ፤ ሁለት አሳብም ያላችሁ እናንተ፥ ልባችሁን አጥሩ።

ቃሉ እንደሚናገረን እግዚአብሔር ትዕቢተኞችን ይቃወማል፥  ለምን ያልን እንደሆነ ሰው ማለት ዛሬ ታይቶ ነገ የሚጠፋ ፍጥረት ሆኖ ሳለ መታበዩ ነው  በእግዚአብሔር ፊት የማይወደደው አሳብ::  

ነገር ግን ለትሑታን ጸጋን ይሰጣል ይላል።  በእምነት ወደ ጸጋ ዙፋኑ እንቅረብና ጸጋን እንጠይቅ  ለምን ያለ ጸጋ እንመላለሳለን ውሰዱ በነፃ እየተባልን የምን መታገል ነው?!   

ወደ እግዚአብሔር ስንቀርብ እርሱም ወደ እኛ ይቀርባል ጌታ ሲቀርብ ደግሞ መሸሽ ያለበት ይሸሻል እርሱም ዲያቢሎስ ነው::  የተሰጠው ትእዛዝ ሽሽ ነው ምንም መታገልም አያስፈልግም የእኛን ማንነት እንዲሁም ከእኛ በላይ ቃሉንም ጥንቅቅ አድርጎ ያውቃልና ጠላት::  ብቻ እንገዛ እራሳችንንም በጌታ ፊት ዝቅ እናድርግ እንጂ ጠላት እድል ፋንታ የለውም የተሸነፈ ነው::  እርሱን በየት ገባ ወጣ ከማለት ይልቅ ወደ ጸጋ ዙፋኑ ቀርበን ከጌታችን ጋር ህብረትን እናድርግና ከመወላወል ወተን ልባችን በጌታ ላይ ይረፍ::  በራሳችንም በጌታም መመካት አይቻልም ይህ መወላወል ነውበእርሱ ላይ ብቻ እንደገፍ:: 

አሜን!

የያዕቆብ መልእክት 4:11-12

11፤ ወንድሞች ሆይ፥ እርስ በርሳችሁ አትተማሙ። ወንድሙን የሚያማ በወንድሙም የሚፈርድ ሕግን ያማል በሕግም ይፈርዳል፤ በሕግም ብትፈርድ ፈራጅ ነህ እንጂ ሕግን አድራጊ አይደለህም። 12፤ ሕግን የሚሰጥና የሚፈርድ አንድ ነው፤ እርሱም ሊያድን ሊያጠፋም የሚችል ነው፤ በሌላው ግን የምትፈርድ አንተ ማን ነህ?

ወንድሞች ሆይ አትተማሙ ይላል ያዕቆብ:- ማማት ምን ማለት ነው መቼም ሀሜት የሚኖረው ስለዚያ ሰው መልካም  የምንናገረው ስለሌለ ነው አይደል የምናማው? ባይሆንማ ወንድማችንን እራሱን ሄደን ወንድሜ ሆይ ይህ ያደረከው መልካም ነው ብለን እንባርከው ነበረ::  አንድ ነገር ማወቅ  ያለብን ሰው ቢደክም ለጌታው ነው ቢበረታም ለጌታው ነው እኛን ፈራጅ ያደረገን ማን አደረገን?!  ሰውየው በሌለበት ስሙን በክፉ አላነሳም የሚል አቋም ይኑረን::

ብዙ ልናይ እንችላለን በቤተክርስቲያን ውስጥ ከቻልን መጸለይ አለበለዚያ ግን በማያገባን እየፈረድንና እያማን በጌታ ዘንድ ደስ የማያሰኘውን  እያደረግን እንዳንገኝ:: ጌታም እራሱ በማቴዎስ 7: 1-2፤ እንዳይፈረድባችሁ አትፍረዱ፤ በምትፈርዱበት ፍርድ ይፈረድባችኋልና፥ በምትሰፍሩበትም መስፈሪያ ይሰፈርባችኋል ብሎናልና አንደበታችንን እንጠብቅ እንደመጣልን ከመግናገርና ከመበየን እንጠበቅ::  ትህትናንና ሰፊ ልብን እንያዝ ሌሎችም ሲያሙ አንፍቀድ:: ይህ የምናማው ሰው ጌታ የሞተለት ነውና እንውደደው እርሱን ነው የተጠየቅነው::

የያዕቆብ መልእክት 4: 11-17

14፤ ሕይወታችሁ ምንድር ነው? ጥቂት ጊዜ ታይቶ ኋላ እንደሚጠፋ እንፍዋለት ናችሁና። 15፤ በዚህ ፈንታ፦ ጌታ ቢፈቅድ ብንኖርም ይህን ወይም ያን እናደርጋለን፡ ማለት ይገባችኋል። 17፤ እንግዲህ በጎ ለማድረግ አውቆ ለማይሠራው ኃጢአት ነው።

አቤት በራሳችን የምንመካ እንፋሎቶች?!!  እግዚአብሔር ይርዳን እንድናስተውል:::  እራሴን ሳየው ስንቱን እቅዴን ይሆን ጌታ ቢፈቅድና ብኖር ብዬ ያቀድኩት?!  ግን ይህንን እውነት አውቀን አለማድረጉ ሐጥያት ነው እያለን ነው ቃሉ::  በእቅዳችን ሁሉ ጌታን እንሹመው እርሱ ሲፈቅድ ነው የሚሆነው::  ደግሞስ ከእቅዳችን በፊት ጌታ ቢመጣስ?  ነገ ምን ይዞ እንደሚመጣ አናውቅምና በልማድ ሳይሆን በእውነት ቢፈቅድና ብንኖር ማለትን እንልመድ:: ማቀድ ሐጥያት ነው እያልኩኝ አይደለም አቅደን እንሰራለን ቃሉም የሚለን አንድ ቀን እንደቅረው መዘጋጀት አንድ ሺ ዓመት እንዳለው ደግሞ ማቀድ ነው ያለብን::

በጎ  የሆነውን እያወቅን አለማድረግ ሀጥያት መሆኑን ካወቅን ብዙ መጎብኘት ያለበት አመለካከት አለብዬ አስባለሁ::  እኛ የእግዚአብሔር እርሻ እንደሆንን ቃሉ ይነግረናል ምን ይሆን የተዘራው በልባችን?  ምን እንድናስብ እንኳን የተነገረን ነን ምክንያቱም በአእምሯችን የተለወጥን እንጂ ይህንን ዓለም እንዳንመስል ነው ጌታ የሚፈልገው::  የዚህ ዓለም ቀመር በመስጠትና በመቀበል ዙሪያ ሲያጠነጥን የጌታ ግን በመስጠት ዙሪያ ነው ::  ብዙ የተቀበልን ነንና አሁን የምንሰጥበት ጊዜ ነው::  እግዚአብሔር ማስተዋልን ይስጠን!

የያዕቆብ መልእክት 5: 1-6

2፤ ሀብታችሁ ተበላሽቶአል፥ ልብሳችሁም በብል ተበልቶአል። 3፤ ወርቃችሁም ብራችሁም ዝጎአል፥ ዝገቱም ምስክር ይሆንባችኋል ሥጋችሁንም እንደ እሳት ይበላል። ለኋለኛው ቀን መዝገብን አከማችታችኋል።

በማቴዎስ 6: 19፤ ብልና ዝገት በሚያጠፉት ሌቦችም ቆፍረው በሚሠርቁት ዘንድ ለእናንተ በምድር ላይ መዝገብ አትሰብስቡ፤ ብሎናል ጌታ ምክንያቱም   ገንዘብ ጌታ ሊሆንብን ስለሚፈልግ አብሮት ብዙ ክፋት ይመጣል::  በምድር ሀብት አይኑራችሁ አልተባልንም ነገር ግን ጌታ እንዳይሆንብን ያስፈልጋል ሀብት መገልገያ ነው መልካምን ስራ እንስራበት::  እነዚህ ሰዎች ለአገልጋዮቻቸው ደሞዝን ያልከፈሉ በሰው ችግር የሚስቁ ልባቸውን ያደለቡ ናቸው::  ሰው ግንዛሬ ታይቶ ነገ እንደሚጠፋ ረስተዋል::  

እነሱን እንተውና እኛ እንዴት ነን ለትምህርታችን ተጽፏልና::  በምድር ላይ ተጣብቀን የጌታ ነገር እንዳይቀልብን  እናስተውል::  ሀብት ቢኖረን ጥሩ የሌላቸውን እናስብ እንርዳቸው ከዚህ ምድር ምንም ይዘን አንሄድምና በሰማይ ግን መዝገባችንን እናከማች ብል የማይበላው ሌባም የማይሰርቀው በዛ ነውና::  የሚያገለግሉንን በሚገባ መክፈልን እንማራለን ከዚህ ቃል ለምን የሬስቶራንት አስተናጋጅ አይሆንም? አገልግሎት የሰጡንን እንባርክ::  በተለይ የቤት ሰራተኛ ካለን መልካም እንሁን ገንዘባቸውንም በጊዜ እንክፈል::  ድሮ አስታውሳለሁ እንዳይሄዱ እየተባለ የተወሰነ ደመወዝ ነበር የሚሰጣቸው ቤተሰቦቻችንም ግፍ አድርገው ከሆነ  ካስታወስን ንስሃ እንግባ:: በእጃችን ግፍ እንዳይገኝ! ጌታ ቸር ነውና ይቅር ይላል:: 

ለጌታ እንገዛ!

የያዕቆብ መልእክት 5: 7-11

7፤ እንግዲህ፥ ወንድሞች ሆይ፥ ጌታ እስኪመጣ ድረስ ታገሡ። እነሆ፥ ገበሬው የፊተኛውንና የኋለኛውን ዝናብ እስኪቀበል ድረስ እርሱን እየታገሠ የከበረውን የመሬት ፍሬ ይጠብቃል። 8፤ እናንተ ደግሞ ታገሡ፥ ልባችሁንም አጽኑ፤ የጌታ መምጣት ቀርቦአልና።

እነዚህ ቅዱሳን በመከራ ውስጥ ያሉናቸው ከስፍራቸው ተፈናቅለው በጥገኝነት ለሀብታሞች እየሰሩና እየተበደሉ ያሉ ናቸው:: በቃሉ የሚመክራቸው እንዲታገሱ ነው እነእዮብን እንዲሁም መከራ የተቀበሉትን ነብያትን እያነሳ ለታገሱ 

ሁሉ ፍሬ እንዳለ ነው የሚነግራቸው::  

መቼም ገጹን እየገለጥን ስናነብ ያሉበት መከራ ብዙም አይገባንም ግን ፈራጅ በደጅ ፊት ቆሟል እያላቸው ነው መግባት ብቻ ነው የቀረው ታገሱ ይላል::  እንደዚሁም ደግሞ የጌታ መምጣት ደርሷል ይላል እነሱ በነበሩበት ጊዜ ደርሷል መምጫው ከተባለ አሁን እኛ ባለንበት ጊዜማ እንዴት የበለጠ የቀረበ ጊዜ ላይ ነው ያለነው?! ጌታ ይመጣል መብራታችን የበራ ዘይታችንም ሙሉ ይሁን::  ዘይቱ መቼም መንፈስ ቅዱስ ነው ዕለት ዕለት እንሞላና እንታደስ መብራቱ እንዳይበራ የሚያግድ በእኛ ውስጥ  አይገኝ:: በራሳችን የምንኖረው አይደለም ክርስትና በእርሱ ላይ ባለን እምነት እንጂ:: 

በምናልፍበት ነገር ሁሉ እንታገስ ጌታ ከመከራ መውጫ በር አለውና:: ይደርስልናል ሁሉ ጊዜያዊ ነው:: በክርስቶስ  ያገኘነው  ህይወት ግን ለዘላለም ነው::

እንበርታ ጌታ ሊመጣ ነው!!! ማራናታ!

የያዕቆብ መልእክት 5: 12-13

12፤ ከሁሉም በፊት፥ ወንድሞቼ ሆይ፥ በሰማይ ቢሆን በምድርም ቢሆን በሌላ መሐላም ቢሆን በምንም አትማሉ፤ ነገር ግን ከፍርድ በታች እንዳትወድቁ ነገራችሁ አዎን ቢሆን አዎን ይሁን፥ አይደለምም ቢሆን አይደለም ይሁን። 13፤ ከእናንተ መከራን የሚቀበል ማንም ቢኖር እርሱ ይጸልይ፤ ደስ የሚለውም ማንም ቢኖር እርሱ ይዘምር።

እከንግዲህ በመሐላ  የምናሳምን ካለን እንተወው::  ምክንያቱም አንዱም ነገር የእኛ አይደለምና ልንምልበት አንችልም::  እግዚአብሔር ለአብርሃም በራሱ ማለለት ይላል በመሐላው አብርሐም አልተካፈለም::  ጌታ በራሱ ማለ እራሱ ሰራ:: ስለዚህመሐላን እናስወግድ::

መከራን የሚቀበል ማንም ቢኖር እርሱ ይጸልይ፤ ይላል ቃሉ::  ጌታም ሐዋርያትን ያላቸው በመጨረሻው ሰዓቱ ላይወደ ፈተና እንዳትገቡ ትጉና ጸልዮ ነበር::  መከራ ውስጥ ከገባንም እንዲሁም እንዳንገባም እንጸልይ::  በአባታችን ሆይ ጸሎትም ውስጥ ወደ ፈተና አታግባን ብለን እንድንጸልይ አስተምሮናል::  አትጠይቁምና ለእናንተ  አይሰጥም እንደሚለው እንዳይሆን የመከራውን መውጫ ጌታ እንዲያሳየን በፊቱ እንውደቅ::  ጠላታችን ዲያብሎስ ዙሪያችንን እንደሚዞር አንርሳው::

ደስ የሚለውም ማንም ቢኖር እርሱ ይዘምር እንደሚል በፊቱ ደስታችንን በዝማሬ እንግለጽ::  በውስጣችን መንፈሳዊ ቅኔ ይፍለቅለቅ::

የያዕቆብ መልእክት 5: 14-15

14፤ ከእናንተ የታመመ ማንም ቢኖር የቤተ ክርስቲያንን ሽምግሌዎች ወደ እርሱ ይጥራ፤ በጌታም ስም እርሱን ዘይት ቀብተው ይጸልዩለት። 15፤ የእምነትም ጸሎት ድውዩን ያድናል ጌታም ያስነሣዋል፤ ኃጢአትንም ሠርቶ እንደ ሆነ ይሰረይለታል።

ከእናንተ የታመመ ማንም ቢኖር:- ማንም የሚለው ላይ ማስመር እፈልጋለሁ::  ማንም እንዲታመም ፈቃዱ አይደለም እግዚአብሔር ስለዚህ በሽታ በአንድ እጁ በሌላ ደግሞ ፈውስ የያዘ አምላክ አይደለም::  ማንም እንዲታመም የማይፈልግ  ስለህመማችን የተገረፈ ጌታ ነው በጠባሳውም ሪሲቱን ይዟል ዋጋ አንድ ጊዜ ነው የሚከፈለው::  አንታመምም አይደለም ግን ብንታመም ፈውስ አለ እያልኩኝ ነው::  ጤንነታችንንና ሰላማችንን የሚፈልግ ጌታ ይባረክ::  

እዚህ  ክፍል ላይ እንደምናየው የቤተክርስቲያን ሽምግሌዎች ወደ እርሱ ይጥራ፤ በጌታም ስም እርሱን ዘይት ቀብተው ይጸልዩለት። በጌታ ስም ነው ፈውስ ያለው እንጂ በዘይቱላይ አይደለም ዓይናችን በሞተውና በተነሳው ዋጋ በከፈለው ላይ መሆን አለበት እንጂ በሽማግሌዎቹም ላይ መሆን የለበትም:: የሚፈውስ ጌታ ነው::  ሐዋርያትም ያሉት በጌታ በእየሱስ ክርስቶስ ስም ተነሳና ተመላለስ ነው::  እኛም አትኩሮታችን በዚህ ስም ላይ ይሁን!

የሚያድነውም የእምነት ጸሎት ነው::  ለሚወላውል ከጌታ ዘንድ አንዳች አይቀበልም በእምነት ስንጸልይ ጌታ የታመመውን ያስነሳል::  አስምሩልኝ ጌታነው የሚያስነሳው::  ከሰው ላይ ዓይናችንን እናንሳ! በኃጥያትም የመጣ ከሆነ ይቅር ይባላል እንዴት ያለ መብት ነው የሰጠን ይገርማል::  ግን ይህ ማለት በኃጥያት እየተመላለስን እንኑር ለማለት አይደለም እንዲያውም አብዝተን ወደእርሱ እየተጠጋን ዓለምን መናቅ ይብዛልን::  በዛም ይሁን በዚህ የእግዚአብሔር ኃይል ለማዳን ነው  እንጂ ለማጥፋት ወይም ለማሰቃየት አይደለም::  እርሱ እጅግ የሚምር የሚራራ ጌታ ነውና::

የያዕቆብ መልእክት 5: 16-20

16፤ እርስ በርሳችሁ በኃጢአታችሁ ተናዘዙ። ትፈወሱም ዘንድ እያንዳንዱ ስለ ሌላው ይጸልይ፤ የጻድቅ ሰው ጸሎት በሥራዋ እጅግ ኃይል ታደርጋለች። 17፤ ኤልያስ እንደ እኛ የሆነ ሰው ነበረ፥ ዝናብም እንዳይዘንብ አጥብቆ ጸለየ፥ በምድርም ላይ ሦስት ዓመት ከስድስት ወር አልዘነበም፤ ሁለተኛም ጸለየ፥  18፤ ሰማዩም ዝናብን ሰጠ ምድሪቱም ፍሬዋን አበቀለች።

ሲጀምር ጸሎቴ ለውጥ ያመጣል ብዬ ማመን አለብኝ እንደሚሰማኝ ማወቅ አለብኝ::  ከሰው ሰው የማይለይ ጌታ እያንዳንዳችንን ይሰማናል!  እንመን!  ኤልያስ እንደኛው ሰው ነበረ በአገር ላይ ነው ሰማዮን የዘጋው ሲከፈትም በአጭር  ጸሎት ነው ::  እንግዲህ እርስ በእርሳችን እውነተኞች መሆን አለብን ኃጥያትን መናዘዝና መተው አለብን::  የጻድቅ ሰው ጸሎት በስራዋ እጅግ ኃይል ታደርጋለች ይላል::  የጸሎትን ጥቅም እንወቅ ጸሎት ማለት አውርቶ መነሳት ሳይሆን ከጌታ ጋር ህብረት ማድረግ ከእርሱም ዘንድ መስማት ማለት ነው ይህንንእንለማመድ ያን ጊዜ ጸሎት ተራራ አይሆንብንም::

እርስ በእርሳችን ልንሸካከም ይገባል አንዱ የሌላውን ሸክም ይሸከም ይላልና ቃሉ::  በዙሪያችን ያሉትን እንመልከት ወንድማችን እንዴት ነው እህታችንስ?  ጌታ ማንን ይጠቀም እኛ በአቅራቢያው እያለን ከሌላ ያምጣሰው? እኛው እንታዘዝ ስንቱ በዙሪያችን መጽናናት ያስፈልገዋል? ዓይናችንን ይክፈት::

ከእውነት የሳተም ካለ ለመመለስ እንጂ ለመፍረድና ለማማት እንቸኩል::  ቢመለስ ነፍሱን ከሞት እንዲያድን፥ የኃጢአትንም ብዛት እንዲሸፍን ይወቅ ይላል ቃሉ።ጌታን ማገልገል ቀላል ነው እራስን በፊቱ ማቅረብ ብቻ ነው የሚጠይቀው::

በዚህ የያዕቆብን መልክት አጠናቀናል  ቃሉ ውስጣችንን ይቀይር ማስተዋልንም ጌታ ይስጠን::

የሐዋርያት ሥራ

የሐዋርያት ሥራ የሚያሳየው እንዴት መንፈስ ቅዱስ እየሱስን እየገለጠውና እያገነነው እንደሆነ ነው:: ቤተክርስትያን በእግዚአብሔር ኃይል እንደተመሰረተችም እናያለን::  ሰው እያየና እየሰማ የእግዚአብሔር መንፈስ በሰው ላይ ወረደ::  ድንገት እንደሚነጥቅ ዓውሎ ነፋስ ድምጽ ከሰማይ መጣ የነበሩበትንም ቤት ሞላው::  

 2: 4፤ በሁሉም መንፈስ ቅዱስ ሞላባቸው፥ መንፈስም ይናገሩ ዘንድ እንደ ሰጣቸው በሌላ ልሳኖች ይናገሩ ጀመር። 6፤ ይህም ድምፅ በሆነ ጊዜ ሕዝብ ሁሉ ተሰበሰቡ፥ እያንዳንዱም በገዛ ቋንቋው ሲናገሩ ይሰማ ስለ ነበር የሚሉትን አጡ።

በቃሉም እንደሚል:- 1: 3፤ ደግሞ አርባ ቀን እየታያቸው ስለ እግዚአብሔርም መንግሥት ነገር እየነገራቸው፥ በብዙ ማስረጃ ከሕማማቱ በኋላ ሕያው ሆኖ ለእነርሱ ራሱን አሳያቸው።

ስለ ትንሳኤው ከእነርሱ በላይ ምስክር ማን መሆን ይችላል?

2: 32፤ ይህን ኢየሱስን እግዚአብሔር አስነሣው ለዚህም ነገር እኛ ሁላችን ምስክሮች ነን፤ 

2: 24፤ እግዚአብሔር ግን የሞትን ጣር አጥፍቶ አስነሣው፥ ሞት ይይዘው ዘንድ አልቻለምና።

ደግሞም ትእዛዝን ሰጣቸው:- 

1: 4፤ ከእነርሱም ጋር አብሮ ሳለ ከኢየሩሳሌም እንዳይወጡ አዘዛቸው፥ ነገር ግን፦ ከእኔ የሰማችሁትን አብ የሰጠውን የተስፋ ቃል ጠብቁ፤ 5፤ ዮሐንስ በውኃ አጥምቆ ነበርና፥ እናንተ ግን ከጥቂት ቀን በኃላ በመንፈስ ቅዱስ ትጠመቃላችሁ፡ አለ።

ይህንንም ቃል ፈጸመው:- 

2: 33፤ ስለዚህ በእግዚአብሔር ቀኝ ከፍ ከፍ ብሎና የመንፈስ ቅዱስን የተስፋ ቃል ከአብ ተቀብሎ ይህን እናንተ አሁን የምታዩትንና የምትሰሙትን አፈሰሰው።

ዛሬም እግዚአብሔር ለእኛ ያለው እቅድ መንፈሱን በልግስና ማፍሰስ ነው :-

 2: 17፤ እግዚአብሔር ይላል፦ በመጨረሻው ቀን እንዲህ ይሆናል፤ ሥጋ በለበሰ ሁሉ ላይ ከመንፈሴ አፈሳለሁ፤ ወንዶችና ሴቶች ልጆቻችሁም ትንቢት ይናገራሉ፥ ጎበዞቻችሁም ራእይ ያያሉ፥ ሽማግሌዎቻችሁም ሕልም ያልማሉ፤ 

አሜን ስራው የእርሱ የሚሰራውም እርሱ ክብርም ለእርሱ ይሁን!!!  አሜን!!!

Introduction
የሐዋርያት ሥራ 1: 1-8
የሐዋርያት ሥራ 1: 9-11
የሐዋርያት ሥራ 1: 12-26
የሐዋርያት ሥራ 2: 1-4
የሐዋርያት ሥራ 2: 5-13
የሐዋርያት ሥራ 2: 14-21
የሐዋርያት ሥራ 2: 22-32
የሐዋርያት ሥራ 2: 33-42
የሐዋርያት ሥራ 2: 43-47
የሐዋርያት ሥራ 3: 1-10
የሐዋርያት ሥራ 3: 11-18
የሐዋርያት ሥራ 3: 19-26
የሐዋርያት ሥራ 4: 1-14
የሐዋርያት ሥራ 4: 15-22
የሐዋርያት ሥራ 4: 23-31
የሐዋርያት ሥራ 4: 32-37
የሐዋርያት ሥራ 5: 1-11
የሐዋርያት ሥራ 5: 12-16
የሐዋርያት ሥራ 5: 17-27
የሐዋርያት ሥራ 5: 28
የሐዋርያት ሥራ 5: 29-42
የሐዋርያት ሥራ 6: 1-7
የሐዋርያት ሥራ 6: 8-15
የሐዋርያት ሥራ 7: 1-60
የሐዋርያት ሥራ 8: 1-8
የሐዋርያት ሥራ 8: 9-25
የሐዋርያት ሥራ 8: 26-40
የሐዋርያት ሥራ 9: 1-9
የሐዋርያት ሥራ 9: 10
የሐዋርያት ሥራ 9: 11-19
የሐዋርያት ሥራ 9: 20-26
የሐዋርያት ሥራ 9: 27-31
የሐዋርያት ሥራ 9: 32-43
የሐዋርያት ሥራ 10: 1-7

የሐዋርያት ሥራ 10: 9-17፤ እነርሱም በነገው ሲሄዱ ወደ ከተማም ሲቀርቡ፥ ጴጥሮስ በስድስት ሰዓት ያህል ይጸልይ ዘንድ ወደ ጣራው ወጣ። 17፤ ጴጥሮስም ስላየው ራእይ፦ ምን ይሆን? ብሎ በልቡ ሲያመነታ፥ እነሆ፥ ቆርኔሌዎስ የላካቸው ሰዎች ስለ ስምዖን ቤት ጠይቀው ወደ ደጁ ቀረቡ፤

እግዚአብሔር እንደዚህ ነገሮችን እያቀናበረ የሚመራ ጌታ ነው::  ዛሬም ይችላልና ምራኝ እንበለው ሲናገረንም የምንሰማበትን ጸጋ ይስጠን::  የመንግስቱን ስራ በእኛም ይስራ::  አሜን

የሐዋርያት ሥራ 10: 38

38፤ እግዚአብሔር የናዝሬቱን ኢየሱስን 

በመንፈስ ቅዱስ 

በኃይልም ቀባው፥ 

እርሱም 

መልካም እያደረገ 

ለዲያብሎስም የተገዙትን ሁሉ እየፈወሰ ዞረ፥ 

እግዚአብሔር ከእርሱ ጋር ነበረና፤

እርሱ ተቀብቶ አገለገለ እኛንም ዛሬ ሲልከን ሁሉን አስታጥቆ ነውና ስራችን እርሱ የጀመረውን መቀጠል ነው::  ማንም ከማንም አይበልጥም እርሱ አባት ነውና ለማንም ሳያዳላ በተጠማ ሁሉ ላይ ኩመንፈሱ ያፈሳል:: መልካም ለማድረግ ምንም ችሎታ የለንም ነገር ግን በመንፈስ ቅዱስ ይቻላል:.  ሌላው ለዳያቢሎስ የተገዙትን መፈወስና መፍታት ነው ስራው ይህንን የሚያደርገው እርሱ እራሱ ነው በእኛ ውስጥ::  እስከ አለም ፍጻሜ ከእናንተ ጋር ነኝ ብሎን የለ ታድያ ለምን አይወስደንም ጎሉ ከእኛ ጋር ብቻ መሆን ከሆነ አይደል እንዴ? ነገር ግን ስራ አለን እርሱ በእኛ ሆኖ የሚሰራው::  የሙሉ ጊዜ አገልጋይ ብሎ የተወሰነ ሰው የለም ሁሉ ድንኳኑን እየሰፋ ሙሉ ጊዜ ያገለግላል አለበለዚያማ ጎዶሎ ጊዜ ልንሰጠው  ነው እርሱ  ሙሉ ዋጋ ከፍሎልን የምን የተሸራረፈ ነገር መስጠት ነ?!!

ተነስተን የጠላታችንን ደጅ እንውረስ!  ጠላትን ከምንሰማ ጌታችንን እንስማ ውጡ ውረሱ እያለን ነው::  ተባረኩ! 

የሐዋርያት ሥራ 11: 15፤ ለመናገርም በጀመርሁ ጊዜ መንፈስ ቅዱስ ለእኛ ደግሞ በመጀመሪያ እንደ ወረደ ለእነርሱ ወረደላቸው።

የአህዛብ ታሪክ የተቀየረበት ሐዋርያቱንም አሀ! ያስባለ ክፍል::  እንደእኔ ከሆነ መቼም ክርስቶስ ለእስራኤሎች የመጣና ርዝራዡ የደረሰኝ ነበር የሚመስለኝ:- እርሱ ግን እራሱን የዳዊት ልጅ ሳይሆን ይል የነበረው የሰው ልጅ ነበር::  በዘላለም እቅዱ ውስጥ እንዳለን ገና አዳም ሲወድቅ እመጣለሁ ብሎ ቃል እንደገባ ለሰው ልጅ ሁሉ መጣ::  አስቦ ወለደን!  እርሱ ፈልጎን መጣ!  ይህ ጌታ እኮ በሲና ተራራ ላይ የተገለጠው ነው ማንም እንዳይቀርብ ብሎ ያለ የቀረበ ሁሉ እንስሳም ቢሆን ይሞት ነበረ::  ሊቀ ካህናቱ እንኳን በአመት አንድ ጊዜ ሲገባ ጎትቶ ማውጫ እግሩ ላይ አስሮ  ነበር::  እንግዲህ ይሄ ጌታ ነው በእኛ ውስጥ ሊኖር የመጣው !!! አይደንቅም!  ማንም የማይለውጠው እውነት!  እግዚአብሔር በሰው ውስጥ መኖሩ!  የቀደሙት ነብያትን የሚጠቀምባቸው እየመጣና እየሄደ ነበር እንጂ አብሮ ኖሮ አይደለም::  ሙሴን እንኳን ከውጪ ነው ያናግረው የነበረው::  ዛሬ የሆነውን ቢያዩ መቼም ይደነግጣሉ እላለሁ ::   የሆነልን ግርም ይላል!  ስሙ ይባረክ ከእኛ ጋር ለሚኖረው ለዚህ ለከበረ ጌታ ክብር ይሁን::  አብሮን ሊኖር ለመጣው ጆሮአችንን ልባችንን እንስጠ እርሱ ሁሌ ይናገራል ይመራል::  ከእስትንፋሳችን ይልቅ ቅርብ ነው::  አሜን

የሐዋርያት ሥራ 12

5፤ ጴጥሮስም በወኅኒ ይጠበቅ ነበር፤ ነገር ግን በቤተ ክርስቲያን ስለ እርሱ ወደ እግዚአብሔር ጸሎት አጥብቆ ይደረግ ነበር።

የጸሎቱም መልስ:- 

የሐዋርያት ሥራ 12

7፤ እነሆም፥ የጌታ መልአክ ቀረበ በቤትም ውስጥ ብርሃን በራ፤ ጴጥሮስንም ጎድኑን መትቶ አነቃውና፦ ፈጥነህ ተነሣ፡ አለው። ሰንሰለቶቹም ከእጁ ወደቁ።

በሮች ሁሉ አውቀው እየተከፈቱ ከሰማይ ለመጣው መልስ ምላሽን ሰጡ::  እየጸለዮ ያሉት ወገኖች ግን ለዚህ ፈጣን መልስ የተዘጋጁ አይመስሉም::

የሐዋርያት ሥራ 12

15፤ እነርሱም፦ አብደሻል፡ አሉአት። እርስዋ ግን እንዲሁ እንደ ሆነ ታስረግጥ ነበር። እነርሱም፦ መልአኩ ነው፡ አሉ።

የሚገርመው:-

እርሱ ሳይሆን መልአኩ ነው::  መልአክ በር ያንኳኳል እንዴ?  ዘው ብሎ  ይገባል እንጂ::  ለማንኛውም ጴጥሮስ ተፈቷል ሰንሰለቱም ከእጁ ወድቆ መልስ ሊሆን በደጅ ላይ ዘገየ::  መጸለይ ብቻ ሳይሆን መቀበልንም እንለማመድ

ጌታ እየሱስ እንደተናገረው:-

የማርቆስ ወንጌል 11

23፤ እውነት እላችኋለሁ፥ ማንም ያለው ነገር እንዲደረግለት ቢያምን በልቡ ሳይጠራጠር፥ ይህን ተራራ፦ ተነቅለህ ወደ ባሕር ተወርወር፡ ቢል ይሆንለታል።

ጸሎት ከእግዚአብሔር ዘንድ መልስን ያመጣል:: መጸለይን ብቻ ሳይሆን መቀበልን በእምነት እንለማመድ!!

የሐዋርያት ሥራ 12

24፤ የእግዚአብሔር ቃል ግን ያድግና ይበዛ ነበር።

ይህ የሆነው ግድያው ማሳደዱ እያለ ነው::  ገዳዩ በትል ተመቶ እንቅፋት ከመሆን ተወገደ ወንጌልን የሚጋፋ አይበጀውም “ሳኦል ሆይ ለምን ታሳድደኛለህ የመውጊያውን ብረት ብትቃወም ለአንተ ይብስብሃል” እንደተባለው ሄሮድስ ላይ ደርሶ እናየዋለን::  እኛን የነካ እርሱን ነክቷል ግን እራሳችንን ጌታ እንደሚያየን እናያለን?!  አንዳንዴ  ጉዲፈቻ የሆንን ነው  የምንመስለው አባት እያለን አልተዋችሁም እያለን ደርሶ የጠላትን ሽንገላ እየሰማን ስንት ጊዜ ይሆን ጌታን ያማነው?  እግዚአብሔር ማስተዋል ይስጠንና እንደተወደዱ ልጆች እንመላለስ ወንጌላችንም መውረሱን ይቀጥል::

የሐዋርያት ሥራ 13

10፤ አንተ ተንኰል ሁሉ ክፋትም ሁሉ የሞላብህ፥ የዲያብሎስ ልጅ፥ የጽድቅም ሁሉ ጠላት፥ የቀናውን የጌታን መንገድ ከማጣመም አታርፍምን?

እንደነዚህ ያሉ ሰዎች በየቦታው አሉ::  መልካም ልብ ይዘው ሰዎች ወንጌልን እንዳይቀበሉ ሰይጣን የሰለጠነባቸው ለማሳት የሚጠቀምባቸው ወይም የዘራነውን ወንጌል የሚያጣጥሉ::  በጌታ በእየሱስ ስም አሁን የጌታን ወንጌል እንሰብካለንና ሊሰሙ ካሉ ሰዎች ዙሪያ ልቀቁ::  መንገዳችሁ ከመንገዳችን አይገናኝ!  ወንጌልን ሊሰሙ የሚፈልጉ ሁሉ መንገዳቸው ከመንገዳችን ይገናኝ!  ጌታ ሆይ ነፍሳትን ወደ ቤትህ ሰብስብ የመከሩ ጌታ ሆይ እኛንም ቀብተህ ላከን::  አሜን!

የሐዋርያት ሥራ 13

17፤ የዚህ የእስራኤል ሕዝብ አምላክ አባቶቻችንን መርጦ በግብፅ አገር በእንግድነት ሳሉ ሕዝቡን ከፍ ከፍ አደረጋቸው፥ ከፍ ባለችውም ክንዱ ከዚያ አወጣቸው። 18፤ በበረሀም አርባ ዓመት ያህል መገባቸው።

ጳውሎስንና በርናባስን ለዮልኝ ብሎ መንፈስ ቅዱስ ለይቶ ላካቸው::  በዚህ ስፍራ ላይ እንዳየነው ወደ ተላኩበት ሄደው ወንጌልን መስበክ ቀጠሉ ::  

እስራኤልን ከግብጽ ሲያወጣ አንዳቸውንም ተማምኖ አይደለም :: እነዚህ ሰዎች በባርነት የደቀቁ ግብጾቹ እንደፈለጉ የሚያደርጏቸው ነበሩ::  ግብጾቹ ደግሞ በጊዜያቸው ኃያላን ምርጥ ጦር ያላቸው ነበሩ ይህም እግዚአብሔርን አልገደደውም ህዝቡን ከፍ ባለው ክንዱ አወጣቸው::  ብቻውን ተዋጋላቸውና ከመከራቸው ገላገላቸው:: በበረሃም ለአርባ ዓመት ይህንን ሁሉ ሚሊዮን ህዝብ መገባቸው::  እንደው ስለለመድነው ነው እንጂ ቃሉን ይህ እኮ ትንግርት ነው::  ተጏድሎበት አያውቅ በየዓለቱ ምግባቸውን ይሰጣቸው ነበር::

ዛሬ ስለነገ አታስቡ ስንባል አንሰማም ዛሬን ሳንኖር ስለነገ እንዳሰብን አለን::  አትጨነቁ ተባልን ፤ እኔ አስብላችኃለሁ ፤  ወላጅ እንደሌላቸው ልጆች አልተዋችሁም እያለን ስንቶቻችን እሺ ታውቅልኛለህ ብለን እርፍ ብለን ነገራችንን ከምስጋና ጋር ሳንጨነቅ የምናሳስበው ይሆን?  እርሱ እኮ ሚሊዮኖችን በምድረበዳ ለአመታት መግቧል አቅርቦት በሌለበት ውስጥ እንኳን አልጎደለበትም::  የእኛ ጌታ እንዲሰራ ሁኔታዎችም መሟላት አያስፈልጋቸድም ምክንያቱም የሌለውን እንዳለ አድርጎ ይጠራዋል::  

እንታመን በዚህ ጌታ ግብጾች በእስራኤል ላይ የተጠበቡት በማድከም ነው ቃሉ ከሰሚዎቹ ጋር ሊዋሀድ አልቻለም ነበር::  ዛሬም  ይሄ ውጊያ ይሰራልና ከጠላት መጠበብ እናምልጥ አንተ ታውቅልኛለህ በማለት እንጽናና ዛሬን እየኖርን የተሰጠንን ተልኮ እንፈጽም እርሱን ወንጌልን መስበክ የጠፉትን መፈለግ ይብዛልን:: ከፍቅርም በቀር እዳ እንዳይኖርብን እንትጋ::  የእግዚአብሔር ጸጋ ይርዳን!!  አሜን

የሐዋርያት ሥራ 13

46፤ ጳውሎስና በርናባስም ገልጠው፦ የእግዚአብሔር ቃል አስቀድሞ ለእናንተ ይነገር ዘንድ ያስፈልጋል፤ ከገፋችሁትና የዘላለም ሕይወት እንዳይገባችሁ በራሳችሁ ከፈረዳችሁ ግን፥ እነሆ፥ ወደ አሕዛብ ዘወር እንላለን።

እኛም የታሰብን ነበርን በእግዚአብሔር ዓይን እንጂ ለእስራኤል የመጣው በረከት ርዝራዥ የደረሰን አይምሰለን::  ጌታ እየሱስ እራሱን የሰው ልጅ ብሎ ይጠራ ነበረ እነርሱ የዳዊት ልጅ ሲሉት::  ልክ ነው ከዳዊት ዘር ነው የመጣው ነገር ግን የሰውን ልጅ ሁሉ ሊታደግ መቷል::  በቅድሚያ ለአይሁድ ከዛም ለአህዛብ ሁሉ ነው ወንጌል::  የታዘዙትም በእየሩሳሌም በይሁዳ በሰማርያ ከዛም በዓለም ዙርያ ምስክሮቼ ሁኑ ነው::

አባት አለን አስቦ የወለደን ይህንንም ሲያስረዳ ዓለም ሳይፈጠር እኔና እናንተ ታስበናል::

ወደ ኤፌሶን 1

4፤ ዓለም ሳይፈጠር፥ በፊቱ ቅዱሳንና ነውር የሌለን በፍቅር እንሆን ዘንድ በክርስቶስ መረጠን።

ጌታ የሰራት ቀን ይህች ናት በእርስዋ ደስ ይበለን ሃሴትም እናድርግ::  እርሱ መልካም አባት ነውና  እንገዛለት በእሽታም መንፈስ እንሞላና የተላክነውን ወንጌልን ማድረስ እንቀጥል የደከሙትን እናበርታ የተቸገሩትን  እንርዳ የታመሙትን እንጠይቅ የታሰሩትን እንጎብኝና የእግዚአብሔርን ፍቅር በዚህ ሁሉ ውስጥ እናሳይ::

ተባረኩ!

የሐዋርያት ሥራ 14

3፤ ምልክትና ድንቅ በእጃቸው ይደረግ ዘንድ እየሰጠ ለጸጋው ቃል ስለ መሰከረው ስለ ጌታ ገልጠው እየተናገሩ ረጅም ወራት ተቀመጡ።

ለጸጋው ቃል እየመሰከረ በምልክትና በድንቅ እያጀበ በጎነቱን የሚያሳይ ጌታ ዛሬም ይሰራል አልተለወጠም::  በዚህ ክፍል ላይ ጳውሎስና በርናባስ ለረጅም ወራት የቆዩት አልጋ በአልጋ ሆኖ አልነበረም አገልግሎት ፈተናን አስነስተውባቸው ነበር ነገር ግን የጌታ መገኘትና ማጀቡ በዛላቸውና ነው::  

የዛን ዘመን ውጊያ ከአሁኑ ጋር ሲተያይ ይለያያል::  ሊገድለን የሚነሳ የለም አሁን ግን በይሉኝታ ተብትቦ እንዲሁም በስራና በጉዳያችን ላይ እንድናተኩር በማድረግ ተቀይሯል::  ይህንን የሰላ የጠላት ውጊያ ጌታ ይስበረው ከላያችንና ወንጌልን መስበክ የጠፉትን መፈለግ ይሁንልን::

አብዛኛዎቻችን ድንቅና ተአምራት በእኛም እንዲሰራ እንፈልጋለን::  መፈለግ ጥሩ ነው የሚመጣው ግን በጣብያው ላይ ነው የሚገለጠ::  እርሱ የጸጋውን ቃል ሊያጸና ይመጣልና አምነን እንሰማራ:: 

ተባረኩ!

የማቴዎስ ወንጌል 24

36፤ ስለዚያች ቀንና ስለዚያች ሰዓት ግን ከአባት ብቻ በቀር የሰማይ መላእክትም ቢሆኑ ልጅም ቢሆን የሚያውቅ የለም። 37፤ የኖኅ ዘመን እንደ ነበረ የሰው ልጅ መምጣት እንዲሁ ይሆናልና።

የመጨረሻው ዘመን ላይ ስለመሆናችን መቼም የሚጠራጠር የለም::  የሚገርመው የመጨረሻው መጨረሻ ላይ ነን::  ይህ የምንሰማው የአንድ አይነት ጾታ ጋብቻም ሆነ በየቦታው የእወቁልን ልፈፋቸው እየጨመረ የሚመጣ ነው ቃሉ እንደሚለው::  የኖኅ ዘመን እንደዛ ነበረና ሰው አምላኩን የረሳበት መብላት መጠጣትና መጋባት ነበረ ስራው::  እግዚአብሔርየሚያመልክና ፊቱን የሚፈልግ አልነበረም::  

ኖኅ ግን በእምነት መርከብን ሰራ መሳቅያ መላገጫ ነበረ ሲሰራው ነገር ግን መርከቡ ከተዘጋ በኃላ ጎርፉም ሲመጣ ልክ ማን እንደነበረ ታየ::  ዛሬም በህይወታችንና በአቅዋማችን የሚሳለቁ ይኖራሉ እኛ ግን ከሞት የተነሳውን ጌታ በህይወታችን ሾመን በመርከቡ ላይ ተሳፍረናል::  እኛ የእኛ አይደለንም የእርሱ ነን:: እንበርታ መምጣቱንም ወንጌልን በመስበክ እናስቸኩል!

ስለዚህ ጻድቁ ጽድቁን ማድረጉን ይቀጥል ኃጥአንም ኅጥያትን:: 

ማራናታ!  ጌታየሱስ ቶሎ ና!!

የሐዋርያት ሥራ 14

19፤ አይሁድ ግን ከአንጾኪያና ከኢቆንዮን መጡ፤ ሕዝቡንም አባብለው ጳውሎስን ወገሩ የሞተም መስሎአቸው ከከተማ ወደ ውጭ ጐተቱት። 20፤ ደቀ መዛሙርት ግን ከበውት ሳሉ፥ ተነስቶ ወደ ከተማ ገባ። በነገውም ከበርናባስ ጋር ወደ ደርቤን ወጣ።

እነዚሁ ሰዎች አማልክት በመካከላችን ናቸው ብለው ለጳውሎስና ለበርናባስ መስዋት እንሰዋ እንዳላሉ ወድያው ደግሞ እስከሞት ድረስ ይወገር ዘንድ ፈቀዱ ወይም ተባበሩ::  ጌታንም ኦሳእና ሲሉት ውለው በስንተኛው ቀን አስወግደው ስቀለው ብለዋል::  ዓለም በክፉ የተሞላ ነው::  ደብዳቢዎቹ ሞቷል ብለው ረክተው እንደሄዱ ብድግ ብሎ ወደ ከተማ ገባ ይላል መንቀሳቅስ እንኳን መቻሉ የሚገርም ነው እርሱ ግን በማግስቱ ረጅም መንገድ ሄደ ወደሚቀጥለው ከተማ ጌታውን ለማስተዋወቅ:: 

አንዳንዶቻችን ግን ይህንን ተናገሩን በክፉ አዩን ብለን የጌታን ስራ ትተን እንቀመጣለን እስኪ ጳውሎስ ያንን ቢያደርግ አስቡት?  ከዚህስ በላይ ይቅርብኝ ቢል?  እርሱ ግን በተአምራት ተፈውሶ ምናልባትም ከሞት አስነስቶት ነው አገልግሎቱን የቀጠለው::  

ምን ላይ ነን?  እራሳችንን እንይ ከሰው ሁሉ ጋር በሰላም እንኑር :: ከፍቅርም በቀር ሌላ እዳ እንዳይኖርብን የተነገረን ነን::  ጌታ ይመጣል ለእያንዳንዱም እንደስራው ይከፍለዋል::

ተባረኩ!

የሐዋርያት ሥራ 15

8፤ ልብንም የሚያውቅ አምላክ ለእኛ ደግሞ እንደ ሰጠን መንፈስ ቅዱስን በመስጠት መሰከረላቸው፤ 9፤ ልባቸውንም በእምነት ሲያነጻ በእኛና በእነርሱ መካከል አንዳች አልለየም።

እግዚአብሔር በእኛና በእስራኤላውያን መካከል አለየም ቀርበው ለነበሩትም ሰላምን እርቀንም ለነበርነው ሰላምን ሰበከን ይላል ቃሉ::  ከመጀመርያም እቅዱ የሰውን ልጅ ወደ ክብሩ መመለስ ነበረና::  አንድ ነገር ማስታወስ ያለብን ቢኖር ጠላት ሁልጊዜ ማንነትን ነው ጥያቄ ውስጥ የሚከተው::  ለሄዋን ያላት ሞትን አትሞቱም እንደ እግዚአብሔር መሆን ነው የሚቀርባችሁ ብሎ እግዚአብሔርን እንድትጠራጠር አደረጋት ከዛ በኃላ እርስዋን መጣል ቀላል ነበር::  የሆነው ምንድነው?

የተደረገልንን እንይ:-

1. መንፈስ ቅዱስንም በመስጠት መሰከረ – ማደርያው

2. ልባችንን በእምነት አነጻው – ቀደሰን

እንዴት ደስ ይላል!!  ልባችንን ስናምነው አነጻውና የራሱ ማደርያ አደረገው መንፈሱን በልባችን አፈሰሰው!!!!  ልብን የሚያውቅ ጌታ ቆሻሻውን፤ የከረፋውን፤ ክፉ አሳብ ማብቀያውን ከስሩ ነቅሎ አውጥቶ ጠራርጎ አሳመረውና ቀደሰውና በመንፈሱ ሞላን::  ልባችን የህይወት መውጫ ነው::  ከልባችን ጉዳይ አለውና ልባችንን ይፈልገዋል::  እኛ የራሳችን አይደለንም የእርሱ ነኝ በዋጋ ተገዝተናልና የሙሴ ህግ ቀንበር ነበርና አላስፈለገንም በእኛ ላይ አልተጫነም::  መዳናችን የከበረ ነው!!

ተመስገን ጌታዬ!!!

አሜን

የሐዋርያት ሥራ 15

24፤ ያላዘዝናቸው ሰዎች ከእኛ ወጥተው፦ ትገረዙ ዘንድና ሕግን ትጠብቁ ዘንድ ይገባችኋል፡ ብለው ልባችሁን እያወኩ በቃል እንዳናወጡአችሁ ስለ ሰማን፥

28-29፤ ለጣዖት ከተሠዋ፥ ከደምም፥ ከታነቀም፥ ከዝሙትም ትርቁ ዘንድ ከዚህ ከሚያስፈልገው በቀር ሌላ ሸክም እንዳንጭንባችሁ እኛና መንፈስ ቅዱስ ፈቅደናልና፤ ከዚህም ሁሉ ራሳችሁን ብትጠብቁ በመልካም ትኖራላችሁ። ጤና ይስጣችሁ።

በአንድ እግር የእግዚአብሔር መንጋ እንዲያነክስ የሚያደርገው ነገር ቢኖር ሕግንና ጸጋን ማቀላቀል ነው::  ሕግ ለእኛ አልተሰጠም ለእስራኤሎች እንጂ እርሱም ደግሞ እንዲፈጽሙት አይደለም እንደማይችሉትማ  ያውቃል ግን የቅድስናውን ልክ ለማሳየት ነበረ የተሰጠው ሁሉ ሐጥያትን አድርገዋል የእግዚአብሔርም ክብር ጎድሏቸዋል እንደሚለው ነው::

ዛሬ አናንክስ የእግዚአብሔር ጸጋ ክርስቶስን ለመምሰል እንድንችል በጣም በቂ ነው ያልተጫነብንን እየጫንን ክርስትና ከባድ ነው አንበል::  ለውጣችን በመንፈስ ቅዱስ ስለሚሰራ መንገር እስከማንችል ድረስ ይሆናል ግን አስር ጊዜ የተዘራውን ቃል ቆፍረን እያወጣል እንዳይበቅልና እንዳይለውጠን አናድርግ::  አሰራሩን እንመን::  በቃሉና በጸሎት በፊቱ እንገኝ ለውጥ የማይቀር ይሆናል::  የመንፈስ ፍሬ በህይወታችን ይታያል አለበለዚያ ማስመሰል ይሆንና ፍሬ ፈልጎ ሲመጣ ቅጠል ብቻ ሆነን እንገኛለን:: 

አድርጉ የተባልነው:

ለጣዖት ከተሠዋ፥  አጋንንትን እያመለኩ እያየን በመካከላቸው ተገኝተን ተካፋይ አለመሆን

ከደምም፥ ከታነቀም፥  ራቁ ነው  ምክንያቱም እንስሳ ሲታረድ ደሙ መፍሰስ እንጂ ለአገልግሎት መዋል የለበትም በደም ውስጥ ህይወት አለና  ደሙም ያልፈሰሰውን የታነቀን እንሰሳ ለምግብ አለመጠቀም ነው:: 

ዝሙት ይሸሻል እንጂ አውጣኝ ተብሎ እዛው መቀመጥ አይደለም::

እነዚህን ከውጪ መቆጣጠር የምንችላቸውን እናስወግድና በጸጋው ላይ እንኑር::

ክርስትና ቀላል ነው በእርሱ እጅ ቁጭ ብሎ መሰራት ነው::  ምክንያቱም ተፈጸመ ብሏል::

ተባረኩ

የሐዋርያት ሥራ 15

36፤ ከጥቂት ቀንም በኋላ ጳውሎስ በርናባስን፦ ተመልሰን የጌታን ቃል በተናገርንበት በየከተማው ሁሉ ወንድሞችን እንጐብኛቸው፥ እንዴት እንዳሉም እንወቅ፡ አለው።

የሐዋርያት ሥራ 15

41፤ አብያተ ክርስትያናትንም እያጸና በሶርያና በኪልቅያ ይዞር ነበር።

ጳውሎስ በልቡ የሚከብድበትንይ ቅድሚያ የሚሰጠው ስለአብያተ ክርስትያን ነው::  እዚህ ክፍል ላይ እንደምናየው ያለ እረፍት ከአንዱ ስፍራ ወደ ሌላው እየሄደ እያገለገለ እያለ እንደገና  መጎብኘትን ፈለገ::  ለማጽናት ያሉበትን ለማወቅ የጎደሉበትም ነገር ካለ  ለመሙላትና ለማስተማር ለማጽናትም ነው::   እኛም ማንንም ሳንጠብቅ የደከሙትን ማበረታታት የበረቱትን ቀጥሉበት በማለት የጌታ ዓይን ባለበት የእኛምዓይኖች ሊሆኑ ይገባል::  ይህ ለሙሉ ጊዜ አገልጋይ የሚተው አይደለም እንደዛማ ከሆነ እኛ የግማሽ ጊዜ አገልጋይ ልንባል ነው እየሱስ ግን ሙሉ ህይወቱን ሰቶን ከሞት ታድጎን ልጁ አድርጎናልና ሙሉ ጊዜ አገልጋይ እንደሆንን እንወቅ:: ሁሉ ካህን ነው የካህናት መንግስት ነው የመሰረተው ለአባቱ ካህናት እንድንሆን አበቃን::  ወደኃላ የለም ባለን ጊዜ ገንዘብ እውቀትና ጸጋ በነጻየተሰጠንን በነጻ እንሰጣለን::  ዓይናችን ወንድምና እህቶቻችን ላይ ይሁን ::  እኔ ብቻ ልደግ አንበል::  እስኪ ዛሬ አንድን የምታውቁትን ሰው ወደ ልባችሁ እንዲያመጣ ጸልዩና ሲያመጣላችሁ ደውላችሁ ወይም በአካልም ከተገናኛችሁ እሰየው ጸልዩለትና ጌታ እንደሚወዳቸው ተናገሩና አሳውቁኝ::  የጌታን ፈቃድና ድምጽ መለማመድ እንጀምር::  እርሱ አሁንም ማን ይላክልናል እያለ ነስ ሁሉ ወደገዛ መንገዱ እየሄደ ስለሆነ እኛ እስኪ ቆም ብለን እኔን ላከኝ እንበለው::  እርሱ ሁሌ ይናገራልና እንስማው::

ተባረኩ!!

የሐዋርያት ሥራ 16

6፤ በእስያም ቃሉን እንዳይናገሩ መንፈስ ቅዱስ ስለ ከለከላቸው በፍርግያና በገላትያ አገር አለፉ፤

የሐዋርያት ሥራ 16

9፤ ራእይም ለጳውሎስ በሌሊት ታየው፤ አንድ የመቄዶንያ ሰው፦ ወደ መቄዶንያ ተሻገርና እርዳን፡ እያለ ቆሞ ሲለምነው ነበር።

መንፈስ ቅዱስ ወዴት መሄድ እንዳለብን በግልጽ የሚናገር ጌታ ነው::  ወደ እስያ ከልክሎ ወደ መቄዶንያ ላካቸው::  እስያ ወንጌል አያስፈልግም እያለ አይደለም ግን ጊዜው አይደለም ወይም የተሻለ እሳብ ስላለው ብቻ ነው::  

እኛም ዛሬ ያልተላክንበት ሄደን ጊዜያችንን ብቻ ሳይሆን የእርሱንም ጊዜ እንዳናባክን እግዚአብሔር ይርዳን::  እግዚአብሔር ወደሚመራን እንሂድ እንጂ ደስ ወዳለን መሆን የለበትም::  የጌታ ዓይኖች ወዴት ነው እያዩ ያሉት?  የእኛም ያንን ማየትና መታዘዝ ይሁንልን:: እርዳታችንን የሚፈልግ ማን ይርዳኝ ፤ ወዴት ልድረስ፤  የሚል አለና እንንቃ በጌታ ቤት ያለ ስራ እንድንቀመጥ ፈቃዱ አይደለም::  በሚሰጠን ጸጋ እናገልግል አለበለዚያ ጸጋ ምን ያደርግልናል?! 

አባት ሆይ በፊትህ ነኝና እኔን ላከኝ ለኔም ለእናንተም ጸሎቴ ነው:: ጌታ ይርዳን!

የሐዋርያት ሥራ 16

14፤ ከትያጥሮን ከተማም የመጣች ቀይ ሐር ሻጭ እግዚአብሔርን የምታመልክ ልድያ የሚሉአት አንዲት ሴት ትሰማ ነበረች፤ ጳውሎስም የሚናገረውን ታዳምጥ ዘንድ ጌታ ልብዋን ከፈተላት።

ሊድያ እዚህ ክፍል ላይ እንደሚናገረው እግዚአብሔርን የምታመልክ ናት ግን ክርስቶስን አላወቀችም ነበረ::  ብዙዎች ዛሬ ለእግዚአብሔር የሚቀኑ እናመልካለን የሚሉ ክርስቶስን በግል የማያውቁ አሉ::  እግዚአብሔር ግን ልባቸውን ለምንናገረው ቃል ካልከፈተ ማስተዋል አይችሉምና ጸሎታችን ውስጥ ማስገባት አለብን::  ልባቸውን ክፈት ብለን ላልዳኑት ቤተሰቦቻችን ብንፀልይ ሌላ የመከሩ ሰራተኛ ሊመሰክርላቸው ይችላልና እንፀልይ::  የጻድቅ ሰው ፀሎት በስራዋ እጅግ ኃይልን ታደርጋለች:: እንደፈቃዱ አንዳች ብንለምን ይሰማናልና::

የሐዋርያት ሥራ 16

17፤ እርስዋ ጳውሎስንና እኛን እየተከተለች፦ የመዳንን መንገድ የሚነግሩአችሁ እነዚህ ሰዎች የልዑል አምላክ ባሪያዎች ናቸው፡ ብላ ትጮኽ ነበር።  18፤ ይህንም እጅግ ቀን አደረገች። ጳውሎስ ግን ተቸገረና ዘወር ብሎ መንፈሱን፦ ከእርስዋ እንድትወጣ በኢየሱስ ክርስቶስ ስም አዝሃለሁ፡ አለው፤ በዚያም ሰዓት ወጣ።

አሜን ዛሮም በስሙ አጋንንት ይወጣል::  አጋንንትን አውጡ ተብለን የተሾምን ነን::  እንዳዘዘው በዚያው ሰዓት ወጣ!!!  ስሙ ይባረክ ይህ የተቀባ ስም ለእኛ ተሰቶናል::

ይህች የሟርተኝነት መንፈስ ያለባት ሴት ምን አጠፋች?  እየተናገረች ያለችው ጥሩ ነገር ነው::  የመዳንን መንገድ የሚናገሩ የልዑል አምላክ ባሪያዎች ናቸው፡  ልክ ናት ነገር ግን ከአጋንንት ምስክርነትን ጌታ አይፈልግም አብሬ የምሰራ ነኝ እያለ እያስመሰለ ወደጸሎት ሲሄዱ ብዙ ቀን አወካቸው::  ማንነቱ ገብቶት ነበረና ጳውሎስ ግን ይህንን መንፈስ አስወጣው::  

መንፈሳችን የነቃ ይሁን የእግዚአብሔርን መንፈስና የአጋንንትን መንፈስ እንለይ::  ትክክለኛ የሚመስልን ቃል የተነበየ ሁሉ ከእግዚአብሔር አይደለምና በዚች ሴት ውስጥ የተናገረው መንፈስ ትክክል ነበረ::  መንፈስን እንመርምር በሰዎች ላይም ያለውን የህይወት ፍሬ እያየን ህብረት እናድርግ::  

ከእንደዚህ አይነት ከረቀቀ የጠላት አሰራር ጌታ እኛንም ቤተክርስቲያንንም እንዲታደግ እና እንዲያነቃ እንጸልይ::

የሐዋርያት ሥራ 16

24፤ እርሱም የዚህን ዓይነት ትእዛዝ ተቀብሎ ወደ ውስጠኛው ወኅኒ ጣላቸው፥ እግራቸውንም በግንድ አጣብቆ ጠረቃቸው። 25፤ በመንፈቀ ሌሊት ግን ጳውሎስና ሲላስ እየጸለዩ እግዚአብሔርን በዜማ ያመሰግኑ ነበር፥ እስረኞቹም ያደምጡአቸው ነበር።  26፤ ድንገትም የወኅኒው መሠረት እስኪናወጥ ድረስ ታላቅ የምድር መንቀጥቀጥ ሆነ፤ በዚያን ጊዜም ደጆቹ ሁሉ ተከፈቱ የሁሉም እስራት ተፈታ።

በምሪት ተመርቶ መቶ መደብደብና ወደ ወህኒ መጣልን ምን ይሉታል?!  ቀጥታ ወደ ጥርጣሬ የሚከት ነገር ነው ቅዥት ነበር ማለት ነው?  አያስብልም? ስንት ጊዜ ጠላት እንደዚህ እያለ ጊዜያችንን በልቶብን ይሆን?  አልጋ በአልጋ ነው አልተባልንም መንገዱ ጌታን ስንከተል የተሰጠን ማረጋገጫ አሸንፌአለሁ አይዟችሁ ነው!!  ጌታ ድል ነስቷል::

ልብሳቸውን ገፈው እንዲደበድቧቸው ገዢዎቹ አዘዙ::  ይህንም አደረጉ እናም ወደ ውስጠኛው እስር ቤት ጥለው እግራቸውንም በግንድ አጣብቆ ጠረቃቸው ይላል ቃሉ::  መቼም ከዚህ በኃላ መሆን የነበረበት እንዴት እዚህ ደረስን? ብሎ ነገሩን ሁሉ ማብላላት ነበር አይደል?!  እነርሱ ግን አምልኮን ጀመሩ::  ስለተደበደብኩኝና ስለቆሰልኩ አምልኮን አልቀንስም አሉ::  እስረኞቹ ሁሉ እየሰሙ አምልኮን ቀጠሉ ምን ይሉናልም አላሉ ::  እስረኞቹ መቼም እዚህ እንዲታሰሩ ያደረጋቸውን እንዴት ይቀጥላሉሳይሉ አይቀርም ቅጣት እኮ እንድንተው ለማስገደድ አይደልእነሱ ግን አብዝተው ቀጠሉ::   የላካቸውን እንዲሁም እየተዋጋቸው ያለውን ጠንቅቀው ያውቁ ነበርና::  አሳሪ ባለስልጣን ነኝ ባይ አስሮ ሲሄድ ጌታ ደግሞ  ፈታ ብላችሁ አምልኩ ብሎ የነሱን ብቻ ሳይሆን እስር ቤቱንም ክፍት አደረገው የኔ ጌታ ሰንሰለቶች ሁሉ ወደቁ::  አምልኮውን የሰሙ ታሳሪዎች ውጤቱንም አዩ:: ሰንሰለቶች ስራቸውን አቆሙ እነዚህን የእግዚአብሔርን ልጆች አናስርም ብለው አመጹ::  ሃሌሉያ!

በምናልፍበት ነገር ያንኑ ነገር አንስተን ብንዘበዝብ መፍትሄ የለውም ሁሉን ወደሚችል ጌታ ዓይናችንን እናንሳና እናምልከው::  እርሱ እጁን ልኮ ካለንበት ጎትቶ ያወጣናልና!!! አሜን!

ስሙ ይባረክ!

የሐዋርያት ሥራ 16: 27-32

27፤ የወኅኒውም ጠባቂ ከእንቅልፉ ነቅቶ የወኅኒው ደጆች ተከፍተው ባየ ጊዜ፥ እስረኞቹ ያመለጡ መስሎት ራሱን ይገድል ዘንድ አስቦ ሰይፉን መዘዘ። 28፤ ጳውሎስ ግን በታላቅ ድምፅ፦ ሁላችን ከዚህ አለንና በራስህ ክፉ ነገር አታድርግ፡ ብሎ ጮኸ። 30፤ ወደ ውጭም አውጥቶ፦ ጌቶች ሆይ፥ እድን ዘንድ ምን ማድረግ ይገባኛል? ኣላቸው። 31፤ እነርሱም፦ በጌታ በኢየሱስ ክርስቶስ እመን፡ አንተና ቤተ ሰዎችህ ትድናላችሁ፡ አሉት።

የወህኒው ጠባቂ የነቃው በምድሩ መናወጥ ይሆናል እንጂ ዝማሬና አምልኮውን አልሰማም::  ያሰራቸው ሁሉ ተፈተው የእስር ቤቱ በር ሁሉ ተከፍቶ ሲያይ እስረኛም አልቀረ ያሰኛል::  ነገር ግን እስረኞቹ እግዚአብሔርን መፍራትና ድንጋጤ ውስጥ ነበሩና አልተነቃነቁም::  ወደዚህ ናና እርዳን ያለው ሰው ይህ ሰው ይሆንን? በዚህ ሰው ጥሪ መተው ከስራቸው ጠላት ሊያጠፋው ነበረ እግዚአብሔር ግን  ጳውሎስን ተጠቅሞ እራስህን አታጥፋ አለው::  ምን ላድርግ እንድድን?  የሚገርም ጥያቄና ጌታም የሚፈልገው ይህንን ነበረ:: መልሱም በጌታ በኢየሱስ ክርስቶስ እመን፡ አንተና ቤተ ሰዎችህ ትድናላችሁ፡ አሉት።  ሰዎች አምነው ይድኑ ዘንድ እኛን ልኳል ጌታ በምንሰራበትም ይሁን በምንውልበት ለጌታ ምስክሮች እንሁን::  ይህ ሰው አሳሪ ይመስላል የታሰረው መፈታት ያለበት ግን እርሱ ነበረና እርሱንና ቤተሰቡን ጌታ አሰበ:: የፊልጵስዮስ ቤተክርስቲያን አባላት መካከል ሊድያ እና ይህ የእስር ቤት ጠባቂ ከነቤተሠቡ ይገኙበታል::  ሲጽፍላቸውም በመልእክቱ እንዴት እንዳልተጠየፉት ይናገራል ምክንያቱም ተደብድቦ ሞተ ብለው ጥለውት ከነበረበት ከተማ ነበር  በማግስቱ ወደዝች እንደገና ደብድባ  ከነቁስሉ በድንጨት ተጠርቆ የታሰረበት ከተማ የመጣው:: ይገርማል!  እኛ ምን ሆንን? እንደዚህ ነበር ወንጌል እኛጋ የደረሰው ዛሬ ግን ግፋ ቢል ግልምጫን ፈርተን ምን ይሉን እያልን ወንጌልን ከመናገር ተቆጥበናል::  ሰዎች በእስራት ላይ ናቸውና መፍትዎችም እኛ ነንና እንነሳና ጌታን ለፍጥረት ሁሉ እንስበክ::

ምስክሮች እንሆን ዘንድ ጌታ ጸጋውን ያብዛልን!  እርሱ ቅርብ ነውና አብሮን ይሰራል::

የሐዋርያት ሥራ 16: 32-40

32፤ ለእርሱና በቤቱም ላሉት ሁሉ የእግዚአብሔርን ቃል ተናገሩአቸው።

33፤ በሌሊትም በዚያች ሰዓት ወስዶ ቍስላቸውን አጠበላቸው፥ ያን ጊዜውንም እርሱ ከቤተ ሰዎቹ ሁሉ ጋር ተጠመቀ፤

በዛችው ለሊት መዳን ከነመላ ው ቤተሰብ ሆነለት ደግሞም ተጠመቁ::  በነጋታው ልቀቁዋቸው የሚለው ትዕዛዝ ሲመጣ ጳውሎስና ሲላስ ስራቸውን ጨርሰዋል::  የሚባክን ጊዜ የለም !  እኛስጋ ?  እግዚአብሔር ይርዳንና የጌታን ሰዓት እንዳናባክን በእርሱ በሚሰራው ታምነን እንሰማራ:;  ዛሬ ሌላውን እናስብ ከራሳችን እንውጣ የእኛን ጌታ ይሰራዋል በዝች ምድር ላይ መጻተኞች እንደሆንን ቃሉ ይነግረናልና::  ጠላት ሁልጊዜ ስለራሳችን ሊያሳየን ነው የሚፈልግው ንስር ሆነን በነፃነት ልንኖር ሲገባን ጥሬ ለቃሚ ዶሮ አድርጎናል::  ፈጽሞ የእግዚአብሔር ፈቃድ የሆነው በመንፈስ ቅዱስ እንድንመራና ክንፎቻችንን ዘርግተን ንፋሱ ወደሚወስደን ልንበር የተጠራን ነን::

አባት ሆይ ኃይልን ስጠንና ምስክሮችህ እንሁን! አሜን

የሐዋርያት ሥራ 17

10፤ ወዲያውም ወንድሞች ጳውሎስንና ሲላስን በሌሊት ወደ ቤርያ ሰደዱአቸው፥ በደረሱም ጊዜ ወደ አይሁድ ምኵራብ ገቡ ፤

11፤ እነዚህም በተሰሎንቄ ከሚኖሩት ይልቅ ልበ ሰፊዎች ነበሩና፦ ነገሩ እንደዚሁ ይሆንን? ብለው ዕለት ዕለት መጻሕፍትን እየመረመሩ ቃሉን በሙሉ ፈቃድ ተቀበሉ።

የጳውሎስ አገልግሎት ፍሬ እያፈራ ጢሞትዮስን የመሰለ ረዳት እግዚአብሔር ሰቶት ፊሊጲስዮስ ፤ ተሰሎንቄ ፤እና ቤሪያ የሚገኙት አብያተ ክርስትያናት ተመስርተዋል ምንም እንኳን ከሁሉ ቦታ እያባረሩት ቢሆንም መንፈስ ቅዱስ አብያተ ክርትያናትን አጽንቷቸዋል::

የቤሪያ ቅዱሳን ግን የሚገርሙት እንደዚህ ይሆንን ቃሉ ብለው መረመሩ::  ጌታ እየሱስ እንደተናገረው መጽሐፍት ሁሉ ስለእኔ ይናገራሉ እንዳለው ከቃሉ እውነትነቱን አመሳከሩ እንጂ በስሜት ወደ መነዳትና መልክቱን ያመጡትን ወደ መጉዳት አልሄዱም:: ልባቸው ለወንጌል የተዘጋጀውን ወደእኛ ያምጣ::  እንደሊድያና እንደ ቤሪያ ሰዎች:: 

ብዙ አይነት ሰው ሊገጥመን ስለሚችል ስንመሰክር እንታገስ አንዲት ጠጠር አስቀጠን ሊሆን ይችላል በአንድ ሰው ህይወት ውስጥ የምንሄደው ሌላው መቶ ደግሞ ሌላውን ይሰራል::  ተስፋ አንቁረጥ በእግዚአብሔር ፊት እንጸልይ ነፍሳትን እንዲሰጠንና እንዲያወርሰን::  ክርስትና ቤተክርስቲያን ስንመጣ ብቻ የምንኖረው ሳይሆን በስራ ስፍራም እቤትም የትም የምንገኝበት ቦታ ሁሉ ላይ መሆን አለበት::  ጌታን እናብለጭልጨው የስራ ስፍራችን የተሰማራንበት  መስካችን ይሁን ጌታን ለማሳየት:: 

ጸጋው እንደሚረዳን አምናለሁኝ እንታዘዝ እርሱ ያስደንቀናል::

ተባረኩ!

የሐዋርያት ሥራ 17

16፤ ጳውሎስም በአቴና ሲጠብቃቸው ሳለ፥ በከተማው ጣዖት መሙላቱን እየተመለከተ መንፈሱ ተበሳጨበት።

አንድ ጥያቄ እራሴን ጠየኩኝ አሁን ጳውሎስን ያበሳጨው ያበሳጨኛል?  ወይስ ተለማመድኩት? ምንም አይደለምወይም ምን ቸገረኝ ይሆን::  እርሱ ግን ጣዖትን ሲያይ ተበሳጨበት መንፈሱ::  አዲስ አበባ እንብርቷ ላይ እሬቻ ሲመለክ አንዳንዱ የሰላም አምላክ ነው ሌላው የምስጋና በዓል ነው እያለ ያሽሞነሙነዋል::  ይሄ ጣዖት ነውና ሊያበሳጨን ልንቃወመው ይገባል እንጂ ስናልፍ ቡናቸውን እንኳን መጠጣት የለብንም::  ሐዋርያት የተውልን አንዱ መመሪያ ለአህዛብ ለጣዖት የተሰዋ አትንኩ ነው:: እግዚአብሔር ከምድራችን ላይ ይስበረው::  በእየሱስ ስም ተመልሶ በዛች ምድር አይመለክ!  እርሱን ማምለክ ከጀመሩ ጀምሮ ምድሪቱ በደምና በረሀብ እየታመሰች ነውና አጥብቀን ጠልተነው ልንቃወም ይገባል ይህ አራጅ መንፈስ ነው እየተመለከ ያለው::  

እኛ እርኩስን አንነካም ለእግዚአብሔር እራሳችንን እንቀድሳለን የምናውቀውንም ወገን ሁሉ በዚህ ሀሳብ እናንቃ ሌላ ረዳት አምላክ የለም አምላካችንስ አንድ አምላክ ሰማይንና ምድርን የፈጠረ በውስጥዋም ያሉትን ሁሉ ያለ ረዳት የፈጠረ ነውና ስሙ ይባረክ!

የሐዋርያት ሥራ 17

24፤ ዓለሙንና በእርሱ ያለውን ሁሉ የፈጠረ አምላክ እርሱ የሰማይና የምድር ጌታ ነውና እጅ በሠራው መቅደስ አይኖርም፤ 25፤ እርሱም ሕይወትንና እስትንፋስን ሁሉንም ለሁሉ ይሰጣልና አንዳች እንደሚጎድለው በሰው እጅ አይገለገልም።

30፤ እንግዲህ እግዚአብሔር ያለማወቅን ወራት አሳልፎ አሁን በየቦታቸው ንስሐ ይገቡ ዘንድ ሰውን ሁሉ ያዛል፤

ጳውሎስ የጀመረው ስብከቱን ከዛው በዙሪያው ካለው ነገር ወይም ሁኔታ ተነስቶ ነው::  ለማይታወቅ አምላክ ብላችሁ የምታመልኩት ላሳውቃችሁ በሚል ነው የጀመረው ጥበብን ለመስበክ መንፈስ ቅዱስ ይሰጠናልና በእርሱ ላይ እንደገፍ::  ይህ ያላወቁት አምላክ ግን ሁሉን የፈጠረ  ህይወትን የሚሰጥ ነው::  ሌሎች አማልክት ግን በሰው የሚገለገሉ ሰው የሚሸከማቸው ናቸው::  የእኛ አምላክ ግን አንዳች እንደሚጎድለው በሰው እጅ አይገለገልም።  ሰውም በሰራው ህንፃ አይኖርም በእኛ ውስጥ እንጂ::  

የእግዚአብሔር ፈቃድ ሰው ሁሉ ወደ ንስሃ እንዲመጣ ነው::  ጌታም ሲመጣ የሰበከው እኛም የተባልነው  የእግዚአብሔር መንግስት ቀርባለችና ንስሃ ግቡ ነውና ተልዕኮአችንን እንፈጽም::  ጌታ ይመጣል አይዘገይም በዚች ምድር ሊፈርድ ይመጣል:: ሁሉም እንዲድኑ ነው ፈቃዱ በዚህም የእግዚአብሔር መንፈስ ረዳታችን ነው::  የሰዎች መጥፋት ግድ ይበለንና ለመድረስ እንሂድ::

ተባረኩ!

የሐዋርያት ሥራ 18

1፤ ከዚህም በኋላ ጳውሎስ ከአቴና ወጥቶ ወደ ቆሮንቶስ መጣ።

9-10፤ ጌታም ሌሊት በራእይ ጳውሎስን፦ እኔ ከአንተ ጋር ነኝ፥ ማንም ክፉ ሊያደርግብህ የሚነሣብህ የለምና አትፍራ፥ ነገር ግን ተናገር ዝምም አትበል፤ በዚህ ከተማ ብዙ ሕዝብ አሉኝና፡ አለው።

እዚህ ክፍል ላይ የምናየው የቆሮንቶስ ቤተክርስቲያን ስትመሰረት ነው::  በዚች ከተማ ብዙ ህዝብ አለኝ ማንም አይነካህም ስራ አለው ጌታ ስለዚህም ጳውሎስ ለ18 ወራት አገለገላቸው::  አይሁድም አንሰማም ስላሉት የልብሱን ትብያ አራግፎ ደማችሁ በእናንተ ላይ ነው ብሎ ወደ አህዛብ ፊቱን አዞረ:: 

በዚሁ ስፍራ ነበረ ድንኳን ሰፊዎች እንደእርሱ የሆኑትን አቂላና ጵርስቅላን  ያገኘው እነርሱም ጌታን ለማገልገል እራሳቸውን የሚሰጡ ባልና ሚስት ናቸው::

እግዚአብሔር ሰዎችን በህይወታችን ላይ ያመጣል  ይሰጠንማል::  እነዚህ ባልና ሚስቶች አብረውት መጏዝን ጀመሩ::  በዙሪያችን ስለሰጠን ሰዎች ጌታን እናመስግን::  ሰው ትልቅ ስጦታ ነውና መንግስቱን አብረን እንወርሳለን በዚህም በምድር  ጌታን በሰጠን ጸጋ እናገለግላለን::   ጌታ ከእኛ ጋር ነው እንበርታ::  በተሰጠንም መክሊት እናገልግልና እናትርፍ::

ተባረኩ!

የሐዋርያት ሥራ 17

31፤ ቀን ቀጥሮአልና፥ በዚያም ቀን ባዘጋጀው ሰው እጅ በዓለሙ ላይ በጽድቅ ሊፈርድ አለው፤ ስለዚህም እርሱን ከሙታን በማስነሣቱ ሁሉን አረጋግጦአል።

መቼም ለዓለም ይህ እውነት የማይገባ ነው::  እነዚህ ፈላስፎች በዝች ትንሽዬ ጭንቅላታቸው ቢያወጡ ቢያወርዱ የትኛውንም ቀመር ቢቀምሩ የማይደርሱበት እውነት ቢኖር ትንሳኤ ነው::  የሙታን ትንሳኤ እንዳለ ሲነግራቸው ግማሹ አሹፎ ሄደ::  የሰው ልጅ ክቡር መሆኑን እንኳን አላወቁም:: 

እኛ ግን ትንሳኤን የምንጠባበቅ ነን::  ከክርስቶስ ጋር የሞትና በትንሳኤውም አብረን የተነሳን  ነን::  ድሉ ተጠናቋል!!  ትንሳኤ ሆነልን!!!

በዚህ የአዲስ ዓመት ዋዜማ ላይ ቆመን ዘመናችንን ለዚህ ሊፈርድ ለሚመጣው ጌታ እንዋጅለትና  እርሱ እንደወደደ  በእኛ ይስራ!  ክብሩንም ይግለጥ!  እኛ የምናመልከው ህያው ጌታ ነውና የሚሰማ የሚመልስ የሚናገር ነው::  ስሙ ይባረክ እንኳንም የራሱ አደደገን::

በእኛ ውስጥ ስላስቀመጠው ማንነቱና ስለሰጠን ድል ጌታን እናመስግን::  አሮጌው ማንነት አልፏል ሁሉ አዲስ ሆንዋል!!!

አሜን

መልካም አዲስ ዓመት!

የሐዋርያት ሥራ 18

12፤ ጋልዮስም በአካይያ አገረ ገዥ በነበረ ጊዜ፥ አይሁድ በአንድ ልብ ሆነው በጳውሎስ ላይ ተነሡ፥ ወደ ፍርድ ወንበርም አምጥተው፦

15፤ ስለ ቃልና ስለ ስሞች ስለ ሕጋችሁም የምትከራከሩ ከሆነ ግን፥ ራሳችሁ ተጠንቀቁ እኔ በዚህ ነገር ፈራጅ እሆን ዘንድ አልፈቅድምና፡ አላቸው።

ጳውሎስን ለመክሰስ በአንድ ልብ ሆነው ተነሱና ወደ ፍርድ ወንበር አመጡት::  ጋልዮስ ግን ነገሩን አፈረሰባቸው::  ጠላት ጳውሎስን ለማዘግየትም ይሁን ለመበቀል እነዚህን ሰዎች አስነስቶ ነበር ነገር ግን አምላኩ እግዚአብሔር ፍርድ እንዲሰጥ ብቻ ሳይሆን ነገሩንም ዋጋ ማሳጣት ይችላልና ብቻ እኛ በጌታ ላይ ይሁን ዓይናችን::  እርሱ የሚሰራውን ያውቃልና ውጊያው የእግዚአብሔር ነው::  ሁሉ በአንድ አፍ ሆነው ሲከሱት እንዴት ዋጋ ያጣል ከሰማይ ካልሆነ በቀር?

ዛሬም የጠላትየሰላው ምክርና ክስ አይሰራም የወንድሞች ከሳሽተጣለ እንደሚል ቃሉ አሁንም በእኛ ላይ አይሰምርለትም::  ስለእኛ የሚማልድ አለ በሰማይ!

ስሙ ይባረክ!

የሐዋርያት ሥራ 18

22፤ ወደ ቂሣርያም በደረሰ ጊዜ ወጥቶ ለቤተ ክርስቲያን ሰላምታ ከሰጠ በኋላ ወደ አንጾኪያ ወረደ።.  23፤ ጥቂት ቀንም ቆይቶ ወጣ፥ ደቀ መዛሙርትንም ሁሉ እያጸና በገላትያ አገርና በፍርግያ በተራ አለፈ።

ጳውሎስ ቅዱሳንን እያጸና ያልፋል ምክንያቱም አንዳች የጏደለ ካለ ለመሙላት ይላል በሌላ ስፍራ::  እንዲሁም የማውቀውን  ሁሉ አሳወኳችሁ ተጋሁ ይላል::  ትጋቱ የሚገርም ነው::  እግዚአብሔር ለእኛም ይህንን ትጋት ይስጠን! 

ቅዱሳንን ማየትና አንዱም የአንዱን ሸክም መሸከምን ያብዛልን

የሐዋርያት ሥራ 18

24፤ በወገኑም የእስክንድርያ ሰው የሆነ ነገር አዋቂ የነበረ አጵሎስ የሚሉት አንድ አይሁዳዊ ሰው ወደ ኤፌሶን ወረደ፤ እርሱም በመጻሕፍት እውቀት የበረታ ነበረ።

26፤ እርሱም በምኵራብ ገልጦ ይናገር ጀመር። ጵርስቅላና አቂላም በሰሙት ጊዜ፥ ወስደው የእግዚአብሔርን መንገድ ከፊት ይልቅ በትክክል ገለጡለት።  27፤ እርሱም ወደ አካይያ ማለፍ በፈቀደ ጊዜ፥ ወንድሞቹ አጸናኑት፥ ይቀበሉትም ዘንድ ወደ ደቀ መዛሙርት ጻፉለት፤ በደረሰም ጊዜ አምነው የነበሩትን በጸጋ እጅግ ይጠቅማቸው ነበር፤

ጳውሎስ ጵርስቅላና አቂላን ደቀመዝሙር አደረገ እነርሱ ደግሞ አጵሎስን አገለገሉ::  የተጠራነው ደቀመዝሙርትን እንድናፈራ ነው::  ይህ ሰው በጸጋ እጅግ  ጠቀማቸው እንደሚል በእያንዳንዳችን ውስጥ ያለው ጸጋ የክርስቶስን አካል ለማገልገል አስፈላጊ ነው::  ጸጋ አልተሰጠኝም የሚል የለምና ለሁላችንም አከፋፍሏል:: የኤፌሶን ቅዱሳን በደንብ የተገለገሉና የተለወጡ ናቸው::  የኤፌሶንንም መልክት ስናየው ጥልቀት ያለው መንፈሳዊ መልእክት  ነው::  ሰው በክርስቶድ ስር መስደድ አለበት የሆነልንን ስናውቅ የጊዜውን እንንቀዋለን::  ስለዚህ ስር እንስደድ  ቃሉን መስማትና መታዘዝ ቃሉንም ማመንዥግ ይብዛልን::

የጸሎት ርእስ:  በሰጠን ጸጋ እንድናገለግል

እንዲሁም ስር ሰደን እንድናድግ የቃሉንም ደጅ እንዲከፍትልን::

የሐዋርያት ሥራ 19

1፤ አጵሎስም በቆሮንቶስ ሳለ ጳውሎስ በላይኛው አገር አልፎ ወደ ኤፌሶን መጣ፥ አንዳንድ ደቀ መዛሙርትንም አገኘ።

2፤ ባመናችሁ ጊዜ መንፈስ ቅዱስን ተቀበላችሁን? አላቸው። እነርሱም፦ አልተቀበልንም፡ መንፈስ ቅዱስ እንዳለ ስንኳ አልሰማንም፡ አሉት።

6፤ ጳውሎስም እጁን በጫነባቸው ጊዜ መንፈስ ቅዱስ ወረደባቸው በልሳኖችም ተናገሩ፥ ትንቢትም ተናገሩ።

ያለ መንፈስ ቅዱስ ክርስትና ከባድ ነው::  ዮሐንስም ያለው እኔ በውሃ አጠምቃችኃለሁ ከኔ በኃላ የሚመጣው ግን በእሳት ያጠምቃችኃል::  እነዚህ ሰዎች የዳኑ ናቸው ለዚህ ነው  አንዳንድ ደቀ መዛሙርትንም አገኘ የሚለው ቃሉ ነገር ግን ስለ መንፈስ ቅዱስ አያውቁም ነበር ምናልባትም አጵሎስ ያገለገላቸው  ሊሆኑ ይችላሉ::  በፊተኛው ምዕራፍ እንዳለው አጵሎስ (18: 25፤ እርሱ የጌታን መንገድ የተማረ ነበረ፥ የዮሐንስንም ጥምቀት ብቻ አውቆ በመንፈስ ሲቃጠል ስለ ኢየሱስ ይናገርና በትክክል ያስተምር ነበር።)

መንፈስ ቅዱስ ክርስቶስን ባመን ስጋ ለባሽ  ሁሉ ላይ ይወርዳል የሚመጣው ሊሰራን ሊያበጃጀንና ለመንግስቱ ስራ ሊሾመን ነው::  ጌታ እየሱስም እኔ ብሄድ ይሻላል  ደግሞም እርስር በመጣ ጊዜ ያከብረኛል ብሎ ነግሮናል:: ዕለት ዕለት በመንፈስ ተሞሉ ተብለናልና እንጸልይ ለሙላቱ!

የሐዋርያት ሥራ 19: 11-20

20፤ እንዲህም የጌታ ቃል በኃይል ያድግና ያሸንፍ ነበር።

ይህ ቃል የመጣው የጳውሎስ የልብስ ቁራጭ ከፈወሰና አጋንንትን ስላስወጣ ነው::  የካህኑ የአስቄዋ 7 ልጆችም አጋንንት ሊያወጡ ሲሞክሩ በርትቶ እንደደበደባቸው በኤፌሶን ከተማ ሁሉ ተሰማ ስለዚህም የጌታ የኢየሱስ ስም ተከበረ::

18. አምነውም ከነበሩት እጅግ ሰዎች ያደረጉትን እየተናዘዙና እየተናገሩ ይመጡ ነበር። 

19፤ ከአስማተኞችም ብዙዎቹ መጽሐፋቸውን ሰብስበው በሰው ሁሉ ፊት አቃጠሉት፤ ዋጋውም ቢታሰብ አምሳ ሺህ ብር ሆኖ ተገኘ።

ይሄ ነው ማደግና ማሸነፍ::  አንድ ሰው እንኳን በዚህ ስም ማሾፍ ወይም ማቃለል አይችልም::  እነዚህ 7 ልጆች እኮ የካህን ልጆች ናቸው ካህናት ለመሆን የታጩ ነገር ግን አሮጌውን ፕሮ አዲድኪዳን ነውና በአሮጌው ማንነት አዲሱን ኪዳን መውረስና ስሙን መጠቀም አልቻሉም:: ምን ብንደክም በህይወታችን አጋንንት ቭን የማን እንደሆንን ጠንቅቆ ያውቃል::  የታደገን ጌታ ስሙ ይባረክ!

ዛሬ ለወንጌል እንውጣ ይህ የከበረ ስም ተስቶናል::  ቃሉ በኃይል ያድጋል ያሸንፍማል እኛ ብቻ ታዘን እኔን ላከኝ ርንበል ይህንን ወንጌል ሳናፍር ለፍጥረት ሁሉ እንስበክ!!!

የሐዋርያት ሥራ 19: 21-41

26፤ ይህም ጳውሎስ፦ በእጅ የተሠሩቱ አማልክት አይደሉም፡ ብሎ፥ በኤፌሶን ብቻ ሳይሆን ከጥቂት ክፍል በቀር በእስያ ሁሉ ብዙ ሕዝብን እንደ አስረዳና እንደ አሳተ አይታችኋል ሰምታችሁማል።

ይህንን የተናገረው እነዚህን አማልክት በመስራት ትርፍ የሚያገኘው ሰው ነው::  ግን ጳውሎስ ሰውን አሳተ እንዴ?!  እንዲያውም ወደ ህይወት መንገድ መራቸው እንጂ::  ሰው ነገሮችን ከራሱ ጋር ነው የሚያያይዘው ወንጌልን ሰብከን ተቃውሞ ቢገጥመን አንዳንዱ ለእግዚአብሔር ቀንቶ ሳይሆን በሆነ ሌላ ምክንያት ይሆናል እኛ ግን ከሞት የተነሳውን የሁሉ ራስ የሆነውን እየሱስን  እንሰብካለን::

ጳውሎስን ለማሰናከልና ካሰበበት መንገድ ጠላት እንደለመደው እስር ቤት ሊያስገባው ወይም በህይወቱ ላይ አደጋ ሊጥል ነበረ እግዚአብሔር ግን ስብስቡ ምንም በኃይል የተደራጀ ቢሆንም በተነው::  ባርያው መድረስ ያለበት ቦታ አለና::  ጠላት ምንያህል ቢጠበብ እግዚአብሔር ካሰበልን ነገር አንጏድልም እንደርሳለን ብቻ ዓይናችን በእርሱ ላይ ይተከል::

ስራችንን በጸጋው በትጋት እንስራ ማንንም አንለፍ ህይወት የማያስፈልግው የለምና!

የሐዋርያት ሥራ 20: 1-12

7፤ ከሳምንቱም በመጀመሪያ ቀን እንጀራ ለመቁረስ ተሰብስበን ሳለን፥ ጳውሎስ በነገው ሊሄድ ስላሰበ ከእነርሱ ጋር ይነጋገር ነበር፥ እስከ መንፈቀ ሌሊትም ነገሩን አስረዘመ።

9፤ አውጤኪስ የሚሉትም አንድ ጎበዝ በመስኮት ተቀምጦ ታላቅ እንቅልፍ አንቀላፍቶ ነበር፤ ጳውሎስም ነገርን ባስረዘመ ጊዜ እንቅልፍ ከብዶት ከሦስተኛው ደርብ ወደ ታች ወደቀ፥ ሞቶም አነሡት።

10፤ ጳውሎስም ወርዶ በላዩ ወደቀ፥ አቅፎም፦ ነፍሱ አለችበትና አትንጫጩ፡ አላቸው።

12፤ ብላቴናውንም ደኅና ሆኖ ወሰዱት እጅግም ተጽናኑ።

ይህ የጳውሎስ የመጨረሻ  ጉብኝ  ነውና  ያለውን  ሁሉ  እውቀት  ሳያስቀር  እየመከረ  ቤተክርስቲያንን  ሁሉ እያጸና ያለበት ጊዜ ነው::   ነገ መንገድ  አለ በፊቴ  ልተኛ  ልረፍ  አይደለም  የሚያስበው  የጌታን  ነገር  እንጂ!!  እስኪነጋ  ድረስ  አገለገለ::  

በዚህ  ምክንያት ነገሩ ሲረዝም ይህ ብላቴና ከእንቅልፍ የተነሳ ወደቀ::  ሲደርሱም ብላቴናው  ሞቶ ነው ያገኙት  ነገር ግን በላዩ ላይ  ወደቀና  ነፍሱ አለችበትና አትንጫጩ፡ አላቸው።  ይህን በጌታ እየሱስ አገልግሎትም አይተናል አይደል? ተኝታለች ሲላቸው  ሳቁበት ልምድ ያላቸው  ነገር ግን እናትና አባትዋን እንዲሁም ሐዋርያትን ይዞ ገባና ተነሺ ሲላት ተነሳች ብላቴናዋ::   ሌላው ደግሞ በኤልሳዕም አገልግሎት የሞተው የሱናማይቱ ልጅ  ከሞት  ተነስቷል ልክ ጳውሎስ እንዳደረገው በላዩ ላይ ወድቆ ነበረ::   ጌታ ህያው ነው! የህይወትም ምንጭ ነው::

ዛሬም ጌታ  አልተለወጠም  የእኛ ማንነት ሳይሆን የስሙ ስልጣን ይሰራል::  ሞቶ ያገኙት ብላቴና  በህይወት ኖረ!!  

ከጳውሎስ የምንማረው ነገር በጌታ ላይ ዓይናችንን  አድርገን  የመንግስቱን ስራ ጊዜ ሳለ በትጋት መወጣት ነው::  በተሰጠን ጸጋ ማገልገል  ይሁንልን::

የሐዋርያት ሥራ 20: 17-21

17፤ ከሚሊጢንም ወደ ኤፌሶን ልኮ የቤተክርስቲያንን ሽማግሌዎች አስጠራቸው፤

18-19፤ ወደ እርሱም በመጡ ጊዜ እንዲህ አላቸው፦ ወደ እስያ ከገባሁበት ከመጀመሪያ ቀን ጀምሮ፥ በትሕትና ሁሉና በእንባ ከአይሁድም ሴራ በደረሰብኝ ፈተና ለጌታ እየተገዛሁ ዘመኑን ሁሉ ከእናንተ ጋር እንዴት እንደ ኖርሁ እናንተው ታውቃላችሁ፤

20-21፤ ወደ እግዚአብሔር ዘንድ ንስሐንና በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ማመንን ለአይሁድና ለግሪክ ሰዎች እየመሰከርሁ በጉባኤም በየቤታችሁም አወራሁላችሁና አስተማርኋችሁ እንጂ፥ ከሚጠቅማችሁ ነገር አንዳች ስንኳ አላስቀረሁባችሁም።

ጳውሎስ እነዚህን ሽማግሌዎች ጠርቶ እራሱንና አገልግሎቱን እየገምእገመ ነው::  ወደ ኤፌሶን መሄድ ስለማይችል ወደ እርሱ ሽማግሌዎችን ጠርቶ እያናገረ ነው::  በአገልግሎቱ አያፍርምና  በሁሉ ፊት እንዴት እንዳገለገለ ይገልጻል:: ያገለገለውም:-

1.    በትሕትና 

2.   በእንባ 

3.   ለጌታ እየተገዛሁ (ከአይሁድም ሴራ በደረሰብኝ ፈተና )

4.   ለአይሁድና ለግሪክ ሰዎች እየመሰከርሁ

5.   በጉባኤም በየቤታችሁም አወራሁላችሁና አስተማርኋችሁ

6.   ከሚጠቅማችሁ ነገር አንዳች ስንኳ አላስቀረሁባችሁም።

ምን አይነት አገልግሎት ነው?!  በመጨረሻው ኤፌሶንን ጥሎ እንዲወጣ ያደረገው የአህዛብ ግፊት ቢሆንም ግን አይሁድም ያሴሩበት ነበር ነገር ግን ለጌታ ተገዛሁ ይላል::  እንደዚህ በአገልግሎት መጨረሻ አገልግሎታችንን  መመዘን እንችል ይሆን?  ወይስ እግዚአብሔር በላይ በሰማይ ያለ የእኛን ህይወት እያሞቀና እያደመቀ ብቻ የሚኖር ነው ለእኛ?  ዛሬ ህይወታችንን እንመርምር ምንድነው ለጌታ የምንሰጠው?  እርሱ የሰጠን እራሱን ነው::  

ሌሎችን የሚጠቅም መንግስቱንም በሚያሰፋ አሳብና ልብ ጌታ ይሙላን::  ትህትናን ከኔ ተማሩ እንደተባልን ጳውሎስም በትህትና እንዳገለገለ እንዲሁ ማገልገል ይሁንልን::  በምድርያለነው እርሱን ለማገልገል ነው!!!

በቤትም በቤተክርስቲያንም መትጋት ይሁንልን::  ወንጌል ቋንቋችን ይሁን!

የሐዋርያት ሥራ 20: 22-27

24፤ ነገር ግን ሩጫዬንና ከጌታ ከኢየሱስ የተቀበልሁትን አገልግሎት እርሱም የእግዚአብሔርን ጸጋ ወንጌልን መመስከር እፈጽም ዘንድ ነፍሴን በእኔ ዘንድ እንደማትከብር እንደ ከንቱ ነገር እቆጥራለሁ።

26፤ ስለዚህ እኔ ከሰው ሁሉ ደም ንጹሕ እንደ ሆንሁ ዛሬ በዚች ቀን እመሰክርላችኋለሁ።

እኔ ከሰው ሁሉ ደም ንጹሕ  ነኝ?! የጳውሎስ አባባል አስደነገጠኝና እራሴን አንቺስ ብዬ ብጠይቅ  መልስ ስላጣሁ ጸለይኩኝ ይህንን ለማለት እንዲያበቃኝ ቃሉ ግን ውስጤን አናጋው:: እኔም አንድ ቀን እንደዚህ ማለት እችል ይሆን?!  

አይደንቅም ጳውሎስ ይህንን ሲል ለሊቱን ሙሉ አስተምሮና  መክሮ ሲጨርስ በዛው ሳይተኛ መንገዱን ወደሌላ አገልግሎት ያቀናል::  ተደብድቦ እያቃሰተ ያመልካል ያችም ለሊት ሳታልፍ አንድ ቤተሰብ ሙሉ ተሰብኮ ተጠምቋል::   ስንቱን ክፍል በእግሩ አዳርሶ ሰብኳን::  በየስፍራውም ሲደርስ  የሚጠብቀው ድብደባና ህይወቱን ማሳደድና ሴራ ነው::  እርሱ ግን ሩጫዬንና ከጌታ ከኢየሱስ የተቀበልሁትን አገልግሎት እፈጽም ዘንድ ነፍሴ በእኔ ዘንድ እንደማትከብር እንደ ከንቱ ነገር እቆጥራለሁ አለ!!!  እኔስ ብለን እንጠይቅ? የተሰጠንን አደራ እንዴት እያደረግን ነው?!  እንጠየቅበታለን የሰው አደራ እንኳን እንዴት ከባድ ነው እንኳንስ የጌታ?!

የማቴዎስ ወንጌል 10

39፤ ነፍሱን የሚያገኝ ያጠፋታል፥ ነፍሱንም ስለ እኔ የሚያጠፋ ያገኛታል። ብሎን የለ ጌታ?  

ሀብታችንን በላይ በሰማይ እናከማች  ተኮፍሰው ወንጌልን የሚንቁትን አትፍሩ ምክንያቱም ነገ የሚጠብቃቸውን እናውቃለንና እንመስክር ቀን ሳለ የጌታን ስራ እንስራ ሁሉ በጸጋውያገልግል  ምን ለውጥ መጣለሁ አንበል  ይህ የጠላት ሽንገላ ነው  የሚሰራው ጌታ መንፈስ ቅዱስ ነው እራሳችንን እንስጠው ያስደንቀናል::  ጊዜያችንን እንዋጅ በፊቱ እንበርከክ ቃሉንም እናመንዥግ!!  እንበርታ እያንዳችን የክርስቶስ አካል ነንና የማይሰራ የሰውነት ክፍል ካሌ ሌላውን ሁሉ እንደሚያውክ የሌላውን ስራ ከመመኘት የተሰጠንን ቅልጥፍ አድርገን በታማኝነት እንስራ::

የሐዋርያት ሥራ 20: 28-38

29-30፤ ከሄድሁ በኋላ ለመንጋው የማይራሩ ጨካኞች ተኩላዎች እንዲገቡባችሁ፥ ደቀ መዛሙርትንም ወደ ኋላቸው ይስቡ ዘንድ ጠማማ ነገርን የሚናገሩ ሰዎች በመካከላችሁ እንዲነሡ እኔ አውቃለሁ። 

32፤ አሁንም ለእግዚአብሔርና ያንጻችሁ ዘንድ በቅዱሳንም ሁሉ መካከል ርስትን ይሰጣችሁ ዘንድ ለሚችል ለጸጋው ቃል አደራ ሰጥቻችኋለሁ።

የኤፌሶን ቤተክርስቲያን ለሶስት ዓመታት በጳውሎስ ተገልግላለች::  ይህ ክፍል የሚያሳየን መሪዎቹን አስጠርቶ የመጨረሻውን የስንብት ምክር እየሰጣቸው ነው::  ምንም እንኳን ይህንን ሁሉ ጊዜ ቢያገለግላቸውም ለመንጋው የማይራሩ ጨካኞች ተኩላዎች እንደሚመጡ እያስጠነቀቃቸው ነው::  ሲመጡም  ደቀ መዛሙርትንም ወደ ኋላቸው ይስቡ ዘንድ ጠማማ ነገርን የሚናገሩ ናቸው::  ስለዚህ ለጸጋው ቃል አደራ ሰጥቻችኋለሁ ይላቸዋል::  ቤቱን ጌታ ይጠብቃል ምንም እንኳን በአሁኑ ዘመን ነገሮች ውጥንቅጣቸው የወጣ ቢመስልም እርሱ ግን አለ በዙፋኑ የሚፈሩትንና  በእውነት  የሚፈልጉትን ያውቃቸዋል::  አይሸነፍም! ያለ ፊት መጨሚደድ ተዘጋጅታ  የምትጠብቀውን  ሙሽራ  ያዘጋጃል!

ጳውሎስ ሲያገለግል በማንም ላይ ሸክም አልነበረም  እንደአሁኑ ዘመን የሙሉ ጊዜ አገልጋይ ተብሎ ቁጭ አላለም ድንኳን እየሰፋ እርሱንና ተርፎት አብረውት ያሉትንም ያኖር ነበረ::  ስለዚህም “አትመኝ!”  እንዳለ ቃሉ ከማንም ብርና ወርቅ አልተመኘሁም ይላል::  ያለኝ ይበቃኛልን እንማር ያለንንም ከሌሎች ጋር በመከፋፈል የተቸገሩትንም በመርዳት እንመላለስ ከሚቀበል ይልቅ የሚሰጥ ብፁዕ ነው፡ እንዳለ፡ የጌታን የኢየሱስን ቃል ልታስቡ ይገባችሁ ዘንድ በሁሉ አሳየኋችሁ ይላል::  እንደዚህ ምሳሌ የሚሆኑንን በቤቱ ያስነሳልን እኛም ምሳሌ መሆን እንድንችል ጌታ ይርዳን::

የሐዋርያት ሥራ 21:1-16

13፤ ጳውሎስ ግን መልሶ፦ እያለቀሳችሁ ልቤንም እየሰበራችሁ ምን ማድረጋችሁ ነው? እኔ ስለ ጌታ ስለ ኢየሱስ ስም በኢየሩሳሌም ለመሞት እንኳ ተሰናድቼአለሁ እንጂ ለእስራት ብቻ አይደለም፡ አለ።

ጳውሎስ ብዙ ጊዜ መልክት መቶለታል ምን እንደሚጠብቀው ወደ እየሩሳሌም ከሄደ ነገር ግን አትሂድ አልተባለም::  ነብይ አጋቦስ በመታጠቅያው ታስሮ የሚጠብቀውን አሳይቶታል የጳውሎስ መልስ ግን እያለቀሳችሁ ልቤንም እየሰበራችሁ ነው ነበር ያለው::  

በመጀመሪያም  ገና ሐናንያ ሲጸልይለት የነገረው ነገር

የሐዋርያት ሥራ 9

15፤ ጌታም አለው፦ ይህ በአሕዛብም በነገሥታትም በእስራኤልም ልጆች ፊት ስሜን ይሸከም ዘንድ ለእኔ የተመረጠ ዕቃ ነውና ሂድ፤ 16፤ ስለ ስሜ ስንት መከራ ሊቀበል እንዲያስፈልገው እኔ አመለክተዋለሁና።

ሁለቱን በሚገባ ፈጽሟል የቀረው በነገስታት ፊት ስሙን መሸከም ነው ለዚህም ሳያቅማማ እየሄደ ነው::  በሚያልፍበት መንገድ ሁሉንም እየተሰናበተ የመጣውም ደግሞ እንደማያያቸው ስለሚያውቅ ነው::  እስከ መጨረሻ መጽናትን እንማራለን ከህይወቱ::  ለመታሰር ብቻ ሳይሆን ለመሞትም ዝግጁ ነበረ::  ህይወቴ በእኔ ዘንድ አርከብርም ባይነው::  እግዚአብሔር  ያየልንን  እንይ እርሱ ይወርሰናል እርሱ በእያንዳንዳችን ላይ ዓላማ አለው ለዛ ዓላማ እንኑር::  ከጌታ የምንሰስተው ምንም የለም እኛም እራሳችን የእኛ አይደለንም የእርሱ እንጂ በዋጋ ተገዝተናል::  እግዚአብሔር ፈርተው ለክብሩ የሚቆሙ ነብያትን ያብዛልን::   እሩጫችንን በትግስት እንሩጥ!

የሐዋርያት ሥራ 21: 17-26

19፤ ሰላምታም ካቀረበላቸው በኋላ በእርሱ ማገልገል እግዚአብሔር በአሕዛብ መካከል ያደረገውን በእያንዳንዱ ተረከላቸው።

21፤ ልጆቻቸውንም እንዳይገርዙ በሥርዓትም እንዳይሄዱ ብለህ በአሕዛብ መካከል ያሉት አይሁድ ሁሉ ሙሴን ይክዱ ዘንድ እንድታስተምር ስለ አንተ ነግረዋቸዋል።

ጳውሎስ እየሩሳሌም ሲመጣ ወገኖች ተቀበሉት ከያዕቆብም ጋር ተገናኘ አገልግሎቱንም ተረከላቸው ጌታንም አመሰገኑ::  ነገር ግን በውሸት እየተከሰሰ እንደሆነ ነገሩትና መፍትሄ ያሉትንም መከሩት:: የመንጻትን ህግ እንዲፈጽምና ህጉን እየጠበቀ መሆኑን እንዲያሳይ ነበር ምክሩ::  ጳውሎስም ተስማማ::  ለምን ይሆን የተስማማው?

የጳውሎስ ትምህርት የብሉይ ህግ መጠበቅ ከጸጋ መውደቅ ነውእያለ አስተምሮ ሲያበቃ እዚህ ጋር አመቻምች ነው የሚሉት?  አይደለም እርሱ ሁልጊዜ የሚናገርበትን መንገድ ለማግኘት ነው ጥረቱ ብዬ ነውየማስበው እንጂ የዚህ የመንጻት ስርአት ምንም እንደማያደርገት ስርአት ብቻ እንደሆነ ጠንቅቆ  ያውቃል::  ስለትን መሳል አያስፈልገንም በጌታ ፊት እንድንሰማ እርሱ እራሱ እንደሚሰማን ነግሮናልና::  ከህግ በላይ ከጸጋ በታች ነንና አለበለዚያ ከክርስቶስ ጸጋ ወድቀናል::  ቅድስና የክርስትና ስር መሰረቱ ሳይሆን ፍሬው ነው::  እርሱን እየመሰልን በመለወጥ በቃሉና በመንፈሱ የሚመጡ እንጂ በውጭ በምናደርገው ስርአት የሚመጣ አይደለም::  ጌታ እንዳናመቻምች ይርዳን!  በጌታና በቃሉ እንዳናፍር በማንኛውም ሁኔታ ውስጥ ቆራጥ ወታደር እንሁን!

የሐዋርያት ሥራ 21: 27-40

30፤ ከተማውም ሁሉ ታወከ ሕዝቡም ሁሉ ተሰበሰቡ ጳውሎስንም ይዘው ከመቅደስ ውጭ ጎተቱት፥ ወዲያውም ደጆች ተዘጉ::

31፤ ሊገድሉትም ሲፈልጉ፦ ኢየሩሳሌም ፈጽማ ታወከች፡ የሚል ወሬ ወደ ጭፍራው ሻለቃ ወጣ፤

32፤ እርሱም ያን ጊዜ ወታደሮችን ከመቶ አለቆች ጋር ይዞ እየሮጠ ወረደባቸው፤ እነርሱም የሻለቃውንና ወታደሮችን ባዩ ጊዜ ጳውሎስን መምታት ተዉ።

ጳውሎስ ህጉን እንደሚጠብቅ ሰው ወደቤተ መቅደስ ቢሆንም አልሰራም::  በእስያ የሚያውቁት ሰዎች እንዲያዝና እንዲደበደብ አደረጉ ሻለቃው መቶ እስኪያስቆም ድረስ::  እግዚአብሔር ከሞት አዳነው ምክንይቱም ስራውን አልጨረሰም ነበር እሱም በነገስታት ፊት መቆም::  ለነገስታቱም ወንጌል ያስፈልጋልና::  ሻለቃው ባይደርስ ኖሮ ህዝቡ በጣም ተናደው ነበረና ምናልባትም ለእግዚአብሔር የቀኑ መስሏቸዋልና ይገድሉት ነበር::  ማዳን የአምላካችን ነው::  የተጠራልነትን ስራ እስክንጨርስ ጌታ ይጠብቀናል እራሳችንን ዝቅ አድርገን አንይ የእግዚአብሔርን አጀንዳ የተሸከምን በእርሱም ጸጋ የምንፈጽም ነን::

ባገኘው አጋጣሚ ሁሉ ወንጌልን ማገልገል የሚፈልገው ጳውሎስ ሻለቃውን አስፈቀደ ለመናገር::  ይህ ህዝብ ወገኑ ነው እኔ ልጥፋ እስኪል ድረስ የሚወደው ህዝብ ነው::  ትልቁን ስራ ሰርተዋል እራሳቸውን ለጌታ  አስገዝተው መሲሁን እየጠበቁ ነበርና::  ተላለፉ እንጂ!  ስለዚህ ለዚህ ህዝብ ቅናት አለው  ወንጌልን ሰብኮ መጋረጃቸው እንዲነሳና እየሱስን እንዲያዩ::  እኛም ዛሬ በዚህ ቅናት ልንወጣ ይገባል::  የደከመውን ማበርታት፤  የጠፉትን መፈለግ ፤ በጨለማ ያሉትንም ወደ ብርሃን መተው ጌታን እንዲያገኙ ተጠርተናል::  ሁሉም በተሰማራበት ተግቶ ማገልገል አለበት::  ጌታ ጸጋውን ያብዛልን!

የሐዋርያት ሥራ 22: 1-30

13፤ እርሱም ወደ እኔ መጥቶ በአጠገቤም ቆሞ፦ ወንድሜ ሳውል ሆይ፥ እይ፡ አለኝ። እኔም ያን ጊዜውን ወደ እርሱ አየሁ።  14፤ እርሱም አለኝ፦ የአባቶቻችን አምላክ ፈቃዱን ታውቅ ዘንድና ጻድቁን ታይ ዘንድ ከአፉም ድምፅን ትሰማ ዘንድ አስቀድሞ መርጦሃል።  15፤ ባየኸውና በሰማኸው በሰው ሁሉ ፊት ምስክር ትሆንለታለህና።

በዚህ ምዕራፍ ላይ ጳውሎስ ለህዝቡ የህይወት ምስክርነቱን እየሰጠ ነው::  ሊታገሱት ቢያቅታቸውም ቅሉ እርሱ ግን ያገኘውን አጋጣሚ ሁሉ መጠቀሙ አይቀርም:: እንዴት ወደዚህ እምነት እንደመጣ ማን እንደነበረ ነገራቸው::  እንደነሱ አሳዳጅ እንደነበረ በእስጢፋኖስ ሞትም እንደተባበረና ብዙዎችንም እንዳሳሰረ  ነገር ግን ከማሳደድ እንዲመለስ ያደረገው እራሱ እየሱስ እንደሆነ መሰከረ::  ሐናንያ የነገረው ነገር ግን በጣም ይገርማል:-

– የአባቶቻችን አምላክ ፈቃዱን ታውቅ ዘንድና 

–  ጻድቁን ታይ ዘንድ 

– ከአፉም ድምፅን ትሰማ ዘንድ አስቀድሞ መርጦሃል

ምን አይነት መመረጥ ነው?! ይህ ግን ለጳውሎስ ብቻ አይደለም በክርስቶስ ላመንን ሁሉ ነው::  ትህትና መስሎን እኔ ትል የማልረባና የተለያዩ ቃላትን እንጠቀማለን ይህ ስህተት ነው::  ንጉሱ መረጠን ደግሜ እላለሁ መረጠን ለራሱ!

1. ፈቃዱን እንድናውቅ ነው:- ፈቃድ ለማወቅ ጠጋ ማለና ልብን መስጠት ያስፈልጋል

2.  ጌታን እንድናይ ነው:-  ማን ይሆን ጌታን ያላየ በገሀዱ አይን ማለቴ አይደለም በመንፈስ እናም መገኘቱን ያላረጋገጠ? እርሱ የቅርብ አምላክ ነው

3. ድምጹን ለመስማት:-  በጎቼ ድምጼን ይሰማሉ አላለም? ግድ ነው የመስማት ብቃቱ  ተሰቶናል

ጌታ አንዱን ከሌላው አይለይም ለጳውሎስ ብቻ ሳይሆን ለእኛም የተሰጠ ነው መርጦናል::  እራሴን እንደጌታ ምርጥ መቁጠር አለብኝ! 

እኔን የሚያሳድድ ጌታን እንዳሳደደ ነው የሚሰድበኝም እንዲሁ::  ግን እራሳችንን እንደዚህ እንቀበላለን? ቃሉ ግን የሚነግረን ይህንን ነው!  ተቀባይነትን ያገኘን ምርጦች ነን::   ስለዚህ በሰው ሁሉ ፊት ምስክር እንሁን::

የሐዋርያት ሥራ 23: – 1-11

1፤ ጳውሎስም ሸንጎውን ትኵር ብሎ ተመልክቶ፦ ወንድሞች ሆይ፥ እኔ እስከዚች ቀን ድረስ በመልካም ሕሊና ሁሉ በእግዚአብሔር ፊት ኖሬአለሁ፡ አለ።

11፤ በሁለተኛውም ሌሊት ጌታ በአጠገቡ ቆሞ፦ ጳውሎስ ሆይ፥ በኢየሩሳሌም ስለ እኔ እንደ መሰከርህ እንዲሁ በሮሜም ትመሰክርልኝ ዘንድ ይገባሃልና አይዞህ፡ አለው።

ጳውሎስ ለምን ታሰረ?! ምን አጠፋ?

ጳውሎስ ጌታውን በትጋት ህይወቱን ሳይሰስት ወደ አህዛብ አዙሮ አገለገለ::  እግሩ እስኪነቃ ድረስ ከአገር ወደ አገር እያስተማረ ዞረ ::  መንገዱ ሁሉ ቀላል አልነበረም ከመከራ ውደ መከራ ነበር::  ከአንድ ስፍራ መዋረድ ወደሚቀጥለው  መዋረድ ምንም ሳያንገራግርናሳያጉረመርም አገልግሏል::  እኔን ምሰሉ እኔ ክርስቶስን እመስላለሁ እያለ ስለሁሉመዳን ሮጠ::

እኔ እርሱን ብሆን የምለው ይህን ሁሉ አገልግዬ አንድ ጊዜ እንኳን እረፍት አይኖረኝም? አልበዛም? ታያለህ ግን? ምን እስክሆን ነው የምትጠብቀው? አንተም ዝም አልከኝ?  እናሌላም ሌላም ልብ የሚኮረኩርና ቁጣዬን የምገልጽበትን መንገድ እፈልግና ማገልገልም እተው ነበር::  ጳውሎስ ግን ያገኘውን አጋጣሚሁሉ ለራሱ ሳይራራ ወደ ስብከት መድረክነት ይቀይረዋል:: መሞት ማለት ለጌታ ይህነው!!!!  እንሙት!!!!

በዚህ ስፍራ የሚለውን ስንመለከት:- እስከዚች ቀን ድረስ በመልካም ሕሊና ሁሉ በእግዚአብሔር ፊት ኖሬአለሁ፡  እኛም መልካም ህሊና በእግዚአብሔር ፊት ሊኖረን ይገባል::  ይህም ማለት ሁልጊዜ መንግስቱን ያስቀደመ ስለሌላው ግድ የሚለው ማንንት ያስፈልገናል::  እንዴት እራሱ ጌታ አይገለጥለትና አያጸናው በእየሩሳሌም ስለእኔ መስክረሀል አለው::  ከዚህ የሚበልጥ ሽልማት ምን አለ?!  የተጠራነው ስለዚህ መልካም ጌታ ልንመሰክር ነውና በጎነቱን ማዳኑንም ለዓለም እንመስክር::

የሐዋርያት ሥራ 23- የሐዋርያት ሥራ 25

20፤ እርሱም፦ አይሁድ ስለ ጳውሎስ ከፊት ይልቅ አጥብቀህ እንደምትመረምር መስለህ፥ ነገ ወደ ሸንጎ ታወርደው ዘንድ ሊለምኑህ ተስማምተዋል። 

21፤ እንግዲህ አንተ በጅ አትበላቸው፤ እስኪገድሉት ድረስ እንዳይበሉና እንዳይጠጡ ተማምለው ከእነርሱ ከአርባ የሚበዙ ሰዎች ያደቡበታልና፤ አሁንም የተዘጋጁ ናቸው የአንተንም ምላሽ ይጠብቃሉ፡ አለው።

ሻለቃው የአይሁድን የምክር ሚስጥር ስለሰማ ወደ አገረ ገዢው ፊሊክስ ወሰደው::  ከሳሾቹም ተከራከሩ ግን አሳማኝ አልነበረም እግዚአብሔር ነገራቸውን ስላቀለለው አልተቀበላቸውም ግን በእስር ቤት ተወው::  ጉቦንም ፈልጎ ብዙ ጊዜ እያመላለስ አነጋገረው (ለሁለት ዓመት) ጳውሎስ ግን ወንጌልን ብቻ ነበር የሚሰብከው::  ስልጣኑንም ሲለቅ ለፊስጦስ በዛው እንደታሰረ ተወው አይሁድን ደስ ለማሰኘት::  ጳውሎስ ምን አይነት ቆራጥነት ነው ያለው?  ገንዘብ ሰጥቼ ከዚህ አምልጬ ልሩጥ አላለም::  በዚህ ሁኔታ ውስጥብንሆን ምን እናደርግ ይሆን ወይም ለወዳጃችን ምን እንመክር ይሆን ወይስ መዋጮ መሰብሰብ እንጀምር ይሆን እሱን ለማስፈታት?  ጳውሎስ የተጠራው  ግን እነዚህ ባለስልጣናት ሁሉ ወንጌልን እንዲሰብክ ነውና ጥሪውን አውቆ በእስር ላይ ሆኖ ያለምንም ማንገራገር ወንጌሉን ይሰብካል:: 

ፊስጦስም እንደገና ክሱን ሰማ ምንም አላገኘበትምና ጳውሎስ ወደ ቄሳር ይግባኝ ጠየቀ::  ከዛም ደግሞ ወደ ንጉስ አግሪጳና በርኔቄ ቀረበ ወንጀል ስላላገኙበትከአንዱ ወደ አንዱ ያስተላልፉታል በዚህ ውስጥ ግን የእግዚአብሔር ፈቃድ እየተከናወነ እንደሆነ ማን አስተዋለ?  ከተላከው ከጳውሎስ በቀር!   እግዚአብሔር በእኛ ላይ ያለውን አጀንዳ ይፈጽም ቢገባንም ባይገባንም እረኛችን ይመራናል:: ስለእኛ ሌሎችን ያስነሳል ልክ እንደጳውሎስ የእህት ልጅና ሻለቃው:: በጌታ እንታመን!

የሐዋርያት ሥራ 26: 1-32

17-18፤ የኃጢአትንም ስርየት በእኔም በማመን በተቀደሱት መካከል ርስትን ያገኙ ዘንድ፥ ከጨለማ ወደ ብርሃን ከሰይጣንም ሥልጣን ወደ እግዚአብሔር ዘወር እንዲሉ ዓይናቸውን ትከፍት ዘንድ፥ ከሕዝቡና ወደ እነርሱ ከምልክህ ከአሕዛብ አድንሃለሁ። 19፤ ንጉሥ አግሪጳ ሆይ፥ ስለዚህ ከሰማይ የታየኝን ራእይ እምቢ አላልሁም።

ጳውሎስ በንጉሱና በአገረ ገዢው ፊት ስለ እምነቱ ሲገልጽ:- ፈሪሳዊ እንደነበረ ይህንንም ስም የሚጠሩትን አሳዳጅ እንደነበረ ነገር ግን በደማስቆ መንገድ ጌታ ሲገናኘው አቅጣጫው እንደተቀየረና ከሰማይ ለታየው ራእይ እምቢ እንዳላለ ገለጸ::  የተሰጠውም አገልግሎት እዚህ ጋር እንደገለጸው

– የኃጢአትንም ስርየት 

– በእኔም በማመን በተቀደሱት መካከል ርስትን ያገኙ ዘንድ፥ 

– ከጨለማ ወደ ብርሃን 

– ከሰይጣንም ሥልጣን ወደ 

– እግዚአብሔር ዘወር እንዲሉ 

– ዓይናቸውን ትከፍት ዘንድ፥ 

ይህንን ትእዛዝ ለእኛም እግዚአብሔር ሰቶናል::  እግዚአብሔር ይርዳን ይህንን እውነት እንግለጥ::  ጳውሎስ ይህንን በመንገዱ ሁሉ ፈጸመው አገለገለ::  እሩጫዬንም ጨረስኩኝ አለ ጊዜን ሳያባክን አገለገለ::

የሐዋርያት ሥራ 27: 1-44

23፤ የእርሱ የምሆንና ደግሞ የማመልከው የእግዚአብሔር መልአክ በዚች ሌሊት በአጠገቤ ቆሞ ነበርና፥

24፤ እርሱም፦ ጳውሎስ ሆይ፥ አትፍራ፤ በቄሣር ፊት ልትቆም ይገባሃል፤ እነሆም፥ እግዚአብሔር ከአንተ ጋር የሚሄዱትን ሁሉ ሰጥቶሃል፡ አለኝ።

25፤ ስለዚህ እናንተ ሰዎች ሆይ፥ አይዞአችሁ፤ እንደ ተናገረኝ እንዲሁ እንዲሆን እግዚአብሔርን አምናለሁና።

ይህ መርከብ 276 ሰዎችን ያሳፈረ ነበር የጳውሎስን ምክር እንቢ ብለው ለታላቅ መከራ ተጋለጡ::  አውራቂስም የእግዚአብሔርን አጀንዳ ሊቃወም ጳውሎስን በመንገድ ሊያስቀር ቢወጣም አይችልም ኃይል የእግዚአብሔር ነውና::  አይደለም ጳውሎስ ሁሉም ከእርሱ የተነሳ ተጠበቁ ምክንያቱም በቄሳር ፊት መቆም አለበትና: :  ወታደሮቹ እንኳን እስረኞቹን እንግደል ብለው ቢማከሩም በአንዱ መቶ አለቃ ምክራቸውን መታው::  የጠላት ምክር ዛሬ በጌታ በእየሱ ስ ም  ከዙሪያችን ይመታ!

እግዚአብሔርን የሚያውቅ እንደ ተናገረኝ እንዲሁ እንዲሆን እግዚአብሔርን አምናለሁ ይላል::  ጌታ የተናገረን ምንድነው እንደዛው ይሆናል የፈለገው ነገር ቢፈጠርም አይለወጥምና በጌታ ልባችን ይጽና::

የሐዋርያት ሥራ 28: 1-10

2፤ አረማውያንም የሚያስገርም ቸርነት አደረጉልን፤ ዝናብ ስለ ሆነም ስለ ብርዱም እሳት አንድደው ሁላችንን ተቀበሉን።

3፤ ጳውሎስ ግን ብዙ ጭራሮ አከማችቶ ወደ እሳት ሲጨምር እፉኝት ከሙቀት የተነሣ ወጥታ እጁን ነደፈችው።

5፤ እርሱ ግን እባቢቱን ወደ እሳት አራገፋት አንዳችም አልጐዳችውም፤

ከዛ ሁሉ እንግልት በኃላ በሰላም እያንዳንዱ ነፍስ ደሴትዋ ላይ ደረሰ::  ቸርነትንም ከህዝቡ አገኙ እግዚአብሔር ሲረዳ ሞገስን ይሰጣልና::  የተሳፈሩበት መርከብ ግን ምልክቱም የለ ተሰባበረ ቃሉን የሰጠ ጌታ ግን ታማኝ ነውና የእርሱ የሆንኩት ብሎ ተማምኖ የተናገረውን ቃል አጸናው::  

የማዕበሉ ነገር አለቀ ሲባል እባብ አገኘችውና ነደፈችው::  የደሴቲቱ  ሰዎች እግዚአብሔር ቀጣው ብለው አብጦ እስኪሞት ሲጠብቁ እርሱ ግን ወደ እሳት አራገፋት አንዳችም አልጐዳችውም ይላል::  መንደፍን ግን ነድፋዋለች ይህንን ሰው ግን መግደል በእባብ መርዝ እንኳን አልተሳካም::  የደሴቲቱ ሰዎች ኃጥያተኛ ነው እንዳላሉ አሁን ደግሞ አለመሞቱን ሲያዩ አምላክ ነው አሉት::  ወይ ዓለም?!  ጠላት በብዙ መንገድ ይዋጋል በመከራ መጣል ሲያቅተው አንዳንዴም በኩራት እንድንኮፈስ ይጥራል እኛ ግን ትህትናን ከጌታ እንማር ክብር ለሚገባው ክብር ይሁን::

ጳውሎስ እስረኛው ከስራ ውጪ አልነበረም በሽተኞችን ፈወሰ ይላል ቃሉ ፈውሱን ሲያዩ መቼም ጌታን ወደማወቅ ይመጣሉ ብዬ አምናለሁ::  በጊዜውም አለጊዜውም ጌታን መመስከር ያስፈልጋል::

በህይወታችን ላይ ምንም እርሱ ያልፈቀደው አይመጣም ከመንገዳችንም አያቆመንም የምናመልከው እርሱ ጌታና ሁሉን ቻይ ነው::  አሜን!

የሐዋርያት ሥራ 28: 11-31

23፤ ቀንም ቀጥረውለት ብዙ ሆነው ወደ መኖሪያው ወደ እርሱ መጡ፤ ስለ እግዚአብሔር መንግሥትም እየመሰከረ ስለ ኢየሱስም ከሙሴ ሕግና ከነቢያት ጠቅሶ እያስረዳቸው፥ ከጥዋት ጀምሮ እስከ ማታ ድረስ ይገልጥላቸው ነበር።

28፤ ሲል መልካም ተናገረ። እንግዲህ ይህ የእግዚአብሔር ደኅንነት ለአሕዛብ እንደ ተላከ በእናንተ ዘንድ የታወቀ ይሁን፤ እነርሱ ደግሞ ይሰሙታል።

31፤ ማንም ሳይከለክለው የእግዚአብሔርን መንግሥት እየሰበከ ስለ ጌታ ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ እጅግ ገልጦ ያስተምር ነበር።

የሚገርመው ነገር ምን ያህል ወንጌል እንደተሰራ ነው እነጳውሎስ በሚሄዱበት  መንገድ ሁሉ ወንድሞችን ያገኛሉ ይህም ጳውሎስን አጽናናው::  የአገልግሎቱን ፍሬ እያየ ነውና ተጽናና የምናፈራው ፍሬ የትም አይሄድም::

በዚህ ስፍራ የአይሁድን  ታላላቆች ጠርቶ ከጠዋት የጀመረ እስከማታ ድረስ  የመጣበትን የክስ ሂደና  እርሱ እየሱስ መሲህ መሆኑን አስተማረ ግማሹ ሲቀበል ግማሹ ተቃወመ በዚህም ይሁን በዛ  ወንጌል ተሰበክ::  

በመጨረሻም ያላቸው ይገርማል:- ይህ የእግዚአብሔር ደኅንነት ለአሕዛብ እንደ ተላከ በእናንተ ዘንድ የታወቀ ይሁን፤ እነርሱ ደግሞ ይሰሙታል።  አሜን እንኳን ወንጌል ለአህዛብም እንዲሆን ጌታ ፈቀደ::  እኛም ሰምተን ድነናልና በቤቱ መጻተኛ  አይደለንም ቤተኛ ነን::  እጁን ዘርግቶ የተቀበለን አምላክ ይባረክ::

በሮሜ የሁለት ዓመት እስር ቆይታው ጳውሎስ ማንም ሳይከለክለው የእግዚአብሔርን መንግሥት እየሰበከ ስለ ጌታ ስለ ኢየሱስ ክርስቶስ እጅግ ገልጦ ያስተምር ነበር ይላል ቃሉ::  እዚህ እስር ላይ እያለ ነው የኤፌሶንን ፤ ፊሊጲስዩስን የጻፈውና በጌታ ደስ ይበላችሁ የሚለው እርሱ እስር ላይ ሆኖ!    እስር ላይ ቢሆንም የሚያሳስበው የቤተክርስቲያን ነገር ነበረ::  እኛ እዚህ ጋር ብንሆን እውነት ያለማጉረምረም በፊታችን ያለውን የመንግስት ስራ እየሰራን ጊዜ እንደሌለው ሰው አተኩረን እንሰራ ይሆን?! ባለንበት በማንኛውም የህይወት ውጣ ውረድ ሁሉ እግዚአብሔርን እንፈልግ  እርሱን እንግለጥና ሌሎችን እናገልግል ዓለም ያልፋል ሁሉም ይቀራል ዓይናችንን በጌታ ላይ እናድርግና በህይወታችን ላይ ያለውን አጀንዳ እንፈጽም:: የጌታ ጸጋ ይብዛልን ማስተዋልንም ይስጠን:: የምንሰስተው ህይወት የለንምየምንኖረው ኑሮ የእኛ አይደለምየእርሱ ነውና!

ወደ ሮሜ ሰዎች

ይህም ወንጌል በሥጋ ከዳዊት ዘር ስለ ተወለደ እንደ ቅድስና መንፈስ ግን ከሙታን መነሣት የተነሣ በኃይል የእግዚአብሔር ልጅ ሆኖ ስለ ተገለጠ ስለ ልጁ ነው፤ እርሱም ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው። (1: 4)

ወደ ሮሜ ሰዎች መግቢያ

ወደ ሮሜ ሰዎች 1: 1-7

ወደ ሮሜ ሰዎች 1: 8-15

ወደ ሮሜ ሰዎች 1: 16-17

ወደ ሮሜ ሰዎች 1: 18-32

ወደ ሮሜ ሰዎች 2: 1-29

ወደ ሮሜ ሰዎች 3: 1-23
ወደ ሮሜ ሰዎች 3: 24-31
ወደ ሮሜ ሰዎች 4: 1-12
ወደ ሮሜ ሰዎች 4: 13-25
ወደ ሮሜ ሰዎች 5: 1-5
ወደ ሮሜ ሰዎች 5: 6-11
ወደ ሮሜ ሰዎች 5: 12-21
ወደ ሮሜ ሰዎች 6: 1-14
ወደ ሮሜ ሰዎች 6: 15-23
ወደ ሮሜ ሰዎች 7: 1-6
ወደ ሮሜ ሰዎች 7: 7-13
ወደ ሮሜ ሰዎች 7: 14-25
ወደ ሮሜ ሰዎች 8: 1-2
ወደ ሮሜ ሰዎች 8: 3-8
ወደ ሮሜ ሰዎች 8: 9-13
ወደ ሮሜ ሰዎች 8: 14-17
ወደ ሮሜ ሰዎች 8: 18-30
ወደ ሮሜ ሰዎች 8: 31-39
ወደ ሮሜ ሰዎች 9: 1-33
ወደ ሮሜ ሰዎች 10: 1-3
ወደ ሮሜ ሰዎች 10: 5-11

ወደ ዕብራውያን

ከጥንት ጀምሮ እግዚአብሔር በብዙ ዓይነትና በብዙ ጎዳና ለአባቶቻችን በነቢያት ተናግሮ፥
 ሁሉን ወራሽ ባደረገው ደግሞም ዓለማትን በፈጠረበት በልጁ በዚህ ዘመን መጨረሻ ለእኛ ተናገረን፤
እርሱም የክብሩ መንጸባረቅና የባሕርዩ ምሳሌ ሆኖ፥ ሁሉን በስልጣኑ ቃል እየደገፈ፥ ኃጢአታችንን በራሱ ካነጻ በኋላ በሰማያት በግርማው ቀኝ ተቀመጠ፤ (1: 1-3)

አምላክ ሆይ፥ ዙፋንህ እስከ ዘላለም ድረስ ይኖራል፤ የመንግሥትህ በትር የቅንነት በትር ነው። (1:8)

አንተ ግን ጸንተህ ትኖራለህ፤ (1: 11)

እግዚአብሔርም እርሱ ራሱ እንደ ፈቀደ በምልክትና በድንቅ ነገር በልዩ ልዩ ተአምራትም፥ መንፈስ ቅዱስንም በማደል አብሮ መሰከረለት። (2: 4)

ነገር ግን በእግዚአብሔር ጸጋ ስለ ሰው ሁሉ ሞትን ይቀምስ ዘንድ፥ ከመላእክት ይልቅ በጥቂት አንሶ የነበረውን ኢየሱስን ከሞት መከራ የተነሣ የክብርና የምስጋናን ዘውድ ተጭኖ እናየዋለን። (2:9)

ብዙ ልጆችን ወደ ክብር ሲያመጣ የመዳናቸውን ራስ በመከራ ይፈጽም ዘንድ፥ ከእርሱ የተነሣ ሁሉ በእርሱም ሁሉ ለሆነ፥ ለእርሱ ተገብቶታልና። (2: 10)

እንግዲህ ልጆቹ በሥጋና በደም ስለሚካፈሉ፥ እርሱ ደግሞ በሞት ላይ ሥልጣን ያለውን በሞት እንዲሽር፥ ይኸውም ዲያብሎስ ነው፥ በሕይወታቸውም ሁሉ ስለ ሞት ፍርሃት በባርነት ይታሰሩ የነበሩትን ሁሉ ነጻ እንዲያወጣ፥ በሥጋና በደም እንዲሁ ተካፈለ። (2: 15)

ስለዚህ፥ ከሰማያዊው ጥሪ ተካፋዮች የሆናችሁ ቅዱሳን ወንድሞች ሆይ፥ የሃይማኖታችንን ሐዋርያና ሊቀ ካህናት ኢየሱስ ክርስቶስን ተመልከቱ፤ (3:1)

ወንድሞች ሆይ፥ ምናልባት ሕያው እግዚአብሔርን የሚያስክዳችሁ ክፉና የማያምን ልብ ከእናንተ በአንዳችሁ እንዳይኖር ተጠንቀቁ፤ (3: 12)

 ዳሩ ግን የሰሙት ቃል ከሰሚዎቹ ጋር በእምነት ስላልተዋሐደ አልጠቀማቸውም። (4:2)

ወደ ዕረፍቱ የገባ፥ እግዚአብሔር ከሥራው እንዳረፈ፥ እርሱ ደግሞ ከሥራው አርፎአልና። እንግዲህ እንደዚያ እንደ አለመታዘዝ ምሳሌ ማንም እንዳይወድቅ ወደዚያ ዕረፍት ለመግባት እንትጋ። (4:10-11)

የእግዚአብሔር ቃል ሕያው ነውና፥ የሚሠራም፥ ሁለትም አፍ ካለው ሰይፍ ሁሉ ይልቅ የተሳለ ነው፥ ነፍስንና መንፈስንም ጅማትንና ቅልጥምንም እስኪለይ ድረስ ይወጋል፥ የልብንም ስሜትና አሳብ ይመረምራል፤  እኛን በሚቆጣጠር በእርሱ ዓይኖቹ ፊት ሁሉ ነገር የተራቆተና የተገለጠ ነው እንጂ፥ በእርሱ ፊት የተሰወረ ፍጥረት የለም። (4: 12-13)

እንግዲህ በሰማያት ያለፈ ትልቅ ሊቀ ካህናት የእግዚአብሔር ልጅ ኢየሱስ ስላለን፥ ጸንተን ሃይማኖታችንን እንጠብቅ። ከኃጢአት በቀር በነገር ሁሉ እንደ እኛ የተፈተነ ነው እንጂ፥ በድካማችን ሊራራልን የማይችል ሊቀ ካህናት የለንም። እንግዲህ ምሕረትን እንድንቀበል በሚያስፈልገንም ጊዜ የሚረዳንን ጸጋ እንድናገኝ ወደ ጸጋው ዙፋን በእምነት እንቅረብ። (4: 14-16)

እርሱም በስጋው ወራት ከሞት ሊያድነው ወደሚችል ከብርቱ ጩኸትና ከእንባ ጋር ጸሎትንና ምልጃን አቀረበእግዚአብሔርንም ስለ መፍራቱ ተሰማለት፤ ምንም ልጅ ቢሆን፥ ከተቀበለው መከራ መታዘዝን ተማረ፤ (5: 7-8)

ወደ ዕብራውያን መግቢያ
ወደ ዕብራውያን 1: 1-3
ወደ ዕብራውያን 1: 4-14
ወደ ዕብራውያን 2: 1-4
ወደ ዕብራውያን 2: 5-9
ወደ ዕብራውያን 2: 10-13
ወደ ዕብራውያን 2: 14-18
ወደ ዕብራውያን 3: 1-6
ወደ ዕብራውያን 3: 7-19
ወደ ዕብራውያን 4: 1-3
ወደ ዕብራውያን 4: 4-11
ወደ ዕብራውያን 4: 12-13
ወደ ዕብራውያን 4: 14-16
ወደ ዕብራውያን 5: 1-10
ወደ ዕብራውያን 5: 11-14
ወደ ዕብራውያን 6: 1-3
ወደ ዕብራውያን 6: 4 – 6
ወደ ዕብራውያን 6: 7-12
ወደ ዕብራውያን 6: 13-20
ወደ ዕብራውያን 7: 1-10
ወደ ዕብራውያን 7: 11-28
ወደ ዕብራውያን 8: 1-3
ወደ ዕብራውያን 8: 4-13
ወደ ዕብራውያን 9: 1-10
ወደ ዕብራውያን 9: 11-22
ወደ ዕብራውያን 9: 23-28
ወደ ዕብራውያን 10: 1-10
ወደ ዕብራውያን 10: 11-18
ወደ ዕብራውያን 10: 19-23
ወደ ዕብራውያን 10: 24-25
ወደ ዕብራውያን 10: 26-39
ወደ ዕብራውያን 11: 1-3
ወደ ዕብራውያን 11: 4-10
ወደ ዕብራውያን 11: 11-40
ወደ ዕብራውያን 12: 1-3
ወደ ዕብራውያን 12: 4-11
ወደ ዕብራውያን 12: 12-17
ወደ ዕብራውያን 12: 18-29
ወደ ዕብራውያን 13: 1-6
ወደ ዕብራውያን 13: 7-25

3ኛ የዮሐንስ መልእክት

ወዳጅ ሆይ፥ ነፍስህ እንደሚከናወን፥ በነገር ሁሉ እንዲከናወንልህና ጤና እንዲኖርህ እጸልያለሁ። (2)

ወዳጅ ሆይ፥ ምንም እንግዶች ቢሆኑ፥ ለወንድሞች በምታደርገው ሁሉ የታመነ ሥራ ትሠራለህ፥ እነርሱም በማኅበር ፊት ስለ ፍቅርህ መስክረዋል፤  ለእግዚአብሔር እንደሚገባ አድርገህ በጉዞአቸው ብትረዳ መልካም ታደርጋለህ፤ (5-6)

ወዳጅ ሆይ፥ በጎ የሆነውን እንጂ ክፉን አትምሰል። በጎ የሚያደርግ ከእግዚአብሔር ነው፤ ክፉን የሚያደርግ ግን እግዚአብሔርን አላየውም። (11)

3ኛ የዮሐንስ 1-15